የዱባይ ግብረ ሰናይ ድርጅት አዲስ አበባ ውስጥ ያስገነባው ትምህርት ቤት ተመረቀ

Home Forums Semonegna Stories የዱባይ ግብረ ሰናይ ድርጅት አዲስ አበባ ውስጥ ያስገነባው ትምህርት ቤት ተመረቀ

Viewing 2 posts - 1 through 2 (of 2 total)
  • Author
    Posts
  • #9171
    Semonegna
    Keymaster

    አል ማክቱም ፋውንዴሽን በየካ ክፍለ ከተማ ካስገነባው ትምህርት ቤት በተጨማሪ በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማም በተመሳሳይ የአፍ መፍቻ ቋንቋቸው አፋን ኦሮሞ የሆኑ ተማሪዎች የሚማሩበት ትምህርት ቤት አስገንብቷል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ተቀማጭነቱን በዱባይ ከተማ ያደረገው አል ማክቱም ፋውንዴሽን የተባለ የተባበሩት አረብ ኤምሬት ግብረ ሰናይ ድርጅት በአርባ ሚሊዮን ብር ወጪ ያስገነባው ትምህርት ቤት ታህሳስ 30 ቀን 2011 ዓ.ም. ተመርቋል። ግብረ ሰናይ ድርጅቱ እስከ አሁን በኢትዮጵያ አራት ትምህርት ቤቶችን ማስገንባቱን የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) ዘግቧል።

    ትምህርት ቤቱ በየካ ክፍለ ከተማ በተለምዶ አያት አደባባይ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ የሚገኝ ሲሆን የአፍ መፍቻ ቋንቋቸው አፋን ኦሮሞ የሆኑ ተማሪዎች የሚማሩበት ነው።

    የትምህር ቤቱ የግንባታና የቁሳቁስ ወጪ በግብረ ሰናይ ድርጅቱ የተሸፈነ ሲሆን ለሚቀጥሉት አምስት ዓመታት የአስተማሪዎችን ሙሉ የደመወዝ ክፍያም በድርጅቱ የሚሸፈን ይሆናል።

    ከ2012 ዓ.ም ጀምሮ በትምህርታቸው የላቀ ውጤት ለሚያመጡ ተማሪዎችም ሱዳን በሚገኘው ‘ኢንተርናሽናል ዩኒቨርሲቲ ኦፍ አፍሪካ’ በተሰኘው ዓለም አቀፍ ትምህርት ቤት የነፃ የትምህርት ዕድል ተጠቃሚ እንደሚሆኑም የአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር ታቦር ገብረመድህን በምርቃት ሥነ ሥርዓቱ ላይ ተናግረዋል።

    በተጨማሪም ለመምህራን የትምህርት ዕድል ለመስጠትና ከሌሎች የአፍሪካ አገራት ጋር የመምህራን የልምድ ልውውጥ ለማድረግ መታቀዱንም ጠቁመዋል። የትምህርት ቤቱን የቅበላ አቅም ለማሳደግ የማስፋፊያ ሥራ ለመሥራት ዝግጅት መጠናቀቁንም ዶ/ር ታቦር ተናገረዋል።

    የትምህርት ቤቱ ርዕሰ መምህር ከድር ጃርሶ በበኩላቸው ትምህርት ቤቱ የአፍ መፍቻቸው አፋን ኦሮሞ ለሆኑ እና ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው ወላጆች ልጆች የትምህርት ዕድል ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው ብለዋል። እንዲሁም ትምህርት ቤቱ በአካባቢው መከፈቱ ለበርካታ ሥራ አጥ ኢትዮጵያውያን የሥራ ዕድል የፈጠረ መሆኑንም ገልጸዋል።

    የአል ማክቱም ፋውንዴሽን የኮሙኒኬሽን ባለሙያ አቶ አብዱልሸኩር መንዛ እንዳሉት ግብረ ሰናይ ድርጅቱ በኢትዮጵያ የትምህርት ዘርፍ የሚያበረክተውን አስተዋጽኦ በማጠናከር በሌሎች ዘርፎች ለመሥራትም ዕቅድ አለው።

    ግብረ ሰናይ ድርጅቱ በኢትዮጵያ የትምህርት ዘርፍ መጠናከር የአገሪቱ መንግስት ላደረገው ቀና ትብብርም አቶ አብዱልሸኩር አመስግነዋል።

    አል ማክቱም ፋውንዴሽን በየካ ክፍለ ከተማ ካስገነባው ትምህርት ቤት በተጨማሪ በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማም በተመሳሳይ የአፍ መፍቻ ቋንቋቸው አፋን ኦሮሞ የሆኑ ተማሪዎች የሚማሩበት ትምህርት ቤት አስገንብቷል።

    በሁለቱም ክፍለ ከተሞች የተገነቡት ትምህርት ቤቶች በአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ ስር እንዲተዳደሩ የኦሮሚያ ትምህርት ቢሮ አስረክቧል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    አል ማክቱም ፋውንዴሽን


    #10173
    Anonymous
    Inactive

    በአዲስ አበባ በ20 ሚሊዮን ብር ወጪ የህጻናት ማሳደጊያ ማዕከል ሊገነባ ነው
    —–

    በአዲስ አበባ ቁስቋም በሚባል አካባቢ ከ20 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪየህጻናት ማሳደጊያ ማዕከል ሊገነባ መሆኑን ተገለፀ።

    ግንባታው የቀዳማዊት እመቤት ጽህፈት ቤት ትምህርት ቤቶችን፣ የህጻናትና ሴቶች ድጋፍ ሰጪ ማዕከላትን ለማስፋፋት የተያዘው ዕቅድ አካል ነው ተብሏል፡።

    ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው ለህጻናት ማሳደጊያ ማዕከሉ ግንባታ የመሰረት ድንጋይ አስቀምጠዋል።

    በዚሁ ወቅት ወይዘሮ ዝናሽ እንደተናገሩት ማዕከሉ ለዘውዲቱ መሸሻ የህጻናትና ቤተሰብ በጎ አድራጎትና ልማት ማህበር የህጻናት ማሳደጊያ የሚበረከት ነው።

    ባለፈው ገና በዓል ዋዜማ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዓብይ አህመድና ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው ኮተቤ የሚገኘውን ይህንኑ የህጻናት ማሳደጊያ መጎብኘታቸው ይታወሳል።

Viewing 2 posts - 1 through 2 (of 2 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.