Search Results for 'አማራ ክልል'

Home Forums Search Search Results for 'አማራ ክልል'

Viewing 15 results - 76 through 90 (of 120 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ደኢህዴን) ማዕከላዊ ኮሚቴ ላለፉት 10 ተከታታይ ቀናት ባካሄደዉ ስብሰባ ሀገራዊ የስላምና ፀጥታ ሁኔታን ከአህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ሁኔታ ጋር በማገናዘብ ገምግሟል።

    ከደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ደኢህዴን) ማዕከላዊ ኮሚቴ የተሰጠ መግለጫ

    ድርጅታችን የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ደኢህዴን) ባለፉት 28 ዓመታት የደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦችን አስተባብሮ በመምራት በክልሉ ዉስጥ የልማት፤ የሰላም፤ የዴሞክራሲ ድሎችን አስመዝግቧል። በሀገራችን ከሚገኙ ብሔሮች ብሔረሰቦች 70 በመቶዉ ይዞ የተደራጀ ነዉ። የደቡብ ብሔሮች፤ ብሔረሰቦችና፤ ሕዝቦች ክልል ሕዝቦችን በህብረ-ብሔራዊ አንድነት እየመራ የሚገኝ ዲሞክራሲያዊና ሕዝባዊ ድርጅት ነው። ይህም ክልላችን የብዝሀነት ማዕከል፤ የአብሮነትና የአንድነት ማሳያ እንዲሆን አድርጓል።

    ደኢህዴን ለሕዝቦች እንድነትና ለሀገር ግንባታ ግንባር ቀደም ሚናዉን የተወጣና እየተወጣ የሚገኝ ድርጅት ሲሆን ሀገራችን የገጠማትን ተግዳሮቶች ለመፍታት መፍትሄ የሚሆኑ ዉሳኔዎችን ያስተላለፈና ስኬቶችን ያስመዘገበ ድርጅት እንደሆነም ገምግሟል። በሀገራችን ያጋጠሙ ችግሮችን ለማለፍ በተደረጉ ትግሎች ከእህት ድርጅቶች ጋር በመሆን የራሱን ጉልህ ሚና የተወጣ ድርጅት ነዉ። በሀገራችን ኢትዮጵያ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ያገጠሙ ችግሮችን ለመፍታት በተደረጉ ትግሎች ሠላማዊ የስልጣን ሸግግር ለማድረግ ታሪካዊ ኃላፊነት ተወጥቷል። ስለሆነም ድርጅታችን ሀገራዊ ለዉጡ እዉን እንዲሆን ግንባር ቀደም ሚና የተወጣና ታሪካዊ ዉሳኔ ያስተላለፈ ድርጅት እንደመሆኑ ለቀጣይነቱም ግንባር ቀደም ሚናዉን እንዲወጣ ማዕካላዊ ኮሚቴዉ አጽንዖት ሰጥቷል።

    የደኢህዴን ማዕከላዊ ኮሚቴ ላለፉት 10 ተከታታይ ቀናት ባካሄደዉ ስብሰባ ሀገራዊ የስላምና ፀጥታ ሁኔታን ከአህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ሁኔታ ጋር በማገናዘብ ገምግሟል።

    አሁን ሀገራችን ያለችበት ሁኔታም በዝርዝር አይቷል። ሁኔታዉን ለመቀየር ሁሉንም ሕዝቦች በማረባረብ ሠላማችንን ማስከበር ከቻልን ግን ብሩህ ተስፋ እንዳለን በአፅንዖት አይቷል።

    የሠላምና የፀጥታ ሁኔታዉ ከመቼዉም ጊዜ በላይ ለመንግስት ብቻ የሚተዉ ሳይሆን የነቃ የሕዝብ ተሳትፎ ጭምር የሚጠይቅ መሆኑን በመገንዘብ ድርጅቱ ሕዝብን በማስተባበር የክልሉን ብሎም የሀገሪቱን የሠላምና የፀጥታ ሁኔታ አስተማማኝ ለማድረግ ግንባር ቀደም ሆኖ እንደሚታገል አስምሮበታል።

    ዛሬም ዋነኛዉ ጠላት ድህነትና ኃላቀርነት መሆኑን የገመገመዉ ማዕከላዊ ኮሚቴዉ ይህንን ሁኔታ ለመቀየር የሚደረገዉን ትግል የሚፈታተኑ ሁኔታዎች መግጠማቸዉን አይቷል። የልማትና መልካም አስተዳደር ስራዎች ትኩረት ማነስ የስራ አጥነትና ድህነት የኑሮ ዉድነት የወጣቶችና የሴቶች ተሳትፎና ተጠቃሚነት ዛሬም ያልተሻሻለ መሆኑን፡ ዘላቂ ሠላም የማረጋገጥና የሕዝቦችን ደህንነት የማረጋገጥ ጉዳይ ትኩረት የሚሹ ተግባራት መሆናቸውን ገምግሟል።

    የክልላችን ሕዝቦች መንግስታዊ አገልግሎት የማግኘት ዕድሉን በሚመለከቱ የተለያዩ የአደረጃጀት ችግሮች በየደረጃው እየፈታ መምጣቱን ማዕከላዊ ኮሚቴው ገምግሟል። የክልል እንሁን ጥያቄዎችን ለመፍታት ሳይንሳዊ ጥናት በምሁራን ቡድን ያስደረገው ድርጅታችን በጥናቱ ግኝት ላይም ሰፊ ውይይት በማካሄድ መግባባት ፈጥሯል። ድርጅታችን የክልሉን ሕዝቦች ጥያቄ በበቂ መረጃና ዕውቀት ላይ ተመስርቶ እና ሕዝቡን ባሳተፈ መንገድ ለመመለስ ላለፉት ሰባት ወራት ባስጠናው ጥናት መሰረት ምላሽ ለመስጠት የተወያየ ሲሆን የሁሉንም ሕዝቦች ተጠቃሚነት ያረጋገጠ ውሳኔም አስተላልፏል።

    ጥናቱ ደረጃውን የጠበቀ አሳታፊ እና ትክክለኛ ውሳኔ ላይ ለመድረስ በሚያግዝ አግባብ መመራቱንም አረጋግጧል። በጥናቱ ደኢህዴን የክልሉን ሕዝብ መምራት ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ የተገኙ ትሩፋቶች፣ ተግዳሮቶች፣ መንስዔዎችና የመፍትሄ አማራጮች የያዘ ስለመሆኑ በጥልቀት በመፈተሸ ለቀጣይ የድርጅት የመሪነት ሚና እና የሕዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ መሆኑን በጥንካሬ ወስዷል።

    በመሆኑም በወቅታዊ ሀገራዊ እና ክልላዊ የፖለቲካ እና የፀጥታ ሁኔታ እንዲሁም በክልሉ የሚነሱ ተጨማሪ ክልል ሆኖ የመደራጀት ጥያቄዎች ላይ ጊዜ ወስዶ በጥልቀት፤ ኃላፊነት በተሞላበትና በሰከነ ሁኔታ የመከረው የደኢህዴን ማዕከላዊ ኮሚቴ የሚከተሉትን ባለ 6 ነጥብ የአቋም መግለጫ አውጥቷል።

    1. ወቅታዊ ሀገራዊ የፖለቲካና የፀጥታ ሁኔታን በተመለከተ በእስካሁኑ ሂደት የታዩ አዎንታዊ ውጤቶችን የሚፈታተኑ ጉዳዮች መኖራቸውን የገመገመው ማዕከላዊ ኮሚቴ በድርጅታችን ኢህአዴግ መሪነትና በሕዝቦች ተሳትፎ የተጀመረው የለውጥ እንቅስቃሴ እንዳይቀለበስ ሁሉም አካላት በጋራ የኃላፊነት መንፈስ እንደሚገባቸው አስምሮበታል። በሀገር ደረጃ የተጀመረው የለውጥ እንቅስቃሴ ተስፋ የፈነጠቁ ጅምር ውጤቶች የታዩበት ሲሆን በጥንቃቄ ካልተያዘ የሀገርን ህልውና የሚፈታተኑና ሕዝባችንን ስጋት ውስጥ ሊያስገቡ የሚችሉ ነባራዊና ህሊናዊ ሁኔታዎች እየተስተዋሉ መሆናቸውን ተገንዝቧል። በቅርቡ የአማራ ክልል ከፍተኛ አመራሮች እና የሀገሪቱ የጦር መኮንኖች እስከ ህይወት ማጥፋት ድረስ የደረሰውን ጥቃት ድርጅታችን በፅኑ ያወግዛል፣ በፅኑም ይታገላል።
    2. በእህት ድርጅቶች መካከል ከድርጅታዊ ዲስፕሊን ውጪ የሚወጡ መግለጫዎች ይህንንም ተከትሎ እየተደረሱ ያሉ ድምዳሜዎች ከኢህአዴግ መርህ ውጪ መሆናቸውን በመገምገም የትኛውም ዓይነት የሃሳብ ልዩነቶችን እንደወትሮው ሁሉ በድርጅቱ ባህል መሠረት ማስተናገድ እንደሚገባ ታይቷል። በሌላ መልኩ ደኢህዴን በውስጡ ያሉ ችግሮችን ታግሎ የሚያርምና የሚያጋጥሙ ችግሮችና ፈተናዎችን ከሕዝቡ ጋር በመሆን የመፍታት ባህልና ልምድ ያለው ድርጅት ነው። ከዚህ ውጪ እኔ አውቅልሃለሁ በሚመስል መንገድ ከሩቅ የሚሰነዘሩ ሂደቱን ያልተከተለ አመራር የማይቀበል መሆኑን ማዕከላዊ ኮሚቴው ያስገነዝባል።
    3. ክልላዊ ወቅታዊ ፖለቲካና ፀጥታ ሁኔታ ልዩ ትኩረት የሚሻ መሆኑን ማዕከላዊ ኮሚቴው በዝርዝር ገምግሟል። ሀገራዊ ፖለቲካ እና ፀጥታ ድባብ ተከትሎ በክልሉ ውስጥ የሚታዩ አዝማማያዎች የህግ የበላይነት አደጋ ውስጥ የመግባት የኢ-መደበኛ አደረጃጀቶች እንቅስቃሴዎች ስርአት መያዝ ያለባቸው መሆኑን ተሰምሮበታል። በዚህ ሂደት ለታዩ ጉድለቶች ሀገራዊ ሁኔታ የራሱ አሉታዊ አስተዋዕፆ ያለው ቢሆንም ዋናው ችግር የድርጅታችን ውስጣዊ ሁኔታ መሆኑን ማዕከላዊ ኮሚቴው በጥልቀት ተወያይቷል። ከድርጅቱ ከፍተኛ አመራሮች ጀምሮ በየደረጃው ያለው አመራር ድርሻ ሰፊ መሆኑም ታይቷል። ስለሆነም እንደ ሀገር እና እንደ ክልል ከገባንበት ያለመረጋጋት ለመውጣት የድርጅቱ ውስጣዊ ጥንካሬ ወሳኝ መሆኑን የድርጅቱ አመራሮች በከፍተኛ የሃላፊነት መንፈስ እና ሕዝባዊ ውግንና መንቀሳቀስ የሚጠይቀን ወቅት ላይ መሆናችንን መተማመን ላይ ተደርሷል። በመብት ጥያቄ ሽፋን የሚደረጉ የትኛውንም ኢ-መደበኛ እንቅስቃሴዎችን ስርዓት ለማስያዝ እንዲሁም የሕዝቦችን ሰላምና ፀጥታ ማረጋገጥ እና የህግ የበላይነትን ማስከበር ለድርድር የማይቀርብ መሆኑን ማዕከላዊ ኮሚቴው ድምዳሜ ላይ ደርሷል።
    4. በክልል የመደራጀት ጥያቄን በተመለከተ የሕዝቦች ህገ-መንግስታዊ መብት መሆኑን ድርጅታችን ይገነዘባል። በክልል የመደራጀት ጥያቄ ሲነሳ የነበረው ከአንድ አካባቢ ብቻ ባይሆንም ጥያቄውን በጥናት ላይ ተመስርቶ ምላሽ ማግኘት እንዳለበት ድርጅቱ በአስረኛ ድርጅታዊ ጉባኤ በወሰደው አቋም መሰረት በዝርዝር ሕዝቡን ያሳተፈ ጥናት ሲያደርግ ቆይቷል። በጥናቱ የቀረቡ አማራጮችን በጥልቀት በመመርመር፣ የሕዝቡን የጋራ ዘላቂ ጥቅም የሚያረጋግጠውን አማራጭ በመውሰድ የክልል አደረጃጀት ጥያቄዎች በሚመለሱበት አግባብ ላይ አቋም ተወስዷል። በክልላችን መላው ሕዝብ ምክክርና ውይይት የሚያደርግበት ሆኖ በአንድ በኩል በጥናቱም የተገኘውን የክልሉ ሕዝቦች አብሮ የመቀጠል ፍላጎትን ባከበረ በሌላ ጎኑ ደግሞ ጉባኤውን ውሳኔ ተግባራዊ ባደረገ መንገድ እና ኃላፊነት በተሞላበት ሁኔታ የመምራት ኃላፊነት ለመወጣት ማዕከላዊ ኮሚቴው ተስማምቷል።
    5. የደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በህብረ-ብሔራዊነት ላይ እየተገነባ ያለው የፌዴራል ሥርዓት ትሩፋቶችን ያስመዘገበ ሲሆን በሂደቱ የታዩ ተግዳሮቶች በማረም ሀገራችን በደረሰችበት የዕድገት ደረጃ በማሻሻል ለፌዴራል ሥርዓቱ ይበልጥ መጎልበትና ቀጣይነት የምንታገል መሆኑን አቋም ተወስዷል። ከሁሉ በላይ ህበረ-ብሔራዊ ኢትዮጵያዊ አንድነታችንን ለማጎልበት ማዕከላዊ ኮሚቴው አጽንኦት ሰጥቷል።
    6. በእያንዳንዱ አከባቢ ያለውን የልማት ሁኔታ በተመለከተ በድርጅታችን መሪነት በክልላችን የተመዘገቡ የልማት ውጤቶች እንደተጠበቁ ሆነው በተለያየ መልኩ የሚገለጽ ፍትሃዊ ተጠቃሚነት የመልካም አስተዳደር እና የአመራር ሥርዓታችን ላይ የሚታዩ ችግሮች መፈታት እንዳለባቸው ተወስዷል። ከዚህም በመነሳት በክልሉ ሁሉም አከባቢዎች የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማረጋገጥና ፍትሃዊ ተጠቃሚነት ችግሮችን ለመፍታት የሚያስችሉ አዳዲስ አሰራሮችን ተግባራዊ በማድረግ በክልሉ ያሉ ሕዝቦች በጋራ መልማት እንዳለብን በመግባባት ሕዝቡን ባሳተፈ ሁኔታ የክልሉን ህገ-መንግስት ከማሻሻል ጀምሮ ሌሎች ዝርዝር የህግ ማዕቀፎች እንዲዘጋጁ አቋም ተወስዷል።

    ውድ የድርጅታችን አመራሮች፥ አባላትና ደጋፊዎች፣ ድርጅታችን ደኢህዴን ዛሬ ለደረሰበት ደረጃ ያበረከታችሁት ድርጅታዊ አስተዋጽኦ ከገባንበት ፈተና ለመውጣት ያስቻለ ሆኗል። የድርጅት ቀጣይነት ለማረጋገጥ ከመቼውም ጊዜ በላይ ቁርጠኛ አቋም የተወሰደበት ወቅት ላይ ደርሰናል። ስለሆነም የተጀመረው ድርጅታዊ ሪፎርም በማጠናከር እንደወትሮ ሁሉ ግንባር ቀደምትነት ሚናችሁን አጠናክራችሁ እንድትቀጥሉ ጥሪ ያቀርባል።

    የተከበራችሁ የክልላችን ሕዝቦች፥ በተለያዬ መልኩ የሚገለጽ የልማት፣ የመልካም አስተዳደር እና የአደረጃጀት ጥያቄዎች ውስጥም ሆናችሁ ምላሽ እንዲሰጣችሁ ላሳያችሁት ትዕግስት ድርጅቱ ምስጋና ያቀርባል። ይህ ትዕግስታችሁ በመሪ ድርጅቱ እና በመንግስት ላይ እምነት በመጣል የሚታዩ ችግሮች በጋራ ቆመን እንድንፈታ የበኩላችሁን አስተዋጽኦ እንዳበረከታችሁ ያሳየን ነው። ችግሮችን በውይይትና በምክክር የመፍታት አማራጭ ብቻ በመከተል ዛሬ ለደረስንበት ደረጃ ያበረከታችሁት አስተዋጽኦ ታሪክ የሚረሳው አይደለም። ዛሬም ድርጅታችን በጽኑ መስመር ላይ በጽናት በመቆም የሚያጋጥሙትን ፈተናዎች በድል ለመወጣት ያለውን ዝግጁነት ያረጋግጣል። ስለሆነም በድርጅቱ ላይ ያላችሁን እምነት በማጎልበት ለውጡን ከዳር ለማድረስ የሚጠበቅባችሁን ሕዝባዊ አስተዋጽኦ እንድታበረክቱ ጥሪ ያቀርባል።

    የተከበራችሁ የክልላችን አርሶ እና አርብቶ አደሮች፥ የክልላችን ሕዝብ አብዘኛውን ቁጥር በመያዛችሁ ብቻ ሳይሆን ባለፉት ዓመታት ለተመዘገበው የኢኮኖሚ ዕድገት፣ ለሕዝቦች ፍትሃዊ ተጠቃሚነት እና ለድርጅታችን ቀጣይነት ዋልታና ማገር መሆናችሁን ነጋሪ አያሻውም። ያገኛችሁትን ትሩፋቶች ጠብቃችሁ በቀጣይ ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር መዋቅራዊ ችግሮች እንዳሉ ተገንዝበናል። በመሆኑም ከድህነት ለመላቀቅና ለተሻለ ህይወት የምታደርጉትን ጥረት ከጎናችሁ በመቆም አለኝታነታችንን ለማረጋገጥ ዛሬም የፀና እምነት እንዳለን እናረጋግጣለን።

    የተከበራችሁ የክልላችን ወጣቶች፥ በክልሉ በሁሉም አከባቢዎች የወጣቶች የተሳትፎና የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ጥያቄ አንገብጋቢና የተለየ ምላሽ መስጠት የሚጠይቅ መሆኑን በጥልቀት ያየው ማዕከላዊ ኮሚቴው በቀጣይ የክልሉ የልማት ኮሪደሮችን ለይቶ የጋራ ሀብቶችን በማልማት፣ ወጣቱን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚሰራ መሆኑን አቅጣጫ አስቀምጧል። በመሆኑም በክልላችን ያለውን የጋራ ፀጋ መሰረት ያደረጉ አዳዲስ የልማት ቀጠናዎችን በመፍጠር የወጣቱን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ቆርጠን መነሳታችንን እንገልጻለን። ስለሆነም የክልላችን ወጣቶች ከድርጅታችን ጎን በመሰለፍ የማይተካ አዎንታዊ ሚናችሁን እንድትወጡ ጥሪ ያቀርባል።

    የተከበራችሁ የክልላችን ሴቶች፥ እስካሁን ለተገኙ ትሩፋቶች ሚናችሁ የላቀ ሲሆን ባጋጠመን ተግዳሮቶች ቀዳሚ ተጎጂ መሆናችሁ ግልጽ ነው። በመሆኑም የሴቶችን ተጠቃሚነት ይበልጥ ለማስፋት በእስካሁኑ ጉዟችን የነበሩ ጉድለቶችንም ለማረም ከምንም ጊዜ በላይ ዝግጁነታችንን እናረጋግጣለን። የክልላችን ሴቶች ከህብረተሰቡ ውስጥ ከቤተሰብ ጀምሮ ያላችሁን ግዙፍ ሚናችሁን ይዛችሁ ከድርጅታችን ጎን ሆናችሁ ትግላችሁን እንድታጠናክሩ ጥሪ ያቀርባል።

    የተከበራችሁ የክልላችን ምሁራን፥ ድርጅታችን ባስመዘገበው ስኬቶች ለነበራችሁ አዎንታዊ አስተዋፅኦ ክብር አለን። አሁንም ከሰፊው የዕውቀት ማዕድ ካገኛችሁት ልምድና የህብረተሰብ ችግሮች ላይ መፍትሄ ለመስጠት ያላችሁ የመተንተን አቅማችሁን ሳትነፍጉ ለሀገራችሁና ለሕዝባችሁ ለወገናችሁ ለማበርከት ከጎናችን እንድትሰለፉ ጥሪ ያቀርባል።

    ውድ የሀገራችን ባለሀብቶችና የንግዱ ማኅበረሰብ፥ በክልላችን ብሎም በሀገራችን ለተመዘገበው ልማት የጀርባ አጥንት በመሆን ለምታበረክቱት ሁለንተናዊ አስተዋጽኦ ምስጋናችንን እናቀርባለን። በክልላችን ያለውን የመልማት ጸጋ በጋራ ለማልማትና ሕዝባችን ተጠቃሚ ለማድረግ ከምንግዜውም በላይ ተዘጋጅተናል። ስለሆነም በግልና በጋራ ሆናችሁ አብረን ለመስራት ጥሪ ያቀርባል።

    ውድ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች፥ የክልላችን ሕዝቦች መለያና መታወቂያ የሆነውና እየተገነባ የመጣውን ደቡባዊ ስነ ልቦና ለክልላችን ሕዝቦችም ሆነ ለሀገር ግንባታ ያለው ፋዳ ትርጉም ያለው ነው። ይሁንን እምቅ አቅም ይበልጥ በማውጣት ረገድ ኪነ ጥበብ ያለው ሃይል ላቅ ያለ በመሆኑ የሕዝቦችን ትስስርና አንድነት በቀጣይነት ለመገንባት እንድታውሉ ጥሪ ያቀርባል።

    የተከበራችሁ እሀት ደርጅቶችና አጋሮች፥ ደኢህዴን/ኢህአዴግ የክልሉን ሕዝቦች ሰላም ልማት ዴሞክራሲ ብሎም ለሀገራዊ አንድነትና ክብር የበኩሉን አዎንታዊ ሚና ሲጫወት የቆየ ድርጅት ነው። በሀገር ግንባታ ሂደት የበኩሉን ሚና እየተወጣ እንደመጣ ሁሉ ዛሬም ለሀገራችንና ለሕዝቦቿ እንዲሁም ለዜጎቿ ክብር መብት ነፃነት ብልጽግና ዴሞክራሲያዊ አንድነት ተግቶ ይታገላል።በዚህ ሂደት ከጎናችን እንደቆማችሁ ሁሉ ዛሬም የተለመደው አዎንታዊ ሚናችሁ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ ያቀርባል።

    የተከበራችሁ ተፎካካሪ ፓርቲዎች፥ በተለያየ ሙያ ውስጥ ያላችሁ በሙሉ ደኢህዴን የስካሁን ስኬቶቹን ጠብቆ ማቆየት ሳይሆን ያጋጠሙትን ተግዳሮቶች በመወጣት ለሀገራችን መፃኢ ተስፋ አዎንታዊ ሚና ለመጫወት ቆርጦ ተነስቷል። ይህ ሂደት የሁላችሁም አዎንታዊ ድጋፍና እይታ ይፈልጋል። ስለሆነም በድርጅታችን የሚቀመጡ አቅጣጫዎችና ውሳኔዎች መመዘን ያለባቸው ከሕዝቡ ሰላምና የህግ የበላይነት ዘላቂ ጥቅም አንጻር መሆናቸው ይታወቃል። ስለሆነም ገንቢ ሚናችሁ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ ያቀርባል።

    የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ደኢህዴን)

    የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ - ደኢህዴን


    Semonegna
    Keymaster

    ማለቂያ የሌላቸው ብዙ ብዙ የውሽት ትርክቶች ሰፊውን የአማራ ሕዝብ ጥቅምም ሆነ ኢትዮጵያን እንደ ሀገር ለማስቀጠል ፈጽሞ የማይበጅ፣ እንዲያውም በአማራው ክልልም ሆነ በበርካታ አካባቢዎች በጎጥና በአካባቢም ጭምር ወርዶ የእርስ በእርስ ግጭቶች ሊወልድ የሚችል አደጋ ያዘለ ሁኔታ እያደገ መሆኑን የሰሞኑ ክስተት ያመላክታል።

    ኢትዮጵያ ሀገራችንን ከጥፋትና ከእልቂት ለማዳን ቆም ብለን በሰከነ ሁኔታ ማሰብና መራመድ እጅግ አስፈላጊና ወሳኝ ጊዜ ላይ እንገኛለን።
    (ነአምን ዘለቀ)

    የአማራ መሰረት ያላችሁ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ፣ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ ሁሉ፥

    ዛሬ ከፊታችን ያፈጠጠው መሰረታዊ ጥያቄ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድን እንደግፍ ወይንም አንደግፍ የሚለው አይደለም። የዛሬው ማዕከላዊ ጥያቄ፣ የዛሬው ዋና ጥያቄ ‘ኢትዮጵያ እንደ ሀገር ትቀጥል ወይንስ አትቀጥል’ የሚለው ነው። አብይ መጣ፣ ከበደ፣ ዋቅጅራ፣ ወይንም ግደይ፣ እቺ ታሪካዊት ሀገር፣ እቺ መከረኛ ሀገር፣ እትብታችን የተቀበረባት፣ የምንወዳት፣ ሌት ተቀን የምንጨነቅላት ኢትዮጵያ ሀገራችን፣ በተማሩ ልጆቹ በተደጋጋሚ የተከዳና የተበደለ፣ በድህነትና በችጋር የሚማቅቀው፣ ነገር ግን ጨዋና ኩሩ የሆነው እብዛኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ አብሮነት እንዴት ይቀጥል ነው ዋናው፣ መሰረታዊው፣ ማዕከላዊው ጥያቄ፣ የዛሬው ጥያቄ፣ የአሁን ሰዓት ዋነኛ ጥያቄ ይሄው ነው።

    ሰሞኑን “ኣማራው ተጠቃ፣ ተበደለ፣ ተገፋ” በሚል ሽፋን፣ በአብይ አህመድ “የኦሮሞ/ የኦዴፓን የበላይነት” ለመጫን እየሠራ የሚገኝ የትሮጃን ፈረስ ተደርጎ በሰፊው የሚነዛው ጥላቻ፣ የሚረጨው ሰፊ መርዝና ቅስቀሳ ሰፊው የአማራ ሕዝብን ጥቅም (በአማራው ክልል ብቻ ሳይሆን በኦጋዴን፣ በሀረር፣ በባሌ፣ በአርሲ፣ በኢሉባቡር፣ በወለጋ፣ ወዘተ… በሌሎች አካባቢዎች የሚገኘውን ከ10 ሚሊዮን በላይ አማራኛ ተናጋሪ ማኅበረሰብ) የአማራውን ሕዝብ ደህንነትና ዋስትና ለማረጋገጥ ምን ያህል እንደሚጠቅም፡ ህልውናውንም እንደምን አርጎ ለማረጋገጥ እንደሚያገለግል ቆም ብሎ የታሰበበት አለመሆኑ ግልጽ ነው።

    በትናንሽና ፍጹም የማይናበቡ፣ የጋራ ራእይ፣ የጋራ ስልት (strategy) በሌላቸው በየጎጡ የተደራጁና አማራን እንወክላለን በሚሉ እንደ አሸን የፈሉ ቡድኖች የሚደረገው ይሄው በጣም የከረረ ጥላቻ፣ ማለቂያ የሌላቸው ብዙ ብዙ የውሽት ትርክቶች ሰፊውን የአማራ ሕዝብ ጥቅምም ሆነ ኢትዮጵያን እንደ ሀገር ለማስቀጠል ፈጽሞ የማይበጅ፣ እንዲያውም በአማራው ክልልም ሆነ በበርካታ አካባቢዎች በጎጥና በአካባቢም ጭምር ወርዶ የእርስ በእርስ ግጭቶች ሊወልድ የሚችል አደጋ ያዘለ ሁኔታ እያደገ መሆኑን የሰሞኑ ክስተት ያመላክታል። ይህ ደግሞ የሶማሊያ፣ የሊቢያ፣ የሶሪያን እልቂትና መበታተን የሚደግም፣ የሚያስከነዳም የምድር ሲኦል እንደሚፈጥር በተረጋጋ አዕምሮ ልብ ያለው ሁሉ ልብ ሊል ይገባል።

    ይልቅዬ በዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ የአማራው ዘላቂ ጥቅም የሚጠበቅበት፣ የሁሉም ሕዝቦች አብሮነት የሚረጋገጥበት፣ የኢትዮጵያ እንድነት የምናስቀጥልበት ሁኔታዎችና መንገዶችን፣ ሰከን ብሎ ማሰብ፣ በስሜት ሳይሆን በስትሪቴጂያዊ አስተሳሰብ፣ በጥበብና በስልት፣ በጋራ፣ ሰጥቶ በመቀበል እንጂ፣ ሰሞኑን በሶሻል ሚዲያ እንደሚራገበው አማራውን እንወክላለን የሚሉ በልዩ ልዩ ቡድኖች የተደራጁም ያልተደራጁም አክራሪ ብሄርተኞች እጅግ በሚያጦዙት መንገድ ፈጽሞ ሊሆን እንደማይችል የሮኬት ሳይንስ አውቀት የማያስፈልገው ሃቅ ይመስለኛል።

    ሰደድ እሳቱ ሲጀመር እያንዳንዱ ቤት አንደሚያንኳኳ ቆም ብሎ ማሰብ፣ ከሌሎች ሀገሮች ውድመት፣ ውድቀትና፣ ምስቅልቅል መማር ሰዓቱ ከመድረሱ በፊት ቆም በሎ ማሰብ ብልህነት፣ አስተውሎትም ነው። ስለዚህ ሰላም፣ መረጋጋት፣ ማዕከላዊ መንግስት የተከፈተውን ምህዳር ተጠቅሞ በሰላማዊ፣ ሕጋዊ፣ ስልታዊና ስትራቴጅካዊ አካሄድ በሰላማዊና በተደራጀ መልክ የአማራውን ሕዝብ ጥቅም፣ ደኅንነት ለማሰጠበቅ መንቀሳቀስ እንጂ፥ የሰፈር የጦር አበጋዞች (በሶማሊያና በሊቢያ እንዳየነው “warlords”)፣ ከሕግና ከስርዓት ውጭ የራሳቸውን ፍላጎት በጉልበት ለመጫን የሚፈልጉ አፈንጋጮችን (በሶሪያ እንደተከሰተው “rogue military commanders”) በማጀገን የአማራውን ሕዝብ ተገፍቻለሁ፣ ተጠቅቻለሁ ብሎ እንዲነሳሳ ሰፊ ቅስቀሳ ማድረግ ታሪክ ይቅር የማይለው፣ የአማራውን ሕዝብንም ሆነ፣ የአማራው ማኅበረሰብ በደም፣ በሕይወቱ፣ በላቡ ገብሮ፣ ለግንባታዋ ብዙ የተዋደቀላት ትላቋና ታሪካዊቷ ኢትዮጵያን የማይበጅ፣ ወደ ጥፋት፣ ወደ እርስ በእርስ ጦርነት፣ አልፎም ወደ ውድመትና ወደ መበታተን ሊያደርሰን የሚችል ሂደት እየተመለከትን ነው።

    በዚህ ሁሉ ትርምስ ደግሞ ዛሬ የሚፈነጥዘው፣ ይህን ሰፊ ትርምስ (turmoil) ለራሱ በሚገባ እየተጠቀመ የሚገኘው፥ እንደ አንድ ሰው የቆመው፣ እስከ አፍንጫው የታጠቀውም ሕዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ (ሕወሃት) ብቻ ነው። ሌላው ተከፋፍሏል፣ በአብይ አህመድ ላይ በሚወርደው የጥላቻ ውርጅብኝም ሀገሪቷን እንደ ሙጫ አጣብቆ ደካማ ቢሆንም የያዘውን ስርዓተ መንግስት (state)፣ ማዕከላዊ መንግስቱንም ለማዳከም ብዙ የድንጋይ ናዳ አየወረደ ነው። በየዕለቱ በተደራጀም በአልተደራጀም መልኩ እየተደረገ የሚገኘው ይሄው ነው።

    ሕዝብን እርስ በእርስ ሊያባላ፣ ሊያጫርስ የሚችል፣ ምንም አማራጭ ሃሳብ፣ ራእይና፣ ድርጅትም ሆነ ስትራቴጂ ለማቅረብ የማይችሉ፣ ነገር ግን አማራውን እንወክላለን የሚሉ፣ እንዲሁም በአብይ አህመድ ላይ የግል ጥላቻና ጥርጣሬ ያላቸው በርካታ ግለሰቦችና ቡድኖች ጭምር ተሳታፊ የሆኑበት ይሄው በከፍተኛ ስሜት በማጦዝ፣ የተገፊነትን ስሜት በመቀስቀስ ላይ የተመሰረተ ሰፊ ዘመቻ ያነጣጠረውና እየሄደ ያለው በዚሁ ግብ ላይ ነው። የእነዚህ ቡድኖች ምንም መናበብም ሆነ፣ የጋራ አማራጭ፣ እንዲሁም ለሀገራችንና ለሕዝባችን አሻግሮ የሚያይ ራእይ ማቅረብ ያማይችሉ፣ እርስ በእርሳቸው እንኳን ተቀምጠው በአግባቡ በምክኒያታዊነት መነጋገርና መደማመጥ የማይችሉ፣ ግለሰቦች፣ ቡድኖችና ኃይሎች የሚገፋውና የሚረጨው መርዝ ሁሉንም (እነሱንም ጨምሮ) ወደ ፍጹማዊ ኪሳራ፣ የዜሮ ድምር ፓለቲካ (zero-sum game) የሚወስድ፣ ማንም ምንም ወደማያተርፍበት የሲኦል መንገድ አገራችንንና ሕዝባችንን እየገፋ መሆኑን ሁሉም ኢትዮጵያዊ ዛሬ ላይ በሚገባ መገንዘብ አስፈላጊ የሆነበት ወቅት ላይ የደረሰን ይመስለኛል። ነገ በጣም ይዘገያል የዘገየ (too little too late) ይሆናል።

    ከዚህ አሳፋሪና ለሀገራችን ህልውና ብሎም ለኢትዮጵያ 105 ሚሊዮን ሕዝብ አብሮነት፣ ለኢትዮጵያ አንድነት ቀጣይነት እጅግ አስጊ ሁኔታ በተፈጠረበት በአሁኑ ወቅት አሸናፊ የሚሆነው ማነው? ሁሉንስ ድልና ወርቅ አፋሽ የሚሆነው ማነው? ብቸኛ ተጠቃሚስ ይኖራል ወይ? በሰላም ደሴት በደስታና በፍሰሃ ሊኖር የሚችለውስ ማነው? ስለእውነት፡ ስለሀቅ ለመናገር ማንም እንደማይሆን፣ ማንም እንደማይተርፍ በእርግጠኝነት መተንበይ ይቻላል። ሁላችንም ተያይዘን ወደ እልቂት፣ ወደ ሁለንተናዊ ውድቀት፣ ወደ ሲኦል እያዘገምን ይመስለኛል።

    ስለዚህ ወግኖቼ፥ ቆም ብለን ማሰብ ብልህነት ነው። ነገን ማሰብ፣ በተረጋጋና በምክንያታዊነት ዛሬን በትዕግስትና በስልት መራመድ አሰፈላጊና ወሳኝም ናቸው። የአማራውንም ጥቅምና ደኅንነት፣ የሌላውን ኢትዮጵያዊ ማኅበረሰቦች/ብሄሮች፣ አብሮነት፣ የአማራውንም ሆነ የሌላውን እኩልነት፣ መብት፣ ደህንነት፣ ለማምጣት በጥንቃቄ፣ በሕግ አግባብ፣ በሰላማዊ መንገድ፣ አስቦ፣ በአስተውሎ መራመድ የነገን ውድመት፣ የሀገር መበታተን፣ የሕዝብንም እልቂት የሚከላከል ሁሉም ሕዝቦች በጋራ በሰላም፡ በዴሞክራሲ፣ በሕግ የበላይነት፡ በእኩልነት የሚኖሩባት ኢትዮጵያን የሚያረጋግጥልን ብቸኛ መንገድ መሆኑን ሁሉም ኢትዮጵያዊ ዜጋ፣ ሁሉም የአማራ መሰረት ያለው ኢትዮጵያዊ ሁሉ በውጭም በሀገር ውስጥም ሊያጤነው የሚገባ ይመስለኛል። የመጨረሻው ደወል እያቃጨለ መሆኑ እየተሰማኝ ነው። ኢትዮጵያ እንደ ሀገር፣ ሁሉም ሕዝቦች፣ ማኅበረስቦች፣ በእኩልነት፣ በፍትህ፣ በሕግ የበላይነት የሚኖርባት ኢትዮጵያን ሁሉም ኢትዮጵያዊ፣ የአማራ መሰረት ያለው ኢትዮጵያውያን ሁሉ በጥሞና አስበን፣ አስተውለን፣ አቅደን መንቀሳቀስና ሀገራችንን ከጥፋት የማዳኛው ወቅት አሁን ነው፣ ዛሬ ነው።

    እግዚአብሔር ሀገራችንና ሕዝባችንን ይጠብቅልን፤ ስላሙን ያውርድልን።
    ነአምን ዘለቀ

    የአማራ ሕዝብ


    Anonymous
    Inactive

    የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ዶ/ር አምባቸው መኮንን መገደላቸው ተረጋገጠ
    —–

    የአማራ ክልል ፕሬዝደንት ዶ/ር አምባቸው መኮንን ትላንት (ሐምሌ 15 ቀን 2011 ዓ.ም.) በነበረው የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ተከትሎ መገደላቸውን የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን አስታውቋል።

    አቶ አምባቸውን ጨምሮ የርዕሰ መስተዳድሩ አደረጃጀት ዘርፍ አማካሪ የሆኑት አቶ እዘዝ ዋሴም በደረሰው ጥቃት ሕይወታቸውን ማጣታቸው ታውቋል። ጥቃቱ የተፈፀመው ግለሰቦቹ ስብሰባ ላይ ባሉበት ወቅት እንደሆነ ኢቲቪ አስታውቋል።

    አቶ አምባቸው መኮንን የቀድሞውን የክልሉን ፕሬዝደንት አቶ ገዱ አንዳርጋቸውን በመተካት የተሾሙት የካቲት 29 ቀን 2011 ዓ.ም. ነበር።

    የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (አዴፓ) ሐምሌ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ተፈፀመ በተባለው የመንፈቅለ መንግሥት ሙከራ እጃቸው አለበት የተባሉ ሰዎችን በቁጥጥር ሥር ማዋሉም ተሰምቷል።

    የክልሉ ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ ብርጋዴር ጀኔራል አሳምነው ፅጌ መንፈቅለ መንግሥቱን አቀነባብረዋል ተብለው በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ፓርቲው አስታውቋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ትላንት ከእኩለ ለሊት በኋላ በብሔራዊው ቴሌቪዥን ቀርበው በሰጡት መግለጫ የአማራ ክልል ባለስልጣናት የተገደሉት እና የቆሰሉት በስብሰባ ላይ እያሉ እንደነበር መናገራቸው አይዘነጋም።

    Anonymous
    Inactive

    በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ላይ የተደረገውን የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ የፌደራል መንግሥት አወገዘ
    —–

    በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ላይ የተደረገው የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ የሀገሪቱን ሕገ መንግሥት የሚፃረር፣ የክልሉ ሕዝብና መንግሥት ለረጅም ጊዜ የታገሉለትን ሰላምና መረጋጋት ለመንጠቅ የተደራጀ በመሆኑ የፌደራል መንግሥት ሙሉ በሙሉ እንደሚያወግዘው የጠቅላይ ሚንስትር ፅህፈት ቤት አስታወቀ።

    የፌደራል መንግሥት የጸጥታ መዋቅር የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራውን ሙሉ በሙሉ በቁጥጥር ሥር አውሎ በፈጸሙት አካላት ላይ ተገቢውን ርምጃ እንዲወስድ ትእዛዝ ተቀብሎ ተፈጻሚ በማድረግ ላይ ይገኛል። ይህ ጥቃት በመንግሥት መዋቅር ላይ ብቻ ሳይሆን በአማራ ሕዝብ ላይ የተቃጣ መሆኑን በመገንዘብ የክልሉ ሕዝብ አካባቢውን በንቃት እንዲጠብቅና ተረጋግቶ ሁኔታዎችን እንዲመለከት ጥሪ ቀርቧል።

    ይህን ሕገ ወጥ ሙከራ ክልሉ ብቻ ሳይሆን ማንኛውም ክልልና መላው ኢትዮጵያዊ ሊያወግዘው የሚገባ ሲሆን የፌደራል መንግሥት የታጠቁ ቡድኖችን ሕገ ወጥ እንቅስቃሴ የመቀልበስ፣ የመግታትና በቁጥጥር ሥር የማዋል ሙሉ ዐቅም ያለው መሆኑን ያረጋግጣል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን

    Semonegna
    Keymaster

    የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ዓላማው ክልሉን ለማተራመስና የህዝቡን ህልውና አደጋላይ ለመጣል ያለመ መሆኑን ገልጸው፥ በአሁኑ ወቅት የፌዴራል መንግስት ሁኔታውን የማስተካከልና ክልሉን የማረጋጋት ትዕዛዝ እንደተሰጠው አቶ ንጉሱ ጥላሁን ገልጸዋል።

    አዲስ አበባ (ኢዜአ) – በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ መደረጉን በኢፌዴሪ ጠቅላይ የሚኒስቴር ፅህፈት ቤት የፕሬስ ሴክሬታሪያት ኃላፊ አቶ ንጉሱ ጥላሁን ገለጹ። አቶ ንጉሱ ሐምሌ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ምሽት ላይ ለኢትዮጵያ ቴሌቪዥን (ኢቲቪ) በሰጡት መግለጫ በክልሉ መንግስት ላይ የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ተደርጓል።

    በተደራጀ ሁኔታ በመንግስት መዋቅር ላይ ጥቃት ለመሰንዘር የተሞከረው የተደራጀ እንቅስቃሴ ከሽፏል ነው ያሉት አቶ ንጉሱ ጥላሁን ።

    የአማራ ክልል ወደ መረጋጋት እየመጣ ባለበትና እና ሕዝቡ ቀደም ሲል ያነሳ የነበረውን የህግ የበላይነት ጥያቄ ለመመለስ እየተሠራ ባለበት ወቅት የተሰነዘረው ጥቃት የክልሉ መንግስት ብቻ ሳይሆን የአማራ ሕዝብ ላይ የተሞከረ ነው ብለዋል።

    ሙከራው ክልሉን ለማተራመስና የህዝቡን ህልውና አደጋላይ ለመጣል ያለመ መሆኑን ገልጸው፥ በአሁኑ ወቅት የፌዴራል መንግስት ሁኔታውን የማስተካከልና ክልሉን የማረጋጋት ትዕዛዝ እንደተሰጠው ገልጸዋል።

    የፌዴራል መንግስቱ ጣልቃ በመግባት ይህን መሰሉን ተግባር የመግታት ሥራ እንደሚሠራና ህብረተሰቡም አካባቢውን በንቃት እንዲጠብቅ መልዕክት አስተላልፈዋል።

    ጸረ-ህገ መንግስትና መፈንቅለ መንግስቶች እንዲሁም በታጠቁ ኃይሎች የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ተቀባይነት እንደሌላቸው ገልጸው፥ ክልሉን ወደነበረበት ሰላማዊ ሁኔታ ለመመለስ ህብረተሰቡ ከመንግስት ጋር በትብብር እንዲሠራ ጥሪ አቅርበዋል።

    አቶ ንጉሱ ጥላሁን በዚህ ጉዳይ ላይ ከኢትዮጵያ ቴለቭዥን ጋዜጠኛ ጋር ያደረጉትን አጭር ቃል ምልልስ እዚህ ጋር በመጫን ያዳምጡ።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ


    Semonegna
    Keymaster

    ሰናይ መልቲሚዲያ በበሳል ባለሙያዎችና በፕሬስ እድገት ውስጥ ከፍተኛ ሚና በተጫወቱ አንጋፋና ወጣት ጋዜጠኞች አስተባባሪነት የተቋቋመ የሕዝብ የሚዲያ ነው።

    ትላንት፣ ዛሬ እና ነገን እንደ ድልድይ የሚያስተሳስር ፣ የኢትዮጵያን ታሪክ፣ የዛሬን ተጨባጭ ሁኔታ ከግምት አስገብቶ፣ ነገ ላይ የተሻለች ኢትዮጵያን ለመፍጠር የሚረዱ አዳዲስ መርሀግብሮችን (ፕሮግራሞች) እና አቀራረቦችን ማስተዋወቅና አሁን በሥራ ላይ ያሉ የመገናኛ ብዙኃን ክፍቶችን መሙላት ዋንኛ ዓላማዉ በማድረግ፣ ሕዝብ በእኩልነት ሃሳቡን መግለጽ የሚቻልበት ሚዲያ ነው። ለዚህም “ሰናይ” ብለን ብዙኃኑ ባለው አቅሙ የድርሻው ባለቤት ሆኖ የእኔ የሚለውን ታላቅ የመልቲሚዲያ ተቋም ይፋ ለማድረግ እንወዳለን።

    ሰናይ መልቲሚዲያ የሕዝብ፣ ለሕዝብ፣ በሕዝብ የሆነ የመጀመሪያ ሚዲያ፤ እያንዳንዱ ዜጋ ያለብሔር ልዩነት፣ ያለጾታ፣ ያለእድሜና ክልል ገደብ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በሰናይ ቴሌቪዥን (ሰናይ ቲቪ)፦

    • የተሻለ ፕሮግራም የሚሰራበት የራሱ ቲቪ አክስዮን ባለድርሻ ይሆናል ፤ምርትና አገልግሎት የሚያስተዋውቅበት ቲቪ አክስዮን ባለድርሻ ይሆናል፤የመረጃ፣ የቁም-ነገር እና የመዝናኛ ፍላጎትንና ጥምን የሚያረካ ቲቪ አክስዮን ባለድርሻ ይሆናል፤
    • የሰናይ ቲቪ የመጀመሪያው የሕዝብ ሚዲያ ኔትወርክ (network) ሲሆን በመጀመሪያ በቴሌቭዥን ሳተላይት ስርጭት ጀምሮ በመቀጠል ወደ ሬድዮ፣ ድረ-ገፅ እና በሶሻል ሚዲያ (social media) የሚያካትት ይሆናል፤
    • በሰናይ ቲቪ እያንዳንዱ ዜጋ ካለበት ቦታ የኔ በሚለው መልኩ በቀጥታ እንዲሳተፍና እቅድ ውስጥ መካተት የሚችልበትን ሁኔታ ይፈጥራል፤ እውነተኛና ነፃ አማራጭ ሚዲያ ይሆናል። ድምፅ አልባ ለሆነውም ለኢትዮጵያ ሕዝብ ሃሳቡን በነፃነት የሚገልጽበት መንገድ ይከፈታል፤ የተለያዩ አመለካከቶችና መልዕክቶች የሚተላለፉበት ጭምር ይሆናል።

    ሰናይ መልቲሚዲያ የተመሰረተው እየታሰሩ፣ እየተፈቱ ለሕዝብ መሰዋዕትነት ሲከፍሉ በቆዩ ነባር የነፃው ፕሬስ ጋዜጠኞች አስተባባሪነት፤ ብዙኃኑ ሕዝብ ሊገዛው በሚያስችል መልኩ ሰላሳ አምስት ሺህ (35,000) አክስዮኖችን በማቅርብ ሲሆን፤ እያንዳንዳቸው አንድ ሺህ ብር ዋጋ ያላቸው በአጠቃላይ የሰላሳ አምስት ሚሊዮን ብር ዕጣ ለሽያጭ አቅርበዋል። በዚህም መሰረት የአንድ አክስዮን ዋጋ 1,000.00 (አንድ ሺህ) ብር ሲሆን፤ ዝቅተኛውና አንድ ሰው ሊገዛ የሚችለው የአክስዮን መጠን 5,000.00 ብር (አምስት ሺህ ብር) ዋጋ ያላቸው አምስት ዕጣዎች ሲሆን፤ አንድ ሰው ሊገዛ የሚችለው ከፍተኛው የአክስዮን ብር መጠን 2,800,000.00 ( ሁለት ሚሊየን ስምንት መቶ ሺህ ብር) ዋጋ ያላቸው 2,800 ( ሁለት ሺህ ስምንት መቶ) የአክስዮን ዕጣዎች ናቸው። ይህ ማለት፤ ማንም ወገን ከስምንት ከመቶ በላይ አክስዮን አንዳይገዛ ገደብ አለበት። ሰናይ መልቲሚዲያ በአንድ ወገን ቁጥጥር ስር እንዳይወድቅ የሚደረግበት ማዕቀፍ ተበጅቷል።

    ሰናይ ቲቪ የማንኛውንም የፖለቲካ ወገንተኝነትን የማያስተናግድ፣ የግለሰቦች የፖለቲካ እምነት የማያንጸባርቅ፣ ፍጹም ገለልተኛ ሚዲያ ነው። በመሆኑም፤ ማንኛውም ሰው፣ ከፖለቲካ ፓርቲዎች እና የሃይማኖት ተቋማት በስተቀር፣ የአክስዮን ባለድርሻ መሆን ይችላል። ለበለጠ መረጃ የፕሮጀክት አማካሪውን “ጌት አማካሪዎች” (GET Business & Investment Consultants) የንግድና ኢንቨስትመንት ማማከር፣ ድርጀቱን በግንባር በመቅረብ ወይም በስልክ-ቁጥር +251 (011) 8 12 12 33/34 በመደወል መረጃ ማግኘት ትችላላችሁ።

    ምንጭ፦ ጌት አማካሪዎች/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ሰናይ መልቲሚዲያ


    Anonymous
    Inactive

    የተከሰተውን የአተት ወረርሽኝ ለመቆጣጠር ግብረ ሃይል ተቋቋመ
    —–

    በአምስት ክልሎች የተከሰተውን የአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት (አተት) ወረርሽኝ ለመቆጣጠር ግብረ ኃይል መቋቋሙን የኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት አሰታወቀ።

    በአምስት ክልልች በተከሰተው የአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት (አተት) ወረርሽኝ እስከአሁን የ15 ሰዎች ሕይወት ማለፉን የኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት አስታወቀ ፡፡

    ወረርሽኙን በአፋጣኝ ለመቆጣጠር የሚያስችሉ የህክምና ግብአቶች በሁሉም ክልሎች ወደሚገኙ የኢትዮጵያ የመድኃኒት አቅርቦት ኤጀንሲ መጋዘኖች መላካቸውንም ኢንስቲትዩቱ ገልጿል፡፡

    እስካሁን ድረስ በኦሮሚያ 138፣ በአማራ 198፣ በሱማሌ 33 እና በትግራይ 8፤ በድምሩ 377 ሰዎች በአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት (አተት) ተይዘዋል ብሏል ኢንስቲትዩቱ።

    ምንጭ፦ ኢቢሲ

    Semonegna
    Keymaster

    ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ከዓርብ ጀምሮ እስካሁን በውል ባልታወቀ ምክንያት የተቀሰቀሰው ግጭት እስከዛሬ (ሰኞ ግንቦት 19 ቀን 2011 ዓ.ም.) ድረስ አለመረጋጋቱን ተማሪዎቹ ገልጸዋል።

    ደብረ ማርቆስ (ቢቢሲ አማርኛ)– በአማራ ክልል ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ በተፈጠረ ግጭት አንድ ተማሪ መሞቱን ተማሪዎች ለቢቢሲ ገለጹ። ሟች ሰዓረ አብርሃ እንደሚባልና የሦስተኛ ዓመት የምጣኔ ሀብት ትምህርት ክፍል (economics department) ተማሪ እንደነበረ ቢቢሲ አማርኛ ዘግቧል።

    በዩኒቨርስቲው ከዓርብ ጀምሮ የተቀሰቀሰው ግጭት እስከዛሬ (ሰኞ ግንቦት 19 ቀን 2011 ዓ.ም.) ድረስ አለመረጋጋቱን ተማሪዎቹ ገልጸዋል።

    የደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ የሕዝብ ግንኙነት እና ኮሙኒኬሽን ኃላፊ አቶ ደሳለው ጌትነትም በተቋሙ ከባለፈው አርብ (ግንቦት 16 ቀን) 12 ሰዓት ጀምሮ ግጭቶች መኖራቸውን አረጋግጠዋል።

    በዚህም አርብ ግንቦት 16 ላይ 3 ልጆች ጉዳት እንደደረሰባቸው ተናግረው ልጆቹ አሁን ሆስፒታል ይገኛሉ ብለዋል። የተጎዱት ተማሪዎች በባህር ዳር እና አዲስ አበባ ሪፈራል ተጽፎላቸው ወደዚያው መወሰዳቸውንም ጨምረው ያስረዳሉ። በግጭቱ ሁለት ተማሪዎች በድንጋይና በስለት ጉዳት እንደደረሰባቸው የዓይን እማኞቹ ለቢቢሲ አረጋግጠዋል።

    በተፈጸመበት ጥቃት ምክንያት አንደኛው ተማሪ ወዲያውኑ ህይወቱ ማለፉንና ሌላኛው ተማሪ ደግሞ ለሕክምና እርዳታ ወደ ባህር ዳር መወሰዱን ከተማሪዎቹ ለመረዳት ተችሏል።

    የረብሻውን ምክንያት እስካሁን ማረጋገጥ አልቻልንም ያሉት የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊው አርብ ዕለት ተሳትፎ የነበራቸውን የተወሰኑ ልጆች ፖሊስ ተከታትሎ ከግቢ ውጭ ይዟቸው ፖሊስ ጣቢያ ስለሚገኙ ጉዳያቸው እየተጣራ ነው በማለት የግጭቱ መንስዔ ከዚያ በኋላ ተጣርቶ የሚታወቅ ይሆናል ብለዋል።

    በአሁኑ ሰዓት በዩኒቨርሲቲው አዳራሽ የተጠለሉ ተማሪዎች እንዳሉ የተገለፀ ሲሆን ትላንት የሟችን አስክሬን ለመሸኘት የተሰበሰቡ ተማሪዎችም “ትምህርቱ ይቅርብን ወደ መጣንበት መልሱን” በማለት ለዩኒቨርሲቱው ፕሬዚዳንት ጥያቄ ማቅረባቸውን ነግረውናል።

    የዚህን ዜና ተጨማሪ መረጃ ቢቢሲ አማርኛ ላይ ማንበብ ይቀጥሉ

    ከዚያው ከአማራ ክልል ሳንወጣ፥ የደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ በምዕራብ እና በማዕከላዊ ጎንደር ዞኖች ለተፈናቀሉ ወገኖች ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ ማድረጉን የአማራ ብዙሃን መገናኛ ድርጅት (አብመድ) ዘግቧል። በቀጣይም ከ967 ሺህ ብር በላይ ድጋፍ ለማድረግ መዘጋጀቱን ዩኒቨርሲቲው አስታውቋል።

    ደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ ለአብመድ በጻፈው ደብዳቤ እንዳመላከተው ተፈናቃዮችን መልሶ ለማቋቋም ከዚህ በፊት በአማራ ክልል በሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ፎረም በኩል የ1 ሚሊዮን ብር ድጋፍ አድርጓል። አሁን ደግሞ የዩኒቨርሲቲው ሠራተኞች 967ሺህ 786 ብር ከወር ደመወዛቸው አዋጥተው ድጋፍ አድርገዋል።

    የተፈናቀሉ ወገኖችን ለማቋቋም በሚደረገው አገራዊ እና ክልላዊ የገንዘብ ማሰባሰብ ሂደት ተማሪዎችም የበኩላቸውን አስተዋፅኦ ማበርከታቸውንም ዩኒቨርሲቲው አስታውቋል።

    ከዚህ በፊት ሠራተኞች እና ዩኒቨርሲቲው የተፈናቀሉ ወገኖችን መልሶ ለማቋቋሙ አንድ ሚሊዮን ብር በአማራ ክልል በሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ፎረም በኩል ድጋፍ ማድረጉም ታውቋል።

    ምንጮች፦ ቢቢሲ አማርኛ እና አብመድ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– በአማራ ክልል የተለያዩ ወረዳዎች የአተት ወረርሽኝ (acute watery diarrhea /AWD/) ምልክት መታየቱን የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ የአተት ወረርሽኙን አስመልከቶ በሰጠው መግለጫ፥ በአማራ ክልል በሰሜን ጎንደር እና ዋግህምራ ዞኖች በተለያዩ ወረዳዎች እየተደረጉ ባሉ የቅኝት ሥራዎች የአተት ወረርሽኝ መከሰቱ የታወቀ ሲሆን የወረርሽኙን መንስዔ ለማረጋገጥ የላብራቶሪ ምርመራ እየተካናወነ መሆኑን አስታውቋል።

    ከዚህ ጋር ተያይዞ የአንድ ታማሚ ናሙና ቫይብርዮ ኮሌራባክቴሪያ (Vibrio cholera bacteria) የተገኘበት ሲሆን ወረርሽኙን ለማረጋገጥ በተጨማሪ ናሙናዎች ላይ የላብራቶሪ ምርመራ እንደሚከናወንም ኢንስቲትዩቱ አስታውቋል።

    ከሚያዝያ 27 ቀን ጀምሮ በአማራ ክልል በዋግህምራ ዞን በአበርጌሌ ወረዳ 58 ሰዎች በበሽታው የተጠረጠሩ ሲሆን በሰሜን ጎንደር ዞን በጠለምት ወረዳ 90 ሰዎች፣ በበየዳ ወረዳ ደግሞ 4 ሰዎች በበሽታው ተጠርጥረዋል።

    እንደ ኢንስቲትዩቱ መግለጫ፥ በአጠቃላይ በክልሉ በበሽታው 151 ሰዎች የተጠረጠሩ ሲሆን ሁሉም በበሽታው የተጠረጠሩ ህሙማን በአቅራቢያው ለዚህ አገልግሎት ብቻ ተብሎ በተቋቋሙ ጊዚያዊ የሕክምና ማዕከላት በቂ ሕክምና እንዲያገኙ የተደረገ ሲሆን፤ በጠለምት ወረዳ ግን 3 ታካሚዎች በሕክምና ላይ እያሉ ህይወታቸው አልፏል።

    በፌደራል፣ በክልልና በዞን ደረጃ ፈጣን ምላሽ ሰጪ የሕክምና ቡድን ወደ አበርጌሌ፣ ጠለምትና በየዳ ወረዳዎች ተልኮ ምላሽ በመስጠት ላይ እንደሚገኝና የዓለም ጤና ድርጅትና ድንበር የለሽ የሃኪሞች ቡድንም በቦታው በመገኘት ድጋፍ እየሰጡ መሆኑም ተገልጿል።

    ከላይ ወደተጠቀሱት ወረዳዎች አስፈላጊ የሕክምና መስጫ መሣሪያዎች፣ መድኃኒቶችና መመርመሪያዎች እንዲቀርቡ መደረጉም ነው የተጠቆመው።

    በአጎራባች ወረዳዎች ወረርሽኙ ቢከሰት በቂ ሕክምና ለመስጠት የሚያስችሉ መድኃኒቶችና የሕክምና ግብአቶች በፍጥነት ማቅረብ እንዲቻል በጎንደር፣ በደሴና በሽሬ በሚገኙ የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅርቦት ኤጀንሲ መጋዘኖች እንዲከማቹ መደረጉንም ኢንስቲትዩቱ አስታውቋል።

    ከዚህ ጋር ተያይዞ ሕብረተሰቡ፡ ወረርሽኙን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የመፀዳጃ ቤት በመሥራት እና በአግባቡ በመጠቀም፣ የመመገቢያ፣ የመጠጫ እና የውሃ ማስቀመጫ እቃዎችን በንጹህ ውሃ በማጠብ እና ከድኖ በማስቀመጥ ከዝንቦችና ከበካይ ነገሮች በመጠበቅ፣ ለማንኛውም አገልግሎት የሚውልን ከጉድጓድ፣ ከምንጭ፣ ከወንዝ እና ከመሳሰሉት የተቀዳ ውሃን በማከም ወይም በማፍላት በመጠቀም፣ ምግብ ከማዘጋጀት፣ ከማቅረብ፣ ከመመገብ በፊት፣ ከመፀዳጃ ቤት መልስ እና ሕፃናትን ካፀዳዱ በኋላ እጅን በመታጠብ፣ ምግብን በሚገባ አብስሎ በመመገብ፣ ከድኖ እና በንጹህ ቦታ በማስቀመጥ ከዝንቦችና ከሌሎች ነፍሳት ንክኪ በመጠበቅ ራሱንና ቤተሰቡን ከተላላፊ በሽታዎች በመከላከል የበኩሉን ሚና እንዲወጣ ጥሪ ቀርቧል።

    የአጣዳፊ ተቅማጥና ትውከት (አተት) ወረርሽኝ በተበከለ ውሃ ወይም ምግብ አማካይነት የሚከሰት ሲሆን ይህንንም ከሚያመጡ ተህዋሲያን መካከል ኮሌራን የሚያስከትለው ቪቢሮ ኮሌሬ የተሰኘው ባክቴሪያ ይገኝበታል።

    በአሁኑ ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ የኮሌራ ወረርሽኝ በህንድ፣ በየመን፣ በኔፓል ፣ በካናዳ ቫንኮቨር ደሴት እንዲሁም በአህጉራችን አፍሪካ በዘጠኝ ሀገራት ማለትም በካሜሩን፣ በኬኒያ፣ በሶማሊያ፣ በሞዛምቢክ፣ በዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮነጎ፣ በታንዛኒያ፣ በሊቢያ፣ በዙምባብዌ እና በዛምቢያ የተከሰተ ሲሆን ሀገራቱ ችግሩን ለመቅርፍ እየሰሩ ናቸው።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የአተት ወረርሽኝ A WHO/UNICEF Risk Communication team member explains AWD prevention and control to health workers (PHOTO: WHO Africa)


    Semonegna
    Keymaster

    መንግስት በሀገር ውስጥ የተለያዩ የሥራ ዕድሎችን በማስፋፋት ለሥራ ፈላጊ ዜጎች አስፈላጊውን ጥቅም ለማዳረስ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል። መሥራት ለሚችሉ ዜጎች ሁሉ በሀገር ውስጥ ላሉ የሥራ ዕድሎች ቅድሚያ በመስጠት ሠርተው የሚለወጡበትን ሁኔታዎች በማመቻቸት ዜጎችን ተጠቃሚ በማድረግ ላይ ይገኛል።

    ኢትዮጵያ ውስጥ ሠርቶ ለመኖር በርካታ መልካም አጋጣሚዎች አሉ። ለዚህም ምሳሌ የሚሆኑ በሀገራቸው ሠርተው የተለወጡ በርካታ ወጣቶችን መጥቀስ ይቻላል።

    ከዚህ ባለፈ ወደ ውጭ ሀገራት ለሥራ መሄድ የሚያስቡ ዜጎች እራሳቸውን ከአቻ ግፊትና ከሕገ-ወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎች ሊጠብቁ ይገባል። ዜጎች ስለሚሄዱበት ሀገር ስላለው እውነታ ያላቸው ግንዛቤና መረጃ ውስንና የተዛባ በመሆኑ ከመሄዳቸው በፊት ስለሚሄዱበት ሀገር ባህል፣ ወግና ልማድ መረዳትና እና የዜጎችን መብት ደህንነትና ክብር ለማስጠበቅ ሲባል በኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የወጣውን አዋጅ ቁጥር 923/2008 ጠንቅቆ ማወቅ ያስፈልጋል።

    ለጉዞ ከመነሳታችን በፊት ምን ማወቅ ይጠበቅብናል?

    ወደ ውጭ ሀገር ሄደን ለመሥራት በምናስብበት ወቅት ጊዜ ሰጥቶ ማሰብ ይገባል። ለምን እንደምንሄድ፣ ከሄድን በኋላ የሚያጋጥሙንን መልካምና መጥፎ አጋጣሚዎች እንዴት መቋቋምና ማለፍ እንደሚገባን፣ የምንሄድበትን ሀገር ባህል፣ ወግ፣ ልማድና ስርዓት እንዴት ተላምደን መኖር እንደምንችል፣ የሠራንበትን ገንዘብ ወደ ሀገራች እንዴት መላክና መቆጠብ እንደምንችል፣ ኮንትራታችንን ጨርሰን መቼ ወደ ሀገራችን መመለስ እንዳለብን አስቀድመን ማቀድ ያስፈልጋል።

    በአዋጅ ቁጥር 923/2008 መሠረት በውጭ አገር ለሥራ የሚሰማሩ ዜጎች እድሜያቸው ከ18 አመት በላይ የሆኑ፣ 8ኛ ክፍል ያጠናቀቁ (ወደ 9ኛ ክፍል የተዛወሩ)፣ በሚሄዱበት የሥራ መስክ ስልጠና ወስደው የብቃት ማረጋገጫ ያገኙ፣ የቅድመ ጉዞ ስልጠና ወስደው ሰርተፊኬት የያዙ፣ የጤና ኢንሹራንስ የተገባላቸው፣ ሙሉ የጤና ምርምራ ያደረጉና ከወንጀል ነጻ ሊሆኑ ይገባል።

    ይህን ያሟሉ ዜጎች በአስቀጣሪ ኤጀንሲ በኩል ወይም በራሳቸው አማካኝነት ሥራውን በማፈላለግ ማለትም በቀጥታ ቅጥር አስፈላጊውን የቅጥር ፎርማሊቲ በማሟላት ቪዛውን አግኝተው መሄድ ይችላሉ። ብዙ ጊዜ በቀጥታ ቅጥር የሚጓዙ ሠራተኞች መደበኛ ስልጠና የወሰዱና ከቤት ሠራተኝነት ውጭ በልዩ ልዩ ሙያዎች የሰለጠኑ ሲሆን የሚሠሩትም በካምፓኒና በልዩ ልዩ አነስተኛ የቢዝነስ ተቋማት ውስጥ ነው። ከዚህ በፊት በውጭ ሀገር ሠርተው የተመለሱ ልምድ ይኖራቸዋል ተብሎ ስለሚታሰብ መረጃ ማቅረብ የሚችሉ ከሆነ ስልጠናውን መውሰድ ግዴታ ባይሆንም የብቃት ማረጋገጫ ሰርተፊኬት ማቅረብ ይኖርባቸዋል።

    ለሥራ የት ሀገር ነው መሄድ የሚቻለው?

    ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በቤት ሠራተኝነት የሚሄድ ከሆነ ሊጓዝ የሚችለው በኤጀንሲዎች አማካኝነት ብቻ መሆኑን ሊረዳ ይገባል። የሥራ ስምሪት ማድረግ የሚችለውም አገሪቷ የሁለትዮሽ ስምምነት ወደተፈራረመችባቸው ሀገራት ብቻ ነው። የሁለትዮሽ ስምምነት የተፈፀመባቸው መዳረሻ ሀገራት ለጊዜው ሳውዲ አረቢያ፣ ኳታርና ጆርዳን ሲሆኑ ከሌሎች አገሮች ጋር የሚደረገው ስምምነትም በሂደት ይቀጥላል።

    ስምምነት በተፈፀመባቸው ሀገሮች የደመወዝ መጠን ስንመለከት ከኳታር መንግስት 1200 ለቤት ሠራተኛና 1300 ለእንክብካቤ (care giver) የኳታር ሪያል፣ ከጆርዳን መንግስት ለጀማሪ 225 ዶላር፣ ልምድ ላላው 250 ዶላር፣ ከሳውዲ አረቢያ መንግሰት ጋር 1000 የሳውዲ ሪያል እንዲሆን ስምምነት ላይ ተደርሷል።

    በሠራተኞችና በአሠሪዎች የሚሸፈኑ ወጪዎች

    አንድ ሠራተኛ በሥራ ለመሰማራት አስፈላጊውን መስፈርት ካሟላና ብቁ ከሆነ በአዋጁ የተደነገጉ የቅጥርና ምልመላ መንገዶችን በመከተል አስፈላጊውን መፈጸም እና ወጪዎችን መሸፈን ይገባል።

    1. አሠሪው ወይንም ኤጀንሲው የሚሸፍናቸው ወጪዎች

    በአሠሪው የሚሸፈኑ ወጪዎች ሠራተኛውን ወደ ተቀባይ አገር ለማድረስ፣ በተቀባይ አገር ያለችግር እንዲቆይና እንዲሠራ ለማድረግ፣ እንዲሁም በሥራ ላይ ደህንነቱ የተጠበቀ እንዲሆን የሚወጡ ወጪዎች ናቸው።

    እነርሱም የተቀባይ አገር የመግቢያ ቪዛ፣ የደርሶ መልስ መጓጓዣ፣ የሥራ ፍቃድ፣ የመኖሪያ ፍቃድ፣ የሥራ ውል ማጽደቂያ ክፍያዎች፣ የመድህን ዋስትና ሽፋን እንዲሁም በኢትዮጵያ ውስጥ ለሚገኝ የተቀባይ አገር ኤምባሲ ወይም ቆንስላ ጽህፈት ቤት የሚከፈል ከቪዛና ከሰነድ ማረጋገጥ ጋር የተያያዘ ማናቸውም ወጪዎች ናቸው።

    1. በሠራተኛው የሚሸፈኑ ወጪዎች

    አንድ ሠራተኛ ለሥራ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ሀገራት በሚጓዝበት ወቅት የሚያወጣው ወጪ በአብዛኛው በህይወት ዘመኑና በማህበራዊ ህይወቱ ውስጥ የትኛውም ሰው ስለሚጠቀምባቸው የሚያወጣቸው ወጪዎች ናቸው።

    እነርሱም ለልደት ሰርተፊኬት፣ ለፓስፖርት፣ ለክትባት፣ ለህክምና ምርመራ፣ ለሙያ ብቃት ማረጋገጫ፣ ከወንጀል ነፃ ማስረጃ ማረጋገጫ ወጪዎች ናቸው። እነኝህ ክፍያዎች በሙሉ አገልግሎቱን ለሰጡ ሌሎች መሥሪያ ቤቶችና ተቋማት የሚከፈል እንጂ ምልመላውን ለሚያከናውነው ኤጀንሲ የሚከፈል አይደለም። ኤጀንሲው ምንም አይነት ክፍያ ከሠራተኛው ቢጠይቅ ህገወጥ ያደርገዋል።

    ይሁን እንጂ ለሥራ ወደ ውጭ አገር ለመሄድ አስፈላጊ ሁኔታዎች ተጠናቀው ያለበቂ ምክንያት ሠራተኛው ወደ ሥራ ባይሰማራ ከቅጥሩ ጋር በተያያዘ አሠሪው ያወጣውን ወጪ ሠራተኛው እንዲከፍለው ሊጠይቅ ይችላል። በተመሳሳይ መንገድ በተራ ቁጥር 2 ላይ የተጠቀሱትን ወጪዎች ሠራተኛው አውጥቶ በራሱ ጉድለት ባልሆነ ምክንያት በሥራ ላይ ካልተሰማራ ኤጀንሲው ወይም አሠሪው የሠራተኛውን ወጪ የመተካት ግዴታ ይኖርበታል።

    ለውጭ አገር ለሥራ ስምሪት የሚሰጡ ስልጠናዎችና ማሰልጠኛ ተቋማቱ

    ለውጭ አገር ሥራ ስምሪት የሚሰጡ ስልጠናዎች ሶስት ሲሆኑ እነሱም በቤት አያያዝ (Household Service) በቤት ውስጥ ሥራ (Domestic Help) እና በእንክብካቤ ሥራ (Care Giving) ናቸው።

    የእነዚህ ሙያዎች የስልጠና መሳሪያዎች፣ የሙያ ደረጃ፤ ሥርዓተ ትምህርት እና የብቃት ማረጋገጫ ምዘና መሳሪያዎች ሲዘጋጁ ለማንኛውም ዜጋ እንዲያገለግል ሲሆን ወንድም ሆነ ሴት በፍላጎቱ ሊሰለጥን ይችላል። ሠልጣኞች ስልጠናውን በግላቸው ሊሠሩበት፣ በአገር ውስጥ ሊቀጠሩበት እንዲሁም ወደውጭ አገር ሊሰማሩበት እንደሚችሉ ሊገነዘቡና በምልመላ ወቅትም ሊነገራቸው ይገባል። በተጨማሪም በስልጠናው የተሳተፈ ሁሉ የብቃት ምዘናውን ያልፋል ማለት አይደለም፣ የብቃት ምዘናውን ያለፈ ሁሉ ቀጣሪ ያገኛል ማለትም አይደለም። በመሆኑም በተጠቀሱት ሙያ እንዲሰለጥኑ የተደረጉ ሁሉ ወደአረብ ሀገር መሄድን እንደመብት ሊያዩት አይገባም።

    ይሁን እንጂ ወደአረብ አገር መሄድ የሚፈልጉ ሰልጣኞች ከላይ በተጠቀሱት ሦስት ሙያዎች ከሰለጠኑ በኋላም የብቃት ምዘና ማረጋገጫ ተፈትነው ማለፍና ሰርተፊኬት መያዝ ይኖርባቸዋል። ስልጠናው በየክልላቸውና በአቅራቢያቸው በሚገኙ በተመረጡ ማሰልጠኛ ተቋማት ይሰጣል። ስልጠናው በየክልላቸውና አቅራቢያቸው የመሰጠቱ ጠቀሜታም የሠራተኞች ምልመላ በየክልላቸው የሚካሄድ በመሆኑ፣ አስፈላጊ መረጃዎችን ለማጣራትና ለማረጋገጥ፣ የዜጎችን ደህንነትና ክብር በቅርብ ለመከታተል እና ከስልጠና፣ ከምልመላ ጋር ተያይዞ ለአላስፈላጊ ወጪና የመብት ጥሰቶች እንዳይጋለጡ ያግዛል።

    ስልጠናን በተመለከተም፣ የመንግስት ማሰልጠኛ ተቋማት ትምህርቱን በነፃ የሚሰጡ ሲሆን ማንኛውም ሰልጣኝ በክልሉ በሚገኝ የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ወይም በየዞኑና ክፍለ ከተማው ወይም ወረዳዎች በሚገኙ የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ጽህፈት ቤቶች በመመዝገብ ለየማሰልጠኛዎቹ በመላክ እንዲሰለጥኑ ይደረጋል።

    በተጨማሪም የመንግስት ማሰልጠኛ ተቋማት የተደራሽነትና የአቅም ውስንነት ስላለባቸው በፌደራልና በክልል በሚገኙት የቴ/ሙ/ት/ስ/ኤጀንሲ ቢሮዎች ለግል ማሰልጠኛ ተቋማት ፍቃድ በመስጠት በማሰልጠን ሥራው እንዲሳተፉ ተደርጓል። በመሆኑም የግል ማሰልጠኛ ተቋማት የስልጠና ጥራታቸው ላይ ጥንቃቄ በማድረግና አስፈላጊ የስልጠና ቁሳቁሶችን በማሟላት የትምህርቱን ጥራት እንዲጠብቁ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን። ፍቃድ ሰጪ አካላትም የጀመሩትን ክትትል፣ ቁጥጥርና ድጋፍ በማጠናከር እገዛ እንዲያደርጉ እንጠይቃለን።

    በየክልሉ የተመረጡ የመንግስት ማሰልጠኛ ተቋማት ዝርዝር

    በመንግስት የተመረጡ 66 ማሰልጠኛ ተቋማት ሲሆኑ ስልጠናውም በሁሉም ክልል በነፃ ይሰጣል።

    የማሰልጠኛ ተቋማት ዝርዝር በየክልሉ፡-

    አማራ ክልል

    1. ባህርዳር ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    2. ወልድያ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    3. ደሴ ወ/ሮ ስህን ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    4. ከሚሴ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ
    5. ደ/ብርሃን ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    6. ጎንደር ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    7. እንጂባራ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    8. ቡሬ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ
    9. ደብረታቦር ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    10. ደብረ ማርቆስ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    11. ሠቆጣ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ

    ደቡብ ክልል

    1. አዋሳ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    2. አርባ ምንጭ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    3. ሶዶ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    4. ዱራሜ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    5. ሆሳዕና ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    6. ወራቤ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    7. ወልቂጤ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    8. ቡታጅራ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    9. ሀላባ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    10. ይርጋለም ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    11. ዲላ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ

    ትግራይ ክልል

    1. መቀሌ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    2. ዶ/ር ተወልደ የጤና ሳይንስ ኮሌጅ
    3. አክሱም ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    4. ዶ/ር አርዕያ ካሳ ኮሌጅ
    5. ውቅሮ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    6. (ማይጨው) ጥላሁን ይግዛው ፖሊቴክኒክ
    7. አላማጣ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ

    አዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር

    1. እንጦጦ የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና (ቴ/ሙ/ት/ስልጠና) ኮሌጅ
    2. ጄነራል ዊንጌት ቴ/ሙ/ት/ስልጠና ኮሌጅ
    3. ንፋስ ስልክ ቴ/ሙ/ት/ስልጠና ኮሌጅ
    4. ምሥራቅ አጠቃላይ ቴ/ሙ/ት/ስልጠና ኮሌጅ
    5. የካ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    6. ልደታ ማኒፋክቸሪንግ ኮሌጅ
    7. አዲስ ከተማ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    8. ቂርቆስ ማኒፋክቸሪንግ ኮሌጅ
    9. አቃቂ ቴ/ሙ/ት/ስልጠና ኮሌጅ

    ድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር

    1. መለስ ዜናዊ ቴ/ሙ/ት/ስልጠና ኮሌጅ

    ኦሮሚያ ክልል

    1. ሀሮማያ ቴክኒክና ሙያ
    2. አሰላ ቴክኒክና ሙያ
    3. ሻሸመኔ ቴክኒክና ሙያ
    4. መርቲ ፖሊ ቴክኒክ
    5. ቢሾፍቱ ቴክኒክና ሙያ
    6. ጂማ ቴክኒክና ሙያ
    7. መቱ ቴክኒክና ሙያ
    8. መቱ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ
    9. ነቀምት ቴክኒክና ሙያ
    10. ነቀምት ጤና ሳይንስ ኮሌጅ
    11. ባቱ ተራራ ቴክኒክና ሙያ
    12. ዶና ባርበር ቴክኒክና ሙያ
    13. ፍቼ ቴክኒክና ሙያ
    14. መርቲ ፖሊ ቴክኒክ
    15. አዳማ ፖሊ ቴክኒክ
    16. አብቦ ፖሊ ቴክኒክ
    17. ሰበታ ፖሊ ቴክኒክ
    18. ወሊሶ ፖሊ ቴክኒክ
    19. አጋሮ ፖሊ ቴክኒከ
    20. አደላ ፖሊ ቴክኒክ
    21. ቡሌ ሆራ ፖሊ ቴክኒክ
    22. ጨርጭር ፖሊ ቴክኒክ
    23. ደደር ፖሊ ቴክኒክ
    24. አርሲ ነገሌ ፖሊ ቴክኒክ
    25. ሀሰሳ ፖሊ ቴክኒክ
    26. ጊምቢ ፖሊ ቴክኒክ
    27. ወንጂ ፖሊ ቴክኒክ

    ምንጭ፦ የሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ለሥራ ወደ መካከለኛው


    Semonegna
    Keymaster

    እንደ አንድ ዜጋ እጠይቃለሁ ― ታማኝ በየነ

    ይድረስ ለኢትዮጵያ መንግስት፤

    እኔ በደረሰኝ መረጃ ከትናንት ጀምሮ በወሎ ከሚሴና በሽዋ አጣዬ በደረሰ ግጭት ንጹሃን ዜጎች እየሞቱ ነው፡፡

    ለመሆኑ ሰላም የነበር አካባቢ በአንዴ ወደ ጦርነት ቀጠና እንዴት ሊለወጥ ቻለ?

    የአማራ ክልል መንግስት በእካባቢው የታጠቁ ሃይሎች ሲገቡና ሲወጡ አላየም ነበር?

    የኦሮሚያ ክልል መንግስትስ ከራሱ ኃይል ውጭ የታጠቀ ኃይል ሲያይ ‘ማን ነህ?’ ብሎ አይጠይቅም ወይ?

    ኦዴፓ (የኦሮሞ ዲሚክራሲያዊ ፓርቲ) እና አዴፓ (የአማራ ዲሚክራሲያዊ ፓርቲ) በእርግጥ እየተነጋገራችሁ ነው የምትሠሩት? ከሆነስ የአንድ ንጹህ ዜጋ ህይወት ከማለፉ በፊት ለምን ግጭቱን ተነጋግራችሁ አትፈቱትም ነበር?

    የፌደራል መንግስት እንደ እኛ ውጭ እንዳለነው እኩል ነው ግጭቱን የሰማው?

    በአጠቃላይ ለተፈጠረው ቀውስ ከፌደራል መንግስቱና ከሁለቱ የክልል መንግስታት ውጭ በዚህ ጉዳይ ተጠያቂ የለም።

    በአጠቃላይ በየቦታው የሚታዩት ግጭቶች ነገን አስፈሪ እያደረጉት ነው፡፡ መንግስት ሁሉንም በእኩል ዓይን አይቶ በጥፋተኛው ላይ የማያዳግም እርምጃ ካልወሰደ ወደ ፈራነው እልቂት እንደምንገባ ለመናገር ትንቢት ተናጋሪ መሆን አያስፈልግም፡፡

    ገና በጠዋት ‘የአብዮታዊ ዲሞክራሲ የዘር ፖለቲካ መሠረት ሲጣል አይበጀንም!’ ብዬ አደባባይ የወጣሁት የዘረ ፖለቲካ መጨረሻው ዛሬ የምናየው በእጅጉ በከፋ ሁኔታ ነገ የምንጋፈጠው መሆኑን በመረዳት ነበር።

    ዛሬ የዘር ፖለቲካ በድርስ ዘዋሪ አፍላ ጎረምሳዎችም፣ እድሜ በተጫናቸው በችግሩ አምጪ አዛውንቶችም በአስፈሪ ሁኔታ እየተራገበ እሳቱ ደግሞ በየቀኑ አገር የቆመችበትን ምሶሶ እየለበለበ የዜጎችን ነፍስ እየቀጠፈ ነው።

    አስገራሚው ነገር በተመሳሳይ ወቅት ያልተማርንበት የሩዋንዳ የዘር ፍጅት መታሰቢያ ለ25ኛ ጊዜ በዓለም መድረክ እየታወሰ ነው። እኛ እንደሌሎቹ ካለፈው መማሩ ቢሳነን ዛሬ እየሆነ ባለው በራሳችን ውድቀት ለመማር እንኳን ዝግጁ የሆንን አንመስልም።

    እርግጥ ነው መንግስት በቅርቡ የአገራችን መሠረታዊ ችግር የምንከተለው የብሔር ፖለቲካ ነው ሲል የደረሰበትን ድምዳሜ በግልፅ ማሳወቁ የተስፋ ምልክት ሆኖ ሊታይ ይችላል።

    ይህ በራሱ ግን ከዛሬው እልቂት የሚታደገን አይደለምና የፌደራል መንግስቱም ሆነ የሁለቱ ክልል መንግስታት በአፋጣኝ ይህን ሁኔታ ቀልብሰው ከዚህ በላይ ሌላ ጉዳት እንዳይደርስ እንዲከላከሉ ይህንን ሰይጣናዊ ተግባር የሚፈፅሙ አካላትንም በሕግ ተጠያቂ እንዲያደርግ እንደ አንድ ዜጋ ለመጠየቅ እወዳለሁ።

    ኢትዮጵያዊው ታማኝ በየነ (አሜሪካ)

    ምንጭ፦ ECADF Ethiopian News / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ተያያዥ ዜና፦ አጣየ፣ ካራቆሬ፣ ማጀቴ እና አካባው በሚኖሩ ዜጎች ላይ የታጠቁ ኃይሎች እያደረሱት ያለው ኢ-ሰብአዊ በደል

    ታማኝ በየነ


     

    Semonegna
    Keymaster

    አጣዬ፣ ማጀቴ እና ካራቆሬ በሚባሉ አካባቢዎች የሚኖሩ ሰዎች እንደተናገሩት፥ ጥቃቱን እያደረሱ ያሉት ኃይሎች በሚገባ ዝግጅት ያደረጉ፣ በቁጥር ብዙ ከመሆናቸው የተነሳ ከ አካባቢዎች የሕግ አስከባሪ ፖሊሶች ቁጥር ጋር ሲነጻጸሩ እጅጉን የበዙ እንደሆኑ ተናግረዋል።

    ደብረ ብርሃን (ሰሞነኛ)– በወገኖቻችን ላይ በታጠቁ ኃይሎች እየደረሰ ያለውን ጥፋት የፌዴራል እና የክልሉ መንግስት በአስቸኳይ ሊያስቆሙ ይገባል፤ ሲሉ የደብረ ብርሃን ከተማ ነዋሪዎች በሰላማዊ ሰልፍ ጠየቁ።

    በአሁኑ ሰዓት በአማራ ክልል መንግስት ሰሜን ሸዋ ዞን የደብረ ብርሃን ከተማ ነዋሪዎች በአጣዬ፣ በካራቆሪ፣ በማጀቴና አካባቢው በሚኖሩ ሰላማዊ ወገኖቻችን ላይ እየደረሰ ያለውን ግድያና ሰቆቃ መንግስት በአፋጣኝ ሊያስቆም ይገባዋል በማለት ድምፃቸውን በሰላማዊ ሰልፍ በመግለፅ ላይ ናቸው።

    አጣዬ፣ ማጀቴ እና ካራቆሬ በሚባሉ አካባቢዎች የሚኖሩ ሰዎች እንደተናገሩት፥ ጥቃቱን እያደረሱ ያሉት ኃይሎች በሚገባ ዝግጅት ያደረጉ፣ በቁጥር ብዙ ከመሆናቸው የተነሳ ከ አካባቢዎች የሕግ አስከባሪ ፖሊሶች ቁጥር ጋር ሲነጻጸሩ እጅጉን የበዙ እንደሆኑ ተናግረዋል።

    በታጠቁ ኃይሎች የመቁስል አደጋ የደረሰባቸው መገኖቻችን ተገቢውን ህክምና እንዲያገኙ የተዘጉ መንገዶችን የሀገር መከላከያ ሠራዊት ጣልቃ ገብቶ እንዲያስከፍትም ጠይቀዋል።

    ሰልፉ እስካሁን በሰላማዊ አግባብ ተካሄዶ የተጠናቀቀ ሲሆን በአጣዬ ከተማ በህብረተሰቡ ላይ ጥቃት እያደረሰ የሚገኘው ኦነግ መሆኑን የሰሜን ሸዋ ዞን አስተዳደርና ፀጥታ ጉዳዮች መምሪያ ኃላፊ አቶ ካሳሁን እምቢያለ ገልጸው ችግሩ ከዞኑ አቅም በላይ በመሆኑ መከላከያ ሠራዊት ገብቶ አካባቢውን እንዲያረጋጋ ድጋፍ የተጠየቀ ቢሆንም በወቅቱና በፍጥነት ባለመግባቱና ከገባም በኋላ እርምጃ እንድወስድ አልታዘዝኩም በማለቱ ችግሩ እየተባባሰ መሄዱን ተናግረዋል።

    በአጣዬ ከተማ የኦነግ (የኦሮሞ ነጻ አዉጪ ግንባር) የታጠቀ ኃይል ባደረሰው ጥቃት በሰው ህይወት እና ንብረት እንድሁም በሀይማኖት ተቋማት ላይ ውድመት መድረሱን ኃላፊው ገልጸዋል።

    ጥቃቱን እየፈጸመ ያለው ኃይል በተለየ መንገድ ስልጠና የወሰደ በመሆኑ ይህን አካል መደምስ ካልታቻለ የሕዝቡን ሰላምና ደህንነት ለማስከበር አስቸጋሪ በመሆኑ የክልሉና የፌዴራል መንግስትን የተቀናጀ መፍትሄ መስጠት አለባቸው ብለዋል።

    ከኦሮሚያ ክልል መንግስት ጋር በሚያዋስኑ ወረዳዎች እና ቀበሌዎች ሰላማዊ ግኑኙነት መኖሩን ጠቁመው፥ በከሚሴ ልዩ ዞን ዙሪያ የተፈጠረውን ክስተት ለመፍታት በየደረጃው የሚገኘው የመንግስት አካል የተለየ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ እንደሆነም ተናግረዋል።

    የአማራ መገናኛ ብዙሃን ድርጅት (አብመድ) ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ እንደዘገበው፥ ወደ አጣየ፣ካራቆሬ እና ማጀቴ መከላከያ ገብቷል፤ ሁኔታውም ከሌሎች ቀናት ይልቅ በአንጻራዊ መሉ እሁድ (መጋቢት 29 ቀን፥ 2011 ዓ.ም.) እየተረጋጋ መምጣቱን፤ ተጨማሪ ፀጥታ አስከባሪ ኃይልም እየገባ መሆኑን የአማራ ክልል የሰላምና ደኅንነት ግንባታ ቢሮ ምክትል ኃላፊ ኮሎኔል አለበል አማረ አስረድተዋል።

    የፀጥታ ችግሩ ሙሉ በሙሉ ባይቀረፍም ከቅዳሜ እና ከእሁድ ረፋዱ (መጋቢት 28–29 ቀን፥ 2011 ዓ.ም.) የተሻለ መሆኑን የተናገሩት ኮሎኔል አለበል፥ ተደራጅቶ ሕዝብን ሰላም እያሳጣ ያለውን ቡድን ሙሉ በሙሉ ለመቆጣጠር የተቀናጀ ሥራ እንደሚከናወንም አረጋግጠዋል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    አጣዬ፣ ማጀቴ እና ካራቆሬ


    Anonymous
    Inactive

    ፖለቲካውን ከክረት በማላቀቅ ሀገሪቱን ከውጥረት ለማውጣት የበኩላችንን ለመወጣት ዝግጁ ነን – ዶክተር አምባቸው መኮንን
    —–

    ፖለቲካውን ከክረት በማላቀቅ ሀገሪቱን ከውጥረት በማውጣት አስተማማኝ ሰላም የሰፈነባት፤ ዜጎቿ በሙሉ ነፃነት የሚንቀሳቀሱባት ለማድረግ የበኩላችንን ለመወጣት ዝግጁ ነን አሉ የአማራ ክልል ርእሰ መስተዳድር ዶክተር አምባቸው መኮንን።

    ዛሬ በክልሉ ምክር ቤት ርእሰ መስተዳደር በመሆን የተሾሙት ዶክተር አምባቸው ቃለ መሃላ ከፈፀሙ በኋላ ለምክር ቤቱ ባቀረቡት ንግግር የአማራ ህዝቦችን የማስተዳደር ሀላፊነት ስለ ተሰጣቸው የተሰማቸውን ደስታ ገልፀዋል።

    አዲሱ ርዕሰ መስተዳደር በንግግራቸው በክልሉ በማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች ቀደም ሲል የተከናወኑ ስራዎች እንዳሉ ሆኖ በቀጣይ ግን የማስተካከያ ስራ የሚፈልጉ እንደ መንገድና መብራትን የመሰሉ የመሰረተ ልማት ስራዎች ክፍተቶች እንዳሉ ጠቁመዋል።

    በክልሉ ርብርብ የሚፈልጉ የህዝብ የመልማት ፍላጎት እንዳለም በማንሳት፥ ያሉትን አወንታዊ እና አሉታዊ ሁኔታዎችን በመገምገም ፈጣን ስምሪት እንደሚከናወን ነው የጠቆሙት።

    የክልሉ መንግስት በቀጣይ ትኩረት የሚያደርግባቸውን ጉዳዮችም በዝርዝር ያስቀመጡ ሲሆን፥ ጠንካራ መንግስታዊ መዋቅር በየደረጃው መዘርጋቱን በማረጋገጥ ጠንካራ የለውጥ አመራር መገንባት አንዱ መሆኑን አንስተዋል።

    ሙሉውን ፋና ላይ ያንብቡ

    Semonegna
    Keymaster

    የአቶ ገዱ አንዳርጋቸውን የስልጣን መልቀቅ ጥያቄ ተከትሎ የአዴፓ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል እና የጠቅላይ ሚኒስትር የመሠረተ ልማት እና የከተማ ልማት አማካሪ ሚኒስትር የሆኑት ዶ/ር አምባቸው መኮንን ርዕስ መስተዳደር ሆነው ተሹመዋል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው መልቀቂያ ጥያቄ አቀረቡ። ርዕሰ መስተዳድሩ እየተካሄደ ባለው የክልሉ ምክር ቤት ስብሰባ ላይ ነው ጥያቄውን ያቀረቡ ሲሆን፥ ምክር ቤቱም ጥያቄያቸውን ተቀብሏል። የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (አዴፓ)በበኩሉም የርዕሰ መስተዳድሩን ጥያቄ መቀበሉን የ አማራ ብዙሃን መገናኛ ድርጅት እና ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ዘግበዋል።

    አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ባለፈው ዓመት የካቲት ወር ለሦስተኛ ዙር በርዕሰ መስተዳድርነት ተመርጠው ሲያገለግሉ እንደነበር ይታወሳል። በአጠቃላይም ከታህሳስ ወር 2006 ዓ.ም. ጀምሮ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር በመሆን አገልግለዋል።

    አቶ ገዱ አንዳርጋቸው “ታላቁን የአማራ ሕዝብ ለመምራት ዕድል የሰጠኝን ፓርቲዬን አመሠግናለሁ፤ በስልጣን ዘመኔ በሰጠኋቸው ውሳኔዎች ያስከፋኋችሁ ካላችሁ ከልብ ይቅርታ እጠይቃለሁ። ወኔና ጉልበት ሆኖኝ የኖረውን የአማራ ሕዝብ አመሠግናለሁ፤ ለአዲሱ ርዕሰ መስተዳድርም መልካም የሥራ ዘመን እመኛለሁ” ብለዋል በመሰናበቻ ንግግራቸው።

    የአቶ ገዱ አንዳርጋቸውን የስልጣን መልቀቅ ጥያቄ ተከትሎ ምክር ቤቱ የአዴፓ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል የሆኑትን ዶ/ር አምባቸው መኮንንን ርዕስ መስተዳደር አደርጎ ሾሟል። ዶ/ር አምባቸው ከአዴፓ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባልነታቸው በተጨማሪ የጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮን የመሠረተ ልማት እና የከተማ ልማት አማካሪ ሚኒስትር በመሆን እያገለገሉ ነበር።

    እድገታቸው ጋይንት፣ ጎንደር ውስጥ የሆነው ዶ/ር አምባቸው መኮንን የጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ ሆነው ከመሾማቸው በፊት በተለያዩ የመንግስት ቦታዎች ለ28 ዓመታት ሠርተዋል።

    ዶ/ር አምባቸው ከኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ ዩንቨርሲቲ በኢኮኖሚክስ፣ ቀጥሎም ደቡብ ኮርያ ከሚገኘው ከኮርያ የልማት ኢንስቲትዩት (Korea Development Institute) በፐብሊክ ፖሊሲ የማስተርስ ዲግሪ፣ ከዚያም እንግሊዝ ሀገር ካንተርበሪ ከተማ ከሚገኘው ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ኬንት (University of Kent) ሌላ ማስተርስ ዲግሪ እና የዶክትሬት ዲግሪያቸውን አግኝተዋል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    ዶ/ር አምባቸው መኮንን


    Semonegna
    Keymaster

    ለመሆኑ እንቦጭን ለማስወገድ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የምርምር ሥራዎች የሚሠሩ የአረም ማስወገጃ ማሽነሪዎች ምን አገልግሎት እየሰጡ ነው? አሁን ሥራ ላይ ያሉት የእንቦጭ ማስወገጃ ማሽኖች ቁጥርስ ምን ያክል ነው?

    ባሕር ዳር – በጣና ኃይቅ ላይ የተከሰተውን የእንቦጭ አረም ለማስወገድ አራት ማስወገጃ መንገዶች በአማራጭነት አገልግሎት ላይ እንዲውሉ ምክረ-ሐሳብ ይቀርባል። ከእነዚህ ማስወገጃ መንገዶች እስካሁን ሁለቱ (የሕዝብ ጉልበት እና ማሽነሪዎች) ጣና ሐይቅ ዙሪያ አገልግሎት ላይ እየዋሉ ነው።

    ለመሆኑ እንቦጭን ለማስወገድ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የምርምር ሥራዎች የሚሠሩ የአረም ማስወገጃ ማሽነሪዎች ምን አገልግሎት እየሰጡ ነው? አሁን ሥራ ላይ ያሉት የማሽኖች ቁጥርስ ምን ያክል ነው? ስንል የአማራ ክልል የአካባቢ ደንና ዱር እንስሳት ጥበቃና ልማት ባለስልጣንን ጠየቅን።

    በዚህ ወቅት አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኙት ሁለት ማሽኖች ብቻ እንደሆኑ የነገሩን በአካባቢ ደንና ዱር እንስሳት ጥበቃና ልማት ባለስልጣን የጣና ሐይቅ ሥርዓተ ምኅዳር ጥበቃ ዳይሬክተር አቶ መዝገቡ ዳኘው ሁለቱ ማሽኖች ካናዳና እሥራኤል ሀገር በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን እና በአማጋ ኃላፊነቱ ተወሰነ የግል ማኅበር ድጋፍ የተገዙ ናቸው ብለዋል።

    “በባሕር ዳር እና ጎንደር ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት (ዩኒቨርሲቲዎች) እየተዘጋጁ ያሉ የእንቦጭ ማስወገጃ ማሽኖች መኖራቸውን አውቃለሁ” ያሉት አቶ መዝገቡ፥ እስካሁን ድረስ ግን ከተቋማቸው ጋር ርክክብ ፈፅመው ወደ ሥራ አለመግባታቸውን ገልጸዋል።

    አብመድ የተሰሩት ማሽኖች ለምን ርክክብ ተፈፅሞ አገልግሎት መስጠት አልጀመሩም ሲል ሁለቱን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት አነጋግሯል። የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የቴክኖሎጂ ኢንስቲቲዩት ከሙላት ኢንድስትሪያል ኢንጂነሪንግ ጋር በመተባበር የሠራው የእንቦጭ ማስወገጃ ማሽን ጥቅምት 24 ቀን 2011 ዓ.ም. የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው በተገኙበት ቢመረቅም ይህ ዜና እስከሚጠናቀርበት ጊዜ ድረስ አገልግሎት አይሰጥም።

    “ማሽኑ አገልግሎት ለመስጠት ምንም ዓይነት ችግር የለበትም፤ በቅርቡም ለሦስት ወራት ያክል የሙከራ ትግበራ ከተደረገ በኋላ ከሚመለከተው አካል ጋር ርክክብ ይደረጋል” ያሉት የቴክኖሎጂ ኢንስቲቲዩት ሳይንቲፊክ ዳይሬክተር ዶ/ር ሰይፉ አድማሱ የዘገየው ማሽኑን ለማንቀሳቀስ የሚሠራ ራሱን የቻለ የሰው ኃይል አደረጃጀት ባለመኖሩ ቅጥርና ምልመላ ለመፈፀም ጊዜ በመውሰዱ መሆኑን አስታውቀዋል።

    ከሙላት ኢንዳስትሪያል ኢንጅነሪንግ ጋር በመተባበር ለባለሙያዎቹ ስልጠና ለመስጠት ቅድመ ዝግጅት መጠናቀቁን ያስታወቁት ዶ/ር ሰይፉ ስልጠናው ከተጠናቀቀ በኋላ ወደ ተግባር እንደሚገቡም ገልፀውልናል። ማሽኑን በዘላቂነት ለማስተዳደርና ሥራውን ለማስተባበር ራሱን የቻለ ተቋማዊ አደረጃጀት እንደሚያስፈልገውም ገልጸዋል።

    በጎርጎራ ወደብ አካባቢ የሚገኘው ሌላው የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የአረም ማስወገጃ ማሽንም ከአካባቢ ደንና ዱር እንስሳት ጥበቃና ልማት ባለስልጣን ጋር ርክክብ ያልተፈፀመበት ማሽን ነው። የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የቴክኖሎጂ ሽግግር ዳይሬክተር ኢንጅነር ሰለሞን መስፍን “ለአካባቢ ደንና ዱር እንስሳት ጥበቃና ልማት ባለስልጣን ርክክብ እንዲፈፀሙ ደብዳቤ ልከናል” ብለዋል። የተዘጋጀው ማሽን አገልግሎት ለመስጠት ሙሉ በሙሉ ዝግጁ መሆኑን የገለጹት ዳይሬክተሩ፥ ማሽኑን የሚያንቀሳቅስ የሰው ኃይል (ኦፕሬተር) ማዘጋጀት የአካባቢ ደንና ዱር እንስሳት ጥበቃና ልማት ባለስልጣን ድርሻ እንደሆነም አስታውቀዋል።

    የአካባቢ ደንና ዱር እንስሳት ጥበቃና ልማት ባለስልጣን በበኩሉ ማሽኖቹን ለመረከብና የሰው ኃይል ለመቅጠር በተግር ሲሠሩ ማየት እፈልጋለሁ ብሏል።

    በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ እና በሙላት ኢንድስትሪያል ኢንጅነሪንግ የተዘጋጀው ማሽን ከ19 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ እንደተደረገበትም ያገኘነው መረጃ ያመላክታል። በዚህ ሳምንት ውጭ በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ድጋፍ የተገዛ ሌላ የእንቦጭ ማስወገጃ ማሽን ጣና ሐይቅ ላይ ደርሶ አገልግሎት መስጠት ጀምሯል።

    ምንጭ፦ አብመድ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የእንቦጭ ማስወገጃ ማሽን


Viewing 15 results - 76 through 90 (of 120 total)