ቮልስዋገን በኢትዮጵያ የመኪና መገጥጠሚያ ፋብሪካ ሊገነባ ነው፤ የጀርመን የቴክኖሎጂ ድርጅቶች በስፋት ለመግባት እያመቻቹ ነው

Home Forums Semonegna Stories ቮልስዋገን በኢትዮጵያ የመኪና መገጥጠሚያ ፋብሪካ ሊገነባ ነው፤ የጀርመን የቴክኖሎጂ ድርጅቶች በስፋት ለመግባት እያመቻቹ ነው

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #9384
    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– ግዙፉ የመኪና አምራች የሆነው የጀርመኑ ኩባንያ ቮልስዋገን በኢትዮጵያ ኢንቨስት ለማድረግ የሚያስችለውን የመግባቢያ ስምምነት ፈረመ። ስምምነቱን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽነር አበባ አበባየሁ እና ከሰሃራ በታች የኩባንያው የአፍሪካ ቀጣና ሥራ አስፈጻሚ ቶማስ ሻፈር ተፈራርመዋል። በስምምነቱ መሠረትም ኩባንያው የመኪና መገጣጠሚያ ፋብሪካ መክፈት፣ የተሽከርካሪ መለዋወጫ ዕቃዎችን ማቅረብ፣ የስልጠና ማዕከል መክፈት እና ተጓዳኝ ሥራዎችን ይሠራል።

    በስምምነቱ ላይ በኢትዮጵያ የሥራ ጉብኝት ላይ የሚገኙት የጀርመኑ ፕሬዚዳንት ፍራንክ ዋልተር ስታይንማየር እና የኢፌዴሪ የገንዘብ ሚኒስትር አቶ አህመድ ሽዴ ተገኝተዋል።

    ቮልስዋገን ኩባንያ ከሰሃራ በታች ካሉ የአፍሪካ አገራት መካከል ኢትዮጵያን የማስፋፊያ ማዕከሉ አድርጎ ሲመርጥ፣ ከኩባንያው ጋር የመግባቢያ ስምምነት በመፈረም ከሰሃራ በታች ካሉ አገራት ኢትዮጵያ ሦስተኛዋ አገር (ከጋና እና ናይጄሪያ ቀጥሎ) ሆናለች።

    ◌ VIDEO: የጀርመኑ ግዙፍ የመኪና አምራች ኩባንያ ኢትዮጵያ ውስጥ ሰፊ ኢንቨስትመንት ለመጀመር እየተንቀሳቀሰ ነው

    ኩባንያው ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር ለመሥራት መስማማቱ በቀጥታ የእሴት ሰንሰለት የተቀናጀ የአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪ ክላስተር ለመፍጠር ወሳኝ ምዕራፍ ይከፍታል ነው የተባለው።

    ኮሚሽነር አበበ አበባየሁ በፊርማ ሥነ-ስርዓቱ ላይ እንዳሉት መንግሥት አገሪቷን ቀዳሚ የኢንቨስትመንት መዳረሻ ለማድረግ በቁርጠኝነት እየተንቀሳቀሰ ነው።

    ”በአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪው መስክ ልዩ ክላስተር እንዲመሠረት መንግሥት ያለሰለሰ ጥረት ያደርጋል” ያሉት ኮሚሽነሩ ይህን ተግባራዊ ለማድረግ ቮልስዋገንን ጨምሮ ፍላጎት ካላቸው ተቋማት ጋር በቅንጅት ለመሥራት ‘ዝግጁ ነው’ ብለዋል።

    ◌ VIDEO: German companies including Volkswagen and Siemens embarking to invest in Ethiopia

    የኩባንያው የአፍሪካ ቀጣና ሥራ አስፈጻሚ ቶማስ ሻፈር በበኩላቸው የኢትዮጵያ መንግሥት ለአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪው እድገት ትኩረት መስጠቱ ‘የሚደነቅ ነው’ ሲሉ ተናግረዋል። ከዚህ በተጨማሪ ቶማስ ሻፈር ‘ኢትዮጵያ ፈጣን እድገት በማስመዝገብ ላይ ያለች እና በሕዝብ ብዛትም ከ አህሪካ አገራት በሁለተኛ ደረጃ የተቀመጠች በመሆኗ፥ ከሰሃራ በታች ባሉ ሀገራት ለመስፋፋት በምናደርገው ጥረት ኢትዮጵያን ሁነኛ ተመራጭ አገር አድርገናታል፤ በተጨማሪም ቮልስዋገን ኩባንያ ሀገሪቱ ያላትን የስትራቴጂ ጥቅም ከግምት በማስገባት በ አውቶሞቲቭ ዘርፍ ከፍትኛ እድገት እንድታስመዘግብ ይተጋል’ ብለዋል።

    ከዚህ ጋር በተያያዘ የጀርመን የቢዝነስ ልኡካን ቡድን ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የሥራ ሃላፊዎችና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በኢትዮጵያ በኢንቨስትመንት መስክ በሚሰማሩበት ሁኔታ ላይ መክረዋል።

    ሲመንስ የተሰኘው በግዙግነቱ ከአውሮፓ ኩባንያዎች ቀዳሚውን ስፍራ የሚይዘው የጀርመን የቴክኖሎጂ ኩባንያ በኢትዮጵያ ከዚህ በፊት ሲሠራቸው ከነበሩ የቴክሎጂ ዘርፍ ሥራዎች በተጨማሪ በተጠናከረ መልኩ ለመሥራት ዝግጁ መሆኑን አሳውቋል።

    NEWS: German automaker Volkswagen develops automotive industry in Ethiopia

    የጀርመን የቴክኖሎጂ ጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ማኅበርም ቢሮውን አዲስ አበባ በመክፈት ወደ ሥራ ለመግባት ፍቃደኛ መሆኑን አሳውቋል። ማኅበሩ ጀርመን ውስጥ ያሉ የቴክኖሎጂ ድርጅቶች ማኅበር እንደመሆኑ ድርጅቶቹ በመስኩ ለመሰማራት የሚያስችላቸውን ሁኔታ ለማመቻቸት መልካም አጋጣሚን እንደሚፈጥር ይታመናል።

    በኢትዮጵያ መንግስት በኩል በጊዜያዊነት በነፃ ቢሮ በመስጠት ጭምር ማንኛውንም እገዛ ለማድረግ ቁርጠኛ መሆኑንም ተገልጿል።
    የልኡካን ቡድኑ አባላት በኢትዮጵያ ውስጥ በኢንቨስትመንት የተሰማሩ ድርጅቶች ከምንዛሬ እጥረት፣ በደላላ ምክንንያት ምርቶቻቸው ተጠቃሚው ጋር በተጋነነ ዋጋ መድረስ የመሳሰሉ ችግሮች እንደገጠሟቸው ተናግረዋል።

    የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ ጌታሁን መኩሪያ (ዶ/ር ኢንጂ.) የኤሌክትሮኒክስ ግብይት ለመጀመር ሥራዎች እየተሰሩ በመሆኑ ወደ ሥራ ሲገባ ችግሩ እንደሚቀረፍ ተናግረዋል።

    ምንጮች፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ቮልስዋገን


Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.