Search Results for 'ብርሃኑ ነጋ'

Home Forums Search Search Results for 'ብርሃኑ ነጋ'

Viewing 3 results - 16 through 18 (of 18 total)
  • Author
    Search Results
  • Anonymous
    Inactive

    ብርሃኑ ነጋ የመረጠውን ሕይወት ለመምረጥ የጨዋ ልጅ መሆን ይጠይቃል፣ የህሊና ሰው መሆን ይጠይቃል፣ ራስን ማክበር ይጠይቃል። የብርሃኑ ነጋን ፅናትና የአቋም ሰውነቱን መካድ ነውር ነው! እሱን በፍርሃትና በአቋም የለሽነት ማማት ብልግና ነው። እሱን በዘርና በጎሳ ጉሊት መመደብ ውለታ ቢስነት ነው!

    የነጋ ቦንገር ልጅ!
    («ዘውድዓለም ታደሠ»)

    የልደቱ አያሌው ድብን ያልኩ አድናቂ ስለሆንኩና ብርሃኑ በልደቱ ጉዳይ የወሰደው አቋም አግባብነት ያለው (fair) ነው ብዬ ስለማላምን ትንሽ አዝኜበታለሁ። ሆኖም ግን እውነት እውነት ነችና ስለብሬ [ብርሃኑ ነጋ] የማልክዳቸው ሃቆች አሉ! (ስለእሱ የሰማኋቸውን “ሴራዎችን” (conspiracies) እዚህ ጋር አላነሳቸውም።)

    ብርሃኑ ነጋ እንደብዙዎቹ ፖለቲከኞቻችን ‘ፖለቲካ ክፍት የሥራ ቦታ ነው’ ብሎ ወደተመታው የኢትዮጵያ ፖለቲካ አልተቀላቀለም። በደርግ ዘመን ብዙዎች በወላጆቻቸው ሽካ ከብሔራዊ ውትድርና አምልጠው ማታ ማታ ገዳም ሰፈር ከቆነጃጅት ጋር ቡጊ ቡጊ ሲጨፍሩ ብሬ በዚያ እድሜው የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) ሆኖ በአገሩ ጉዳይ ከሞት ጋር ሌባና ፖሊስ ይጫወት ነበር። (የሚወዳት እህቱንም አጥቷል።)

    በኢህአዴግም ግዜ ከመለስ፣ ከታምራትና ከበረከት ጋር ባለው ልዩ ወዳጅነት (special friendship) ተሞዳሙዶ ቢያሻው ስልጣን፣ ቢያሻው መሬት ሸምቶ፣ ቢያሻው ሚኒስትር፣ ቢያሻው ቀጭን ኢንቨስተር ሆኖ ዘንጦ መኖር ሲችል ላመነበት ነገር ጎምበስ ቀና ሳይል የተቃዋሚውን ጎራ ተቀላቅሏል።

    ምንም እንኳ በየትኛውም ዓለም ቢሄድ እጁን ስመው የሚቀበሉት ምርጥ ምሁር ቢሆንም ከምቾቱ ይልቅ ወደወህኒ ወርዶ ሞት ተፈርዶበታል። እስር ቤት ውስጥ የረሃብ አድማ አድርጓል። በስተርጅና ዘመኑም እንዳቅሚቲ የትጥቅ ትግል ለማድረግ ተሟሙቷል። በተደጋጋሚ በርሃ ወርዷል። የፖለቲካ አኪያሄዱን ወደድነውም ጠላነውም በሚችለው አቅም ለአገሩ ህዝብ ድምፅ ሆኗል! ይሄ የማይካድ ሃቅ ነው!

    ከግማሽ ምእተ-ዓመት በላይ የሃብት ማማ ላይ ከተቀመጠ ቤተሰብ ተወልዶ፣ ዩኒቨርሲቲ ደሞዙን ለምስኪን ተማሪዎች እየሰጠ አስተምሮ፣ እድሜውን ሙሉ ባለሰባት ኮከብ (seven-star) ሆቴል እንደፓፍ ዳዲ አምስት ቺኮች አቅፎ መዝናናት እየቻለ ያሻው አገር ሄዶ በዕውቀቱ ተከብሮ መሥራት እየቻለ፣ በአፍሪካ ገናና የሆነ የጦር ኃይል አለኝ የሚልን ኃይል በጦርነት አሸንፋለሁ ብሎ በወኔ የተነሳ፣ ቤተሰቡን ጥሎ በእስር የማቀቀ፣ አገሩ ላይከፍተኛ ዕውቅና እንዳለው ግለሰብ (VIP standard) መኖር ሲችል በአሸባሪነት ተፈርጆ ብላክ ሊስት (black list) ውስጥ የገባ አንድ ሰው ባፈላልግ ያገኘሁት ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋን ብቻ ነው!

    አሁን ደግሞ ብሬ በተጋዳላይ ታርጋ የሚንቀሳቀስ ፓርቲውን አክስሞ አዲስ ፓርቲ በማቋቋም ከመጀመሪያው “ሀ” ብሎ (from the scratch) ሊነሳ ነው። ይህን ሁሉ የሚያደርገው ለምንድን ነው? ለሀብት እንዳንል እንኳን እሱ ዘር ማንዘሩም ሃብታም ነው። ለስልጣን እንዳንል ገና ድሮ በቀላሉ ማግኘት ይችል ነበር! እና ለምንድነው ህይወቱን እንዲህ በከባድ ወጥ ውረዶች የተሞላ (tragedy) ያረገው?… መልሱ ቀላል ነው። ብሬ (ብርሃኑ ነጋ) የአቋም ሰው ነው! ብሬ ላመነበት ነገር ከገገመ ገገመ ነው! አዲዮስ!

    እኔ ከላይ እንደነገርኳችሁ ‘ለብሬ እሰዋለታለሁ፣ ብርሃኑ ነጋ ያማልዳል፣…’ ምናምን የምል አድናቂው አይደለሁም። ነገር ግን አክባሪው ነኝ። ፅናትና የአቋም ሰውነቱን መካድ ነውር ነው! እሱን በፍርሃትና በአቋም የለሽነት ማማት ብልግና ነው። እሱን በዘርና በጎሳ ጉሊት መመደብ ውለታ ቢስነት ነው!

    […] የባቄላ ፍሬ የምታህል ዛኒጋባ ቤት ሳትኖርህ ቫንዳም፣ ቫንዳም መጫወት፣ የምታጣው ነገር ሳይኖር ኃላፊነት (risk) መውሰድና ከባዱን የሕይወት መንገድ መምረጥ’ኮ ያለና የነበረ ነው። ነገር ግን ሁሉ ሞልቶልህ ብርሃኑ ነጋ የመረጠውን ሕይወት ለመምረጥ የጨዋ ልጅ መሆን ይጠይቃል፣ የህሊና ሰው መሆን ይጠይቃል፣ ራስን ማክበር ይጠይቃል! ይኸው ነው!

    ረጅም ዕድሜ ለነጋ ቦንገር ልጅ!

    [ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ እና አቶ አንዱአለም አራጌ የኢትዮጵያ ዜጎች ማህበራዊ ፍትህ ፓርቲ መሪና ምክትል መሪ በመሆን ተመረጡ። ግንቦት 2 ቀን 2011 ዓ.ም. በተካሄደው ምርጫ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ 912 ድምፅ በማግኘት የፓርቲው መሪ በመሆን ተመርጠዋል። በተመሳሳይ አቶ አንዱአለም አራጌ የፓርቲው ምክትል መሪ በመሆን ተመርጠዋል። እንደዚሁም አቶ የሺዋስ አሰፋ 722 ድምፅ በማግኘት ሊቀመንበር ሆነው ሲመረጡ፥ ዶ/ር ጫኔ ከበደ ምክትል ሊቀመንበር በመሆን ተመርጠዋል። — ሰሞነኛ ኢትዮጵያ]

    ብርሃኑ ነጋ የኢትዮጵያ ዜጎች ማህበራዊ ፍትህ ፓርቲ


     

    Semonegna
    Keymaster

    ግልጽ ደብዳቤ ለኢትዮጵያ ሕዝብ በአቶ ነአምን ዘለቀ ― አቶ ነአምን ዘለቀ ራሳቸውን ከአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ አገለሉ
    ———

    ለአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ አባላት፣ የሠራዊት አባላት፣ ደጋፊዎችና፣ በልዩ ልዩ መደረኮች ለምታውቁኝ ኢትዮጵያውያን በሙሉ፦

    በሀገራችን የመጣውን ለውጥ ተከትሎ የአርበኞች ግንቦት 7 የዴሞክራሲና የአንድነት ንቅናቄ (አግ7) አመራር አባላት እ.ኤ.አ. በሀምሌ (July) ወር 2018 በአሜሪካን ሀገር ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ጋር በተደረገ ስብሰባ ላይ ከተደረሱት የስምምነት ነጥቦች መካከል አንዱ የአግ7 ንቅናቄ ሠራዊት ከኤርትራ በርሃና ከሀገር ውስጥም የነበሩት የአግ7 ታጣቂዎች ወደ ሀገር ወደ ሰላማዊ ኑሮ መመለስና ማቋቋምን የሚመለከት ነበር። በዚህም መሠረት በኤርትራ የነበሩ የንቅናቄው ሠራዊት አባላት እንዲሁም በየበረሃው የነበሩ የንቅናቄው ታጣቂዎች ወደ ልዩ ልዩ ካምፖች በየጊዜው እንዲገቡ መደረጉ ይታወቃል። በብዙ መቶ የሚቆጠሩ የንቅናቄው አባላትም ከልዩ ልዩ እስር ቤቶች ቀደም ሲል በተከታታይም እንደተለቀቁ ይታወቃል። በኃላፊነት ስመራ በቆየሁት በውጪው ዘርፍ ስር የማኅበራዊ ፈንድ ኮሚቴ እንዲቋቋም በማድረግ በውጭው ዓለም በሚገኙ በንቅናቄው አባላት፣ በደጋፊዎች፣ እንዲሁም አገር ወዳዶች ትብብር መጠነ ሰፊ ገንዘብ በማሰባሰብ በየእስር ቤቱ የነበሩት ተጋዮች ለሦስት ተከታታይ ወራት እንዲረዱ እንዲሁም ከኤርትራ በረሃ ለመጡትና በካምፕና ከካምፕ ውጭ ለሚገኙትም በልዩ ልዩ መንገዶች እርዳታዎች እንዲያገኙ ለማድረግ ተችሏል።

    ከኤርትራ በረሃ ወደ አገር ቤት እንዲገቡ የተደረጉትን የአርበኞች ግንቦት 7 የቀድሞ ታጣቂዎች እንዲሁም የሌሎች የፓለቲካ ድርጅቶች ታጣቂዎችን መልሶ የማቋቋሚያ ፕሮጄክት ጽ/ቤት በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት ስር ከ7 ወራት በፊት የተመሠረተ ሲሆን፥ የውጭ መንግስታትም በተለይም የጀርመን መንግስት ለዚሁ የሚውል ገንዘብ ለመስጠት ከበርካታ ወራት በፊት ተስማምተው ነበር። ሆኖም ከተቋቋመው ጽ/ቤት አቅም ማነስ እንዲሁም ጉዳዩ ተገቢውን ውሳኔዎች ሳያገኝ እየተጓተተ በመቆየቱ ሳቢያ የአርበኞች ግንቦት 7 ሠራዊት አባላት (በተለይም ከካምፕ ውጪ እንዲቆዩ ተደርገው መልሶ የማቋቋሚያ ድጋፍ እንዲጠብቁ የተነገራቸው ጭምር) ለከፍተኛ ችግር መዳረጋቸው ለህሊና እረፍት በሚነሳ ሁኔታ ውስጥ እራሴን አግኝቼ ነበር።

    የንቅናቄው ሊቀመንበር ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ እንዲሁም ዋና ጸሃፊ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ችግሩ መፍትሄ እንዲያገኝ በየጊዜው ከጠቅላይ ሚንስትሩና ከሌሎች የመንግስት ኃላፊዎች ጋር የሚያደርጉት ግንኙነትና ክትትል እንደተጠበቀ ሆኖ፤ በችግር ላይ የነበሩ የሠራዊት አባላት ሁኔታ አየተደራረበ የጭንቀት ድምጾች እየተበራከቱ በመምጣታቸው፣ ይህ ጉዳይ የንቅናቄውን ሊቀመንበርና ዋና ጸሐፊውን ብቻ የሚመለከት ሳይሆን አባላትና ሠራዊቱ የመረጡን የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላትን በሙሉ በተናጠልም ሆነ በጋራ የሚያስጠይቅ፣ ለሠራዊቱም ሆነ ለአባላት ኃላፊነት አለብን በሚል መንፈስ ይህ ለውጡን ለሚመራው መንግስትም የጸጥታና የፓለቲካ ችግር የሚፈጥር ሁኔታ፣ ከሞራልም ሆነ ከፓለቲካ እኳያ የንቅናቄውንም ውስጣዊ ጤንነት እየተፈታተነ የነበረ ትልቅ ችግር እየሆነ በመምጣቱ፣ ለችግሩ አፋጣኝ መፍትሄ እንዲሰጥ እርዳታ ለመስጠት ቃል ከገቡና ለመርዳት ፈቃደኛ ከሁኑ መንግስታት በተለይም ከጀርመን አምባሳደር፣ ከስዊድን መንግስት ኃላፊዎችና የፓርላማ አባላት፣ ከልዩ ልዩ የመንግስት ኃላፊዎችና ከመንግስት መዋቅር ውጭ የሚገኙ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሚቀርቡ ግለሰቦች ጋር በመገናኘት ለማስረዳትና መፍትሄ እንዲያገኝ የበኩሌን አስተዋጽዖ ለማድረግ ጥረቶች ሳደርግ ቆይቻለሁ።

    ብዙ ዝርዝሮች ያሉትና ወራት ያስቆጠረ ሂደት ቢሆንም፣ በዚህ አጋጣሚ ለዚህ ችግር መፍትሄ በማፈላለግ ሊያዳምጡን በራቸውን ለከፈቱ የልዩ ልዩ የመንግስት ተቋማት ኃላፊዎች፣ በተለይም የብሄራዊ አደጋና መከላከል ኮሚሽነር ምትኩ ካሳ፣ አምባሳደር ብርቱካን አያኖ፣ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት አማካሪ አምባሳደር ግርማ ብሩ፣ ጠቅላይ አቃቤ ሕግ አቶ ብርሃኑ ጸጋዬ፣ እንዲሁም ከመንግስት መዋቅር ውጭ ያሉና ከለውጡ በኋላ ከጠቅላይ ሚንስትሩ ሊያገኙን እንደሚፈልጉ በላለቤቴ በኩል መልክት የላኩብኝ የጠቅላይ ሚኒስሩ የአርቅ ኮሚቴ አባል አቶ ብርሃን ተድላ፣ በበርካታ የሕዝብና የሀገር ጉዳዮች ያላሰለሰ አስተዋጽኦ የሚያደርጉትና የረጅም ጊዜ ወዳጄ ለሆኑት ዶ/ር አምባሳደር ካሳ ከበደ፣ በጉዳዩ ላይ ትኩረት ሰጥተው ለመርዳት ለተንቀሳቀሱት፣ በእርዳታና በመልሶ ማቋቋም ከፍተኛ ልምድና ዕውቀት ያላቸው ለሻለቃ ዳዊት ወልደ ጊዮርጊስ፣ እንዲሁም ለመለሶ ማቋቋም የተቋቋመው መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ኣፍሪድ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ቴዎድሮስ ይልማ፣ ሌሎችም ለችግሩ መፍሄ ለማግኘት ያገኘኋቸውን ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ሁሉ እስከአሁኑ ቀን ድረስ ለከፍተኛ ችግር ተዳርገው በሚገኙት የሠራዊት አባላት ስም ምስጋና ሳላቀርብ አላልፍም፡፡ በአንጻሩ ደግሞ ትላንት ከለውጡ በፊት እንኳን እነሱን ደጅ ልንጠና ቀርቶ አጠገባቸው ለመድረስ እንኳን የምንጸየፋቸው፣ የተቀመጡበት የኃላፊነትና የአማካሪነት ቦታ የሀገርና የህዝብ ችግሮች ለመፍታት መሆኑ እምብዛም የሚያስጨንቃቸው የማይመስሉ፣ ራሳቸውን የኮፈሱ አድርባዮች፣ ከንቱና ግብዝ የመንግስት ባለሟሎች በዚህ ሂደት ለመታዘብ ችያለሁ።

    የሆነ ሆነ ይህ ከፍተኛ ችግር መፍትሄ እንዲያገኝና በውጭ የሚገኙትም ሆኑ በካምፕ ውስጥ የሚገኙት የንቅናቄያችን ሠራዊት አባላት ቢያንስ አቅም ባለው፣ ሠራዊቱ የሚገኝበትን ችግር ለማቃለል ብቃትና ተቋማዊ ቁመና ለዓመታት ባካበተ የመንግስት ኮሚሽን በኩል እንዲሆን የሚያስችል እርምጃ እንዲወሰድ በቅርብ ቀን መወሰኑን አዲስ አበባ በነበሩኩባቸው አራት ሳምንታት ከሚመለከታቸው የመንግስት ኃላፊዎች ጋር በተደረገ ውይይት አረጋግጫለሁ። ይህም እርምጃ ለወራት የቆየን ከባድ የህሊና ሸክም ያቃለለ ቢሆንም፣ አሁንም ከካምፕ ውጭ የሚገኙ የሠራዊቱ አባላት የሚገኙበትን ዘርፈ ብዙ ማኅበራዊ ችግሮች አስመልክቶ በየዕለቱ በርካታ መረጃዎች እየደረሰን በመሆኑ ከካምፕ ውጭም ሆነ ከካምፕ ውስጥ የሠራዊቱ አባላት ቃል የተገባላቸው እርዳታ እንዲደርሳቸው፣ የመልሶ ማቋቋሙ ሂደት በቶሎ እንዲጀመር፣ የንቅናቄው የሥራ አፈጻሚ ኮሜቴ እንዲሁም ጉዳዩ የሚመለከታቸው የመንግስት ኃላፊዎች የሚያስፈልገው ያልተቋረጠ ትኩረትና ክትትል እንዲያደርጉ በድጋሚ ለማሳሰብ እወዳለሁ።

    ሀገራችን ኢትዮጵያ ዘርፈ ብዙ ተግዳሮቶችና ህልውናዋን የሚፈታተኑ ስጋቶች የተጋረጡባት ከመሆኗም በሻገር ከምንጊዜውም በባሰ መልኩ መስቀለኛ መንገድ ላይ የምትገኝ መሆኑን በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ሁሉ የሚስማሙ ይመሰለኛል። ይህን አደጋ ለመቋቋም ደግሞ በርካታና ዘርፈ ብዙ ሕዝብ አቀፍ እንቅስቃሴዎች ያስፈልጋሉ። ስለዚህም ውስብስብ በሆኑና ስር በሰደዱ መጠነ ሰፊ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፓለቲካዊ ችግሮች አውድና ከባቢ ውስጥ ተዘፍቀው ለኢትዮጵያ ዴሞክራሲ፣ ፍትህና፣ የሕግ የበላይነትን ለማስፈን እየተደረገ በሚገኘው የለውጥ ጅማሮ እንዳይቀለበስ የለውጡን አራማጆች፣ ለውጡን ለማስቀጠል በተጨባጭ እርምጃዎች እስከተንቀሳቀሱ ድረስ ማገዝ አማራጭ የሌለው ነው ብዬ አምናለሁ።

    ሀገራችንን ቅርጫ ለማድረግ ሲሉ የ100 ሚሊዮን ህዝብ ዕጣ ፈንታ ላይ ቁማር የሚጫወቱ፣ የሕዝብን የተሻለ ህይወት፣ ለሁሉም የኢትዮጵያ ልጆች የታገሉለትን፣ የሚመኙትን ፍትህ፣ ነጻነትና የነገን ተስፋ እየረጋገጡ የሚገኙ እጅግ ራስ ወዳድ፣ ስግብግብ ህሊና ቢሶች፣ የኢትዮጵያን ልዩ ልዩ ማኅበረሶቦች አብሮነት አጥፍተው ለራሳቸው ጠባብ ብሄረተኝነት እጀንዳ ጥቅምና ስልጣን ለማምጣትም ሆነ ለማስቀጠል በየአካባቢው ትርምስ የሚፈጥሩ፣ ክቡር የሆነውን ሰብዓዊነት ረግጠው ወደ አራዊትነት በተጠጋ የለየለት ጽንፈኝነትና አክራሪነት የታወሩ ጥቂቶች፣ ከራሳቸው ግላዊ ፍላጎትና ጥቅም ውጭ ለሕዝብና የሀገር ደህንነት፣ ለሰላም፣ ለፍትህና፡ ለሕግ የበላይነት ምንም ቁብ የማይሰጡ የጥፋት ኃይሎች በአብዛኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች እንደአሸን በፈሉበት ሁኔታ ከኢትዮጵያዊነት ውጪ፣ ከፍትህ፡ ከእኩልነትና፣ ከሕዝብ አብሮነት የተለየ ሌላ አማራጭ እንደሌለ፣ ሌላ ሀገር፣ ሌላ ምድርም አለመኖሩን በሚገባ የተረዱ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ሁሉ በየአካባቢያቸው እያፈጠጠ፣ እያገጠጠ ከሚገኘውን የህልውና አደጋ ከእነዚህ አክራሪና ጽንፈኛ የጥፋት ኃይሎች ሊያመጡት ከሚችሉት የሀገራችንን የመኖር አለመኖር ህልውና የሚፈታተን የሲኦል ጎዳና ራሳቸውን፣ ቤተስባቸውንም ለመከላከል፣ ተከላካይ በሆነ መልኩ እርስ በእርስ መደራጀት፣ እንዲሁም ራስን በራስ ማደራጀትና፣ ብሎም ነቅቶ መጠበቅ ሌላው አስፈላጊና ወቅታዊ ተግባር ነው ብዬ አምናለሁ።

    ለአገራችን ሕልውና፣ ለሕዝባችን ሰላም፣ ፍትሕና ዴሞክራሲያዊ ስርዓት የሰፈነባት ኢትዮጵያ እንድትኖር የሚያስችል የፓለቲካ ስርዓት እንዲረጋገጥ የሚጨነቁ ኢትዮጵያውያን ሁሉ እልህ አስጨራሽ ሁኔታ ውስጥ ብንገኝም ከዚህም ከዚያም የሀገሪቱን ህልውና አደጋ ላይ እየጣሉ የሚገኙ አክራሪና ጽንፈኛ ብሄረተኞችና የለውጥ ቅልበሳ ቡድኖች ወጥመድ ሰላባ ላለመሆን በስልት፣ በሰከነ ጥበብና በሃገራዊ ኃላፊነት መንቀሳቀስ የግድ ነው ብዬ አምናለሁ። ለኢትዮጵያዊነት፣ ለሁሉም ኢትዮጵያዊያን ዜጎች እኩልነትና ሁለንተናዊ መብቶች የቆሙ የፓለቲካ ኃይሎች፣ የሲቪክ ተቋማት፣ እንዲሁም የፕሬስ ድርጅቶችን ማጠናከር እንዲሁ ሌላቅ የወቅቱ ዐቢይ ተግባራት ይመስሉኛል።

    በሀገራችን የተጀመረው ለውጥ ከመጣ ከጥቂት ወራት በኋላ ንቅናቄው የፓለቲካ ፓርቲ እንደሚሆን ስምምነት በተደረሰ ጊዜ የፓለቲካ ፓርቲ አመራርም ሆነ አባል ሆኜ ለመቀጠል ፍላጎት እንደሌለኝ በአመራሩ ላይ ለሚገኙ ሁሉ በተለያዩ ጊዜያት ገልጬ ነበር። እስካሁንም ድረስ የቆየሁት ከመሪዎች አንዱ ሆኜ እንዳገለግል ለመረጡኝ አባላትና የሠራዊት አባላት ባለኝ ኃላፊነትና ተጠያቂነት ቢያንስ ከኤርትራ በርሃና በኢትዮጵያም ውስጥ ሆነው በጨለማው ዘመን ለኢትዮጵያ አንድነትና ለሕዝብችን ነጻነት ህይወታቸውን ለመገበር ለቆረጡ እነዚህ ዛሬ በካምፕ ውስጥና ከካምፕ ውጭ የሚገኙ የሠራዊት አባላትና ታጋዮች ህይወት ተገቢውን መስመር እስኪይዝ ነበር።

    ቀደም ሲል መልቀቂያ አስገብቸ የነበረ ቢሆንም እንኳን የንቅናቄው ዋና ጸሀፊ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ጨምሮ የተለያዩ የንቅናቄው አመራሮች በኃላፊነቴ እንድቆይ በነበራቸው ፍላጎት፣ እኔም ከነሱ ጋር ባደረኳቸው ውይይቶች በቦታው መቆየቴ ሠራዊቱን ይጠቅማል ብዬ ስላመንኩ እስካሁን ድረስ በተሰጠኝ የኃላፊነት ቦታ ላይ የምችለውን እያገዝኩ ቆይቻለሁ። ሆኖም ለቆሙለት ዓላማ፣ ለንቅናቄያቸውና ለሀገራቸው ክብር መተኪያ የሌላት ህይወታቸውን ለመክፈል የቆረጡ የትግል ጓዶቸ ላለፉት 7 ወራት በከፍተኛ ችግሮች ውስጥ ወድቀው ማየት ለኔ እንቅልፍ የሚነሳ ጉዳይ መሆኑ አልቀረም።

    ለኢትዮጵያ አንድነት፣ ለዴሞክራሲና ለኢትዮጵያ ሕዝብ ሁለንተናዊ መብቶች መረጋገጥ የበኩሌን አስተዋጽኦ ሳደርግ ቆይቻለሁ። ባለፉት ሁለት አስርት አመታት በላይ በውጭው ዓለም በተደረገው ትግል ልዩ ልዩ የትግል መድረኮችን በመሥራችነት፣ በአባልነት፣ በአስተባባሪነት፣ እንዲሁም በአመራር ኃላፊነቶች የዜግነት ግዴታዬን ከሚጠበቅብኝ በላይ አስተዋጽኦ በማድረግ ለ26 ዓመታት ያልተቋረጠ የትግል አስተዋጽኦ አድርጌያለሁ። የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቭዥንን(ኢሳት) በማቋቋም፣ በመገንባት ሂደትና እስከ 2015 ድረስም በዋና ሥራ አስፈጻሚነት ፣ እሰከአሁኑ ድረስም በቦርድ ሥራ አስፈጽሚ አባልነት የበኩሌን አስተዋጽኦ ተወጥቻለሁ።

    ባለፉት 8 ዓመታት የአርበኞች ግንቦት 7 የአንድነትና ለዴሞክራሲ ንቅናቄ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባልና ልዩ ልዩ የሥራ ኃላፊነቶች ላይ በመሰማራት፣ እ.ኤ.አ ከመስከረም (September) ወር 2017 ከተደረገው የንቅናቄው ጉባኤ ላይ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል ሆኜ ከተመረጥኩኝ በኋላም የንቅናቄው የውጪው ዘርፍ ኃላፊ በመሆን እስካሁን ድረስ በቅንነትና በምችለው እቅም ኃላፊነቴን ተወጥቻለሁ። በአሁኑ ወቅት ከአርበኞች ግንቦት 7 የሥራ አስፈጻሚ ኮሜቴ አባልነት፣ እንዲሁም ንቅናቄው የውጭ ዘርፍ ኃላፊነት በገዛ ራሴ ፈቃድ መልቀቄን ለአርበኞች ግንቦት 7 አባላት፣ ደጋፊዎች፣ በልዩ ልዩ የትግል መድረኮች ለምታውቁኝ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ለማሳወቅ እወዳለሁ።

    የአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ በቅርብ ጊዜ ጉባኤ በማድረግ ይከስማል። አዲስ ሀገራዊና በኢትዮጵያዊነት፣ በዜግነትና በማኅበራዊ ፍትህ ላይ የቆመ የፓለቲካ ፓርቲ የምሥረታ ሂደት ወደ ማገባደጃው በመድረሱ በአዲሱ ፓርቱ ለሚመረጡ አመራሮች እንዲሁም አባላትና ደጋፊዎች ሁሉ ያለኝን ጽኑና መልካም ምኞቴን እገልጻለሁ። ለወደፊቱ ለኢትዮጵያ ሀገራችን እንዲሁም ለዓዝባችን ፋይዳና ጥቅም በሚያስገኙ ልዩ ልዩ ተግባራት ላይ በመሳተፍ እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ ዜጋ ድርሻዬን እንደምወጣ ለምታከብሩኝ፡ ለምትወዱኝና ለማከብራችሁና ለምወዳችሁ ወገኖቼ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ለማረጋገጥ እወዳለሁ። እዚህ ላይ የንቅናቄው ወዳጆችም ሆናችሁ ሌሎች እንድታውቁት ላሰምርበትም የምፈልገው በንቅናቄው አጠቃላይ የፓለቲካ ራዕይና ተልእኮ፣ በሚመሠረተው የፓለቲካ ፓርቲ ዓላማና ተልዕኮ፣ እንዲሁም ከማንም የንቅናቄው አመራር አባላት ጋር በግል ሆነ በፓለቲካ ምንም ዓይነት ቅራኔ የሌለኝ መሆኑን ለማረጋገጥ እወዳለሁ። ዘለአለማዊ ክብርና ሞገስ ለኢትዮጵያ አንድነት፣ ለዓባችን ነጻነትና፣ ለፍትህ ሲሉ አይተኬ የህይወት መስዋዕትነት ለከፈሉ የኢትዮጵያ ልጆች ሁሉ! ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!

    ነአምን ዘለቀ ቦጋለ
    ቨርጂኒያ፣ ዩናይትድ ስቴትስ ኦፍ አሜሪካ
    ማርች 18 ቀን፣ 2019

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ነአምን ዘለቀ


    Semonegna
    Keymaster

    በመቀሌ ከተማ በ147 ሚሊዮን ብር ካፒታል ሙሉ ብርሃን ኢንዱስቱሪና ንግድ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ያቋቋመው ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ምሶሶ ማምረቻ ፋብሪካ ከ200 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል ፈጥሯል።

    መቀሌ (ኢዜአ) – በ147 ሚሊዮን ብር ካፒታል የተቋቋመው ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ገመድ ተሸካሚ የኮንክሪት ምሶሶ ማምረቻ ፋብሪካ ምርት ማከፋፈል መጀመሩን አስታወቀ።

    “ሙሉ ብርሃን ኢንዱስቱሪና ንግድ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር” በሚል የተቋቋመው ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ምሶሶ ማምረቻ ፋብሪካ ከ200 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል ፈጥሯል።

    የፋብሪካው ሥራ አስኪያጅ አቶ እሥራኤል ብርሃኑ ለኢዜአ እንደገለጹት ፋብሪካው በአገር አቀፍ ደራጃ ያለውን የኮንክሪት ምሶሶ ችግር ለመፍታት ታሳቢ ተደርጎ የተቋቋመ ነው።

    ፋብሪካው በአሁኑ ወቅት በቀን እስከ 90 የሚደርስ ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ኃይል ተሸካሚ ምሶሶዎችን በማምረት ላይ ሲሆን በሙሉ አቅሙ ሥራ ሲጀምር በቀን እስከ 300 የተለያዩ ደረጃ ያላቸው ምሶሶዎችን የማምረት አቅም እንደሚኖረው ሥራ አስኪያጁ ተናግረዋል።

    ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ጋር በመነጋገር ፋብሪካው ምርቶቹን ለትግራይአማራአፋር ክልሎች ማከፋፈል መጀመሩን አቶ እሥራኤል አስታውቀዋል።

    ፋብሪካው ከአገር ውስጥ ስሚንቶ፣ አሸዋና ጠጠር የሚጠቀም ሲሆን ለምሶሶው መሥሪያ የሚውሉ ብረቶችን ከውጭ በማስገባት ለአገልግሎት ያውላል።

    ፋብሪካው በሚያመርተው ምርት መንግስት በከተማና በገጠር የኤሌክትሪክ ሽፋን ለማዳረስ እያከናወነ ላለው ሥራ አጋዥ መሆኑን ሥራ አስኪያጁ ተናግረዋል።

    የክልሉ መንግስት በቦታ አቅርቦትና ብድር በማመቻቸት እገዛ እንዳደረገላቸው የገለጹት አቶ እሥራኤል ፋብሪካው በሙሉ አቅሙ ማምረት እንዲችል ከውጭ ለሚመጡ ጥሬ ዕቃዎች መግዣ የውጭ ምንዛሬ አቅርቦት እንዲመቻችላቸው ጠይቀዋል።

    በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የትግራይ ቅርንጫፍ ሥራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ገብረመድህን የኮንክሪት ምሶሶ ማምረቻ ፋብሪካው ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ምርቶች ማምረት መጀመሩን ተናግረዋል።

    የኮንክሪት ምሶሶ ማምረቻ ፋብሪካው በመቀሌ ማምረት መጀመሩ ከአሁን ቀደም ከአዲስ አበባ ለማጓጓዝ ለትራንስፖርት ይወጣ የነበረውን ወጪ ይቀንሳል ብለዋል።

    ከፍትኛ የኤሌክትሪክ ምሶሶዎች ለ20 ዓመታት ዋስትና ያላቸው መሆኑን የገለጹት ሥራ አስፈፃሚው ካሁን በፊት ለአገልግሎት ይውሉ የነበሩ የባህርዛፍ ምሶሶዎች በጉዳት ምክንያት ያደርሱ የነበሩትን አደጋና የኤሌክትሪክ መቆራረጥ የሚቀንስ ነው።

    የትግራይ ክልል ኢንቨስትመንት ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሃፍቶም ፋንታሁን እንደገለጹት የምሶሶ ማምረቻ ፋብሪካው በመቀሌ ከተማ ለተለያዩ የኢንቨስትመንት ሥራዎች ቦታ ከተሰጣቸው ባለሀብቶች መካከል በፍጥነት ወደ ማምረት ሥራ መሸጋገር መቻሉ በአርያነቱ እንዲቀመጥ የሚያደርገው ነው።

    የትግራይ ክልል የተረጋጋ ሰላም ያለው በመሆኑ በርካታ የውጭና የአገር ውስጥ ባለሀብቶች በተለያዩ የኢንቨስትመንት ሥራዎች እየተሳተፉ መሆናቸውን የጽህፈት ቤት ኃላፊው ገልጸዋል።

    በመካኒካል ምህንድስና የተመረቀው ወጣት አማኑኤል ሀይሉ በፋብሪካው በመቀጠር በወር 6ሺህ ብር የወር ደሞዝ እየተከፈለው ይሠራል። በፋብሪካው የሥራ እድል በማግኘቱ ደስተኛ መሆኑን የሚናገረው ወጣት አማኑኤል ገቢ ማግኘት መጀመሩ ከቤተሰብ ጥገኝነት ወጥቶ የራሱን ቤተሰብ ለመመስረት መቻሉን ገልጿል።

    ወጣት ዙፋን ኪዳኑ በበኩሏ “ማኅበሩ በዘርፉ ኢንቨስት በማድረጉ የአካባቢውን ወጣቶች የሥራ አድል ተጠቃሚ አድርጎናል” ብላለች።

    በትግራይ ክልል በ2010 ዓ.ም 24 ቢልዮን ብር ካፒታል ያስመዘገቡ 1ሺህ 328 ባለሀብቶች በሥራ እንዳሉ ከክልሉ ኢንቨስትመንት ጽህፈት ቤት የተገኘ መረጃ ያመልክታል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    የኤሌክትሪክ ምሶሶ

Viewing 3 results - 16 through 18 (of 18 total)