“በምንም ተአምር ለኢትዮያ ሕዝብ ውሸት አልነግርም” ከኮሚሽነር ጄነራል ዘይኑ ጀማል ጋር ያደረጉትን ቃለ ምልልስ

Home Forums Semonegna Stories “በምንም ተአምር ለኢትዮያ ሕዝብ ውሸት አልነግርም” ከኮሚሽነር ጄነራል ዘይኑ ጀማል ጋር ያደረጉትን ቃለ ምልልስ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #8183
    Semonegna
    Keymaster

    በምንም ተአምር ለኢትዮያ ሕዝብ ውሸት አልነግርም። ዕድሜዬም፤ ሥነ ምግባሬም አይፈቅድልኝም። ኢንጂነር ስመኘው በቀለ ሕይወታቸው ያለፈው በሰው በደረሰባቸው ጥቃት አይደለም ― ኮሚሽነር ጄነራል ዘይኑ ጀማል

    (ኤስ.ቢ.ኤስ ሬድዮ)–በሜልበርን ከተማ (አውስትራልያ) ተቀማጭነቱን ያደረገው ኤስ.ቢ.ኤስ ሬድዮ (SBS Radio) የአማርኛ ዝግጅት ክፍል ጋዜጠኛ ካሣሁን ሰቦቃ ኢትዮጵያ በነበረበት ጊዜ ከኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን፤ ኮሚሽነር ጄነራል ዘይኑ ጀማል ጋር ቆይታ አድርጎ ነበር። የተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮችን እያነሳም ቃለ ምልልስ አድርጎላቸው ነበር። ቃለ ምልልሱ የተደደረገው በሐዋሳ ከተማ ነበር – የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ደኢሕዴን) ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል ሆነው በተመረጡ ማግስት።

    ዋነኛ ርዕሰ ነገራቸውም ሕግና ሥርዓትን በአገር አቀፍ ደረጃ ማስፈንና ተዓማኒ የምርመራ ውጤቶችን በወቅቱ ለሕዝብ ይፋ ማድረግ ናቸው።

    አቶ ዘይኑ፤ እንደ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጄኔራልነታቸው የሕግ የበላይነት ለዲሞክራሲ እስትንፋስ መሆኑን ጠንቅቀው ያውቃሉ። ለተጀመረው የለውጥ ሂደት እጅጉን ቀናዒ ናቸው።

    “የሕግ የበላይነት ሳይከበር ዲሞክራሲ የሚታሰብ አይደለም። የዲሞክራሲ፣ የሰላምና የነፃነት ሀ ሁ የሕግ የበላይነት ነው” ይላሉ። ይህ ፅንሰ ሃሳብ ነው። ግብሩ የፖሊስ ኃይላቸው ፖለቲካዊ ሁከትን የመግታት ደረጃ ላይ አለመድረሱ ነው።

    የጸጥታ ሥራ ያለ ሕዝብ ትብብር ዕውን እንደማይሆን ስለሚረዱም ፤ ሕዝቡ ከጸጥታ ኃይሉ ጎን ቆሞ ሰላሙን እንዲያስከብር፤ ዲሞክራሲያዊ ሂደቱን እንዲታደግ ጥሪ ያቀርባሉ።

    የሁከት ምንጮችን በሰላማዊ መንገድ ለመታገል ወደ አገር ውስጥ በገቡ ተፎካካሪ ድርጅቶች ላይ በጅምላ ማላከኩ ተገቢ አይደለም በማለትም ያስገነዝባሉ።

    በሳቸው አተያይ ለአገረ ኢትዮጵያ የጸጥታ መደፍረስ ዋነኛ አስባቦች፡ –
    • የሕግ የበላይነትን ጠንቅቆ ካለመረዳት የሚከሰቱ የእርስ በርስ ግችቶች፣
    • ከነፃነት መግለጫ መንገዶች ጋር ተያያዥ የሆኑ የሕግ ግድፈቶችና
    • ጥቅማቸው የተነካባቸውና ያኮረፉ ኃይላት ድርጊቶች እንደሆኑ በዋቤነት ይነቅሳሉ።

    የፌዴራል ፖሊስ የምርመራ ውጤች መጓተትን አስመልክተው “ጥፍር እየነቀልን ምርመራ ስለማናካሂድ ማስረጃዎችን ለማሰባሰብ ጊዜ ይወስዳል” ባይ ናቸው፤ የፖሊስ ኃይሉ አቅም ደረጃም ታክሎበት።

    የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ፕሮጀክት ሥራ አስኪያጅ የነበሩት ኢንጂነር ስመኘው በቀለን አሟሟት አስመልክቶ መግለጫቸው በሕዝብ ዘንድ ሙሉ አመኔታን እንዳላሳደረ ላነሳንላቸው ጥያቄ ሲመልሱ፤

    በምንም ተአምር ለኢትዮያ ሕዝብ ውሸት አልነግርም። ዕድሜዬም፤ ሥነ ምግባሬም አይፈቅድልኝም። ኢንጂነር ስመኘው ሕይወታቸው ያለፈው በሰው በደረሰባቸው ጥቃት አይደለም

    በማለት በእርግጠኛነት ተናግረዋል።

    ለወደመው ንብረት፤ ለባከነው ሐብትና ከኢንጂነሩ ሞት ጀርባ ተጠያቂ ስለሚሆኑ አካላት ሲመልሱ፤ “ከኢንጂነር ስመኘው ሞት ጀርባ ያሉትን ፖሊስ ለፍርድ ያቀርባል። ያ እስከሚሆን ድረስ ፖሊስ ዕንቅልፍ አይኖረውም” ብለዋል።

    አንዱ አንኳር መልዕክታቸው “አንድም ሰው ቢሆን ጠብመንጃ ይዘናል ብለን ተኩሰን መግደል አንፈልግም። ግድያ፣ እስር፣ እንግልት ይበቃናል። ለዘመናት አይተነዋል። ለዘመናት ተሰቃይተንበታል። እዚህ ጋር ሊቆም ይገባል” የሚል ነው።

    ኮሚሽነር ጄነራል ዘይኑ ጀማል ከጋዜጠኛ ካሣሁን ሰቦቃ ጋር ያደረጉትን ቃለ ምልልስ ከተያያዘው የድምፅ ፋይል ያድምጡ።

    ዘጋቢ ካሣሁን ሰቦቃ ለኤስ.ቢ.ኤስ ሬድዮ የአማርኛ ዝግጅት ክፍል

    ዘይኑ ጀማል

Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.