Search Results for 'ኢትዮጵያዊ'

Home Forums Search Search Results for 'ኢትዮጵያዊ'

Viewing 15 results - 91 through 105 (of 124 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቤተ መዛግብት እና ቤተ መፃሕፍት ኤጀንሲ አሠራሩን ለማዘመን የሚያግዙ ሀሳቦች ላይ ከእንግሊዝ ቤተ መዛግብት ኃላፊዎች ጋር ምክክር አደረገ።

    በምክክሩ የቤተመዛግብት እና ቤተ መፃሕፍት አያይዝን ለማዘመን በሚቻልበት ሁኔታ ላይ የእንግሊዙ አቻ ተቋም ልምድ ምን እንደሆነ ያወያየ ምክክር ሚያዚያ 29 ቀን 2011 ዓ.ም. በኤጀንሲዉ የቪዲዮ ኮንፈረንስ አዳራሽ ተካሄደ። ለውይይቱ መክፈቻ የኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር የሆኑት አቶ የኩኖአምላክ መዝገቡ ለእንግዶቹ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ካስተላለፉ በኋላ ኢትዮጵያ የብዙ መዛግብቶች መገኛና ባለቤት ብትሆንም እንኳን ያላትን ሀብት ለራሷም ለዓለምም ለማበርከት የዘመናዊ ቴክኖሎጂ እጥረት እንዳለባት በማንሳት ይህንን ክፍተት የእንግሊዝ ቤተ መዛግብት የቴክኖሎጂ ሽግግር እገዛ አንዲያደርግላቸዉ ጠይቀዋል።

    በመቀጠል በእንግሊዝ ቤተ መዛግብት የኤሲያና የአፍሪካ የመዛግብት ስብስብ ኃላፊ የሆኑት ዶ/ር ሊዊሳ ኤሌና ሜንጎሊ (Luisa Elena Mengoni, Head of Asian and African Collections at the British Library) እንዳሉት በሁለቱ ሀገራት ዉስጥ ያሉ ተመራማሪዎች፣ ደራሲያን፣ እንዲሁም ሌሎች ፀሐፍት የእርስ በእርስ የልምድ ልዉዉጥ እንዲያደርጉ መንገዱን ማመቻቸት ለስነ-ፅሑፍ እድገት አስፈላጊ እንደሆነ ተናግረዋል።

    አቶ ክርስቲያን ጄንሰን (Kristian Jensen) የእንግሊዝ ቤተ መዛግብት ኃላፊ እንዲህ አይነት የምክክር መድረኮች ክፍተቶችን ለመለየትና መፍትሔ ለማበጀት እንደሚጠቅሙና ቀጣይነት እዲኖራቸዉ በተለይም የሥነ-ፅሑፍ ታሪኳ ከአክሱም ዘመነ መንግስት ጀምሮ ረጅም ዘመን ያስቆጠረ እንደ ኢትዮጵያ ያለች ሀገር ቤተ መፅሐፍቷና ቤተ መዛግብቷን በማዘመን ረገድ የእንግሊዝ ቤተመዛግብት እንደሚያግዝ ተናግረዉ፥ ኃላፊዉ የማይክሮ ፊልም (የመፅሐፍት ላይ ፅሑፎችን ወደ ሶፍት ኮፒ የሚቀይር መሣሪያ) በእርዳታ መስጠቷ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሚኒስትር በዶ/ር ሂሩት ካሳዉ በኩል ለኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር ለአቶ የኩኖአምላክ መዝገቡ ርክክብ ከተደረገ በኋላ ባህላዊ የቡና ጠጡ ሥነ-ስርዓት ተከናዉኖ ዝግጅቱ ተጠናቋል።

    ምንጭ፦ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ሌሎች ዜናዎች፦

    ቤተ መዛግብት


    Semonegna
    Keymaster

    መንግስት በሀገር ውስጥ የተለያዩ የሥራ ዕድሎችን በማስፋፋት ለሥራ ፈላጊ ዜጎች አስፈላጊውን ጥቅም ለማዳረስ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል። መሥራት ለሚችሉ ዜጎች ሁሉ በሀገር ውስጥ ላሉ የሥራ ዕድሎች ቅድሚያ በመስጠት ሠርተው የሚለወጡበትን ሁኔታዎች በማመቻቸት ዜጎችን ተጠቃሚ በማድረግ ላይ ይገኛል።

    ኢትዮጵያ ውስጥ ሠርቶ ለመኖር በርካታ መልካም አጋጣሚዎች አሉ። ለዚህም ምሳሌ የሚሆኑ በሀገራቸው ሠርተው የተለወጡ በርካታ ወጣቶችን መጥቀስ ይቻላል።

    ከዚህ ባለፈ ወደ ውጭ ሀገራት ለሥራ መሄድ የሚያስቡ ዜጎች እራሳቸውን ከአቻ ግፊትና ከሕገ-ወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎች ሊጠብቁ ይገባል። ዜጎች ስለሚሄዱበት ሀገር ስላለው እውነታ ያላቸው ግንዛቤና መረጃ ውስንና የተዛባ በመሆኑ ከመሄዳቸው በፊት ስለሚሄዱበት ሀገር ባህል፣ ወግና ልማድ መረዳትና እና የዜጎችን መብት ደህንነትና ክብር ለማስጠበቅ ሲባል በኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የወጣውን አዋጅ ቁጥር 923/2008 ጠንቅቆ ማወቅ ያስፈልጋል።

    ለጉዞ ከመነሳታችን በፊት ምን ማወቅ ይጠበቅብናል?

    ወደ ውጭ ሀገር ሄደን ለመሥራት በምናስብበት ወቅት ጊዜ ሰጥቶ ማሰብ ይገባል። ለምን እንደምንሄድ፣ ከሄድን በኋላ የሚያጋጥሙንን መልካምና መጥፎ አጋጣሚዎች እንዴት መቋቋምና ማለፍ እንደሚገባን፣ የምንሄድበትን ሀገር ባህል፣ ወግ፣ ልማድና ስርዓት እንዴት ተላምደን መኖር እንደምንችል፣ የሠራንበትን ገንዘብ ወደ ሀገራች እንዴት መላክና መቆጠብ እንደምንችል፣ ኮንትራታችንን ጨርሰን መቼ ወደ ሀገራችን መመለስ እንዳለብን አስቀድመን ማቀድ ያስፈልጋል።

    በአዋጅ ቁጥር 923/2008 መሠረት በውጭ አገር ለሥራ የሚሰማሩ ዜጎች እድሜያቸው ከ18 አመት በላይ የሆኑ፣ 8ኛ ክፍል ያጠናቀቁ (ወደ 9ኛ ክፍል የተዛወሩ)፣ በሚሄዱበት የሥራ መስክ ስልጠና ወስደው የብቃት ማረጋገጫ ያገኙ፣ የቅድመ ጉዞ ስልጠና ወስደው ሰርተፊኬት የያዙ፣ የጤና ኢንሹራንስ የተገባላቸው፣ ሙሉ የጤና ምርምራ ያደረጉና ከወንጀል ነጻ ሊሆኑ ይገባል።

    ይህን ያሟሉ ዜጎች በአስቀጣሪ ኤጀንሲ በኩል ወይም በራሳቸው አማካኝነት ሥራውን በማፈላለግ ማለትም በቀጥታ ቅጥር አስፈላጊውን የቅጥር ፎርማሊቲ በማሟላት ቪዛውን አግኝተው መሄድ ይችላሉ። ብዙ ጊዜ በቀጥታ ቅጥር የሚጓዙ ሠራተኞች መደበኛ ስልጠና የወሰዱና ከቤት ሠራተኝነት ውጭ በልዩ ልዩ ሙያዎች የሰለጠኑ ሲሆን የሚሠሩትም በካምፓኒና በልዩ ልዩ አነስተኛ የቢዝነስ ተቋማት ውስጥ ነው። ከዚህ በፊት በውጭ ሀገር ሠርተው የተመለሱ ልምድ ይኖራቸዋል ተብሎ ስለሚታሰብ መረጃ ማቅረብ የሚችሉ ከሆነ ስልጠናውን መውሰድ ግዴታ ባይሆንም የብቃት ማረጋገጫ ሰርተፊኬት ማቅረብ ይኖርባቸዋል።

    ለሥራ የት ሀገር ነው መሄድ የሚቻለው?

    ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በቤት ሠራተኝነት የሚሄድ ከሆነ ሊጓዝ የሚችለው በኤጀንሲዎች አማካኝነት ብቻ መሆኑን ሊረዳ ይገባል። የሥራ ስምሪት ማድረግ የሚችለውም አገሪቷ የሁለትዮሽ ስምምነት ወደተፈራረመችባቸው ሀገራት ብቻ ነው። የሁለትዮሽ ስምምነት የተፈፀመባቸው መዳረሻ ሀገራት ለጊዜው ሳውዲ አረቢያ፣ ኳታርና ጆርዳን ሲሆኑ ከሌሎች አገሮች ጋር የሚደረገው ስምምነትም በሂደት ይቀጥላል።

    ስምምነት በተፈፀመባቸው ሀገሮች የደመወዝ መጠን ስንመለከት ከኳታር መንግስት 1200 ለቤት ሠራተኛና 1300 ለእንክብካቤ (care giver) የኳታር ሪያል፣ ከጆርዳን መንግስት ለጀማሪ 225 ዶላር፣ ልምድ ላላው 250 ዶላር፣ ከሳውዲ አረቢያ መንግሰት ጋር 1000 የሳውዲ ሪያል እንዲሆን ስምምነት ላይ ተደርሷል።

    በሠራተኞችና በአሠሪዎች የሚሸፈኑ ወጪዎች

    አንድ ሠራተኛ በሥራ ለመሰማራት አስፈላጊውን መስፈርት ካሟላና ብቁ ከሆነ በአዋጁ የተደነገጉ የቅጥርና ምልመላ መንገዶችን በመከተል አስፈላጊውን መፈጸም እና ወጪዎችን መሸፈን ይገባል።

    1. አሠሪው ወይንም ኤጀንሲው የሚሸፍናቸው ወጪዎች

    በአሠሪው የሚሸፈኑ ወጪዎች ሠራተኛውን ወደ ተቀባይ አገር ለማድረስ፣ በተቀባይ አገር ያለችግር እንዲቆይና እንዲሠራ ለማድረግ፣ እንዲሁም በሥራ ላይ ደህንነቱ የተጠበቀ እንዲሆን የሚወጡ ወጪዎች ናቸው።

    እነርሱም የተቀባይ አገር የመግቢያ ቪዛ፣ የደርሶ መልስ መጓጓዣ፣ የሥራ ፍቃድ፣ የመኖሪያ ፍቃድ፣ የሥራ ውል ማጽደቂያ ክፍያዎች፣ የመድህን ዋስትና ሽፋን እንዲሁም በኢትዮጵያ ውስጥ ለሚገኝ የተቀባይ አገር ኤምባሲ ወይም ቆንስላ ጽህፈት ቤት የሚከፈል ከቪዛና ከሰነድ ማረጋገጥ ጋር የተያያዘ ማናቸውም ወጪዎች ናቸው።

    1. በሠራተኛው የሚሸፈኑ ወጪዎች

    አንድ ሠራተኛ ለሥራ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ሀገራት በሚጓዝበት ወቅት የሚያወጣው ወጪ በአብዛኛው በህይወት ዘመኑና በማህበራዊ ህይወቱ ውስጥ የትኛውም ሰው ስለሚጠቀምባቸው የሚያወጣቸው ወጪዎች ናቸው።

    እነርሱም ለልደት ሰርተፊኬት፣ ለፓስፖርት፣ ለክትባት፣ ለህክምና ምርመራ፣ ለሙያ ብቃት ማረጋገጫ፣ ከወንጀል ነፃ ማስረጃ ማረጋገጫ ወጪዎች ናቸው። እነኝህ ክፍያዎች በሙሉ አገልግሎቱን ለሰጡ ሌሎች መሥሪያ ቤቶችና ተቋማት የሚከፈል እንጂ ምልመላውን ለሚያከናውነው ኤጀንሲ የሚከፈል አይደለም። ኤጀንሲው ምንም አይነት ክፍያ ከሠራተኛው ቢጠይቅ ህገወጥ ያደርገዋል።

    ይሁን እንጂ ለሥራ ወደ ውጭ አገር ለመሄድ አስፈላጊ ሁኔታዎች ተጠናቀው ያለበቂ ምክንያት ሠራተኛው ወደ ሥራ ባይሰማራ ከቅጥሩ ጋር በተያያዘ አሠሪው ያወጣውን ወጪ ሠራተኛው እንዲከፍለው ሊጠይቅ ይችላል። በተመሳሳይ መንገድ በተራ ቁጥር 2 ላይ የተጠቀሱትን ወጪዎች ሠራተኛው አውጥቶ በራሱ ጉድለት ባልሆነ ምክንያት በሥራ ላይ ካልተሰማራ ኤጀንሲው ወይም አሠሪው የሠራተኛውን ወጪ የመተካት ግዴታ ይኖርበታል።

    ለውጭ አገር ለሥራ ስምሪት የሚሰጡ ስልጠናዎችና ማሰልጠኛ ተቋማቱ

    ለውጭ አገር ሥራ ስምሪት የሚሰጡ ስልጠናዎች ሶስት ሲሆኑ እነሱም በቤት አያያዝ (Household Service) በቤት ውስጥ ሥራ (Domestic Help) እና በእንክብካቤ ሥራ (Care Giving) ናቸው።

    የእነዚህ ሙያዎች የስልጠና መሳሪያዎች፣ የሙያ ደረጃ፤ ሥርዓተ ትምህርት እና የብቃት ማረጋገጫ ምዘና መሳሪያዎች ሲዘጋጁ ለማንኛውም ዜጋ እንዲያገለግል ሲሆን ወንድም ሆነ ሴት በፍላጎቱ ሊሰለጥን ይችላል። ሠልጣኞች ስልጠናውን በግላቸው ሊሠሩበት፣ በአገር ውስጥ ሊቀጠሩበት እንዲሁም ወደውጭ አገር ሊሰማሩበት እንደሚችሉ ሊገነዘቡና በምልመላ ወቅትም ሊነገራቸው ይገባል። በተጨማሪም በስልጠናው የተሳተፈ ሁሉ የብቃት ምዘናውን ያልፋል ማለት አይደለም፣ የብቃት ምዘናውን ያለፈ ሁሉ ቀጣሪ ያገኛል ማለትም አይደለም። በመሆኑም በተጠቀሱት ሙያ እንዲሰለጥኑ የተደረጉ ሁሉ ወደአረብ ሀገር መሄድን እንደመብት ሊያዩት አይገባም።

    ይሁን እንጂ ወደአረብ አገር መሄድ የሚፈልጉ ሰልጣኞች ከላይ በተጠቀሱት ሦስት ሙያዎች ከሰለጠኑ በኋላም የብቃት ምዘና ማረጋገጫ ተፈትነው ማለፍና ሰርተፊኬት መያዝ ይኖርባቸዋል። ስልጠናው በየክልላቸውና በአቅራቢያቸው በሚገኙ በተመረጡ ማሰልጠኛ ተቋማት ይሰጣል። ስልጠናው በየክልላቸውና አቅራቢያቸው የመሰጠቱ ጠቀሜታም የሠራተኞች ምልመላ በየክልላቸው የሚካሄድ በመሆኑ፣ አስፈላጊ መረጃዎችን ለማጣራትና ለማረጋገጥ፣ የዜጎችን ደህንነትና ክብር በቅርብ ለመከታተል እና ከስልጠና፣ ከምልመላ ጋር ተያይዞ ለአላስፈላጊ ወጪና የመብት ጥሰቶች እንዳይጋለጡ ያግዛል።

    ስልጠናን በተመለከተም፣ የመንግስት ማሰልጠኛ ተቋማት ትምህርቱን በነፃ የሚሰጡ ሲሆን ማንኛውም ሰልጣኝ በክልሉ በሚገኝ የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ወይም በየዞኑና ክፍለ ከተማው ወይም ወረዳዎች በሚገኙ የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ጽህፈት ቤቶች በመመዝገብ ለየማሰልጠኛዎቹ በመላክ እንዲሰለጥኑ ይደረጋል።

    በተጨማሪም የመንግስት ማሰልጠኛ ተቋማት የተደራሽነትና የአቅም ውስንነት ስላለባቸው በፌደራልና በክልል በሚገኙት የቴ/ሙ/ት/ስ/ኤጀንሲ ቢሮዎች ለግል ማሰልጠኛ ተቋማት ፍቃድ በመስጠት በማሰልጠን ሥራው እንዲሳተፉ ተደርጓል። በመሆኑም የግል ማሰልጠኛ ተቋማት የስልጠና ጥራታቸው ላይ ጥንቃቄ በማድረግና አስፈላጊ የስልጠና ቁሳቁሶችን በማሟላት የትምህርቱን ጥራት እንዲጠብቁ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን። ፍቃድ ሰጪ አካላትም የጀመሩትን ክትትል፣ ቁጥጥርና ድጋፍ በማጠናከር እገዛ እንዲያደርጉ እንጠይቃለን።

    በየክልሉ የተመረጡ የመንግስት ማሰልጠኛ ተቋማት ዝርዝር

    በመንግስት የተመረጡ 66 ማሰልጠኛ ተቋማት ሲሆኑ ስልጠናውም በሁሉም ክልል በነፃ ይሰጣል።

    የማሰልጠኛ ተቋማት ዝርዝር በየክልሉ፡-

    አማራ ክልል

    1. ባህርዳር ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    2. ወልድያ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    3. ደሴ ወ/ሮ ስህን ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    4. ከሚሴ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ
    5. ደ/ብርሃን ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    6. ጎንደር ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    7. እንጂባራ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    8. ቡሬ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ
    9. ደብረታቦር ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    10. ደብረ ማርቆስ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    11. ሠቆጣ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ

    ደቡብ ክልል

    1. አዋሳ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    2. አርባ ምንጭ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    3. ሶዶ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    4. ዱራሜ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    5. ሆሳዕና ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    6. ወራቤ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    7. ወልቂጤ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    8. ቡታጅራ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    9. ሀላባ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    10. ይርጋለም ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    11. ዲላ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ

    ትግራይ ክልል

    1. መቀሌ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    2. ዶ/ር ተወልደ የጤና ሳይንስ ኮሌጅ
    3. አክሱም ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    4. ዶ/ር አርዕያ ካሳ ኮሌጅ
    5. ውቅሮ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ
    6. (ማይጨው) ጥላሁን ይግዛው ፖሊቴክኒክ
    7. አላማጣ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ

    አዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር

    1. እንጦጦ የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና (ቴ/ሙ/ት/ስልጠና) ኮሌጅ
    2. ጄነራል ዊንጌት ቴ/ሙ/ት/ስልጠና ኮሌጅ
    3. ንፋስ ስልክ ቴ/ሙ/ት/ስልጠና ኮሌጅ
    4. ምሥራቅ አጠቃላይ ቴ/ሙ/ት/ስልጠና ኮሌጅ
    5. የካ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    6. ልደታ ማኒፋክቸሪንግ ኮሌጅ
    7. አዲስ ከተማ ኢንዱስትሪያል ኮሌጅ
    8. ቂርቆስ ማኒፋክቸሪንግ ኮሌጅ
    9. አቃቂ ቴ/ሙ/ት/ስልጠና ኮሌጅ

    ድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር

    1. መለስ ዜናዊ ቴ/ሙ/ት/ስልጠና ኮሌጅ

    ኦሮሚያ ክልል

    1. ሀሮማያ ቴክኒክና ሙያ
    2. አሰላ ቴክኒክና ሙያ
    3. ሻሸመኔ ቴክኒክና ሙያ
    4. መርቲ ፖሊ ቴክኒክ
    5. ቢሾፍቱ ቴክኒክና ሙያ
    6. ጂማ ቴክኒክና ሙያ
    7. መቱ ቴክኒክና ሙያ
    8. መቱ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ
    9. ነቀምት ቴክኒክና ሙያ
    10. ነቀምት ጤና ሳይንስ ኮሌጅ
    11. ባቱ ተራራ ቴክኒክና ሙያ
    12. ዶና ባርበር ቴክኒክና ሙያ
    13. ፍቼ ቴክኒክና ሙያ
    14. መርቲ ፖሊ ቴክኒክ
    15. አዳማ ፖሊ ቴክኒክ
    16. አብቦ ፖሊ ቴክኒክ
    17. ሰበታ ፖሊ ቴክኒክ
    18. ወሊሶ ፖሊ ቴክኒክ
    19. አጋሮ ፖሊ ቴክኒከ
    20. አደላ ፖሊ ቴክኒክ
    21. ቡሌ ሆራ ፖሊ ቴክኒክ
    22. ጨርጭር ፖሊ ቴክኒክ
    23. ደደር ፖሊ ቴክኒክ
    24. አርሲ ነገሌ ፖሊ ቴክኒክ
    25. ሀሰሳ ፖሊ ቴክኒክ
    26. ጊምቢ ፖሊ ቴክኒክ
    27. ወንጂ ፖሊ ቴክኒክ

    ምንጭ፦ የሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ለሥራ ወደ መካከለኛው


    Anonymous
    Inactive

    አንዳንድ ሰዎች በቅርቡ ሸዋ ዳቦ መጋገሪያ በአንድ ዳቦ ላይ 100 ፐርሰንት ዋጋ ጨምሯል ብለው ኢትዮጵያዊ በዚህ ሳቢያ አብዮት ያነሳል ብለው ሲሰጉ ባየሁ ጊዜ ስቄያለሁ። የኢትዮጵያዊነት ስነልቦና አልገባንም ማለት ነው።

    “የዳቦ ፖለቲካ!!”
    በጋዜጠኛ መላኩ ብርሃኑ – አዲስ አበባ

    አንድ ወቅት ግብጽ ላይ የዳቦ ዋጋ 10 ሳንቲም ጨመረ ተብሎ አብዮት ተነስቶ እንደነበር አስታውሳለሁ፤ በቅርቡም ሱዳን ላይ እንዲሁ ሆኖ ነበር።

    አንዳንድ ‘ፌስቡካውያን’ ሸዋ ዳቦ በቅርቡ በአንድ ዳቦ ላይ 100 ፐርሰንት ዋጋ ጨምሯል ብለው ኢትዮጵያዊ በዚህ ሳቢያ አብዮት ያነሳል ብለው ሲሰጉ ባየሁ ጊዜ ስቄያለሁ። በዳቦ ዋጋ ጭማሪ ኢትዮጵያ ውስጥ አብዮት ይነሳል ካልን የኢትዮጵያዊነት ስነልቦና አልገባንም ማለት ነው።

    ኢትዮጵያዊ ከዳቦ ዋጋ በላይም የየዕለት ኑሮውን የሚፈትን ስንት የዋጋ ንረት ጫንቃው ላይ እያናጠረበት መልካም ቀን በተስፋ የሚጠብቅ ሕዝብ እንደሆነ ለናንተ አልነግራችሁም።

    ኢትዮጵያዊ አንድ ሊትር ኬሮሲን (kerosene) ከ400 ፐርሰንት በላይ ዋጋ ጨምሮበት እንኳን ወደከሰል ምድጃው ተመልሶ እሳት እፍ ሲል እንጂ አብዮት ሲቀሰቅስ አታውቁትም።

    ኢትዮጵያዊ 5 ብር የሚገዛው ስኳር 20 ብር ሆኖበት እንኳን እንደ ድሮው ቡና በጨው ሲጠጣ እንጂ አብዮት ሲቀሰቅስ አላየነውም።

    ኢትዮጵያዊ የግል ትምህርት ቤት ክፍያ በየዓመቱ በ50 በመቶ ሲጨምርበት ልጆቹን ወደመንግስት ትምህርት ቤት ሲያዛውር እንጂ በቁጣ አብዮት ሲያነሳ አይቶት የሚያውቅ የለም።

    ኢትዮጵያዊ የትራንስፖርት ዋጋ በዓመት ስንት ጊዜ ሲጨምርበት “እንደውም ጤና ነው” ብሎ በእግሩ ሲገሰግስ እንጂ አብዮት አንስቶ ሲሯሯጥ አልታየም።

    ኢትዮጵያዊ የነዳጅ ዋጋ ከኪሱ በላይ ሲሆንበት መኪናውን አቁሞ በእግሩ ሲንከላወስ እናየው ይሆናል እንጂ “ምቾቴ ተጓደለ!” ብሎ አብዮት ሲቀሰቅስ አልታየም።

    ኢትዮጵያዊ በመሥሪያ ቤቱ ውስጥ ከእሁድ እስከ እሁድ እንዲሠራ ተደርጎ አንድ ሰዓት ቢዘገይ “አረፈድክ” ተብሎ ደሞዙ ሲቆረጥ የመጣውን በጸጋ ሲቀበል እንጂ አመጽ አቀጣጥሎ አብዮት ሲጠራ አላየንም።

    ኢትዮጵያዊ ውስጥ የመኖሪያ ቤት ማግኘት ሰማይ ቤት አንደመግባት ዕድል ሆኖ እንኳን አከራዮች በየወሩ ኪራይ ሲቆልሉበት እንባውን ወደላይ ይረጭ ይሆናል እንጂ መርሮት አብዮት ሲቀሰቅስ አይተነው አናውቅም

    ኢትዮጵያዊ አንድ ኩንታል ጤፍ 3 ሺህ ብር ሲገባ “ልመደው ሆዴ” ብሎ ስንዴ ደባልቆ ሲያስፈጭ እንጂ መረረኝ ብሎ አብዮት ሲያነሳ ያየው ማንም የለም።

    ኢትዮጵያዊ ማለት ይህ ሁሉ የኑሮ መርግ ተጭኖት እንኳን ደሞዝ ስላልተጨመረለት አደባባይ ወጥቶ አብዮት ሲለኩስ የታየ ሕዝብ አይደለም።

    እናም ኢትዮጵያዊ ይህን ሁሉ ሆኖ እንኳን እንደ ቆርቆሮ የሚንኳኳ ሕዝብ ሳይሆን ሲቀጠቅጡት ቢውሉ ድምጹ ጎልቶ የማይሰማ ሕዝብ ነው።

    የሚደንቀው ነገር ሰዎች ይህ ሁሉ ፍርሃት፣ ሞኝነት፣ ባርነት የሚመስለው ሰው መብዛቱ ነው። በፍጹም!

    ኢትዮጵያዊ ስሜታዊ ሕዝብ አይደለም። “የረጋ ወተት ቅቤ ይወጣዋል” ባይ ታጋሽ ሕዝብ ነው። “የጅብ ችኩል ቀንድ ይነክሳል” ባይ እርጋታን ወዳድ ሕዝብ ነው። የመጣውን መንግስት ሁሉ “እንየው! ጊዜ እንስጠው! እንታገሰው” የሚል ሕዝብ ነው።

    ኢትዮጵያዊ ቁጣው እንደግስላ፣ ትዕግስቱ እንደግመል፣ የዋህነቱ እንደርግብ፣ ብልጠቱ እንደእባብ የሆነ ረቂቅ ሕዝብ ነው።

    ችግር የሚመጣው ዝምታው እንዳላዋቂነት፣ ታጋሽነቱ እንደጅልነት፣ ታዛዠነቱን እንደባርነት የተቆጠረበት ጊዜ ነው። ልብ በሉ!

    ያኔ “ከረጋ ውሃና ዝም ካለ ሰው” ብሎ መውደቂያህን ያፈጥነዋል። “መከበር በከንፈር” ብሎ የአፍህን ዋጋ ይከፍልሃል። ክብር ይፈልጋል። ንቄትን ይጠላል። ካከበርከው ያገንንሃል። ከነገርከው ይ’ረዳሃል። ካሴርክበት ድራሽህን ያጠፋዋል።

    እናም ይግባህ! በኢትዮጵያ ውስጥ ቅሬታ አብዮት ወልዶ የማታየው ለዚህ ነው። ህዝቡ ቅሬታውን ነገ ይስተካከላል በሚል ተስፋ መርሳት እና ‘እስኪ የሚሆነውን እንጠብቅ’ በሚል ትዕግስት ማመቻመች የሚችል ባህሪ ያለው ሕዝብ ነው። ዋናው ነገር ቅሬታው ተጠራቅሞ ብሶት እስኪሆን አለመጠበቅ ነው።

    በተረፈ የሕዝቡ ዛሬን በትዕግስት ማለፍን ለነገ ሃገር ዋጋ ከመስጠት ጋር እንጂ ጀርባን ለዱላ ከማመቻቸት የባርነት መንፈስ ጋር አዳብለህ አትይበት ! በትንሽ በትልቁ እንደቆርቆሮ እንዲንኳኳም አትጠብቀው። የኛ ፖለቲከኞች ትልቁ ችግር እንመራዋለን የሚሉትን ሕዝብ አለማወቃቸው ነው!

    እና ምን ለማለት ፈልጌ ነው ….

    አብዮት የናፈቀው ሰው ‘አብዮት ፍሬ’ የሚባለው ትምህርት ቤት ሄዶ እጁን ይስጥ … (ቦታውን ከፈለጋችሁ እጠቁማችኋለሁ)።

    በጋዜጠኛ መላኩ ብርሃኑ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ሸዋ ዳቦ


    Semonegna
    Keymaster

    ለተከበሩ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚንስትር ዶክተር አብይ አህመድ ― ድምጻዊ ዳን አድማሱ
    አዲስ አበባ፥ ኢትዮጵያ

    ለተከበሩ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚንስትር ዶክተር አብይ አህመድ፥ እኔ እንደ አንድ ኢትዮጽያዊ ወጣት ይህን ማለት እወዳለሁ ተወልጄ ባደኩባት ሀገር ነፍስ ካወኩባት ጊዜ በሀገሬ ጉዳይ በነፍስ በስጋዬ ስሟገት እዚህ ደርሻለሁ።

    በተለይም እድሜ ለቅንጅት ፓርቲ ወጣቱ መብቱን እንዲጠይቅ አንቅቶታል ብዬ አምናለሁ፤ ከ1997 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ ሁሉም ኢትዮጵያዊ እየተገደለ፣ እየተቀጠቀጠ፣ እየታሰረ እዚህ ወንበር ላይ እርሶን አምጥቷታል።

    እኔ የለውጡን ዋጋ የምሰጠው ለእግዚአብሔር ነው። ለውጡ የመጣው ፈጣሪ ለዚህች የቃልኪዳን ምድር ስለራራላት ነው፤ እንዲራራላት ደግሞ ወይባ ለብሰው በገረገራ የፆሙ፣ የፀለዩ፣ በየመስጊዱ ውስባህ ይዘው ዱአ ያደረጉ፣ የትውልድ ወላጆች ፈጣሪ ከሰማይ እንዲወርድ፣ ከመንበሩ እንዲነሳ አድርገውታል። ሲቀጥል የደም ትንሽ ትልቅ የለውም፤ ድፍን ኢትዮጵያዊ ዋጋ ከፍሏል፤ የድሀ እንባ፣ የወጣት ደም፣ የእናት፥ የአባት ለቅሶ ወደ ላይ ጮሆ አምላክ ለኢትዮጵያ ወርዷል፤ በዚች የአኬልዳማ ምድር ግን የአቤል ደም አሁንም ይጮሀል።

    በሰኔ 16 ቀን 2010 ዓ.ም. በሀገሪቱ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ ‘ሆ!’ ብለን ስንወጣ፥ ስለ እርሶ በቂ ዕውቀት እንኳን ኖሮን አይደለም። መጀመሪያ ሰው ኖት፤ ሲቀጥል ‘ኢትዮጽያ’ ብለው መጡ። ያኔ ሁለቴ አላሰብንም! እንደ ምድር አሸዋ በዝተን፣ እንደ ሰማይ ኮከብ ደምቀን መጣን። የኢትዮጵያ አምላክ ቀድሞን ባይወጣ ኖሮ እነዛ ሰማዕትት ከሁለት ሰው ወደ ሀያ ሚሊየን ላለመድረሳቸው ማንም እርግጠኛ አልነበረም። ወጣቱ ሰማዕት ከሞት ጋር ተናንቆ ‘የኔ ችግር የለም፤ አብይን አደራ’ ሲል ምን እንደተሰማዎት ባላቅም ኢትዮጵያን አደራ እያሎትም ጭምር ነበር። ከዛች ቀን ጀምሮ በርካታ መልካም ጅማሮዎትን አይተን እግር በእግር እየተከተልን ምስጋናን እና ማበረታታትን አልተውንም፤ ግን እውነቱን ማወቅ ከፈለጉ ይህን አንድ ዓመት በጥፍር ቆመን አሳልፈናል፤ ጠዋት ስንነቃ ከአዋውፋት መዝሙር ይልቅ የሕዝብ እሮሮ ቅርባችን ነው፤ ማታ የእንቁራሪት ሲርሲርታ ሳይሆን የሕዝቦች ዋይታ ቤታችን ነው።

    ለምን ደጋግመው ሲሉት እንደሰማሁት ማሰር እና መግደል ስለማያዋጣ እየታገስን ነው ማለት ምን ማለት ነው? በማን ደም ነው ትዕግስት የምንለማመደው? በማንስ ለቅሶ ነው ትከሻ የምናሰፋው? በጌዲኦ፣ በአጣዬ የሚሞተው ህፃን የእርሶ ልጅ ቢሆን ትንሽ ልታገስ ይሉ ነበር? ቆይ ታግሰው ሁለተኛ ልጆን ቢነጠቁ ‘መግደል መሸነፍ ነው’ ይላሉ? አይመስለኝም።

    ስለዚህ እርሶ ኪጋሊ፣ ሩዋንዳ ያስቀመጡትን አበባ የሩዋንዳው ፕሬዝደንት ፖል ካጋሜ እዚህ መጥተው እንዳያስቀምጡት ትዕግስቱ ገደብ ቢኖረው የተሻለ ነው እላለሁ። ይህን ሁሉ ችግር መፍታት ቀላል እንዳልሆነ ብንረዳም ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ እና የአዲስ አበባ ልጅ ላይ የተሰጠውን ጠንከር ያለ መግለጫ ዓይነት መስጠት ግን ከባድ አይመስለኝም። እዚህ ላይ መጨመር የምፈልገው ከእያንዳንዱ ችግር ጀርባ በሚሊየን የሚቆጠረውን ደግ እና ሀገር ወዳድ የኦሮሞ ህዝብ ለእያንዳንዱ ችግር አብረን ባንወቅጠው ጥሩ ነው፤ ካልሆነ ግን እኛ እርሶን ከልባችን ላለማውጣት የምንታገለውን ያክል እርሶ ከልባችን ለመውጣት እየታገሉ ይመስለኛል።

    ዳን አድማሱ (ድምጻዊ)
    አንድ ኢትዮጵያ
    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ዳን አድማሱ


    Semonegna
    Keymaster

    እንደ አንድ ዜጋ እጠይቃለሁ ― ታማኝ በየነ

    ይድረስ ለኢትዮጵያ መንግስት፤

    እኔ በደረሰኝ መረጃ ከትናንት ጀምሮ በወሎ ከሚሴና በሽዋ አጣዬ በደረሰ ግጭት ንጹሃን ዜጎች እየሞቱ ነው፡፡

    ለመሆኑ ሰላም የነበር አካባቢ በአንዴ ወደ ጦርነት ቀጠና እንዴት ሊለወጥ ቻለ?

    የአማራ ክልል መንግስት በእካባቢው የታጠቁ ሃይሎች ሲገቡና ሲወጡ አላየም ነበር?

    የኦሮሚያ ክልል መንግስትስ ከራሱ ኃይል ውጭ የታጠቀ ኃይል ሲያይ ‘ማን ነህ?’ ብሎ አይጠይቅም ወይ?

    ኦዴፓ (የኦሮሞ ዲሚክራሲያዊ ፓርቲ) እና አዴፓ (የአማራ ዲሚክራሲያዊ ፓርቲ) በእርግጥ እየተነጋገራችሁ ነው የምትሠሩት? ከሆነስ የአንድ ንጹህ ዜጋ ህይወት ከማለፉ በፊት ለምን ግጭቱን ተነጋግራችሁ አትፈቱትም ነበር?

    የፌደራል መንግስት እንደ እኛ ውጭ እንዳለነው እኩል ነው ግጭቱን የሰማው?

    በአጠቃላይ ለተፈጠረው ቀውስ ከፌደራል መንግስቱና ከሁለቱ የክልል መንግስታት ውጭ በዚህ ጉዳይ ተጠያቂ የለም።

    በአጠቃላይ በየቦታው የሚታዩት ግጭቶች ነገን አስፈሪ እያደረጉት ነው፡፡ መንግስት ሁሉንም በእኩል ዓይን አይቶ በጥፋተኛው ላይ የማያዳግም እርምጃ ካልወሰደ ወደ ፈራነው እልቂት እንደምንገባ ለመናገር ትንቢት ተናጋሪ መሆን አያስፈልግም፡፡

    ገና በጠዋት ‘የአብዮታዊ ዲሞክራሲ የዘር ፖለቲካ መሠረት ሲጣል አይበጀንም!’ ብዬ አደባባይ የወጣሁት የዘረ ፖለቲካ መጨረሻው ዛሬ የምናየው በእጅጉ በከፋ ሁኔታ ነገ የምንጋፈጠው መሆኑን በመረዳት ነበር።

    ዛሬ የዘር ፖለቲካ በድርስ ዘዋሪ አፍላ ጎረምሳዎችም፣ እድሜ በተጫናቸው በችግሩ አምጪ አዛውንቶችም በአስፈሪ ሁኔታ እየተራገበ እሳቱ ደግሞ በየቀኑ አገር የቆመችበትን ምሶሶ እየለበለበ የዜጎችን ነፍስ እየቀጠፈ ነው።

    አስገራሚው ነገር በተመሳሳይ ወቅት ያልተማርንበት የሩዋንዳ የዘር ፍጅት መታሰቢያ ለ25ኛ ጊዜ በዓለም መድረክ እየታወሰ ነው። እኛ እንደሌሎቹ ካለፈው መማሩ ቢሳነን ዛሬ እየሆነ ባለው በራሳችን ውድቀት ለመማር እንኳን ዝግጁ የሆንን አንመስልም።

    እርግጥ ነው መንግስት በቅርቡ የአገራችን መሠረታዊ ችግር የምንከተለው የብሔር ፖለቲካ ነው ሲል የደረሰበትን ድምዳሜ በግልፅ ማሳወቁ የተስፋ ምልክት ሆኖ ሊታይ ይችላል።

    ይህ በራሱ ግን ከዛሬው እልቂት የሚታደገን አይደለምና የፌደራል መንግስቱም ሆነ የሁለቱ ክልል መንግስታት በአፋጣኝ ይህን ሁኔታ ቀልብሰው ከዚህ በላይ ሌላ ጉዳት እንዳይደርስ እንዲከላከሉ ይህንን ሰይጣናዊ ተግባር የሚፈፅሙ አካላትንም በሕግ ተጠያቂ እንዲያደርግ እንደ አንድ ዜጋ ለመጠየቅ እወዳለሁ።

    ኢትዮጵያዊው ታማኝ በየነ (አሜሪካ)

    ምንጭ፦ ECADF Ethiopian News / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ተያያዥ ዜና፦ አጣየ፣ ካራቆሬ፣ ማጀቴ እና አካባው በሚኖሩ ዜጎች ላይ የታጠቁ ኃይሎች እያደረሱት ያለው ኢ-ሰብአዊ በደል

    ታማኝ በየነ


     

    Anonymous
    Inactive

    “ገና በጠዋቱ ሀገሪቱ መሪ እያላት ስርዓት አልበኝነት ነገሰ፣ ሕግ ረከሰ፣ የንፁሃን ደም በከንቱ ፈሰሰ የሚል ጩኸት ብዙዎች ቢያሰሙም የሽግግር ባኅሪው ነው በሚል ሚዛናዊ ምላሽ መስጠት አልተቻለም።”
    ———–

    ሚዛናዊነት ከራስ ቢጀምር ― ለክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር)

    አለማየሁ ገበየሁ

    ፍርድ ቤት የቆመችው የፍትህ ምስል /Lady Justice/ ተጠሪነቷና ምሳሌነቷ ለፍርድ ቤት ሥራ ብቻ አይመስለኝም። አይኗን ሸፍና ያላጋደለ ሚዛን የያዘችው አስተዳዳሪዎች በሞራል ሕግ ተመርተው ለዜጎች ሁሉ ሚዛናዊ አገልግሎትና ውሳኔ እንዲያስተላልፉ ነው።

    ዶ/ር አብይ አህመድ ደጋግመው ስለሚዛናዊነት ይሰብካሉ። ጋዜጠኞች የተመጣጠነ ዜና እንዲያቀርቡ፣ አክቲቪስቶች ከዋልታ-ረገጥ ሀሳብ ወደ መሃል እንዲመጡ፣ ፖለቲከኞች እኔ ብቻ ነኝ አዳኝህ ወይም የማውቅልህ ከሚለው አባዜ ተላቀው ለሌላውም ሥራ እውቅና እንዲሰጡ ወዘተ…

    የሚዛን መንሻፈፍ ግለሰብን፣ ማኅበረሰብንና ሀገርን እየቆየ እንደሚጎዳና ለማይጠገን ቀውስ እንደሚዳርግ የሚገነዘብ ሁሉ በዚህ ሀሳብ ይስማማል። ችግሩ ዶ/ር አብይ እንዳሉት ሁሉም ቀድሞ ጣቱን የሚቀስረው ሌሎች ላይ የመሆኑ አባዜ ነው። ይህ የጣት ቅሰራ ራሳቸው ዶ/ር አብይንም ይመለከታል። አንዱን ትልቅ ጥፋት ሸፋፍነህ ሌላው ላይ ጣትህን ስትቀስር ሚዛናዊነት ይንጋደዳል። አንዱን ትልቅ ጥፋት አላየሁም ብለህ አይንህን ከሸፈንክ ሌላኛው ጥፋት ላይ የአይንህን መጋረጃ ቀደህ ለመጣል ሞራል ታጣለህ።

    ከብዙ ምሳሌዎች የተወሰኑትን ብቻ እናንሳ። ገና በጠዋቱ ሀገሪቱ መሪ እያላት ስርዓት አልበኝነት ነገሰ፣ ሕግ ረከሰ፣ የንፁሃን ደም በከንቱ ፈሰሰ የሚል ጩኸት ብዙዎች ቢያሰሙም የሽግግር ባኅሪው ነው በሚል ሚዛናዊ ምላሽ መስጠት አልተቻለም። ከዚህ ይልቅ በቅድሚያ ለውጡ ያመጣቸውን ትሩፋቶች ሳትደባብቁ አሞግሱ ማለት መጣ። ትክክል ነው ሚዛናዊ ለመሆን የበርካታ ባኅሪያት/ ጥሩ ተናጋሪ፣ ትዕግስተኛ፣ ይቅር ባይ፣ ትሁትና የሰላም አጋር/ መሆናቸውን መመስከር ይቻላል። በዚህ ጥሩ ባኅሪ በመታገዝም መንግስታቸው አስደሳች ፖለቲካዊ ድሎች አስመዝግቧል። ይህ ማለት ግን ለውጡ መሳ ለመሳ እየተጓዘ ያለው ከነውጥ ጋር ነው ነው ማለት ስህተት አይደለም። ሕገ-ወጥነት ሀገሪቷን የወረረው ይቅርባይነት ስለበዛ ነው የሚል የቄለ ግምገማ የለኝም – በዚህ ረገድ መንግስታቸው ስትራተጂካዊ ብቃት የለውም የሚለው ሀሳብ የበለጠ ቅርብ ነው። አሁን በቅርቡ እንኳን የሀገራችን ስርዓት አልበኝነት ተግባር ከ8 እስከ 10 ወራት ይቀጥላል በማለት እንደ ዓመታዊ ዕቅድ ነግረውናል። ሕገ-ወጥነትን አምርሮ ከመታገል ይልቅ ከሕገ-ወጥነት ጋር ተቻቻሎ ለመኖር ማሰብ ገራሚ አቋም ነው። በተሸፋፈነች ፍትሃዊ አይን ሚዛናዊነትን እንይ ከተባለ ከዚህም በላይ ነው።

    መንግስት ባለበት ሀገር አሥራ ምናምን ባንኮች በጠራራ ፀሐይ ሲዘረፉ የሽግግር ሂደት ባኅሪው ነው የምትል ከሆነ ሌላውን ሌባ ወይም ሙሰኛ ለመገሰጥም ሆነ ፍርድቤት ለማቆም ይከብዳል። ምክንያቱም ፍ/ቤት የቆመችው የፍትህ ምስል ስለምትታዘብ። ለተቃውሞ ዱላና ገጀራ አደባባይ ይዞ የወጣ ማኅበረሰብ በቸልታ አልፈህ ያለዱላ ስብሰባ የከተመውን ወጣት በማያሳምን ምክንያት አስረህ የምታሸማቅቅ ከሆነ የሚዛናዊነት መሠረትህ ተናደ ማለት ነው። ይከበር እየተባለ የሚለፈፈው ሕግ ባለመከበሩ ዱላና ገጀራው አድጎ እነሆ ዛሬ የጦር መሣሪያ ይዞ አደባባይ መውጣት ተጀምሯል። በገዛ ፍቃድህ ሚዛናዊ ካልሆንክ ብሎም ቸልተኝነት እንደ ኩይሳ ካሳደግክ ሌሎች አደባባይ የተገተረውን የፍትህ ሚዛን በሌላ ጡንቻ ይሰብሩብሃል። ትርፉና ውጤቱም ይሄው ነው።

    የቸገረው የከተማ ህዝብ ከሰውነት ተራ ወጥቶ በሠራው ኮንዶሚኒየም አትገባም ተብሎ ገጀራ ሲወደርበት “የባለገጀራዎች ሀሳብ ይለምልም” ብሎ መግለጫ ማውጣት እንዴት ሚዛናዊ ሊሆን ይችላል? በቡራዩና ለገጣፎ ሰላማዊ ዜጎች ላይ የደረሰው መፈናቀል፣ እንግልትና አግላይ ርምጃዋች ከልብ ሳታወግዝ ሌላ ታፔላ ለጥፎ አደባብሶ ማለፍ የሚዛናዊነትን ጥያቄ ያስነሳል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሀገር የሚበትኑ ሀሳቦች ይወገዙ ይላሉ። በሀገሪቱ ያለው ሁለት መንግስት የአብይና የቄሮ ይባላል የሚል ትንታኔ የሚሰጠው ጃዋር የበርካታ በታኝ ሀሳቦች ባለቤት ቢሆንም ውግዘት አይመለከተውም። ኦሮሞ ከቋንቋው ውጭ ሌሎችን ማነጋገር የለበትም፤ ከሌሎች ጋር መጋባትም ማቆም አለበት የሚለው የ“ምሁሩ” በቀለ ገርባ አፓርታይዳዊ አስተያየት ለመመርመርም ሆነ ለመተቸት አልተፈለገም። በተቃራኒው የአዲስ አበባ ነዋሪዎችን ጥቅም ለማስጠበቅ በሚንቀሳቀሰው እስክንድር ነጋ ላይ ግልጽ ጦርነት እናውጃለን ተብሏል። ሲጠቃለል ዶ/ር አብይ በበቀለ፣ በኦነግ፣ በጃዋር፣ በሕገወጥ ፖለቲከኞችም ሆነ በእስክንድር ሀሳብ ላይ ሚዛናዊ መሆን አልቻሉም።

    ለዚህም ነው ማንኛውም ሚዛናዊ ለመሆን የሚጥር ሰው ለምን የሚል ቀጥተኛ ጥያቄና እንዴት የሚል የጀርባ ምፀት ለማንሳት የሚገደደው። ግዜ የሰጠው ቅል ድንጋይ እንዲሰብር ብሂሉ ስለሚያስገድድ? ምንም ቢሆን ዘር ከልጓም ስለሚስብ?… ኢትዮጵያዊነትን መርህ አድርጌያለሁ የሚል መሪ ለጃዋርም ሆነ ለእስክንድር ሀሳቦች እኩል የድጋፍም ሆነ የተግሳጽ መስፈርት ማበጀት ካልቻለ መርሁ ሁሉ ፈጥኖም ሆነ ዘግይቶ ለራሱ ችግር ይፈጥሩበታል (backfire ያደርግበታል)። ዶ/ር አብይ ከጊዜ ወደጊዜ እየገረጣ የመጣባቸውን ሕዝባዊ እምነት ስር ሳይሰድ ለማከም ከፈለጉ ሚዛናዊነት ከራሳቸው መጀመር ያለባቸው ይመስለኛል። ጥሩ መሪ ደግሞ እንደዛ ነው። መንገዱን የሚያውቅ፣ በመንገዱ የሚሄድ እና መንገዱን የሚያሳይ ስለሚሆን። ባለጊዜ ነን በሚሉ ቡድኖች የሚጊሩ አስከፊና አቀያያሚ ጉዳዮችን አደብ ማስገዛት፣ አቅም ቢያጥር እንኳን በግልጽ ‘አካፋን አካፋ’ በማለት ማውገዝ መጀመር አለባቸው። ከዚህ ከጀመሩ ሌላኛውን ብልሹ ሀሳብና ተግባር ለማረቅ ምቹ መደላድል ይፈጥራል። ይህ አካሄድ ልበ ሙሉነትን በቀላሉ ማትረፍ የሚያስችል ሲሆን፥ ከሁሉም አቅጣጫ በቂ ድጋፍ ያስገኛል። አክባቢዎን በሚያውቋቸው ሰዎች መሙላት ብቻ ሳይሆን ገለልተኛና ሚዛናዊ ሀሳብ የሚሰጡትንም አማካሪዋች ቢያበዙ ጭልጥ ብሎ ከመሳሳትም ያድናል።

    አለማየሁ ገበየሁ

    ሚዛናዊ


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ኢዜአ) – የአጼ ቴዎድሮስ ልጅ የልዑል አለማየሁ አፅም ከሀገረ እንግሊዝ ወደ እናት ሀገሩ እንዲመለስ ኢትዮጵያ ተጠየቀ። በተጨማሪም ለንደን ከተማ ውስጥ በቪክቶሪያ እና አልበርት ሙዚየም (Victoria and Albert Museum) የሚገኙ የኢትዮጵያ ቅርሶች ወደ አገራቸው እንዲመለሱ ጥያቄ ቀርቧል።

    በኢፌዴሪ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትር ዶ/ር ሂሩት ካሳው የተመራው የልዑካን ቡድን መጋቢት 13 ቀን 2011 ዓ.ም. በለንደን ጉብኝት አድርገዋል።

    በዚሁ ወቅትም በለንደን የዊንዶዘር ቤተመንግስት (Windsor Castle) የልዑል አለማየሁ ቴዎድሮስን መካነ መቃብር እና በቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን አፄ ሃይለስላሴ ይጸልዩበት የነበረውን ወንበር ጎብኝተዋል።

    ዶ/ር ሂሩት ካሳው በአጼ ቴዎድሮስ ልጅ ልዑል አለማየሁ መቃብር ላይ የአበባ ጉንጉን ማስቀመጣቸውን የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴርን እንደመረጃ ምንጭነት በመጥቀስ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) ዘግቧል።

    በጉብኝቱ ወቅትም “የአጼ ቴዎድሮስን ፀጉር ማግኘታችን ደስ ብሎናል፤ ይሁን እንጂ ከትውልድ ቦታው ተለይቶ ህይወቱ ያለፈው ልዑል አለማየሁ አፅም በትውልድ ሀገሩ እንዲያርፍ የኢትዮጵያዊያን ጥያቄ ስለሆነ በክብር ወደ አገሩ እንዲመለስ” ሲሉ ዶክተር ሂሩት ጠይቀዋል።

    አፅሙ ወደኢትዮጵያ ተመልሶ ከአባቱ አጼ ቴዎድሮስና ከኢትዮጵያ ህዝብ ጋር መቀላቀል እንደሚገባውና የዊንዶዘር ቤተመንግስት ለሚመለከተው አካል ጥያቄውን አቅርቦ በአፈጣኝ ምላሽ እንዲሰጥም ጥሪ አቅርበዋል።

    በዕለቱ ልዑካን ቡድኑን በመቀበል ከቡድኑ ጋር የተወያዩት የዊንዶዘር ቤተ-መንግስት ሃላፊ ዶ/ር ማርክ ፓወል በበኩላቸው በጉዳዩ ላይ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር እንነጋገርበታለን ብለዋል። ሂደቱን በተመለከተ በለንደን የኢትዮጵያ ኤምባሲ በመከታተል እልባት እንዲያገኝ አስፈላጊውን ጥረት እንደሚያደርግም ሚኒስቴሩ ተገልጿል።

    በሌላ በኩል የልዑካን ቡድኑ መጋቢት 12 ቀን 2011 ዓ.ም. ለንደን የሚገኘውን የቪክቶሪያ እና አልበርት ሙዚየም ጎብኝቷል። በዶ/ር ሂሩት ካሳው የተመራው የልዑካን ቡድኑና በለንደን የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ከሙዚየሙ ዳይሬክተር ዶ/ር ትሪስታራም ኸንት (Tristram Hunt, PhD) ጋር ተወያይቷል። በውይይቱ ወቅት በቪክቶሪያ እና አልበርት ሙዚየም የሚገኙ የመቅደላ ስብስብ ቅርሶች ወደ አገራቸው እንዲመለሱ ጥያቄ ቀርቧል።

    እ.አ.አ በ2018 የቪክቶሪያ እና አልበርት ሙዚየም የሚገኙ የመቅደላ ስብስብ ቅርሶች ለኢትዮጵያ መመለስ እንደማይችል፤ ነገር ግን በረጅም ጊዜ ውሰት ወደ ኢትዮጵያ እንዲገቡ ማድረግ እንደሚቻል መገለጹ ይታወቃል። የሙዚየሙ ዳይሬክተር ዶ/ር ትሪስታራም ኸንት ጥያቄው ተገቢ መሆኑን ጠቅሰው ውሰት የሚለው ቃልም ለኢትዮጵያውያን ከባድ መሆኑን እንደተረዱት ተናግረዋል። በመሆኑም “የተቸገሩት ጉዳዩ የሕግ ጉዳይ በመሆኑና ምላሽ ለመስጠት ያለን አማራጭ ይህ ብቻ ስለሆነ ነው ” ብለዋል።

    “ያለን አማራጭ ይህን ቀዳዳ በመጠቀም ሊስተካከሉ የሚችሉ አባባሎችን ተጠቅመን የሚመለሱበትን ሁኔታ መፍጠር፤ ይህን ካላደረግን ግን በሕጉ ላይ ጸንተን ወደፊት የሚሆነውን ነገር መመልከት ይኖርብናል” ሲሉም ዶ/ር ኸንት አክለዋል።

    የባህል ሚኒስትሯ ዶ/ር ሂሩት ቅርሶቹ የኢትዮጵያ በመሆናቸው በረጅም ጊዜ ውሰት ሳይሆን በቋሚነት ቅርሶቹ ለኢትዮጵያ መመለስ የሚችሉበት አማራጭ መፍትሄ ሙዚየሙ ሊያበጅ እንደሚገባ አመልክተዋል።

    በኤምባሲውና በሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ በኩል በአስቸኳይ መግባቢያ ሰነድ በመፈራረም፣ ካለው ሕግ ጋር በማይጋጭና የኢትዮጵያን ጥያቄ ሊመልስ በሚችልበት ሁኔታ በመንቀሳቀስ ጉዳዩ በሚቀጥሉት ጥቂት ወራት እልባት እንደሚያገኝ ዳይሬክተሩ ገልጸፀዋል።

    በለንደን ያለው የኢትዮጵያ ኤምባሲም ባለው ሙሉ አቅምና ጊዜ የሚጠበቅበትን ኃላፊነት በመወጣት ቅርሶቹ ወደ አገራቸው እንዲገቡ እንደሚያደርጉ በብሪታኒያ የኢትዮጵያ አምባሳደር ፍስሃ ሻወል ገብሬ ገልጸዋል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ልዑል አለማየሁ


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– ከ12 ቀናት በፊት የተከሰከሰው ንብረትነቱ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሆነው የቦይንግ 737 ማክስ 8 (Boeing 737 MAX 8) አውሮፕን አብራሪ ተገቢዉን የምሰለ በረራ (simulator) ስልጠና አልወሰደም በሚል መጋቢት 11 ቀን 2011 ዓ.ም. ዘ ኒው ዮርክ ታይምስ (The New York Times) ሰላም ገብረኪዳን በተባለች ትውልደ ኢትዮጵያዊት ጋዜጠኛ ፀሐፊነት ያወጣው ዘገባ ከእውነት የራቀ መሆኑን የኢትዮጵያ አየር መንገድ አስታወቀ።

    “ምንም እንኳን የኢትዮጵያ አየር መንገድ ማክስ ምስለ በረራ ቢኖረውም የተከሰከሰውን አውሮፕላን ያበር የነበረው ፓይለት የዚህ ምስለ በረራ ስልጠና አልተሰጠውም” (Ethiopian Airlines had a Max 8 simulator, but pilot on doomed flight didn’t receive training on it) በሚል ርዕስ ኒው ዮርክ ታይምስ ያወጣው ዘገባው ከእውነት የራቀና ኃላፊነት የጎደለው መሆኑንም አየር መንገዱ አመለክቷል።

    የአደጋው መንስዔ እየተጣራ ባለበት በአሁኑ ሰዓት ሁሉም አካላት እንዲህ መሰል አሳሳች መረጃ ከማሰራጨት እንዲታቀቡም አየር በሚገባ መንገዱ በአጽንዖት አሳስቧል።

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ ጉዳዩን አስመልክቶ ባወጣው መረጃ፥ የተከሰከሰው አውሮፕላን አብራሪ ሁሉንም አግባብነት ያላቸው የበረራ ስልጠናዎችን መውሰዱን አስታውቋል።

    ● SEMONEGNA on Social Media: FacebookTwitterInstagramPinterest

    አውሮፕላን አብራሪው በቦይንግ የአውሮፕን አምራች ኩባንያ (The Boeing Company) እና በአሜሪካ አቪዬሽን አስተዳደር (US Federal Aviation Administration) የተቀመጡ ሁሉንም የበረራ ስልጠናዎችን መውሰዱንም ነው በመግለጫው የገለጸው።

    ዋና አብራሪው ከወራት በፊት በኢንዶኔዥያው ላየን ኤየር (Lion Air) በደረሰው ተመሳሳይ የአውሮፕላን አደጋ ጋር በተያያዘ አስፈላጊዉን የአደጋ ጊዜ የበረራ መመሪያ በቂ ግንዛቤ እንደተሰጠዉም ተገልጿል።

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ አብራሪዎቹን ለማሰልጠን የሚያስችሉ የተሟሉ 7 ምስለ በረራዎች ወይም የበረራ ማሰልጠኛዎች እንዳሉት አስታውቋል። በአሁን ወቅት ብቁና የተሟሉ ኪው 400፣ ቢ737 ኤን ጂ፣ ቢ 737 ማክስ፣ ቢ 767 ፣ ቢ 787 ፣ ቢ 777 እና ኤ 350 የተሰኙ ሰባት ምስለ በረራዎች እንዳሉት ይፋ አድርጓል።

    በአፍሪካም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከተሟላ የስልጠና መሣሪያ ጋር በቂ ስልጠና ከሚሰጡት ጥቂት ተቋማት መካከል አንዱ መሆኑንም ነው ያስታወቀው – የኢትዮጵያ አየር መንገድ። ባለፉት አምስት ዓመታት ብቻ ባልተለመደ ሁኔታ ከስልጠና ጋር ተያይዞ ለመሠረተ ልማት ግንባታ ከግማሽ ቢሊየን ዶላር በላይ ወጭ እንዳደረገ ተነግሯል።

    የዓለም አቀፍ ሕግን በመከተል የአደጋው መንስዔ ተጣርቶ ይፋ እስከሚደረግ ድረስ በትዕግስት መጠበቅ ተገቢ መሆኑንም አየር መንገዱ አስታውቋል።

    ምንጭ፡- የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ዘ ኒው ዮርክ ታይምስ


    Semonegna
    Keymaster

    ከአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት የተሰጠ መግለጫ

    የተከበራችሁ የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች !!

    አገራችን ኢትዮጵያ 76 ብሄር፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች የሚኖሩባት ታላቅ አገር ነች። የሕዝባችን አብሮ የመኖር እሴት የሰው ልጆች መደበኛ ማኅበራዊ ግንኙነት ተሻግሮ በደም ዝምድና ተጋምዶ በባህል ተሳስሮ ላይለያይ ተቆራኝቷል። ይህ ህብረት የብሄር ማንነት እና የእምነት ልዩነት ሳይለያየው ለሺህ ዓመታት፣ ሺህ ችግሮችን ተጋፍጦ ይሄው ዛሬም ድረስ በጋራ ዘልቋል።

    የዚህ አኩሪ ታሪክ ጉዞ አልጋ ባልጋ ያልነበረ ከመሆኑ ባሻገር፣ ሕዝባችን የሚያነሳቸው የፍትህ፣ የዴሞክራሲና የልማት ጥያቄዎች በተለያዩ ጊዜያት የነበሩትን መንግሥታት በመታገል ለመብቱ የተከራከረበት ወቅትም በርካታ እንደነበር የሚታወቅ ነው። በተለይም ባለፉት ሦስት ዓመታት በአገሪቱ የተለያዩ ቦታዎች የተነሱት የፍትህ፣ የዴሞክራሲ፣ የመልካም አስተዳደር፣ የሰብዓዊ መብትና ሌሎች መሠረታዊ ጥያቄዎች ምክንያት በአገሪቱ ለውጥ አንዲመጣ አድርጓል።

    ከለውጡ ማግስት ጀምሮ ኢትዮጵያዊንን እና ሌላውን ዓለም ያስደመሙ በርካታ የለውጥ እርምጃዎች ተወስደዋል። ከተማችንም ዘመን ተሻጋሪና ተጨባጭ ውጤቶች እየተከናወኑና ቀደም ሲል ሕዝባችን ያነሳቸው የነበሩ የፍትህ፣ የዴሞክራሲ፣ የእኩልነት፣ የልማትና መሰል አጀንዳዎች ቅድሚያ ተሰጥቷቸው እንዲመለሱ እየተደረገ ይገኛል።

    በመሪ ድርጅታችን ኢህአዴግ የሚመራው የከተማችን አስተዳደር ሰላም፣ ልማትና ዴሞክራሲ መርሆዎችን ተከትሎ የአዲስ አበባ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊ ችግሮችን ለመፍታት ከፍተኛ እንቅስቃሴ በማካሄድ ውጤታማ ሥራዎች መከናወናቸው የከተማው ነዋሪ የሚመሰክረው ሃቅ ነው።

    በሌላ በኩል የከተማችን ነዋሪዎች ሕገ-መንግሥቱ በሰጣቸው ሥልጣን መሠረት በከተማው ሕዝብ ተሳትፎ ወኪሎችን በመምረጥ ሕዝቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ በርካታ ሥራዎች ተከናውነዋል፤ እየተከናወኑም ይገኛሉ። ይህ ሲባል ሕዝቡ ከአስፈፃሚው አካል ጐን ሆኖ ባያግዝና ባይሳተፍ ኖሮ አሁን የተገኘውን ውጤት ማስመዝገብ አይቻልም ነበር።

    ስለሆነም የከተማችን ነዋሪዎች በሁሉም የሥራ መስኮች ያልተቋረጠ ድጋፍ ያደረገና እያደረገ ያለ ሲሆን በተለይም የአዲስ አበባ ሰላም ተጠብቆ እንዲቀጥል በማድረግ ለሁሉም የአገራችን አካባቢዎች ትልቅ ትልቅ ተምሳሌት ሆኖ ይገኛል። በመሆኑም ሕዝቡ ላበረከተው አስተዋጽኦ ከፍተኛ ምስጋናና ዕውቅና ሊቸረው ይገባል።

    ይሁንና አሁንም በከተማችን የሚስተዋሉና በልዩ ትኩረት ሊፈቱ የሚገባቸው ችግሮች እንዳሉ በመገንዘብ ችግሮችን ለመፍታት የከተማው አስተዳደር ያላሰለሰ ጥረት እያደረገ እንደሆነ እና ምከር ቤቶችም የክትትል ድጋፍና ቁጥጥር ሥራችን አጠናክረን የተጠያቂነት አሠራር በጥብቅ ዲስፒሊን እየተመራ ተግባራዊ አየተደረገ ይገኛል።

    ከምክርቤቱ የምርጫ ዘመንጋር ተያይዞ ለሚነሱ ጥያቄዎች የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መካሄድ የነበረበትን የአዲስ አበባ ከተማ ምርጫ እንዲራዘም በወሰነው መሠረት እና እንዲሁም ሰኔ 30 ቀን 2010 ዓ.ም. የከተማውን አስተዳደር ቻርተር አዋጅ ቁጥር 361/1995ን ለማሻሻል ባወጣው አዋጅ ቁጥር 1094/2010 አንቀጽ 2 ንዑስ አንቀጽ 2 መሠረት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የምርጫ ጊዜ እንዲራዘም የወሰነ እና “ምርጫ ተደርጐ በምርጫው መሠረት አዲስ አስተዳደር እስኪደራጅ ድረስ በሥራ ላይ ያለው ምክር ቤቱ እና አጠቃላይ የከተማው የአስተዳደሩ በነበረበት ሁኔታ ይቀጥላል” በሚል በደነገገውና በወሰነው ውሳኔ መሠረት ህጋዋ ዕውቅና አግኝቶ የቀጠለ አስተዳደር እንደሆነ ሊታወቅ የሚገባው ሲሆን በዚሁ አዋጅ ቁጥር 1094/2010 አንቀጽ 3 ስር “ምክትል ከንቲባው ከምክር ቤት አባላት ውስጥ ወይም ከምክር ቤት አባላት ውጭ የሚሾም ሆኖ የሥራ ዘመኑ የምክር ቤቱ የሥራ ዘመን ይሆናል”ተብሎ በግልጽ በተደነገገው መሠረት የከተማው ምክር ቤት ሐምሌ 10 ቀን 2010 ዓ.ም. ባካሄደው ስብሰባ የከተማውን ምክትል ከንቲባ ሹመት በወቅቱ በተገኙት ምክር ቤቱ አባላት በሙሉ ድምፅ አጽድቋል።

    ስለሆነም “የከተማውን ምክትል ከንቲባ ሹመት የነዋሪው ውክልና የለውም” ህጋዊ አይደለም በሚል የሚነሱ የተሳሳቱ አስተሰሰቦች ምንም ዓይነት ህጋዊ መሠረት የሌላቸው እና በስሜት ብቻ የሚንጸባረቁ እንዲሁም በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የወጣውን አዋጅ ቁጥር 1094/2010 የሚፃረር እና ህገወጥ እንደሆነ ሁሉም የከተማችን ነዋሪ ሊረዳው ይገባል።

    ይሁንና አስተዳደሩ በከተማችን ነዋሪ ተሳትፎ ጭምር በአገር ደረጃ የተጀመረውን የለውጥ ጉዞ ለማስቀጠል ሌት ተቀን ደፋ ቀና በሚልበትና በዕቅድ ተይዘው እየተተገበሩ ያሉ በርካታ የልማትና የመልካም አስተዳደር ተግባራትን ለማሳካት እየተረባረበ እና ከፍተኛ ውጤት እያስመዘገበ ባለበት በዚህ ወቅት አንዳንድ ወገኖች በሕግ የተቋቋመውን የአስተዳደሩን ተግባራት በማደናቀፍ የሕዝብ ያልሆኑ ጥያቄዎችን የሕዝብ በማስመሰል ሲንቀሳቀሱ ይስተዋላል።

    ስለሆነም በአገራችን ብሎም በከተማችን የመጣውን ለውጥ ለማደናቀፍ በቅርቡ በከተማችን ሰላምን ለማደፍረስ እየታዩ ያሉ ኢ-ሕገመንግሥታዊ እንቅስቃሴዎችን በትኩረት በመከታተልና ሕገወጥ እንቅስቃሴ አድራጊዎችን በሰላማዊ መንገድ በመታገል የከተማችን ነዋሪዎች እንደወትሮው ሁሉ የከተማችንን ሰላም በማስከበር የተጀመረውን ልማት በማስቀጠል የበኩሉን አስተዋጽኦ በማድረግ ከከተማው አስተዳደር ጐን እንደሚቆም ያለንን ጽኑ እምነት እየገለጽን፡-

    1ኛ. ሕዝብን ከሕዝብ የሚያጋጩ፣ ከአንድነት ይልቅ ልዩነትን የሚያራግቡ፣ በህጋዊ መንገድ በተመረጠው አስተዳደር ላይ አመጽ የሚያነሳሱ ማናቸውም ድርጊቶች ለማንም የማይጠቅም ህገወጥ ድርጊት እና ፀረ-ህገመንግሥትም ስለሆነ ባስቸኳይ እንዲቆም፤

    2ኛ. አሁን ያለው የከተማው አስተዳደር ህጋዊ መሠረት ያለው እና በም/ቤቱ ፀድቆ የተሾሙ በመሆኑ መላው የከተማው ነዋሪዎች ከከተማው አስተዳደር ጐን በመቆም በከተማችን ነዋሪዎች ድምፅ ውክልና የተሰጠውን ም/ቤት ሥልጣን ወደጐን በመተው እየተነሱ ያሉ የማደናገሪያ አስተሳሰቦችን አምርሮ እንዲታገል፤

    3ኛ. በከተማችን ውስጥ የላቀ ልማት ለማስመዝገብ፣ ዘላቂ ሰላምና ዋስትና ያለው ዴሞክራሲ እንዲሰፍን ለማድረግ የሁሉም ወገኖች የጋራ ጥረትን የሚጠይቅ በመሆኑ ለውጡን ባስተማማኝ ሁኔታ ለማስቀጠል የከተማችን ነዋሪዎች ሁሉን አቀፍ ትብብር እንዲያደርጉ እና ከከተማው አስተዳደር ጐን እንዲቆሙ ጥሪ እያቀረብን፣ የብሄርብሄረሰቦችና ሕዝቦች የቃልኪዳን ሠነድ እና የህጐች ሁሉ የበላይ የሆነውን ሕገመንግሥት የማክበር፣ የማስከበርና የመጠበቅ ኃላፊነታችሁን በመወጣት ሕዝቡን በማደናገር የከተማችንን ሰላም ለማደፍረስ ሌት ተቀን የሚጥሩ ኃይሎችን በመታገል ከከተማ አስተዳደሩና ከምክርቤቱ ጐን በመሆን የበኩላችሁን አስተዋጽኦ እንድታደርጉ፤

    4ኛ. የአዲስ አበባ ጉዳይን በተመለከተ ከተማችን የሁሉም ብሄር ብሄረሰቦችና ሕዝቦች በፍቅር፣ በመተሳሰብና በመቻቻል በአብሮነት ለሰላም ልማትና ዴሞክራሲ ዘብ የቆመ ሕዝብ የሚኖርባት የሁላችንም ከተማ የአፍሪካ መዲና፣ የዓለም አቀፍ ዲፕሎማቶች መኖሪያ መሆንዋ ታውቆ ከከተማው ጋር ተያይዞ የሚነሱ ጥያቄዎች የሕጐች ሁሉ የበላይ በሆነው የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ሕገ-መንግሥት ምላሽ የሚያገኝ ስለሆነ ፍጸም የግጭት መንስኤ መሆን አይገባውም፤

    5ኛ. የከተማው አስተዳደር እንደሌላው ጊዜ ሁሉ የከተማውን ሰላምና ፀጥታ ከማስከበር ባሻገር እያከናወነ ያላቸውን የልማትና የመልካም አስተዳደር ፕሮግራሞችን አጠናክሮ እንዲቀጥል እያሳሰብን፣ እንደወትሮው ሁሉ የከተማችን ነዋሪዎችም ህግና ሥርዓት እንዲከበርከ አስተዳደሩ፣ ከሕግ እና የፀጥታ አስከባሪ አካላት ጐን በመሆን ለሰላም ዘብ በመቆም የተለመደው ትብብሩን እንዲቀጥል እንጠይቃለን።

    እናመሰግናለን!

    ወ/ሮ አበበች ነጋሽ
    የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ
    አዲስ አበባ
    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት


    Semonegna
    Keymaster

    ግልጽ ደብዳቤ ለኢትዮጵያ ሕዝብ በአቶ ነአምን ዘለቀ ― አቶ ነአምን ዘለቀ ራሳቸውን ከአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ አገለሉ
    ———

    ለአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ አባላት፣ የሠራዊት አባላት፣ ደጋፊዎችና፣ በልዩ ልዩ መደረኮች ለምታውቁኝ ኢትዮጵያውያን በሙሉ፦

    በሀገራችን የመጣውን ለውጥ ተከትሎ የአርበኞች ግንቦት 7 የዴሞክራሲና የአንድነት ንቅናቄ (አግ7) አመራር አባላት እ.ኤ.አ. በሀምሌ (July) ወር 2018 በአሜሪካን ሀገር ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ጋር በተደረገ ስብሰባ ላይ ከተደረሱት የስምምነት ነጥቦች መካከል አንዱ የአግ7 ንቅናቄ ሠራዊት ከኤርትራ በርሃና ከሀገር ውስጥም የነበሩት የአግ7 ታጣቂዎች ወደ ሀገር ወደ ሰላማዊ ኑሮ መመለስና ማቋቋምን የሚመለከት ነበር። በዚህም መሠረት በኤርትራ የነበሩ የንቅናቄው ሠራዊት አባላት እንዲሁም በየበረሃው የነበሩ የንቅናቄው ታጣቂዎች ወደ ልዩ ልዩ ካምፖች በየጊዜው እንዲገቡ መደረጉ ይታወቃል። በብዙ መቶ የሚቆጠሩ የንቅናቄው አባላትም ከልዩ ልዩ እስር ቤቶች ቀደም ሲል በተከታታይም እንደተለቀቁ ይታወቃል። በኃላፊነት ስመራ በቆየሁት በውጪው ዘርፍ ስር የማኅበራዊ ፈንድ ኮሚቴ እንዲቋቋም በማድረግ በውጭው ዓለም በሚገኙ በንቅናቄው አባላት፣ በደጋፊዎች፣ እንዲሁም አገር ወዳዶች ትብብር መጠነ ሰፊ ገንዘብ በማሰባሰብ በየእስር ቤቱ የነበሩት ተጋዮች ለሦስት ተከታታይ ወራት እንዲረዱ እንዲሁም ከኤርትራ በረሃ ለመጡትና በካምፕና ከካምፕ ውጭ ለሚገኙትም በልዩ ልዩ መንገዶች እርዳታዎች እንዲያገኙ ለማድረግ ተችሏል።

    ከኤርትራ በረሃ ወደ አገር ቤት እንዲገቡ የተደረጉትን የአርበኞች ግንቦት 7 የቀድሞ ታጣቂዎች እንዲሁም የሌሎች የፓለቲካ ድርጅቶች ታጣቂዎችን መልሶ የማቋቋሚያ ፕሮጄክት ጽ/ቤት በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት ስር ከ7 ወራት በፊት የተመሠረተ ሲሆን፥ የውጭ መንግስታትም በተለይም የጀርመን መንግስት ለዚሁ የሚውል ገንዘብ ለመስጠት ከበርካታ ወራት በፊት ተስማምተው ነበር። ሆኖም ከተቋቋመው ጽ/ቤት አቅም ማነስ እንዲሁም ጉዳዩ ተገቢውን ውሳኔዎች ሳያገኝ እየተጓተተ በመቆየቱ ሳቢያ የአርበኞች ግንቦት 7 ሠራዊት አባላት (በተለይም ከካምፕ ውጪ እንዲቆዩ ተደርገው መልሶ የማቋቋሚያ ድጋፍ እንዲጠብቁ የተነገራቸው ጭምር) ለከፍተኛ ችግር መዳረጋቸው ለህሊና እረፍት በሚነሳ ሁኔታ ውስጥ እራሴን አግኝቼ ነበር።

    የንቅናቄው ሊቀመንበር ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ እንዲሁም ዋና ጸሃፊ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ችግሩ መፍትሄ እንዲያገኝ በየጊዜው ከጠቅላይ ሚንስትሩና ከሌሎች የመንግስት ኃላፊዎች ጋር የሚያደርጉት ግንኙነትና ክትትል እንደተጠበቀ ሆኖ፤ በችግር ላይ የነበሩ የሠራዊት አባላት ሁኔታ አየተደራረበ የጭንቀት ድምጾች እየተበራከቱ በመምጣታቸው፣ ይህ ጉዳይ የንቅናቄውን ሊቀመንበርና ዋና ጸሐፊውን ብቻ የሚመለከት ሳይሆን አባላትና ሠራዊቱ የመረጡን የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላትን በሙሉ በተናጠልም ሆነ በጋራ የሚያስጠይቅ፣ ለሠራዊቱም ሆነ ለአባላት ኃላፊነት አለብን በሚል መንፈስ ይህ ለውጡን ለሚመራው መንግስትም የጸጥታና የፓለቲካ ችግር የሚፈጥር ሁኔታ፣ ከሞራልም ሆነ ከፓለቲካ እኳያ የንቅናቄውንም ውስጣዊ ጤንነት እየተፈታተነ የነበረ ትልቅ ችግር እየሆነ በመምጣቱ፣ ለችግሩ አፋጣኝ መፍትሄ እንዲሰጥ እርዳታ ለመስጠት ቃል ከገቡና ለመርዳት ፈቃደኛ ከሁኑ መንግስታት በተለይም ከጀርመን አምባሳደር፣ ከስዊድን መንግስት ኃላፊዎችና የፓርላማ አባላት፣ ከልዩ ልዩ የመንግስት ኃላፊዎችና ከመንግስት መዋቅር ውጭ የሚገኙ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሚቀርቡ ግለሰቦች ጋር በመገናኘት ለማስረዳትና መፍትሄ እንዲያገኝ የበኩሌን አስተዋጽዖ ለማድረግ ጥረቶች ሳደርግ ቆይቻለሁ።

    ብዙ ዝርዝሮች ያሉትና ወራት ያስቆጠረ ሂደት ቢሆንም፣ በዚህ አጋጣሚ ለዚህ ችግር መፍትሄ በማፈላለግ ሊያዳምጡን በራቸውን ለከፈቱ የልዩ ልዩ የመንግስት ተቋማት ኃላፊዎች፣ በተለይም የብሄራዊ አደጋና መከላከል ኮሚሽነር ምትኩ ካሳ፣ አምባሳደር ብርቱካን አያኖ፣ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት አማካሪ አምባሳደር ግርማ ብሩ፣ ጠቅላይ አቃቤ ሕግ አቶ ብርሃኑ ጸጋዬ፣ እንዲሁም ከመንግስት መዋቅር ውጭ ያሉና ከለውጡ በኋላ ከጠቅላይ ሚንስትሩ ሊያገኙን እንደሚፈልጉ በላለቤቴ በኩል መልክት የላኩብኝ የጠቅላይ ሚኒስሩ የአርቅ ኮሚቴ አባል አቶ ብርሃን ተድላ፣ በበርካታ የሕዝብና የሀገር ጉዳዮች ያላሰለሰ አስተዋጽኦ የሚያደርጉትና የረጅም ጊዜ ወዳጄ ለሆኑት ዶ/ር አምባሳደር ካሳ ከበደ፣ በጉዳዩ ላይ ትኩረት ሰጥተው ለመርዳት ለተንቀሳቀሱት፣ በእርዳታና በመልሶ ማቋቋም ከፍተኛ ልምድና ዕውቀት ያላቸው ለሻለቃ ዳዊት ወልደ ጊዮርጊስ፣ እንዲሁም ለመለሶ ማቋቋም የተቋቋመው መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ኣፍሪድ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ቴዎድሮስ ይልማ፣ ሌሎችም ለችግሩ መፍሄ ለማግኘት ያገኘኋቸውን ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ሁሉ እስከአሁኑ ቀን ድረስ ለከፍተኛ ችግር ተዳርገው በሚገኙት የሠራዊት አባላት ስም ምስጋና ሳላቀርብ አላልፍም፡፡ በአንጻሩ ደግሞ ትላንት ከለውጡ በፊት እንኳን እነሱን ደጅ ልንጠና ቀርቶ አጠገባቸው ለመድረስ እንኳን የምንጸየፋቸው፣ የተቀመጡበት የኃላፊነትና የአማካሪነት ቦታ የሀገርና የህዝብ ችግሮች ለመፍታት መሆኑ እምብዛም የሚያስጨንቃቸው የማይመስሉ፣ ራሳቸውን የኮፈሱ አድርባዮች፣ ከንቱና ግብዝ የመንግስት ባለሟሎች በዚህ ሂደት ለመታዘብ ችያለሁ።

    የሆነ ሆነ ይህ ከፍተኛ ችግር መፍትሄ እንዲያገኝና በውጭ የሚገኙትም ሆኑ በካምፕ ውስጥ የሚገኙት የንቅናቄያችን ሠራዊት አባላት ቢያንስ አቅም ባለው፣ ሠራዊቱ የሚገኝበትን ችግር ለማቃለል ብቃትና ተቋማዊ ቁመና ለዓመታት ባካበተ የመንግስት ኮሚሽን በኩል እንዲሆን የሚያስችል እርምጃ እንዲወሰድ በቅርብ ቀን መወሰኑን አዲስ አበባ በነበሩኩባቸው አራት ሳምንታት ከሚመለከታቸው የመንግስት ኃላፊዎች ጋር በተደረገ ውይይት አረጋግጫለሁ። ይህም እርምጃ ለወራት የቆየን ከባድ የህሊና ሸክም ያቃለለ ቢሆንም፣ አሁንም ከካምፕ ውጭ የሚገኙ የሠራዊቱ አባላት የሚገኙበትን ዘርፈ ብዙ ማኅበራዊ ችግሮች አስመልክቶ በየዕለቱ በርካታ መረጃዎች እየደረሰን በመሆኑ ከካምፕ ውጭም ሆነ ከካምፕ ውስጥ የሠራዊቱ አባላት ቃል የተገባላቸው እርዳታ እንዲደርሳቸው፣ የመልሶ ማቋቋሙ ሂደት በቶሎ እንዲጀመር፣ የንቅናቄው የሥራ አፈጻሚ ኮሜቴ እንዲሁም ጉዳዩ የሚመለከታቸው የመንግስት ኃላፊዎች የሚያስፈልገው ያልተቋረጠ ትኩረትና ክትትል እንዲያደርጉ በድጋሚ ለማሳሰብ እወዳለሁ።

    ሀገራችን ኢትዮጵያ ዘርፈ ብዙ ተግዳሮቶችና ህልውናዋን የሚፈታተኑ ስጋቶች የተጋረጡባት ከመሆኗም በሻገር ከምንጊዜውም በባሰ መልኩ መስቀለኛ መንገድ ላይ የምትገኝ መሆኑን በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ሁሉ የሚስማሙ ይመሰለኛል። ይህን አደጋ ለመቋቋም ደግሞ በርካታና ዘርፈ ብዙ ሕዝብ አቀፍ እንቅስቃሴዎች ያስፈልጋሉ። ስለዚህም ውስብስብ በሆኑና ስር በሰደዱ መጠነ ሰፊ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፓለቲካዊ ችግሮች አውድና ከባቢ ውስጥ ተዘፍቀው ለኢትዮጵያ ዴሞክራሲ፣ ፍትህና፣ የሕግ የበላይነትን ለማስፈን እየተደረገ በሚገኘው የለውጥ ጅማሮ እንዳይቀለበስ የለውጡን አራማጆች፣ ለውጡን ለማስቀጠል በተጨባጭ እርምጃዎች እስከተንቀሳቀሱ ድረስ ማገዝ አማራጭ የሌለው ነው ብዬ አምናለሁ።

    ሀገራችንን ቅርጫ ለማድረግ ሲሉ የ100 ሚሊዮን ህዝብ ዕጣ ፈንታ ላይ ቁማር የሚጫወቱ፣ የሕዝብን የተሻለ ህይወት፣ ለሁሉም የኢትዮጵያ ልጆች የታገሉለትን፣ የሚመኙትን ፍትህ፣ ነጻነትና የነገን ተስፋ እየረጋገጡ የሚገኙ እጅግ ራስ ወዳድ፣ ስግብግብ ህሊና ቢሶች፣ የኢትዮጵያን ልዩ ልዩ ማኅበረሶቦች አብሮነት አጥፍተው ለራሳቸው ጠባብ ብሄረተኝነት እጀንዳ ጥቅምና ስልጣን ለማምጣትም ሆነ ለማስቀጠል በየአካባቢው ትርምስ የሚፈጥሩ፣ ክቡር የሆነውን ሰብዓዊነት ረግጠው ወደ አራዊትነት በተጠጋ የለየለት ጽንፈኝነትና አክራሪነት የታወሩ ጥቂቶች፣ ከራሳቸው ግላዊ ፍላጎትና ጥቅም ውጭ ለሕዝብና የሀገር ደህንነት፣ ለሰላም፣ ለፍትህና፡ ለሕግ የበላይነት ምንም ቁብ የማይሰጡ የጥፋት ኃይሎች በአብዛኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች እንደአሸን በፈሉበት ሁኔታ ከኢትዮጵያዊነት ውጪ፣ ከፍትህ፡ ከእኩልነትና፣ ከሕዝብ አብሮነት የተለየ ሌላ አማራጭ እንደሌለ፣ ሌላ ሀገር፣ ሌላ ምድርም አለመኖሩን በሚገባ የተረዱ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ሁሉ በየአካባቢያቸው እያፈጠጠ፣ እያገጠጠ ከሚገኘውን የህልውና አደጋ ከእነዚህ አክራሪና ጽንፈኛ የጥፋት ኃይሎች ሊያመጡት ከሚችሉት የሀገራችንን የመኖር አለመኖር ህልውና የሚፈታተን የሲኦል ጎዳና ራሳቸውን፣ ቤተስባቸውንም ለመከላከል፣ ተከላካይ በሆነ መልኩ እርስ በእርስ መደራጀት፣ እንዲሁም ራስን በራስ ማደራጀትና፣ ብሎም ነቅቶ መጠበቅ ሌላው አስፈላጊና ወቅታዊ ተግባር ነው ብዬ አምናለሁ።

    ለአገራችን ሕልውና፣ ለሕዝባችን ሰላም፣ ፍትሕና ዴሞክራሲያዊ ስርዓት የሰፈነባት ኢትዮጵያ እንድትኖር የሚያስችል የፓለቲካ ስርዓት እንዲረጋገጥ የሚጨነቁ ኢትዮጵያውያን ሁሉ እልህ አስጨራሽ ሁኔታ ውስጥ ብንገኝም ከዚህም ከዚያም የሀገሪቱን ህልውና አደጋ ላይ እየጣሉ የሚገኙ አክራሪና ጽንፈኛ ብሄረተኞችና የለውጥ ቅልበሳ ቡድኖች ወጥመድ ሰላባ ላለመሆን በስልት፣ በሰከነ ጥበብና በሃገራዊ ኃላፊነት መንቀሳቀስ የግድ ነው ብዬ አምናለሁ። ለኢትዮጵያዊነት፣ ለሁሉም ኢትዮጵያዊያን ዜጎች እኩልነትና ሁለንተናዊ መብቶች የቆሙ የፓለቲካ ኃይሎች፣ የሲቪክ ተቋማት፣ እንዲሁም የፕሬስ ድርጅቶችን ማጠናከር እንዲሁ ሌላቅ የወቅቱ ዐቢይ ተግባራት ይመስሉኛል።

    በሀገራችን የተጀመረው ለውጥ ከመጣ ከጥቂት ወራት በኋላ ንቅናቄው የፓለቲካ ፓርቲ እንደሚሆን ስምምነት በተደረሰ ጊዜ የፓለቲካ ፓርቲ አመራርም ሆነ አባል ሆኜ ለመቀጠል ፍላጎት እንደሌለኝ በአመራሩ ላይ ለሚገኙ ሁሉ በተለያዩ ጊዜያት ገልጬ ነበር። እስካሁንም ድረስ የቆየሁት ከመሪዎች አንዱ ሆኜ እንዳገለግል ለመረጡኝ አባላትና የሠራዊት አባላት ባለኝ ኃላፊነትና ተጠያቂነት ቢያንስ ከኤርትራ በርሃና በኢትዮጵያም ውስጥ ሆነው በጨለማው ዘመን ለኢትዮጵያ አንድነትና ለሕዝብችን ነጻነት ህይወታቸውን ለመገበር ለቆረጡ እነዚህ ዛሬ በካምፕ ውስጥና ከካምፕ ውጭ የሚገኙ የሠራዊት አባላትና ታጋዮች ህይወት ተገቢውን መስመር እስኪይዝ ነበር።

    ቀደም ሲል መልቀቂያ አስገብቸ የነበረ ቢሆንም እንኳን የንቅናቄው ዋና ጸሀፊ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ጨምሮ የተለያዩ የንቅናቄው አመራሮች በኃላፊነቴ እንድቆይ በነበራቸው ፍላጎት፣ እኔም ከነሱ ጋር ባደረኳቸው ውይይቶች በቦታው መቆየቴ ሠራዊቱን ይጠቅማል ብዬ ስላመንኩ እስካሁን ድረስ በተሰጠኝ የኃላፊነት ቦታ ላይ የምችለውን እያገዝኩ ቆይቻለሁ። ሆኖም ለቆሙለት ዓላማ፣ ለንቅናቄያቸውና ለሀገራቸው ክብር መተኪያ የሌላት ህይወታቸውን ለመክፈል የቆረጡ የትግል ጓዶቸ ላለፉት 7 ወራት በከፍተኛ ችግሮች ውስጥ ወድቀው ማየት ለኔ እንቅልፍ የሚነሳ ጉዳይ መሆኑ አልቀረም።

    ለኢትዮጵያ አንድነት፣ ለዴሞክራሲና ለኢትዮጵያ ሕዝብ ሁለንተናዊ መብቶች መረጋገጥ የበኩሌን አስተዋጽኦ ሳደርግ ቆይቻለሁ። ባለፉት ሁለት አስርት አመታት በላይ በውጭው ዓለም በተደረገው ትግል ልዩ ልዩ የትግል መድረኮችን በመሥራችነት፣ በአባልነት፣ በአስተባባሪነት፣ እንዲሁም በአመራር ኃላፊነቶች የዜግነት ግዴታዬን ከሚጠበቅብኝ በላይ አስተዋጽኦ በማድረግ ለ26 ዓመታት ያልተቋረጠ የትግል አስተዋጽኦ አድርጌያለሁ። የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቭዥንን(ኢሳት) በማቋቋም፣ በመገንባት ሂደትና እስከ 2015 ድረስም በዋና ሥራ አስፈጻሚነት ፣ እሰከአሁኑ ድረስም በቦርድ ሥራ አስፈጽሚ አባልነት የበኩሌን አስተዋጽኦ ተወጥቻለሁ።

    ባለፉት 8 ዓመታት የአርበኞች ግንቦት 7 የአንድነትና ለዴሞክራሲ ንቅናቄ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባልና ልዩ ልዩ የሥራ ኃላፊነቶች ላይ በመሰማራት፣ እ.ኤ.አ ከመስከረም (September) ወር 2017 ከተደረገው የንቅናቄው ጉባኤ ላይ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል ሆኜ ከተመረጥኩኝ በኋላም የንቅናቄው የውጪው ዘርፍ ኃላፊ በመሆን እስካሁን ድረስ በቅንነትና በምችለው እቅም ኃላፊነቴን ተወጥቻለሁ። በአሁኑ ወቅት ከአርበኞች ግንቦት 7 የሥራ አስፈጻሚ ኮሜቴ አባልነት፣ እንዲሁም ንቅናቄው የውጭ ዘርፍ ኃላፊነት በገዛ ራሴ ፈቃድ መልቀቄን ለአርበኞች ግንቦት 7 አባላት፣ ደጋፊዎች፣ በልዩ ልዩ የትግል መድረኮች ለምታውቁኝ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ለማሳወቅ እወዳለሁ።

    የአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ በቅርብ ጊዜ ጉባኤ በማድረግ ይከስማል። አዲስ ሀገራዊና በኢትዮጵያዊነት፣ በዜግነትና በማኅበራዊ ፍትህ ላይ የቆመ የፓለቲካ ፓርቲ የምሥረታ ሂደት ወደ ማገባደጃው በመድረሱ በአዲሱ ፓርቱ ለሚመረጡ አመራሮች እንዲሁም አባላትና ደጋፊዎች ሁሉ ያለኝን ጽኑና መልካም ምኞቴን እገልጻለሁ። ለወደፊቱ ለኢትዮጵያ ሀገራችን እንዲሁም ለዓዝባችን ፋይዳና ጥቅም በሚያስገኙ ልዩ ልዩ ተግባራት ላይ በመሳተፍ እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ ዜጋ ድርሻዬን እንደምወጣ ለምታከብሩኝ፡ ለምትወዱኝና ለማከብራችሁና ለምወዳችሁ ወገኖቼ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ለማረጋገጥ እወዳለሁ። እዚህ ላይ የንቅናቄው ወዳጆችም ሆናችሁ ሌሎች እንድታውቁት ላሰምርበትም የምፈልገው በንቅናቄው አጠቃላይ የፓለቲካ ራዕይና ተልእኮ፣ በሚመሠረተው የፓለቲካ ፓርቲ ዓላማና ተልዕኮ፣ እንዲሁም ከማንም የንቅናቄው አመራር አባላት ጋር በግል ሆነ በፓለቲካ ምንም ዓይነት ቅራኔ የሌለኝ መሆኑን ለማረጋገጥ እወዳለሁ። ዘለአለማዊ ክብርና ሞገስ ለኢትዮጵያ አንድነት፣ ለዓባችን ነጻነትና፣ ለፍትህ ሲሉ አይተኬ የህይወት መስዋዕትነት ለከፈሉ የኢትዮጵያ ልጆች ሁሉ! ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!

    ነአምን ዘለቀ ቦጋለ
    ቨርጂኒያ፣ ዩናይትድ ስቴትስ ኦፍ አሜሪካ
    ማርች 18 ቀን፣ 2019

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ነአምን ዘለቀ


    Semonegna
    Keymaster

    ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ዳያስፖራዎች ልዑካን ቡድን አባላት የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ትውልደ ኢትዮጵያውያን ሀገራቸውን በሙያቸው እንዲያግዙ ጥሪ ማቅረባቸውን ተክተሎ የመጡ ናቸው።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– በኢትዮጵያ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ሲካሄድ የቆየው መንግስት ቴክኖሎጂ ለመጠቀም ያለውን ዝግጁነት የሚለይና ለችግሮች የመፍትሄ አቅጣጫ የሚያስቀምጥ አውደ-ጥናት ተጠናቀቀ።

    በአውደ ጥናቱ የመንግስት አግልግሎት አሰጣጥ፣ ቴክኖሎጂ ለመጠቀም ያለው ዝግጁነት፣ የፋይናንስ አስተዳደር ስርዓት ክፍተት ተለይተውበታል – ሚኒስቴሩ እንደዘገበው።

    የጤና አስተዳደር፣ የታክስ አሰባሰብ ስርዓት፣ የመረጃ ግንኙነት (ኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን) ቴክኖሎጂ ደኅንነት፣ በባንክ አገልግሎት፣ በኢንሹራንስ አገልግሎት፣ ትምህርት ሚኒስቴር፣ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ በኦዲት አገልግሎት፣ የአደጋ መከላከልና ዝግጁነት፣ የውሃ አወጋገድ ላይ ክፍተቶች ተለይተዋል።

    አሜሪካ ውስጥ ቨርጂንያ ኢንተርናሽናል ዩኒቨርሲቲ (Virginia International University; Fairfax, VA) መምህር በሆኑት ዶ/ር ተፈራ በየነ የተመራው ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ባለሙያዎች ልዑክ ክፍተቶቹን ከለዩ በኋላ የመፍትሄ አቅጣጫዎችን አስቀምጠዋል።

    ከ7ሺህ 800 በላይ አዳዲስ አነስተኛና መካከለኛ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎች በመላው አገሪቱ ሊቋቋሙ ነው

    ባለሙያዎቹ በኢንሹራንስ፣ በህክምና ቴክኖሎጂ፣ በዲፕሎማሲ፣ በኢንፎርሜሽን ኮሙኑኬሽን ቴክኖሎጂ ዘርፍ በአሜሪካን ሀገር በተለያዩ መሥሪያ ቤቶች ከፍተኛ ልምድ ያካበቱ ኢትዮጵያዊያን ናቸው።

    ሚኒስትሮች፣ ሚኒስትር ዴኤታዎች፣ የፋይናንስ ዳይሬክተሮች እና ሌሎችም ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከታቸው አካላት ከቡድኑ ጋር ለ1 ሳምንት ክፍተቶችን እና ጉድለቶችን የመለየት ሥራ ሲሠሩ ቆይተዋል።

    የሚመለከታቸው አካላት በየዘርፉ የሚደረጉ ማስተካከያዎችን በኃላፊነት ወስደው ወደ ተግባር የመቀየር ኃላፊነት ተሰጥቷቸዋል። በማጠቃለያው ላይ፥ ልዑካኑ የኢትዮጵያ መንግስት ወይም የሚመለከተው መንግስታዊ ተቋም ዕድሉን ከሰጠን የሀገራችንን ችግር ለመፍታት በቂ አቅም አለን ብለዋል። ወደፊትም በማንኛውም መልኩ ሀገራቸውን ለማገዝ ቃል ገብተዋል።

    የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታዎች ሹመቴ ግዛው (ዶ/ር) እና ጀማል በከር ልዑካኑ ሀገራቸውን ለመረዳት ያላቸውን ቁርጠኝነት በማድነቅ ምስጋና አቅርበዋል።

    የልዑካን ቡድኑ የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ትውልደ ኢትዮጵያውያን ሀገራቸውን በሙያቸው እንዲያግዙ ጥሪ ማቅረባቸውን ተክተሎ የመጡ ናቸው።

    ምንጭ፦ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ትውልደ ኢትዮጵያዊያን


    Anonymous
    Inactive

    አየር መንገዱ በአደጋው ማዘኑንና ለተጎጂ ቤተሰቦች አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ገለጸ
    —–

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአውሮፕላን መከስከስ አደጋው ማዘኑንና ለተጎጂ ቤተሰቦች አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ገለጸ።

    አደጋውን አስመልክቶ የአየር መንገዱ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ተወልደ ገብረማርያም በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳብራሩት አውሮፕላኑ ከጠዋት 2 ሰዓት ከ38 ደቂቃ ከቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ ቢነሳም ከስድስት ደቂቃ በኋላ ከራዳር ውጪ ሆኗል።

    አውሮፕላኑ 149 ተሳፋሪዎችንና ስምንት የበረራ ሰራተኞችን ይዞ ሲጓዝ በነበረበት ወቅት በቢሾፍቱና ሞጆ መካከል በምትገኘው ኤጄሪ አካባቢ መከስከሱን ነው ያስረዱት።

    አየር መንገዱ ቦይንግ 737 የተሰኘውን ይህን አውሮፕላን ከአራት ወራት በፊት መረከቡን ገልፀው ከአውሮፕላኑ አዲስነት በተጨማሪ በበረራው የተሳተፉት አብራሪውና ረዳቱ ልምድ ያላቸው መሆናቸውን ተናግረዋል።

    አውሮፕላኑ ባለፈው ወር ምርመራ እንደተደረገለትና ከደቡብ አፍሪካ ጆሃንስበርግ ከበረራ የተመለሰ መሆኑንም አስረድተዋል።

    ከጆሃንስበርግ መልስ ለሶስት ሰዓታት እረፍት ማድረጉንና በዚህም ወቅት የቴክኒክ ምርመራ ተደርጎለት እንደነበርም ዋና ስራ አስፈፃሚው ገልፀዋል።

    ይሁንና የአውሮፕላኑ አብራሪው ችግር ገጥሞት እንደነበር ለአየር ትራፊክ ተቆጣጣሪዎች አሳውቆ እንደነበር ነው አቶ ተወልደ የተናገሩት።

    የአደጋው መንስኤ እየተጣራ መሆኑን የተናገሩት አቶ ተወልደ በአደጋው 32 ኬኒያውያን፣ 18 ካናዳዊያን፣ 17 ኢትዮጵያዊያን እንዲሁም የሌሎች አገራት ዜጎች ተሳፍረው እንደነበር ነው የገለፁት ።

    አየር መንገዱ ለሟች ቤተሰቦች የሚችለውን እንደሚያደርግ የተናገሩት አቶ ተወልደ ለመንገደኞችና ለሰራተኞቹ ቤተሰብና ወዳጅ ዘመዶች መፅናናትን ተመኝተዋል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ

    Semonegna
    Keymaster

    በአደጋው የሁሉም ህይወት (157 ሰዎች) ያለፈ ሲሆን፥ ከተሳፋሪዎቹ መካከል 32ቱ ኬኒያዊያን ሲሆኑ፤ 17ቱ ኢትዮጵያዊያን ቀሪዎቹ ደግሞ የሌሎች አገራት ዜጎች መሆናቸውን የኢትዮጵያ አየር መንገድ አስታውቋል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– በዛሬው ዕለት የተከሰከሰው የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን ተሳፋሪዎች በሙሉ ህይወታቸው ማለፉ ተገለጸ።

    ከአዲስ አበባ ወደ ናይሮቢ (ኬንያ) ሲጓዝ በምሥራቅ ሸዋ ዞን ጊምቢቹ ወረዳ ላይ የተከሰከሰው የበረራ ቁጥር ET302 የሆነው ቦይንግ 737 የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን የ33 አገራት 149 መንገደኞችና ስምንት የበረራ አስተናጋጆችን ይዞ ነበር።

    ከተሳፋሪዎቹ መካከል 32ቱ ኬኒያዊያን ሲሆኑ፤ 17ቱ ኢትዮጵያዊያን ቀሪዎቹ ደግሞ የሌሎች አገራት ዜጎች መሆናቸውን አየር መንገዱ ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት አስታውቋል።

    አውሮፕላኑ አደጋው የደረሰበት ዛሬ ማለዳ ከቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት በተነሳ በስድስት ደቂቃ ልዩነት መሆኑ የተገለጸ ሲሆን የአደጋው መንስዔ እስካሁን አልታወቀም።

    በአደጋው የሁሉም ህይወት (157 ሰዎች) ያለፈ ሲሆን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት በአደጋው የተሰማውን ሀዘን በመግለጽ ለሟች ቤተሰቦችና ወዳጅ ዘመዶች መጽናናትን ተመኝቷል።

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቦይንግ 737 በረራ ዛሬ ጠዋት ከአዲስ አበባ ተነሥቶ ወደ ኬንያ ናይሮቢ ይበር በነበረው አውሮፕላን በደረሰው የመከስከስ አደጋ ወዳጅ ዘመዶቻቸውን ላጡ ሁሉ የጠ/ሚር ጽ/ቤት በኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት ስም ኀዘኑን ይገልጻል።የኢትዮጵያ ተቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ያሰፈረው።

    በተመሳሳይ የኬኒያው ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ በአደጋው የተሰማቸውን ሀዘን ገልጸው ለአደጋው ሰለባ ቤተሰቦች መፅናናትን ተመኝተዋል።

    የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ በአደጋው ህይወታቸውን ላጡ ሰዎች ቤተሰቦች የተሰማቸውን ሀዘን ገልጸዋል። ፕሬዝዳንቷ የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን ከአዲስ አበባ ወደ ናይሮቢ በመጓዝ ላይ እያለ አደጋ አጋጥሞት የመከስከሱን ዜና በከፍተኛ ድንጋጤና መሪር ሀዘን እንደሰሙ ገልጸዋል።

    ፈጣሪ አምላክ በቸርነቱ ለቤተሰቦቻቸው በሙሉ፣ ከብዙ በጥቂቱ ናይሮቢ ለማውቃቸው ለካፒቴን ያሬድ ወላጆች፣ ዶ/ር ጌታቸውና ዶ/ር ራያን፣ ለሆስተስ ሣራ ባለቤትና ሕጻን ልጆቿ፣ ከጥቂት ሳምንታት በፊት ላየኋት የጂቡቲዋ ራሻ ቤተስብ… መጽናናትን ይስጥልን። ዛሬ በ157 ሟች ቤተሰቦች ላይ የወደቀው መሪር ሐዘን እኔና ቤተሰቤ ኮሞሮስ በደረሰው አደጋ ያየነው በመሆኑ የሚያሳልፉትን ከባድ ፈተና ከማንም በላይ እረዳዋለሁ። 149 መንገደኞችና 8 የበረራ ሠራተኞችን ይዞ ከአዲስ አበባ ወደ ናይሮቢ ሲግዋዝ የነበረው [ET 302] በረራ ላይ በደረሰው የመከስከስ አደጋ በውስጡ የነበሩት ኢትዮጵያውያንና የ33 አገሮች ዜጎች ሕይወት ማለፍ ልቤን ሰንጥቆታል፤ እጅግ በጣም ነው ያዘንኩት።ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ በትዊተር ገጻቸው ላይ ያሰፈሩት።

    “ለኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊያን ትልቅ የሀዘን ቀን ነው” ያሉት ፕሬዝዳንቷ “በዜጎቻችንና ሌሎች የአየር መንገዱ ደንበኛ መንገደኞች ላይ በደረሰው አደጋ ልቤ ተሰብሯል” ብለዋል። በአደጋው ተጎጂ ለሆኑ ቤተሰቦች ፣ ወዳጅ ዘመዶችና ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብም መጽናናትን ተመኝተዋል።

    በተመሳሳይ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከአዲስ አበባ ወደ ናይሮቢ ሲበር በተከሰከሰው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቦይንግ 737 አውሮፕላን አደጋ ጥልቅ ሀዘን እንደተሰማው ገልጾ በአደጋው ቤተሰቦቻቸውን ላጡ መፅናናትን ተመኝቷል።

    የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባርም (ኢህአዴግ) እንዲሁ በአደጋው የተሰማውን ሀዘን በመግለጽ የሟች ወገኖች ነፍስ በአፀደ ገነት እንዲያርፍ ፣ ለወዳጅ ዘመድ ቤተሰቦቻቸውና ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብም መፅናናትን ተመኝቷል።

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ በበኩሉ በደረሰው አደጋ የሰው ሕይወት በመጥፋቱ የተሰማውን ጥልቅ ሃዘን ገልጿል። አውሮፕላኑ ምንም ዓይነት ቴክኒካዊ ችግር እንዳልነበረበትም አመልክቷል።

    የአየር መንገዱ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ተወልደ ገብረማርያም በሰጡት መግለጫ፤ በአውሮፕላኑ መከስከስ የመንገደኞችና የአውሮፕላኑ ሠራተኞች ሕይወት በማለፉ ከፍተኛ ሃዘን እንደተሰማቸው ገልጸዋል። ህይወታቸው ያለፉት ቤተሰቦችና ወገኖች ማስተናገጃ በአዲስ አበባ እና በናይሮቢ ቢሮ መከፈቱን ተናግረዋል።

    በአጠቃላይ 1ሺ 200 ሰዓታትን የበረራ ሰዓት ያስመዘገበው አውሮፕላን ከአዲስ አበባ ለበረራ የተነሳው 2 ሰዓት ከ38 ደቂቃ ሲሆን፤ 2 ሰዓት ከ40 ላይ ችግር እንዳጋጠመውና ከራዳር እይታ ውጪ እንደሆነም ገልጸዋል።

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከቦይንግ ኩባንያ ከተረከበው አራት ወር የሆነው ቦይንግ 737 ወደ ኬንያ የሚያደርገወን ጉዞ ከመጀመሩ በፊት ከጆሃንስበርግ ደቡብ አፍሪካ ተመልሶ ለሦስት ሰዓት ያህል አርፏል።

    ይሄው በዋና አብራሪ ካፒቴን ያሬድ ሙሉጌታ ወደ ኬንያ እየተጓዘ የነበረው አውሮፕላን፤ ቀደም ብሎ በተካሄደ የቴክኒክ ፍተሻ ምንም ዓይነት ችግር እንዳልነበረበት አመልክተዋል። ረዳት አብራሪው አህመድ ኑር መሃመድ ኑር የሚባል ሲሆን፤ ከ200 ሰዓታት በላይ መብረሩም ተገልጿል።

    የአደጋው መንሰኤ አለማቀፍ የአቬሽን ሕግን በተከተለ መልኩ ዓለምአቀፍ ምርመራ ተካሂዶ ዝርዝር መረጃው ወደፊት እንደሚገለጽ አመልክተዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ


     

    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ የተከፈተው ቆንስላ ጽ/ቤት ቆንሱል ጄኔራል አምባሳደር እውነቱ ብላታ ቆንስላ የጽ/ቤቱ መከፈት በሚኒሶታ ግዛት ለሚኖሩ በሺዎች ለሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን ዳያስፖራ አባላት ምቹ ሁኔታና መነቃቃትን እንደሚፈጥር ገልጸዋል።

    ዋሽንግተን፥ ዲሲ (ሰሞነኛ) – የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢፌዴሪ) መንግስት በሀገረ አሜሪካ በሎስ አንጀለስ ከተማ (ካሊፎርንያ ግዛት) ከሚገኘው ቆንጽላ ጽ/ቤት ቀጥሎ ሁለተኛውን ቆንጽላ ጽ/ቤት በሴይንት ፓል ከተማ (ሚኖሶታ ግዛት) ከፍቷል።

    ቆንስላ ጄኔራል ጽ/ቤቱ የተከፈተው የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ክቡር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ባሳለፍነው ዓመት ነሃሴ ወር ላይ በአሜሪካ ባደረጉት ጉብኝት በገቡት ቃል መሠረት ነው።

    በመክፈቻ ሥነ-ስርዓቱ ላይ የኦሮሚያ ክልል መንግስት ፕሬዝዳንት አቶ ለማ መገርሳ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ክብርት ብርቱካን አያኖ፣ የሴይንት ፓል ከተማ ከንቲባ ሚስተር ሜልቪን ካርተር፣ ከአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እንዲሁም በርካታ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን የዳያስፖራ አባላት ተገኝተዋል።

    ክቡር አቶ ለማ መገርሳ እንደገለጹት የቆንስላ ጽ/ቤቱ መከፈት ለአካባቢው ብሎም በመላው አሜሪካ የሚኖረውን ዳያስፖራ ለማገልግል የጎላ ፋይዳ ይኖረዋል። ዳያስፖራው በኢትዮጵያ እየተካሄደ ባለው የኢኮኖሚና ፖለቲካ ለውጥ የበኩሉን ሚና እንዲወጣ፣ ለዚህም የኢትዮጵያ መንግስት ከምንጊዜውንም በላይ ቁርጠኛ መሆኑን ገልጸዋል።

    አዲስ የተከፈተው ቆንስላ ጽ/ቤት ቆንሱል ጄኔራል አምባሳደር እውነቱ ብላታ በበኩላቸው የጽ/ቤቱ መከፈት በሚኒሶታ ግዛት ለሚኖሩ በሺዎች ለሚቆጠሩ የዳያስፖራ አባላት ምቹ ሁኔታና መነቃቃትን እንደሚፈጥር ገልጸዋል።

    የሴይንት ፖል ከተማ ከንቲባ ሚስተር ማልቪን ካርተር በዚሁ ወቅት ባደረጉት ንግግር ከቆንስላ ጄኔራል ጽ/ቤቱ ጋር ተቀራርቦ ለመሥራትና አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርጉ ገልጸዋል። የካቲት 23 ቀን 2011 ዓ.ም. (ማርች 2 ቀን 2019) በከተማ ደረጃ “የኢትዮጵያ ቀን” ተብሎ እንዲከበር መወሰኑንም ጠቁመዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ኤምባሲ፤ ዋሽንግተን፥ ዲሲ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    ቆንስላ ጽ/ቤት


    Semonegna
    Keymaster

    የአድዋ ድል ለኢትዮጵያ ነጻነትና ኩራትን፣ በዓለም ዙሪያ በተለይ በአሜሪካዎቹ ሰፋፊ እርሻዎች ለ500 አመታት በባርነት ለተጋዙ ጥቁር ሕዝቦች ደግሞ፥ የማንነት ማረጋገጫ፣ የዘመናት ጭቆናና የስነ-ልቦና ቁስልን አውልቆ የመጣያ የተስፋ ትንሳኤ ሆኖ ነበር።

    ሰለሞን ተሰራ (ኢዜአ)

    በርሊን ከተማ ውስጥ የጀርመን ግዛት አስተዳዳሪ (ቻንስለር)በነበረው ኦቶ ቫን ቢስማርክ (Otto von Bismarck) መኖርያ ሳሎን ፌሽታ በፌሽታ ሆኗል። እለቱ እንደ አውሮጳውያን አቆጣጠር (እ.አ.አ) የካቲት 16 ቀን 1885 ሶስት ወር ሙሉ አሰልቺ ውይይት የተደረገበትና ዋና ዋናዎቹ የአውሮፓ ቅኝ ገዢዎች ተሰብስበው ”አንተ ይሄን ያዝ አንተ ያንን ያዝ” ተባብለው ከወታደራዊ ዘመቻ በፊት አፍሪካን የተቃረጡት።

    በስብሰባው ከ80 በመቶ በላይ የሚሆነውን የአፍሪካ መሬት የሃሳብ መስመር እያሰመሩ ያለከልካይ ተከፋፈሉት። ከሦስት ወራት በላይ (እ.አ.አ ከኅዳር 15 ቀን 1884 እስከ የካቲት 26 ቀን 1885) ሲካሄድ የነበረው የበርሊን ጉባዔ (Berlin Conference) መደምደሚያ የነበረው ‘የበርሊን ጉባዔ ጠቅላላ ግብአተ ሰንድ’ (በእንግሊዝኛው፥ General Act of Berlin conference) በታሪክ አጥኚዎችና ፖለቲካ ተመራማሪዎች ዘንድ በ አብዛኛው “አፍሪካን የመቀራመት ጉባዔ” (“The Division of Africa” ወይም “Scramble of Africa”) ተብሎ ይታወቃል። በጉባዔው ላይ የጀርመን፣ ኦስትሮ-ሀንጋሪ፣ ቤልጅየም፣ ዴንማርክ፣ ፈረንሳይ፣ ብሪታንያ፣ ጣልያን፣ ኔዘርላንድስና ፖርቱጋል ተወካዮች ተገኝተዋል።

    አውሮፓውያን አፍሪካን ለመቀራመት በበርሊን ስምምነት ሲያደርጉ፤ አፍሪካዊያን ደግሞ የውጭ ወራሪዎችን ለመከላከል ከዚህ አለፍ ሲልም እርስ-በርሳቸው መተነኳኮስ የጀመሩበት ጊዜ እንደነበር ታሪክ ያስረዳል። ወቅቱ በአራቱም የአህጉሪቷ አቅጣጫዎች የሚገኙ ነገስታት እና የጭፍራ አለቆች በተናጠል ከአውሮፓውያኑ ጋር በገጠሟቸው ውጊያዎች ትርጉም ያለው ስኬት ሳያገኙ፤ አፍሪካውያን በቅኝ ግዛት መውደቅ የጀመሩበት ነው።

    ይህን ተከትሎ ጣልያንም ኢትዮጵያን በቁጥጥሯ ስር ለማድረግ ብትነሳም እምቢተኛው ጥቁር ሕዝብ ማንነቱንና ክብሩን አሳልፎ ላለመስጠት በመወሰኑ ያልተመጣጠነ ውጊያ ቢገጥሙም አሳፍሮ መልሷታል። ዘመናዊ የጦር መሣሪያ የታጠቀው የጣልያን ጦር የቅኝ ግዛት ተልእኮውን እውን ለማድረግ የተመመው በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ በአግባቡ የሰለጠኑ ወታደሮችን ይዞ ነው። ነገሩ እንደታቀደው ሳይሆን ቀርቶ የጣልያን ጦር በአድዋ ድል ተነሳ። ታሪክም ይህን ጦርነት <የአድዋ ጦርነት> (The Battle of Adwa) በማለት፣ ለጥቁር ሕዝቦች ታላቅ መነቃቃትና ተስፋ የሰጠውን የጦርነቱን ድል ደግሞ <የአድዋ ድል> (The Victory of Adwa) ብሎ ሲገዝበው ይኖራል።

    የታሪክ ሊቃውንት እንደሚያስቀምጡት የአድዋ ጦርነት በአፍሪካ ምድርና ታሪክ ከተከናወኑት ጦርነቶች ከፍተኛውን የዋጋና የክብር ስፍራ ይዟል። የሰሜን አፍሪካን በስፋት ይገዛ የነበረው አኒባል የአልፕን ተራሮች ዞሮ የአውሮፓን ኃያል መንግሥት ካሸነፈ ወዲህ (Hannibal’s crossing of the Alps)፣ አንድ አውሮፓዊ ጦር በአፍሪካውያን ጦር ሲሸነፍ ለመጀመሪያ ጊዜ ነበር። ስለሆነም፣ ጦርነቱ ብዙ መልክና ብዙ ቅጽል ተሰጥቶታል።

    የአድዋ ድል ለኢትዮጵያ ነጻነትና ኩራትን፣ በዓለም ዙሪያ በተለይ በአሜሪካዎቹ ሰፋፊ እርሻዎች ለ500 አመታት በባርነት ለተጋዙ ጥቁር ሕዝቦች ደግሞ፥ የማንነት ማረጋገጫ፣ የዘመናት ጭቆናና የስነ-ልቦና ቁስልን አውልቆ የመጣያ የተስፋ ትንሳኤ ሆኖም ነበር።

    የታሪክ ተመራማሪና ደራሲውፖል ሄንዝ በጻፉት ንብረ ጊዜ፥ የኢትዮጵያ ታሪክ (Layers of Time: A History of Ethiopia, by Paul B. Henze) በተሰኘው የታሪክ ድርሳናቸው “አውሮፓውያን የፈለጉትን ገድለዋል፣ ባሪያ ፈንግለዋል፣ አካባቢን፣ ሀብትን፣ ጉልበትን መዝብረዋል፤ ምክንያቱ በግልጽ ባይታወቅም ‘ኢትዮጵያን በጦር ከማስገበር ይልቅ እንቃረጣት ብለው’ ብሪታኒያ፣ ፈረንሳይና ጣልያን የሦስትዮሽ ስምምነት (Tripartite Agreement) ተፈራርመው አጼ ምኒልክን ‘እወቁልን’ ብለው ጦማር ሰደዋል። አጼ ምኒልክም ‘ስለነገራችሁኝ አመሰግናለሁ፣ ነገር ግን እኔ በሌለሁበት የተወሰነውን አላውቅም’ በማለታቸው ጣልያን ኢትዮጵያን በወረራ ያዘች።

    ወረራውን ለመቀልበስ በአጼ ምኒልክ የሚመራው የኢትዮጵያ መንግስት ሰላማዊ ትግል ቢያደርግም የወራሪዎቹ ብልጣብልጥነት ጦርነቱን አይቀሬ አደረገው። ወደ ጦርነት ተገዶ የገባው የኢትዮጵያ የጦር ኃይል በአምባላጌ፣ በመቀሌና በአድዋ በተከታታይ ባደረገው ጦርነት የበላይነት ወስዶ የካቲት 23 ቀን 1988 ዓ.ም. ላይ በአድዋ የድል ባለቤት መሆኑ ተበሰረ። የድሉ ዜና እንደናኘ በአፍሪካ ተስፋ፣ በአውሮፓ ድንጋጤ ፈጠረ። የኢትዮጵያ ድል አውሮፓውያን በዓለም የነበራቸውን ልዕለ ኃያልነት ለመጀመሪያው ጊዜ ጥያቄ ውስጥ ከቷል። ፖል ሄንዝ ”ዛሬ ላይ ሆነን ስናየው” የኢትዮጵያ ድል የአውሮፓ ተሰሚነት የቁልቁለት ጉዞ መነሻ ነበር” ሲሉ በጽሁፍ አስፍረዋል።

    ድሉ ታላቋ ብሪታንያን ኢትዮጵያን በእኩል ዓይን ዓይታ ”የምስራቁን የደቡቡን የምእራቡን ድንበራችንን እንካለል” ብላ በፊርማ እንድታጸድቅ አስገድዷታል። ከዚህ በተጨማሪ በአውሮፓ ቅኝ ግዛት መዳፍ ስር ሲማቅቁ የነበሩትን አፍሪካውያን እና ካሪቢያን ጥቁሮች ለነፃነታቸው እንዲታገሉ ብርታት እና ምሳሌ ሆኗቸዋል። ለጥቁር አሜሪካውያን ምሁራን ከፍተኛ የመንፈስ መነቃቃት እንዲያገኙ አድርጓል።

    የአድዋ ድል (ማለትም፥ በአውሮፓውያን ዘንድ የአድዋ ጦርነት ሽንፈት) በተሸናፊ የአውሮፓ ገዢዎች ዘንድ ቁጭት ፈጥሮ ከ30 ዓመት በኋላ ፋሺዝም በጣልያን ውስጥ ስር እንዲሰድ እና መሪ የፖለቲካ ርዕዮተ ዓለም (አይዲዮሎጂ) እንዲሆን ምክንያት ሆኗል። ለኢትዮጵያ ደግሞ የተረጋጋ መንግስታዊ አስተዳደር አስገኝቷል። በዚህ የከሸፈ የቅኝ-ግዛት ዕቅድና የአውሮፓውያን ተስፋፊነት የተደሰቱ ሶሻሊስት አመለካከት ያላቸው ወገኖች በጣልያን፣ በብሪታንያና በፈረንሣይም ነበሩ።

    ዕውቁ የታሪክ ተመራማሪና የአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ ፕሮፌሰር የነበሩት ሪቻርድ ፓንክረስት እና ሌላው ኢትዮጵያዊ የታሪክ ተማራማሪ ዶ/ር አብዱልሳማድ አህመድ በጋራ በጻፉት ስለ አድዋ ድል በጻፉት መጽሐፍ (Adwa Victory Centenary Conference, 26 February – 2 March 1996) ውስጥ እንዳሰፈሩት የኢጣሊያኑ ክሪቲካ ሶሻሌ (Critica Sociale) ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ፊሊፖ ቱራቲ (Filippo Turati) በወኔና በምልዓት ለእውነት ስለእውነት ጻፈ። “ጣልያን ወደ አድዋና ወደ ሌሎችም ከኢትዮጵያ ጋር ወደ ተደረጉት ጦርነቶች የገባችው፣ ለእንግሊዛውያን አገልጋይና አሽከር ሆና ነው። በዚህም የተነሳ የጣሊያናውያን ሀብትና ደም ያላግባብ ፈሰሰ” ሲል ወረራውን በማውገዝ ድፍረት የተሞላበት ጽሁፉን ማስነበቡን ይገልጻሉ።

    ጋዜጠኛው በጽሁፉ “የጣልያንና የእንግሊዝ መንግሥታት በአፍሪካ ስለተቀዳጁት የቅኝ-ግዛትና የተስፋፊነት ድል እንደጽጌረዳ የፈካ ውሸት እየፈበረኩ ይመጻደቁ እንጂ፣ በእርግጥ ኢትዮጵያ ድል አድርጋለች… ቪቫ ምኒልክ! ቪቫ ኢትዮጵያ!” ሲል አወድሷል።

    በአጼ ምኒልክ መሪነት የኢትዮጵያ ኃይል በጣልያን ወራሪ ኃይል ላይ በአድዋ የተቀዳጀው ድል ድልድይ ሆኖ የጥንታዊቷን ኢትዮጵያ የታላቅነት ክብር ከዘመናዊ ዓለም ጋር ያገናኘ ድልድይ ሆኗል። ታዲያ ይህ ድልድይ በ1890ዎቹ ግንባታው የተጀመረው የተቀረው የአፍሪካ ክፍል በውጭ ኃይሎች አገዛዝ ቀንበር ስር ሲወድቅ ኢትዮጵያውያን ብቻ በተከታታይ የተሰነዘረባቸውን ወረራ በድል ሲመልሱ ነበር።

    በዚያው ክፍለ ዘመን ኢትዮጵያውያን ለውጭ ወራሪዎች የማይንበረከኩ መሆናቸውን ማሳየታቸውን ማስታወስ ይቻላል። በ1870ዎቹ የግብፃውያንን፣ በ1880ዎቹ የመሃዲስቶችን ተደጋጋሚ ጥቃቶች መክተው መልሰዋል። የአድዋ ድል ደግሞ ይህን የነፃነት ቀናዒነት ይበልጥ ከማድመቅ አልፎ የዓለምን ትኩረት ስቧል።

    የአውሮፓ መንግሥታት ዲፕሎማቶቻቸውን ወደአዲስ አበባ እንዲልኩ፣ ከኢትዮጵያ ጋር 19 ድንበርን የሚመለከቱ ስምምነቶችን እንዲፈራረሙ አደረጋቸው ። በአርነት ትግሉ መስክ በቅኝ ግዛት ሥር ለነበሩት እህት የአፍሪካ አገሮች ታጋዮችም ኢትዮጵያ ፋና ወጊ መብራታቸውና የራዕይ ምንጫቸው ነበረች።

    የአድዋ ድል የፓን አፍሪካን ንቅናቄ መሠረት መሆኑን የኢትዮጵያውያንን የአድዋ ውሎ ከዘከሩ የታሪክ ጠበብት መካከል የዋሽንግተኑ የታሪክ ሊቅ ፕሮፌሰር ራየሞንድ ጆናስ፥ “የአድዋ ጦርነት – የአፍሪካውያን ድል በዘመነ ግዛት” (The Battle of Adwa: African Victory in the Age of Empire, by Raymond Jonas” በሚለው መጽሐፋቸው አስፍረዋል፡፡ በዚህ ጽሁፋቸው “የአድዋ ድል ለአፍሪካውያን ቅኝ አገዛዝን ታግሎ መጣል እንደሚቻል ያሳየ፣ የኢትዮጵያንም ታላቅነት ያስመሰከረ” ስለመሆኑ ደጋግመው አውስተዋል።

    ለዚህም ነው የናይጄሪያ ድኀረ ነፃነት የመጀመሪያ ፕሬዚዳንት የነበሩት ዶ/ር ናምዲ አዚኪዊ (Nnamdi Azikiwe) “ኢትዮጵያ ጥቁር ራሱን በራሱ የሚያስተዳድርባት አገር ነች። በዚህ ክፍለ አህጉር ላይ የአፍሪካ ቀደምት አባቶች የመሠረቱት መንግሥት የታሪክ ዋቢ ነች። ኢትዮጵያ ከዘመን ወደ ዘመን እየተሸጋገረች ህልውናዋን ጠብቃ መኖሯ የሚደነቅና መደነቅም ያለበት ነው” በማለት የተናገሩት።

    ከአድዋው ድል አርባ ዓመት በኋላ ጣልያን ቂሟን ልትወጣ ወረራ ስታካሂድ በግልጽም ይሁን በተዘዋዋሪ የአውሮፓና የአሜሪካ መንግሥታት ከእሷ ጎን ቆመዋል። በተቃራኒው ድሉ በአፍሪካም ይሁን በተቀረው ዓለም የተቀጣጠለውን የአፍሪካዊነት የትግል ስሜት አነሳስቷል፤ እልህ አጭሯል። በአጠቃላይ መላው ጥቁር ሕዝብ፣ በቁጥር አነስተኛ ቢሆኑም ለፍትህ የታመኑ አውሮፓዊያን ነጮችም ለኢትዮጵያ ያላቸውን ወገናዊነት እንዲያጠናክሩ ጥርጊያውን አመቻችቷል። የነኝህም ጥረት በውጭ የነበረውን ሕዝባዊ ድጋፍ ወደ ኢትዮጵያ ያደላ እንዲሆን አድርጎታል። ባህላዊ እሴቶቻቸውን ያልጣሉ የአፍሪካ ምሁራን ከነበሩባቸው የአህጉሩ ከተሞች፣ ከካርቢያን ደሴቶች፣ ከጥቁር አሜሪካዊያን በኩል ተሰባስበው ወረራው ያጫረባቸውን የመጠቃት ስሜት በይፋ አንጸባርቀዋል።

    ደቡብ አፍሪካ ውስጥ ለነበሩት የአፍቃሪ ኢትዮጵያዊነት እንቅስቃሴ መሪዎችም የአድዋው ድል የሞራል እርሾ ሆኗቸዋል። ከእንቅስቃሴው ግንባር ቀደም መሪዎች አንዱ ጀምስ ድዋኔ (James Mata Dwane) ግብጽና ሱዳን ውስጥ ያሉትን ክርስቲያን አፍሪካዊያን ሁኔታ ትኩረት ሰጥተው መፍትሄ ይፈልጉለት ዘንድ ለአጼ ምኒልክ ደብዳቤ የፃፉት የአድዋውን ድል ተከትሎ ነበር።

    ስለአድዋ ድል የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት ዊንስተን ቸርችል “የካቲት 23 ቀን 1888 የአድዋ ጦርነት ተካሂዶ፥ ጣልያን በኢትዮጵያውያን የደረሰባት ሽንፈት ደረሰባት። (ይህም) ሌሎች ሕዝቦችን የሚነካ ሁለት ውጤቶች አስከተለ፤ አንደኛ፥ ሰሜን አፍሪካ ላይ አውሮፓዊ ክብርን ትልቅ ምች መታው። ሁለተኛ፥ በአውሮፓ ፖለቲካ ማንነት ረገድ የኢጣልያ ዋጋ ወደታች ወረደ” ብለው ጽፈዋል።

    ዊንስተን ቸርችል ስለ ኢጣልያ ሽንፈትና ውጤቱ ከመጻፍ ይልቅ ስለ ኢትዮጵያ ድልና በአፍሪካና በሌሎቹ ጭቁን አገሮች ዘንድ የኢትዮጵያን ማንነት ሽቅብ መናሩን መግለጽ አልፈለጉም። ይህ ሊሆን የቻለው ምናልባትም አድዋ ላይ የተገኘው ድል ለጥቁር ሕዝቦች ከነጻነት ለመውጣት የተስፋ እርሹ በመሆኑ፣ ለአውሮፓውያኑ የቅኝ ግዛቶቻቸውን ሊያጡ የሚችሉበት ጅምር በመሆኑ ሊሆን ይችላል።

    የሆነ ሆኖ አድዋ ላይ የተለኮሰው የድል ችቦ በቅኝ ግዛት ስር ለነበሩት የአፍሪካ አገሮች ቀንዲል ሆኗል። ለዚህም ክብር ለመስጠት 17 የአፍሪካ አገሮች የሰንደቅ ዓላማ ቀለማቸውን ከኢትዮጵያ ወስደዋል። አረንጓዴ፣ ቢጫና ቀይ የሆነው የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ቀለም ማሊ፣ ጋና፣ ካሜሩን … አገሮች በተለያየ ቅርጽ የአገራቸው መለያ ሰንደቅ አላማ እንዲሆን አድርገዋል።

    Pankhurst, Richard. “”Viva Menelik!”: The Reactions of Critica Sociale to the Battle and to Italian Colonialism” In Adwa Victory Centenary Conference, 26 February – 2 March 1996, edited by Abdussamad Ahmad and Richard Pankhurst, 517-548. Addis Ababa: Institute of Ethiopian Studies, Addis Ababa University, 1998.

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የአድዋ ድል


Viewing 15 results - 91 through 105 (of 124 total)