Search Results for 'ኢትዮጵያዊ'

Home Forums Search Search Results for 'ኢትዮጵያዊ'

Viewing 15 results - 106 through 120 (of 124 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    “በርቱ! ባየሁት ነገር ተደስቻለሁ… የሥራ ፍላጎት ተነሳሽነት ለለውጥ ወሳኝ መሆኑን ከጴጥሮስ መረዳት እንችላለን” – የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ገብረየሱስ 

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ገብረየሱስ የካቲት 1 ቀን 2011 ዓ.ም. ቅዱስ ጴጥሮስ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ተገኘተው የሥራ እንቅስቃሴን ተዘዋውረው ጎብኝተዋል።

    በቆይታቸውም የቅዱስ ጴጥሮስ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታልና የቅዱስ ጳውሎስ ሚሊኒየም ሜዲካል ኮሌጅ በጋራ ያስገነቡትን የልብ ህክምና ማዕከል፣ በሀገሪቱ ብቸኛና የመጀመሪያ የሆነውን የተመረዙ ሰዎች የሚታከሙበት የቶክሲኮሎጂ ህክምና ማዕከል እንዲሁም የእናቶችና ህጻናት የህክምና ከፍልን ዋና ዳይሬክተሩ ጎብኝተዋል።

    በሆስፒታሉ ፈጣን እድገት ተደስቻለሁ ያሉት ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም የልብ ህክምና አገልግሎት መስጠት መጀመሩና በሀገሪቱ ካለው የህክምና እጥረት አኳያ ትልቅ ፋይዳ እንደሚኖረው ገልጸው ብዙም ትኩረት ያልተሰጠበት የመመረዝ ህክምና በሆስፒታሉ መሰጠቱም ይበል የሚያሰኝ ነው ብለዋል።

    ቪዲዮ፦ የኢትዮጵያዊያን-አሜሪካዊያን ዶክተሮች ቡድን እያስገነባ ያለው ግዙፉ ዓለምአቀፋዊ ሆስፒታል በአዲስ አበባ

    ሆስፒታሉ የሰሳንባ ነቀርሳ (ቲቢ) ህክምና ብቻ ይሰጥ እንደነበር ያስታወሱት ዶ/ር ቴዎድሮስ በአሁኑ ሰዓት አጠቃላይ መሠረታዊ የሆስፒታል አገልግሎቶችን መስጠት መጀመሩና የተወሰኑ የህክምና አገልግሎቶች ላይም የበለጠ ስፔሻላይዝድ ለማድረግ መሥራቱ በጣም እንዳስደሰታቸው ተናግረዋል።

    ከዚህ ሌላም የሆስፒታሉ ሰራተኞች የሥራ ተነሳሽነትም በጣም እንዳስደሰታቸው ተናግረዋል። ለሆስፒታሉ ፈጣን ዕድገትም ሁሉም የሆስፒታሉ ሠራተኞች ዋና ተዋናይ መሆናቸውን እንዳዩ ገልጸው በዚህም የሥራ ፍላጎት መኖር ለለውጥ ወሳኝ መሆኑን ከጴጥሮስ መረዳት እንችላለን ብለዋል።

    የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተሩ ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም በዚሁ ዕለት የቅዱስ ጴጥሮስ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታልን ከመጎብኘታቸው በተጨማሪም ከየኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢፌዴሪ) የጤና ሚኒስትር አሚር አማን (ዶ/ር) እንዲሁም ከኢፌዴሪ ፕሬዝደንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ጋር ተገናኝትው በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ተወያይተዋል።

    ከሰኔ 24 ቀን 2009 ዓ.ም. ቀን ጀምሮ ዋና መቀመጫው ጄነቭ፣ ስዊዘርላንድ የሆነውን የዓለም ጤና ድርጅትን (WHO) በዋና ዳይረክተርነት የሚመሩት ኢትዮጵያዊው ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም ከዚህ ስልጣናቸው በፊት ከ ከኅዳር 20 ቀን 2005 ዓ.ም. እስከ ጥቅምት 22 ቀን 2009 ዓ.ም. ድረስ የኢፌዴሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፣ ከጥቅምት 2 ቀን 1998ዓ.ም. እስከ ኅዳር 19 ቀን 2005 ዓ.ም. ደግሞ የኢፌዴሪ የጤና ሚኒስትር ሆነው አገልግለዋል።

    ምንጭ፦ የቅዱስ ጴጥሮስ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

     

    የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሃኖም


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– በ2006 ዓ.ም. በሰባት የየመገናኛ ብዙሃን (ሚዲያ) እና ኪነ ጥበብ ባለሙያዎች የተቋቋመው ጉዞ ዓድዋ፥ አንድ ሺሕ አስር ኪሎሜትሮችን የሚሸፍን፣ ከኢትዮጵያ ዋና ከተማ አዲስ አበባ ተነስቶ መዳረሻውን የዓድዋ ድል አምባ ተራሮች ጫፍ ላይ የሚያደርግ ረዥም የእግር ጉዞ ነው። ላለፉት ስድስት ዓመታት ከጥር ወር ጀምሮ የዓድዋ ድል በዓል እስከ ሚከበርበት የካቲት 23 ቀን ድረስ ከስድስት ሳምንታት ላላነሰ በየዓመቱ ሳይቋረጥ የቆየው ጉዞ ዓድዋ፥ ዘንድሮ የኢትዮጵያዊነቱ ስሜት እጅግ ጎልቶ በጉዞው ላይ የሚሳተፉት ቁጥርም ጨምሯል። በዘንድሮው ጊዞ ዓድዋ 44 ተጋዦች ከአዲስ አበባ እና 4 ተጓዦች ከሐረር በአጠቃላይ 48 ተጓዦች ጥር 7 ቀን 2011 ዓ.ም. ቀን ከአዲስ አበባ ተነስተዋል።

    የመላው አፍሪቃውያን ድል እስከመባል የደረሰው ታላቁ የዓድዋ ድል፥ የግዝፈቱን ያህል ክብር እና መታወሻ ሥነሥርዐት ሳይኖረው እየተከታተለ ከመጣው ትውልድ ጋር የበዓሉ አከባበር ዐውድ እየወረደ ጭራሽ እየተዘነጋ እና እየደበዘዘ መሔድ ያሳሰባቸው የጉዞ ዓድዋ መሥራቾች ትውልዱ ትኩረት ሰጥቶ የድሉን መንፈስ እንዲጋራ ለማድረግ ይህንን የጉዞ ሐሳብ አመንጭተዋል።

    ◌ የጉዞ ዓድዋ ተጓዦችና የኢትዮጵያዊያን አስተያየት

    በዚህም የተነሣ ጉዞ ዓድዋ ባለፉት ስድስት ዓመታት ብቻ ከታለመው ዓላማ አንጻር ከፍተኛ የሆነ አመርቂ ውጤት በማስመዝገብ የዓድዋ ድል በዓል ቀድሞ ከነበረበት አከባበር የላቀ ተሳትፎ ያለው የድል በዓል እንዲሆን አስተዋጽዖ ለማድረግ ተችሏል።

    ጉዞውን ከማካሔድ በተጓዳኝ በየመንገዱ ተንቀሳቃሽ የመጻሕፍት ንባብ መሰናዶ በማካሔድ በየዓመቱ የሚጓዙ አባላትን በዓድዋ ጦርነት እና ድል ዙሪያ በቂ የሆነ ግንዛቤ እና ዕውቀት የማጋራት ዝግጅቶችን ሲያካሂድ ቆይቷል። ከአንድ ወር በላይ በተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን ሰፊ ሽፋን የሚሰጠው የጉዞው የዕለት ተእለት ውሎ፣ በዓሉ ከመድረሱ አስቀድሞ በበርካታው ሕዝባችን ላይ የካቲት 23 ዕለትን በጉጉት የመጠበቅ ስሜት እንዲፈጠር አድርጓል።

    ◌ የዓድዋ ድል በዓል በጎሰኞች ዓይን የዲያቆን ዳንኤል ክብረት መጣጥፍ

    ከዚህ ቀደም የድል በዓሉ በብቸኝነት ከሚከበርባቸው የአዲስ አበባ እና የዓድዋ ከተሞች በተጨማሪ ከ28 በላይየሚሆኑ የክልል ከተሞች እና በርካታ ሕዝብ የሚኖርባቸው የገጠር ወረዳዎች ተጓዥ ቡድኑ በየደረሰበት በሚኖሩ ደማቅ አቀባበሎች ላይ በሚሰጡ የግንዛቤ መስጫ መልዕክቶች ስለ ዓድዋ ድል ታሪክ ግንዛቤ በመሰጠቱ የበዓሉአከባበር ከፍተኛ ለውጥ በማምጣት ላይ ይገኛል። የጉዞ ዓድዋ ትሩፋቶች፦

    • በዓድዋ ከተማ ውስጥ በአምስት ዓመት አንድ ጊዜ ብቻ የነበረው የዓድዋ ድል በዓል አከባበር ሥነ ሥርዐትበየዓመቱ እንዲካሔድ አስችሏል።
    • የበዓሉ አከባበር በፌደራል መንግሥት ደረጃ እንዲከበር ልዩ ትኩረት እንዲሰጠው ከፍተኛ አስተዋጽዖ አድርጓል።
    • ከ120 ዓመታት በፊት መቀሌ ከተማ በሚገኘው የእንዳየሱስን ምሽግ ለማስለቀቅ ከጣሊያን ጦር ጋር ሲዋጉ ሕይወታቸው ያለፉ ጀግና ኢትዮጵያውያን አጽም የትም ተበታትኖ በመቅረቱ፥ ጉዞ ዓድዋ በአሁኑ ሰዓት የቦታው አስተዳዳሪ የሆነውን የመቀሌ ዩኒቨርሲቲ በማንቃት፤ የካቲት 26 ቀን 2008 ዓ. ም አጽማቸውን አሰባስቦ በክብር እንዲያርፍ ተደርጓል። ከዚህም ባሻገር በዓመቱ የካቲት 26 ቀን 2009 ዓ.ም በመቀሌ ዩኒቨርሲቲ ወጪ “የጀግኖች ኢትዮጵያዊያን መታሰቢያ ሙዚየም” የተሰኘ ጣራ አልባ ቤተ መዘክር በእንዳየሱስ ታሪካዊ ምሽግ ላይ ተገንብቶ ለመመረቅ በቅቷል።
    • የዓድዋ ጦርነት መንስዔ የሆነው የዉጫሌ ውል የተፈረመበት “ይስማ ንጉሥ” የተባለው ታሪካዊ ቦታ ተከልሎ ጥበቃ እንዲደረግለት በማድረግ ጉዞ ዓድዋ ቁልፍ ሚና ተጫውቷል። ከዚህም በተጨማሪ ውሉ በተፈረመበት ዕለት ሚያዝያ 25 ቀን በየዓመቱ፤ ምሁራዊ ተዋስዖ የሚደረግባቸው መድረኮች በመፍጠር፣ ላለፉት ስድስት ዓመታት ባበረከተው የላቀ አስተጽዖ የአምባሰል ወረዳ የዓድዋ ድልን ለመዘከርና ቦታውን የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ ያለመቋሚ ቤተ መዘክር በቦታው ላይ እንዲገነባ የሚያስችል የ19 ሚልዮን ብር የበጀት ድጋፍ ከአማራ ክልል መንግሥት እንዲያገኝ ጉዞ ዓድዋ ቁልፍ ሚና ተጫውቷል።
    • ለበርካታ ዓመታት አገልግሎቱ ተዘግቶ የቆየው በዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ የትውልድ መንደር “አንጎለላ” የሚገኘው የዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ መታሰቢያ ክሊኒክ እንዲከፈት ከፍተኛ ቅስቀሳ በማድረግ፤ በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ድጋፍ ክሊኒኩ ታዳጊ የጤና ጣቢያ ሆኖ በድጋሚ አገልግሎት እንዲሰጥ ጉዞ ዓድዋ አስተዋጽዖ ካደረጉ መካከል ግንባር ቀደሙን ሚና ተጫውቷል።
    • የዓድዋ ጀግና የሆኑት ራስ አሉላ አባ ነጋ የቀብር ቦታ በሆነው የአባ ገሪማ ገዳም ውስጥ ለሁለቱም ጾታዎች ጉብኝት ምቹ በሆነ ቦታ ላይ ሐውልት እንዲቆምላቸው ጉዞ ዓድዋ ባመቻቸው ዕድል በአንድ ባለ ሀብት ሐውልታቸው ተሠርቶ ለምረቃ በቅቷል።
    • በየዓመቱ በሚካሔዱ ጉዞዎች ከዓድዋ ድል ጋር ግንኙነት ያላቸው ቦታዋችን እና ልዩ ታሪካዊ መረጃዎችን በምስል እና በጽሑፍ በመሰብሰብ ለጥናትና ምርምር አስተዋጽዖ ማበርከት የሚችሉ የታሪክ ግብዓቶችን በማደራጀት በተለያዩ የመገናኛ ዘዴዎች በተለይም የማኅበራዊ ድረ ገጽን በመጠቀም ቅርሶችን የማስተዋወቅና የመጠበቅ ሥራዎችንበ መሥራት ላይ ይገኛል።

    የጉዞ ዓድዋ ማኅበር የዓድዋ ድል በዓል በኢትዮጵያውያን እንዲሁም በጥቁር አፍሪካውያን ዘንድ የሚገባውን ክብር እንዲያገኝ ላደረገው ጥረት፣ ከላይ ለተጠቀሱት እና በየዓመቱ በሚያደርጋቸው እጅግ አመርቂ ክንዋኔዎች ምክንያት በ2009 ዓም በቅርስና ባሕል ዘርፍ የዓመቱ በጎ ሰው ተሸላሚ ሆኗል።

    ላይ የሚሳተፉ ተጓዦች በጉዞአቸው ላይ የሚያደርጓቸውን የተለያዩ ክንዋኔዎችና የሚዘግቧቸውን ታሪክ ተኮር ዘገባዎች ለመከታተል የማኅበሩን የፌስቦክ ገጽ ይጎብኙ።

    ◌ ዓፄ ዘርዓ ያዕቆብ እና ዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ በደብረ ብርሃን ከተማ ሃውልት ሊቆምላቸው ነው

    ምንጭ፦ በጎ ሰው ሽልማት / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ጉዞ ዓድዋ


    Semonegna
    Keymaster

    የከተማዋን የቱሪዝም ዕድገት ከፍ ለማድረግ የዓፄ ዘርዓ ያዕቆብ እና ዳግማዊ ምኒልክ ሃውልቶችን የከተማ አስተዳደሩ ኅብረተሰቡን በማሳተፍ ያስገነባል። ስለሆነም የሁለቱ ታላላቅ መሪዎች ሃውልት በከተማዋ እንዲቆም እንቅስቃሴ እየተደረገ ነው።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ከ6 መቶ ዓመታት በላይ ባስቆጠረችው የድሮዋ ደብረ ኤባ የዛሬዋ ደብረ ብርሃን ከተማ ለዓፄ ዘርዓ ያዕቆብ እና ዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ ሃውልት ሊቆምላቸው እንቅስቃሴ መጀመሩን ከተማ አስተዳደሩ አስታውቋል።

    የከተማዋ ምክትል ከንቲባ እና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ብርሃን ገብረሕይወት ጥር 9 ቀን 2011 ዓ.ም. አዲስ አበባ ላይ በሰጡት መግለጫ ደብረ ብርሃን ከተማን የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ የከተማ አስተዳደሩ እየሠራ ነው፤ ከተማዋን የኮንፈረንስ ቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግም ከተማ አስተዳደሩ ባዛሮችን በተለያዩ ጊዚያት እንደሚያካሂድ ተገልጿል።

    የከተማዋን የቱሪዝም ዕድገት ከፍ ለማድረግ የዓፄ ዘርዓ ያዕቆብ እና ዳግማዊ ምኒልክ ሃውልቶችን የከተማ አስተዳደሩ ኅብረተሰቡን በማሳተፍ ያስገነባል። ስለሆነም የሁለቱ ታላላቅ መሪዎች ሃውልት በከተማዋ እንዲቆም እንቅስቃሴ እየተደረገ ነውም ተብሏል።

    ደብረ ብርሃን ኢንዱስትሪ ፓርክ በከተማዋ ለሚኖሩ ዜጎች የተለያዩ የሥራ ዕድሎችን ፈጥሯል

    ከተማ አስተዳደሩ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ እየሠራ እንደሆነም አስታውቋል። ደብረ ብርሃን ከተማ በዓፄ ዘርዓ ያዕቆብ መመሥረቷ ይታወቃል።

    አጼ ዘርአ ያዕቆብ

    አጼ ዘርአ ያዕቆብ በዘውድ ስማቸው ቆስጠንጥንዮስ ከአባታቸው ቀዳማዊ ዳዊት እና ከእናታቸው ንግስትክብረ እግዚ እ.ኤ.አ. በ1399 ከአዋሽ ወንዝ አጠቀብ ትገኝ በነበረው ትልቅ ተብላ በምትጠራው መንደር የድሮው ፈታጃር ክፍለ ሀገር ተወለዱ። የነገሡበትም ዘመን እ.ኤ.አ. ከ 1434 እስከ 1468 (እስከሞቱበት ጊዜ) ነበር። ያረፉትም በደጋ ደሴት፣ ጣና ሃይቅ ነው።

    ዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ

    ዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ ከአባታችው ከሸዋው ንጉሥ ኃይለ መለኮት ሣህለ ሥላሴና ከእናታቸው ወይዘሮ እጅጋየሁ ለማ አድያም እ.ኤ.አ. ነሐሴ 17 ቀን 1844 ደብረ ብርሃን አካባቢ አንጎለላ ከሚባል ሥፍራ ተወልደው፤ በአንጎለላ መቅደላ ኪዳነ ምኅረት ቤተ ክርስቲያን ክርስትና ተነሱ። የነገሡበትም ዘመን እ.ኤ.አ. ከ 1889 እስከ 1913 (እስከሞቱበት ጊዜ) ነበር። ያረፉትም ተዓካ ነገሥት ለማርያም ወደብረ መንክራት ስዕል ቤት ኪዳነ ምኅረት ገዳም (አዲስ አበባ) ነው።

    ምንጭ፦ የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    ዓፄ ዘርዓ ያዕቆብ እና ዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ ሃውልት


    Semonegna
    Keymaster

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ጥር 6 ቀን ለኢትዮጵያ ዲፕሎማቶች በሰጡት ገለጻ አስካሁን ባለው ሂደት ኢትዮጵያዊያን ዳያስፖራዎች በቀረበላቸው ሀገራዊ ጥሪ አማካኝነት በዳያስፖራ ትረስት ፈንድ በኩል 1 ነጥበ 9 ሚሊዮን ዶላር አዋጥተዋል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – በዳያስፖራ ትረስት ፈንድ አንድ ነጥብ ዘጠኝ ሚሊዮን ዶላር መሰብሰቡን ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ጥር 6 ቀን 2011 ዓ.ም. አስታወቁ። እስካሁን ባለው ሂደት በትረስት ፈንዱ አማካኝነት 12 ሺህ 9 መቶ ዳያስፖራዎች መዋጮ አድርገዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርበው የ2011 ዓ.ም. አገራዊ በጀትን በአስጸደቁበት ወቅት ኢትዮጵያዊ ዳያስፖራ ሁሉ በአገሩ ልማት ላይ እንዲሳተፍ በቀን የ1 ዶላር መዋጮ መጠየቃቸው ይታወሳል። ይሁን እንጂ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ዳያስፖራው ለጠቅላይ ሚነስትሩ የሰጠው ምላሽ አጥጋቢ እንዳልሆነ ሲነገር ቆይቷል።

    Commercial Bank of Ethiopia to start diaspora mortgage loan to ease Ethiopians’ home ownership

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ጥር 6 ቀን ለኢትዮጵያ ዲፕሎማቶች በሰጡት ገለጻ አስካሁን ባለው ሂደት ዳያስፖራው በቀረበለት ፈንድ አማካኝነት 1 ነጥበ 9 ሚሊዮን ዶላር አዋጥቷል።

    በመዋጮውም 12 ሺህ 900 ዳያስፖራዎች እንደተሳተፉ የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ ከዚህም ውስጥ 10 ሺህ 300 የሚሆኑት በአሜሪካ የሚኖሩ ናቸው። 1ነጥብ 6 ሚሊዮን ዶላሩ ከእነዚህ በአሜሪካ ከሚኖሩ ዳያስፖራዎች መሰብሰቡን አክለዋል።

    በአሜሪካ ካሉ ግዛቶች መካከል ሜሪላንድና ካሊፎርኒያ እንደቅደም ተከተል ከፍተኛ መዋጮ የተገኘባቸው አካባቢዎች መሆናቸውንም ገልጸዋል።

    በዓለም ላይ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዳያስፖራዎች ቢኖሩም መዋጮው እምብዛም ያልሆነበት ምክንያት መተማመኑ ባለመፈጠሩ መሆኑንም ጠቅላይ ሚንስትሩ አስገንዝበዋል።

    The case of Ethiopian diaspora, their interest to invest in Ethiopia and bureaucratic bottlenecks

    የሚዋጣውን ነገር በሚታይ ነገር ላይ በማዋል መተማመንን ለመፍጠር እንደሚሠራ የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በፈንዱ የተሰበሰበው ገንዘብ ግን 10 ሚሊዮን ዶላር አስኪደርስ ጥቅም ላይ እንደማይውል ገልጸዋል።

    ይህ የሚሆነውም በክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች መካካል ፍትሃዊ ክፍፍልን ለመፍጠር መሆኑንም ጠቁመዋል።

    የኢትዮጵያውያን ዳያስፖራ ትርስት ፈንድ የተቋቋመው በነሀሴ ወር 2011 ዓ.ም. በጠቅላይ ሚኒስትሩ ዋና ሰብሳቢነት ሲሆን፥ በዋነኝነት በተለያዩ የአርሜሪካ ግዛቶች የሚኖሩ 15 ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያንን በአማካሪ ካንስል አባልነት ያቀፈ ቡድን በበላይነት ይከታተለዋል።

    የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ትረስት ፈንድ ድረ-ገጽ: EDTF

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ተመሳሳይ ዜናዎች፦

    ዳያስፖራ ትርስት ፈንድ


    Semonegna
    Keymaster

    እንደ ፕሮፈሰር ጣሰው ወልደሃና ገለጻ፥ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ባለፉት ስድስት ወራት በተጽዕኖ የሚካሄዱ የፖለቲካ አሠራሮችን በማጽዳትና የፖለቲካ ሃሳቦችን በነጻ የሚያራምዱበት የጋራ መድረክ በማዘጋጀት የተሻለ ሰላም ማምጣት ችሏል።

    አዲስ አበባ (ኢዜአ) – የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን ከፖለቲካ ተጽዕኖ በማላቀቅ በሰላም አብሮ የመኖር ባህልን ማሳደግ እንደሚገባ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ፕሮፈሰር ጣሰው ወልደሃና ተናገሩ።

    ዩኒቨርሲቲው ከሰላም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ”ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለሰላም” በሚል ጥር 4 ቀን 2011 ዓ.ም. መክረዋል።

    ፕሮፌሰር ጣሰው በዚሁ ወቅት፥ የሰላማዊ አብሮ የመኖር ባህልን በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለማሳደግ ተማሪዎችን ከፖለቲካ እንቅስቃሴና ፉክክር ነጻ ማድረግ ይገባል። ባለፉት ዓመታት ሰላም ላይ ትኩረት ተደርጎ ባለመሠራቱ ተማሪዎች በዘር የመከፋፈልና እርስ በእርስ ያለመታማመን ችግሮች አጋጥሟቸዋል። ይህም በአንዳንድ ዩኒቨርሲቲዎች ግጭትና ሁከትን በመቀስቀስ የመማር ማስተማር ሂደቱ ላይ ያመጣው አሉታዊ ተጽዕኖ ከፍተኛ ነው ብለዋል።

    ተማሪዎችና መምህራን በፖለቲካ እንቅስቃሴ ውስጥ የሚያደርጉት ፉክክርና አንዳንድ ድርጅቶችም የፖለቲካ እንቅስቃሴያቸውን ያለገደብ በተቋማቱ ማራመዳቸው የተማሪዎችን አብሮነት እንደሸረሸረውም ነው ፕሮፌሰሩ ያብራሩት። የዩኒቨርሲቲዎች ዋነኛ ተግባር ማስተማርና መመራመር መሆኑን አጽንዖት ሊሰጡት እንደሚገባም አመልክተዋል።

    ትውልድን በመቅረጽ፣ አገርን በመገንባት በኩል መምህራን የበኩላቸውን አስተዋጽዖ መወጣት ይጠበቅባቸዋል ― ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ

    እንደ ፕሮፈሰሩ ገለጻ፥ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ባለፉት ስድስት ወራት በተጽዕኖ የሚካሄዱ የፖለቲካ አሠራሮችን በማጽዳትና የፖለቲካ ሃሳቦችን በነጻ የሚያራምዱበት የጋራ መድረክ በማዘጋጀት የተሻለ ሰላም ማምጣት ችሏል።

    ዩኒቨርሲቲው በሰላም ዙሪያ የሚመራመርና ሃሰቦችን የሚያፈልቅ አስር አባላት ያሉት ቡድን አዋቅሮ በተቋሙ ቀጣይነተ ያለው ሰላም ለማምጣት እየሠራ ነውም ብለዋል – ፕሮፌሰር ጣሰው። ለቡድኑም አንድ ሚሊዮን ብር ዩኒቨርሲቲው መመደቡን አስታውቀዋል።
    ሌሎችም ዩኒቨርሲቲዎች ይህንን ተሞክሮ በማስፋት ለአገር ሰላምና ለአብሮነት የሚያደርጉትን ጥረት ማጠናከር እንዳለባቸውም ተመላክቷል።

    በመድረኩ “ሰላምና ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት” በሚል ጽሁፍ ያቀረቡት በዩኒቨርሲቲው የፖለቲካ ሳይንስ ምሁር ፕሮፌሰር ካሳሁን ብርሃኑ በበኩላቸው ሰላምን ለማስፈን ተቋማቱን ከፖለቲካ ተጽዕኖ ነጻ ማድረግ ተቀዳሚ ተግባር ሊሆን ይገባል።

    በተለይ በተቋማቱ የሰላም እጦት መንግስትና ምሁራን በሰላም ላይ ያልተገበሯቸው በርካታ ተግባራት ለመኖራቸው ዋቢ ነው ብለዋል – ፕሮፈሰሩ።

    በቀጣይም ኢትዮጵያዊ አብሮነትን ያካተተ መርሃ ግብር በመቅረጽ፤ በጎሳና በዘር የተከፋፈለውን የምደባ ስርዓት በመከለስ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የፌዴራል ተቋማት መሆናቸውን ማጉላትና የተማሪዎች ህብረትን ከፖለቲካ የጸዱ ማድረግ ይገባል ብለዋል። አክለውም ምሁራን የግጭት አራጋቢዎች ከመሆንና የሥራ መርሃ ግብራቸውን በአግባቡ ካለመወጣት ተቆጥበው ትውልድ የመቅረጽ ሚናቸውን ሊወጡ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።

    የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ ወ/ሮ አልማዝ መኮንን እንዳሉት ምሁራን ለሀገሩ ቀና የሆነ ዜጋንና ስለአገሩ ሰላምና ዲሞክራሲ የሚተጋ ዜጋን የማፍራት ኃላፊነት እንዳለባቸው በመጥቀስ፥ በተለይ ምሁራን አገሪቷ አሁን ከገጠማት የሰላም እጦት ለመውጣት ሙያዊና የዜግነት ግዴታቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል።

    ለአንድ ቀን ብቻ በተደረገው የምከክር መድረኩ ላይ ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የተወከሉ መምህራን፣ የተማሪዎች መማክርት፣ የሰላም መልዕክተኞችና ሌሎችም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ጣሰው ወልደሃና


    Semonegna
    Keymaster

    5ኛውን አዲስ ፎቶ ፌስት የፎቶግራፍ አውደ ርዕይ ያዘጋጁት ደስታ ለአፍሪካ [የፈጠራ አማካሪ] ከስዊዘርላንድ ኤምባሲ በኢትዮጵያ ጋር በመተባበር ሲሆን፥ አውደ ርዕዩ እስከ ታህሳስ 1 ቀን 2011 ዓ.ም. ድረስ ይቆያል።

    አዲስ አበባ (ቢቢሲ አማርኛ) – በአፍሪካ ውስጥ ስመጥር ከሆኑት የፎቶ ፌስቲቫሎች ከፍተኛ ቦታ ያለው አዲስ ፎቶ ፌስት ኅዳር 27 ቀን 2011 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ሸራተን ሆቴል ተከፍቷል።

    ለአምስተኛ ጊዜ በተካሄደው በዚህ አውደ ርዕይ ላይ ከ61 ሃገራት የተወጣጡ 152 የፎቶ ግራፍ ባለሙያዎች የተለያዩ ሥራዎቻቸውን ያቀርባሉ። ይህ አውደ ርዕይ በየዓመቱ አሳታፊነቱ እየጨመረ የመጣ እንደሆነ የምትናገረው ‘ደስታለ አፍሪካ የፈጠራ አማካሪ’ (Desta for Africa Creative Consulting) የተባለ ድርጅት መሥራችና የአዲስ ፎቶ ፌስት ዋና አዘጋጅ የሆነችው የፎቶ ባለሙያዋ አይዳ ሙሉነህ ዋና ትኩረቱም የውክልና ጉዳይ ነው ትላለች።

    አፍሪካ በተለያዩ ምስሎችም ሆነ በውጭው ዓለማት የምትታወቀው ሁሌም ከችግር፣ ድርቅና ረሀብ ጋር ብቻ ከመሆኑ አንፃር አዲስ ፎቶ ፌስት በጎ ጎኗንም ለማሳየት እንዳለመ አይዳ ታስረዳለች።

    “ይህንን የፎቶ አውደ ርዕይ የምናየው እንደ አቅም ግንባታ ነው፤ እነዚህን ሁሉ ወጣት የፎቶ ባለሙያዎች ስናሰባስብ ወይም ስልጠና ስንሰጥ የኢትዮጵያን እውነታ በምን መንገድ ሊያሳዩ ይችላሉ የሚለውን ለማሳየት ነው” በማለት ታስረዳለች አይዳ።

    በተለይም አፍሪካ እንደ ጨለምተኛ ብቻ አህጉር ተደርጋ መታየቷ ትክክለኛ እይታ እንዳልሆነ የምትናገረው አይዳ “ሁሉም ነገር በጎ አይደለም፤ ነገር ግን ሁሉም ነገር ደግሞ መጥፎ አይደለም። በዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ጎልቶና ገኖ የሚታየው መጥፎ ነገር ነው” በማለት ይህንንም ለመቀየር ኢትዮጵያዊ ወይም አፍሪካዊ ፎቶ ባለሙያዎችን ማፍራትና እይታዎችንም መፍጠር እንደሚያስፈልግ አፅንኦት ትሰጣለች።

    በዚህ ዓመት አዲስ ፎቶ ፌስት ዓውደ ርዕይ ላይ 1200 ፎቶዎች የሚቀርቡ ሲሆን ከዓመት ወደ ዓመት የተሳታፊዎች ቁጥር እየጨመረ እንደሆነ አይዳ ሙሉነህ ተናገራለች።

    በባለፈው አመት ለመሳተፍ የጠየቁ የፎቶ ባለሙያዎች ቁጥር 500 የነበረ ሲሆን በዚህ አመት ወደ 832 ደርሷል። ከነሱም ውስጥ 152 ባለሙያዎች ተመርጠው ተሳታፊ ሆነዋል። ለአይዳ ሙሉነህ የተሳታፊዎች ቁጥር መብዛት የሚያሳየው አዲስ ፎቶ ፌስት በዓለም ላይ ያለው ስፍራ እየጨመረ መሆኑን ነው።

    በተጀመረበት ወቅት አምስትዓ የፎቶግራፍ ባለሙያዎች ከኢትዮጵያ ያሳተፉ ሲሆን በአሁኑ ሰዓትም 35 እንደደረሱ አይዳ ትናገራለች። ምንም እንኳን በፈተናዎች የተሞላ መሆኑን አይዳ ባትክድም “ይሄን ሁሉ ሥራ የምንሰራው ሃገሪቷን ለማሳወቅ ነው” ትላለች።

    5ኛውን አዲስ ፎቶ ፌስት የፎቶግራፍ አውደ ርዕይ ያዘጋጁት ደስታ ለአፍሪካ የፈጠራ አማካሪ ከስዊዘርላንድ ኤምባሲ በኢትዮጵያ ጋር በመተባበር ሲሆን፥ አውደ ርዕዩ እስከ ታህሳስ 1 ቀን 2011 ዓ.ም. ድረስ ይቆያል።

    ምንጭ፦ ቢቢሲ አማርኛ | ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    አዲስ ፎቶ ፌስት

    Semonegna
    Keymaster

    ኢትዮጵያዊያን አያሌ የሚያስተሳስሯቸው ነገሮች ያሏቸው በመሆኑ የሚያለያዩዋቸውን ጥቂት ነገሮች በመቻቻል አንድነታቸውን የሚያጎለብቱ ጉዳዮችን ጎልቶ እንዲወጣ የብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በዓል አስተዋጽኦ ያበረክታል ተብሏል።

    አዲስ አበባ (ኢ.ፕ.ድ) – የዘንድሮ የብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በዓል ከልዩነት በላይ ለሕዝቦች አንድነት መጠናከር ትኩረት እንደሚሰጥ የፊዴሬሽን ምክር ቤት ገለፀ።

    የፊታችን ህዳር 29 ቀን 2011 ዓ.ም. ቀን በአዲስ አበባ ከተማ የሚከበረው የብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በዓል ዝግጅት መጠናቀቁንም ምክር ቤቱ አስታውቋል።

    ዘንድሮ ለ13ኛ ጊዜ የሚከበረውን በዓል ከልዩነት በላይ ለሕዝቦች አንድነት መጠናከር ትኩረት እንደሚሰጥ በምክር ቤቱ የሕዝብ ግንኙነትና ኮሚኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ገብሩ ገብረሥላሴ በተለይ ለኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢ.ቢ.ሲ) ተናግረዋል። በዚህም ብሔረሰቦች የራሳቸውን ባህል ከማስተዋወቅ በዘለለ የባህል ልውውጥ የሚያደርጉበት መድረክ እንደሚፈጠር ገልፀዋል።

    በዚህም አንዱ ብሔር የሌላውን ባህል እንዲያንፀባርቅ በማድረግ የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነቱ እንዲጎለብት ይደረጋል ሲሉ ተናግረዋል ዳይሬክተሩ አቶ ገብሩ።

    ኢትዮጵያዊያን አያሌ የሚያስተሳስሯቸው ነገሮች ያሏቸው በመሆኑ የሚያለያዩዋቸውን ጥቂት ነገሮች በመቻቻል አንድነታቸውን የሚያጎለብቱ ጉዳዮችን ጎልቶ እንዲወጣ በዓሉ አስተዋጽኦ ያበረክታል ብለዋል።

    አቶ ገብሩ አክለውም ዘንድሮ በአዲስ አበባ የሚከበረው የብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን የዝግጅት ሥራዎች ተጠናቀው የበዓሉ ተሳታፊዎች እየተጠበቁ መሆኑን ገልፀዋል። በበዓሉ ዕለትም በክልሎች ብሎም በሀገር አቀፍ ደረጃ ሲምፖዚየሞች፣ የተለያዩ ውይይቶችና ዝግጅቶች እንደሚካሄዱም ይጠበቃል ብለዋል።

    በበዓሉ በሚካሄዱ ውይይቶች ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበው በሀገሪቱ ዘላቂ ሰላም ለማስፈን በግጭቶች መንስዔ ዙሪያ ምክክር ተደርጎ የመፍትሄ ሀሳቦች እንዲቀመጡም እንደሚደረግ አቶ ገብሩ አመላክተዋል።

    የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢፌዲሪ) ሕገ-መንግስት የፀደቀበት ቀን የሆነው ህዳር 29 ቀን‹‹በብዝሃነት የደቀመ ኢትዮጵያዊ አንድነት›› በሚል መሪ ቃል ዘንድሮ ይከበራል።

    በበዓሉ ቅድመ ዝግጅት ወቅትም የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነቶችን የሚያጠናክሩ የሰላም ጉባኤዎች በተለያዩ ክልሎች ሲካሄዱ መቆየታቸውንም ምክር ቤት አስታውቋል። ባለፈው ዓመት 12ኛው የብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በዓል በአፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ዋና ከተማ በሆነችው ሰመራ መከበሩ ይታወሳል

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት (ኢ.ፕ.ድ) | ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በዓል

    Semonegna
    Keymaster

    ሑመራ (ኢዜአ)– በትግራይ ክልል የሰቲት ሑመራ ከተማ ነዋሪዎች የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ዶ/ር ደብረጽዮን ገብረሚካኤል ክልላዊና ሀገራዊ ጉዳዮችን አስመልክተው በቅርቡ ላደረጉት ንግግር ድጋፋቸውን በሰላማዊ ሰልፍ ገለጹ።

    ነዋሪዎቹ ለዶ/ር ደብረጽዮን ያላቸውን ድጋፍ ለመግለጽ ትናንት በተሽከርካሪዎች የጀመሩት ሰላማዊ ሰልፍ ዛሬ ወጣቶችን ጨምሮ በሰቲት ሑመራ ከተማ ነዋሪዎች ተጠናክሮ ቀጥሏል።

    በሰልፉ ላይ የተሳተፉት ወጣቶች፣ ማኅበራትና ነዋሪዎች “የትግራይ ሕዝብ ታሪክ የሚያኮራ እንጂ የሚያሳፍር ታሪክ የለውም! የሕግ በላይነት ይከበር! በሙስና የተጠረጠሩ በቁጥጥር መዋላቸውን ብንደግፍም በሙስናና ኢ-ሰብዓዊ አያያዝ ሽፋን ብሔር ተኮር ጥቃት ይቁም! የውጭ ጣልቃ ገብነት ይቁም!” የሚሉና ሌሎች የተለያዩ መፈክሮች ይዘው ሰልፉ ላይ ታይተዋል። የትግራይ ሕዝብ ለሰላም፣ ለእኩልነት፣ ለፍትህና ለዴሞክራሲ የቆመ ነው ሲሉም ድምጻቸውን አሰምተዋል።

    መንግስት የሕግ በላይነት ለማስከበር የጀመረው እንቅስቃሴ እንደሚደግፉት የገለጹት ሰላማዊ ሰልፈኞቹ፣ ሕግን የማስከበር ሥራው በሁሉም አካላትና የመሥሪያ ቤት ዘርፎች እንዲተገበር ጠይቀዋል።

    በሰልፉ ላይ የተሳተፉ የቃፍታ ሑመራ ወረዳ ነዋሪ አቶ ተመስገን ካሕሳይ “የትግራይሕዝብ በእኩልነትና በፍትህ ያምናል፤ ለዓመታት የታገለውም የሕግ በላይነት እንዲረጋገጥ ነው” በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

    የትግራይ ሕዝብ ከሌሎች ወገኖቹ ጋር መስዋዕትነት የከፈለው ለህግ ልዕልና መረጋገጥ ነው – የክልሉ መንግስት

    ወጣት የዕብዮ ኃይሉ የተባለ ሌላው የወረዳው ነዋሪ በበኩሉ “እኛ ሕግ የጣሰና በሙስና የተዘፈቀ መደበቂያ አንሆንም፤ መጠየቅ ያለባቸው በትግራይ ብቻ ሳይሆን በሁሉም ክልሎች ያሉ በመሆኑ ሕግ የማስከበር ሥራ በሁሉም ሊተገበር ይገባል” ብሏል። የትግራይ ሕዝብ ከሌሎች ኢትዮጵያዊ ወንድሞቹ ጋር ሆኖ መታገሉን ገልጾ አሁንም የሕግ የበላይነትን ለማስከበር በሚደረጉ ጥረቶች ማንኛውም መስዋዕትነት ለመክፈል ዝግጁ መሆኑን አመልክቷል።

    የሰቲት ሑሞራ ከተማ ነዋሪ አቶ ሰለሞን አረጋይ በበኩላቸው “ዶ/ር ደብረጽዮን ያደረጉት ንግግር ሰላምና ልማትን የሚፈልግ ማንኛውንም ብሔር የሚመለከት በመሆኑ ድጋፌን ለመግለጽ ወጥቻለሁ” ሲሉ ገልጿል።

    The recent action to impose the rule of law in Ethiopia is getting political agenda – Dr. Debretsion

    ወጣት መሰለ ዕቁባይ በበኩሉ ስለ ሰላም እየዘመሩ የትግራይ ሕዝብን ሰላም ለማወክ መሞከር አግባብ ያልሆነና ተቀባይነት እንደሌለው ተናግሯል። የትግራይ ሕዝብ ከሌሎች የኢትዮጵያ ሕዝቦች ጋር ሆኖ የታገለው ሰላምና የሕግ የበላይነት እንዲረጋገጥ በመሆኑ ማንኛውንም ጭቆና እንደማይሸከም አመልክቷል።

    በሰልፉ መክፈቻ ላይ ንግግር ያደረጉት የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ርስቁ አለማው እንዳሉት ሰላምና የሕግ የበላይነት እንዲከበር የትግራይ ሕዝብ ከሌሎች የኢትዮጵያ ወገኖቹ ጋር በመሆን መስዋዕት ከፍሏል። በአሁኑ ወቅትም ከሌሎች ሰላም ወዳድ የአገሪቱ ሕዝቦች ጋር በመሆን ሕግ ለማስከበር ድምጹን በሰላማዊ መንገድ እያሰማ መሆኑን ተናግረዋል።

    “በዞናችን የማንነት ጥያቄ ባይኖርም አንዳንድ ሰላም የማይፈልጉ አካላት ሰላሙን ለመንሳት ሌት ተቀን ቢሠሩም ሕዝቡ በትዕግስት እና በሰላም ድምጹን እያሰማ ነው” ብለዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    ሰቲት ሑመራ

    Semonegna
    Keymaster

    ፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ የያሬድ የሙዚቃ ትምህርት ቤት ከተከፈተበት ከ1959 ዓ.ም. ጀምሮ ተቋሙንም በመምራት እንዲሁም ታላላቅ ባለሙያዎችን በማፍራት ለሙዚቃ ዕድገት አስተዋፅዖው የጎላ መሆኑን ለተሳታፊዎች አቶ ሠርፀ ፍሬስብሐት አውስቷል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)–በኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ ሥር ያለው የብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደሥላሴ የሥነ-ጥበባት ማዕከል 40ኛ የጥበብ ውሎ መድረኩን ቅዳሜ ኅዳር 8 ቀን 2011 ዓ.ም ከሰዓት በኋላ አካሒዷል።

    በዝግጅቱ ላይ የዕውቁ ኢትዮጵያዊ የሙዚቃ ሰው የፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ ሕይወትና ሥራዎች ላይ ውይይት እየተደረገ ተደርጓል። ሥራዎቹን እና ሕይወቱን አስመልክቶ የሙዚቃ ባለሙያ እና በቅርቡ የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅት ዳይሬክተር ጀነራል ሆኖ የተሾመው አቶ ሠርፀ ፍሬስብሐት የውይይት መነሻ ጥናት አቅርቦ በታዳሚዎች ውይይት ተካሂዶ ነበር።

    “ፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ <ባለዋሽንቱ እረኛ>(The Shepherd Flutist)  በተሰኘ ታላቂ ሥራ የኢትዮጵያን መልክ በረቂቅ ሙዚቃ ያሳዩ ናቸው” በማለት አቶ ሠርፀ የገለጿቸው የሙዚቃውን ረቂቅነት በመጥቀስ ሲሆን፤ ፕሮፌሰር አሸናፊ የያሬድ የሙዚቃ ትምህርት ቤት ከተከፈተበት ከ1959 ዓ.ም. ጀምሮ ተቋሙንም በመምራት እንዲሁም ታላላቅ ባለሙያዎችን በማፍራት ለሙዚቃ ዕድገት አስተዋፅዖው የጎላ መሆኑን ለተሳታፊዎች አውስቷል።

    በሙዚቃ ላይ ከሠሯቸው ከበርካታ የምርምር ሥራዎቻቸው ውስጥ “Roots of Black Music” የተሰኘው መጽሐፋቸው በብዙ የዓለማችን የሙዚቃ አጥኚዎች የተዘነጉ (የተዘለሉ) የአፍሪካ/የምሥራቁ ዓለምን የሙዚቃ ስልትና ፍልስፍናን አጉልተው ለተቀረው ዓለም ያሳዩበት እንደሆነም አቅራቢው አብራርተዋል።

    በውይይቱም ከተሳታፊዎች የኢትዮጵያ ሙዚቃ በዘመናት መካከል የመድመቅና መልሶ የመደብዘዝ ችግር ከምን የመነጨ እንደሆነ ጥያቄ የቀረበ ሲሆን፥ “ዋናው ችግር በተለያዩ ምክንያቶች የኢትዮጵያ ሙዚቃ ተቋም ፈርሷል፤ እሱን መልሶ መገንባት የቤት ሥራችን ነው” ብለዋል አቶ ሠርፀ። አክለውም የኢትዮጵያ የሙዚቃ ትምህርት ሥርዓት ከተመሠረተበት ዘመን ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ ከምዕራባውያን የሙዚቃ ሥርዓተ-ትምህርት ነፃ መውጣት ያለመቻሉም ሌላ ምክንያት እንደሆነ አቅራቢው ጠቅሰዋል።

    ውይቱን የመሩት የብላቴን ጌታ ኅሩይ ወልደሥላሴ የሥነጥበባት ማዕከል ዳይሬክተር አቶ እንዳለጌታ ከበደ በበኩላቸው ለኢትዮጵያ ሥነ ጥበብ ማደግ ብርቱ ጥረት ያደረጉ የጥበብ ሰዎችን ፈለግ እና ሥራዎቻቸውን ለተተኪው ትውልድ ለማውረስ በሁሉም አካላት ጥረት መደረግ አለበት ብለዋል።

    ፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ አዲስ አበባ ግንቦት 8 ቀን 1930 ዓ.ም አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ተወለዱ። አባታቸው ግራዝማች ከበደ አድነው፣ እናታቸው ደግሞ ወ/ሮ ፋንታዬ ነከሬ ያባሉ ነበር። የሙዚቃ ፍቅርን ገና በልጅነታቸው ያሳደሩባቸው እናታቸው ቢሆኑም ታዳጊው አሸናፊ ገና የዘጠኝ ዓመት ልጅ ሳሉ እናታቸውን በሞት አጥተዋል።

    ፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ መሠረታዊ ትምህርታቸውን በዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት እና በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት (አሁን ኮከበ ጽባሕ 2ኛ ደረጃና መሰናዶ ትምህርት ቤት የሚባለው) ካጠናቀቁ በኋላ ከሐረር የመምህራን ማሠልጠኛ ኮሌጅ ተመርቀዋል። ከዚያም ወደ አሜሪካ በማቅናት ኒው ዮርክ ክፍለ-ሀገር ከሚገኘው ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ሮቸስተር፣ ኢስትማን የሙዚቃ ትምህርት ቤት (University of Rochester’s Eastman School of Music) በ1954 ዓ.ም በመጀመሪያ ዲግሪ ከተመረቁ በኋላ ወደ ኢትዮጵያ በመመለሰ የያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤትን መሥርተዋል። የትምህርት ቤቱም የመጀመሪያው ዳይሬክተር ከመሆናቸውም ባሻገር በመሆን ሙዚቃን ከማስተማሩ ባሻገር አገልግለዋል። በተጨማሪም በአዲስ አበባ የወጣት ወንዶች ክርስቲያናዊ ማኅበር (ወ.ወ.ክ.ማ.)፣ በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የበጎ አድራጎት ድርጅት መርሓ-ዕውራን ትምህርት ቤት እና በመሳሰሉ የወጣቶች ማኅበራት እየተገኙ የሙዚቃ ትምህርት ይሰጡ ነበር።

    በድጋሚ ለከፍተኛ ትምህርት ወደ አሜሪካ ተመልሰው፣ ኮነቲከት ክፍለ-ሀገር ከሚገኘው ዌስልያን ዩኒቨርሲቲ (Wesleyan University) በ1961 ዓ.ም የማስትሬት፣ እንዲሁም በ1963 ዓ.ም የዶክትሬት ዲግሪያቸውን ምዕራባዊ ባልሆኑ ሙዚቃዎች ምርምር (ethnomusicology) አግኝተዋል።

    ከሙዚቃው መምህርነትና ተመራማሪነት ባሻገር ፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ ደራሲም ነበሩ። እ.ኤ.አ በ1964 ዓ.ም ኮንፌሽን (Confession)፣ እ.ኤ.አ በ1982 ዓ.ም ሩትስ ኦፍ ብላክ ሙዚክ (Roots of Black Music) የሚሉ መጻሕፍትን ያሳተሙ ሲሆን፣ በሙዚቃ ላይ ያተኮሩ በርካታ ጽሁፎችን፥ በተለይም ደግሞ በአፍሪካ-አሜሪካውያን ባህልና አኗኗር ላይ ለሚያተኩረው “The Chronicler” ለተሰኘው መጽሔት ጽፈዋል።

    በአሜሪካ ፕሮፌሰር አሸናፊ ኑሯቸው ፍሎሪዳ ክፍለ ሀገር በሚገኘው ፍሎሪዳ ስቴት ዩኒቨርሲቲ (Florida State University) የሙዚቃ ኮሌጅ ውስጥ በመምህርነት የሠራ ሲሆን፣ ተቀማጭነቱን እዚያው አሜሪካ ያደረገውናታዋቂውን የኢትዮጵያ ምርምር ካውንስልን (Ethiopian Research Council) በዳይረክተርነት መርቷል።

    ፕሮፌሰር አሸናፊ ከመጀመሪያ ኢትዮጵያዊ ባለቤታቸው (ወ/ሮ እሌኒ ገብረመስቀል) እና ሁለተኛ ባለቤታቸው (አሜሪካዊ) አራት ልጆችን (ሦስት ሴቶችና አንድ ወንድ) ልጆችን አፍርተዋል። ፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ የ60ኛ የልደት በዓላቸው ዕለት በመኖሪያ ቤታቸው ግልጽ ባልሆነ ምክንያት ሞተው የተገኙ ሲሆን፤ ምናልባትም የራሳቸውን ሕይወት ሳያጠፉ እንዳልቀሩ ብዙዎች ይገምታሉ።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ
    PHOTO: Ethiopian Academy of Sciences

    Semonegna
    Keymaster

    በኢትዮጵያውያን የኪነ ጥበብ አድናቂዎች ዘንድ ተወዳጅነት እያተረፈ የመጣው ለዛ የአድማጮች ምርጫ ሽልማት ዘንድሮ ለስምንተኛ ጊዜ ጥቅምት 13 ቀን 2011 ዓ.ም በሂልተን ሆቴል፣ አዲስ አበባ፣ እጅግ በደመቀ ሁኔታ ተከናውኗል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – በሀገራችን የሙዚቃ ታሪክ እጅግ መቀዛቀዝ፣ የሙዚቃ አልበምም ህትመት መፍዘዝ፣ ፊልም ሠሪዎችም ሥራዎቻችውን ተመልካቾች ፊታቸውን ባዞሩባቸው በዚያ ወቅት እንደ አንድ የኪነጥበብ አባልና የሚዲያ ባለሙያ አቅማቸው በፈቀደ የበኩላቸውን አስተዋጽዖ ለማበርከት፣ እንዲሁም አድማጭ ተመልካቹን ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ለማነቃቃት በማሰብ ነበር ጋዜጠኛ ብርሀኑ ድጋፌ እና ባልደረቦቹ በሸገር ኤፍ ኤም 102.1 ሬድዮ ላይ “ለዛ የአድማጮች ምርጫ ሽልማት” ሥነ ስርዓትን የየጀመሩት።

    በእርግጥ ኪነ ጥበብና ኢትዮጵያ ሀገራችን በባህላዊውም ሆነ በዘመናዊው መንገድ እጅግ ብዙ ዓመታትን ያስቆጠረ ቁርኝት ቢኖራቸውም ቅሉ የኪነ ጥበብ ሙያዉን እንደተከበረ ሙያ ባለሙያዉንም የተከበረ ሙያ እንዳለው ቆጥሮ ወቅት ጠብቆ በተገደበ የጊዜ ኡደት ለሙያውና ለባለሙያው ተገቢውን ዕውቅና፣ ብሎም ክብር የሚሰጥ ቋሚ ተቋም ባለመኖሩ ያለመኖሩን በማስገንዘብ የሥነ ስርዓቱ ሀሳብ ጠንሳሾች “ለምን እኛ የቻልነውን አናደርግም?” በሚል ነበር የኪነ ጥበብ ሰዎችን በዓመት አንድ ጊዜ እያሰባሰቡ ለማወያየት፣ በዓመቱ በሙያውና በሙያቸው ጉልህ አስተዋጽዖ ያደረጉትን “በጎ ሥራ ሠርታችኋል! ይበል!” ለማለት ለዛ የኤድማጮች ምርጫ ሽልማትን በ2003 ዓ.ም የጀመሩት።




    በ2003 ዓ.ም በተደረገው የመጀመሪያ ሽልማት ‘የዓመቱ ምርጥ ነጠላ ዜማ’፣ ‘ምርጥ ተዋናይት’፣ ‘የዓመቱ ምርጥ ተዋናይ’፣ ‘የዓመቱ ምርጥ ፊልም’ እና ‘የዓመቱ ምርጥ አልበም’ በሚሉ አምስት ዘርፎች (ዘውጎች) ኢትዮጵያውያን የኪነ ጠበብ ሰዎች ተመርጠው የተሸለሙ ሲሆን ሽልማቱም ያገኙትም ከያኒት ዘሪቱ ከበደ “አርቴፍሻል” በሚለው ነጠላ ሙዚቃዋ፣ ተዋናይት ሰሃር አብዱልከሪም “ያንቺው ሌባ” በተሰኘ ፊቸር ፊልም ላይ ባሳየችው ትወና፣ ጋሽ አበበ ባልቻ “ሄሮሺማ” በተሰኘ ፊቸር ፊልም ላይ ባሳየው ትወና፣ “ሄሮሺማ” ፊቸር ፊልም በምርጥ በፊልምነት፣ እንዲሁም ከያኒ ናትናኤል አያሌው (ናቲ ማን) በመጀመሪያው አልበሙ በአምስቱ የተዘረዘሩት ዘርፎች አሸናፊዎች ሆነው የሥነ ስርዓቱ የበኩር ተሸላሚዎች ሆኑ።

    በዚህ መልኩ የተጀመረው ለዛ የአድማጮች ምርጫ በየዓመቱ ከጥቅምት ወር ጀምሮ እስከ ሃምሌ ድረስ የሚወጡ የኪነ ጥበብ ሰዎችንና ሥራዎችን በአድማጮች ምርጫ አወዳድሮ ዕውቅና እየሰጠ፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ ተሳታፊዎችን እያበዛ፣ በባለሙያዉም፣ በመራጭነት በሚሳተፈውም ይሁን በየበይ ተመልካችነት በሚከታተለው ኢትዮጵያዊ ዘንድም ተወዳጅነት እያተረፈ ዘንድሮ ለስምንተኛ ጊዜ ጥቅምት 13 ቀን 2011 ዓ.ም በሂልተን ሆቴል፣ አዲስ አበባ፣ እጅግ በደመቀ ሁኔታ ተከናውኗል። ከሁለት ወራት በፊት በተካሔደው ዘጠነኛው አዲስ የሙዚቃ ፌቲቫል ላይ የዓመቱ ምርጥ አርቲስት ተብሎ የተሸለመው ድምጻዊ ሮፍናን ኑሪ በዚህ ሥነ ስርዓትም ላይ ተመሳሳይ ሽልማት፣ ሌሎች ሁለት ሽልማቶችን ጨምሮ አሸንፏል። በስምንተኛው ለዛ የአድማጮች ምርጫ ሽልማት፦

    ● ምርጥ ነጠላ ዜማ፦ “ጨረቃ” (ሮፍናን ኑሪ)፣
    ● ምርጥ አዲስ ድምፃዊ፦ ሮፍናን ኑሪ (“ነፀብራቅ” በተባለው የሙዚቃ አልበሙ)
    ● ምርጥ የሙዚቃ አልበም፦ ነፀብራቅ (ሮፍናን ኑሪ)
    ● ምርጥ የሙዚቃ ክሊፕ፦- የመጀመርያዬ (ናትናኤል አያሌው/ናቲ ማን):-
    ● ምርጥ ተዋናይት፦ አዚዛ አህመድ “ትህትና” በተሰኘ ፊቸር ፊልም ላይ ባሳየችው ትወና፣
    ● ምርጥ ተዋናይ፦ አለማየው ታደሰ “ድንግሉ” በተሰኘ ፊቸር ፊልም ላይ ባሳየው ትወና፣
    ● ምርጥ ፊልም፦ “ድንግሉ”
    ● ምርጥ ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ፦ ምን ልታዘዝ?

    አሸናፊ ሆነው ተሸልመዋል። በዚህ ሥነ ስርዓት ላይ እጅግ ለበርካታ ሙዚቀኞች የዘፈን ግጥም በመስጠት በኢትዮጵያ ሙዚቃ ውስጥ ስሙ እጅጉን ጎልቶ የሚታወቀው የሙዚቃ ግጥም ገጣሚ (lyricist) ይልማ ገብረአብ “የ2010 ዓ.ም የኪነ ጥበባ በለውለታ” ሆኖ ልዩ የክብር ሽልማት ተሸልሟል። ገጣሚ ይልማ ገብረ አብ ከአንድ ሺህ በላይ የሙዚቃ ግጥሞችን ጽፎ ለተለያዩ ድምጻውያን አበርክቷል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ለዛ የአድማጮች ምርጫ


    Semonegna
    Keymaster

    የአሜሪካ ድምፅ ለባለሞያዎቹ ሥልጠና ሲሰጥ ያገር ውስጥ ጋዜጠኞችንም ቢያካትት ፍላጎታቸው መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ስልጠና ለመስጠት አዲስ አበባ ከሚገኙ የአሜሪካ ድምጽ ጋዜጠኞች ጋር በተገናኙበት ጊዜ አስታውቀዋል።

    አዲስ አበባ – የአሜሪካ ድምፅ ለባለሞያዎቹ ሥልጠና ሲሰጥ ያገር ውስጥ ጋዜጠኞችንም ቢያካትት ፍላጎታቸው መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) አስታውቀዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የአሜሪካ ድምፅ የአፍሪካ ዲቪዥን ዳይሬክተር አቶ ንጉሤ መንገሻን እና የአፍሪካ ቀንድ ማኔጂንግ ኤዲተር ጋዜጠኛ ትዝታ በላቸውን በቢሯቸው ተቀብለው አነጋግረዋል።

    የአሜሪካ ድምፅ በኢትዮጵያና በጎረቤት ሃገሮች ለሚገኙ ዘጋቢዎቹ እስካለፈው ዓርብ የቆየ የአንድ ሣምንት ሥልጠና አዲስ አበባ ላይ ሰጥቷል።

    በኢሕአዴግ መንግሥትና በአሜሪካ ድምፅ መካከል ላለፉት 27 ዓመታት ከዘለቀ ውጣ ውረድ ያልተለየው ግንኙነት በኋላ አንድ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር የጣቢያውን ኃላፊዎች ተቀብሎ ሲያነጋግር ይህ የመጀመሪያው ነው።

    ለተጨማሪ መረጃ የተያያዘውን የድምፅ ፋይል ያዳምጡ። ዘጋቢ እስክንድር ፍሬው ለአሜሪካ ድምጽ የአማርኛ ዝግጅት ክፍል

    ጋዜጠኛ ንጉሤ መንገሻ
    ትውልደ ኢትዮጵያዊው ንጉሤ መንገሻ ከ2014 (እ.ኤ.አ) ጀምሮ የአሜሪካ ድምጽ የአፍሪካ ዲቪዥን ዳይሬክተር (Africa Division Director) ሆኖ እያገለገለ ይገኛል። ጋዜጠኛ ንጉሤ ወደ አሜሪካ የመጣው እ.ኤ.አ በ1981 ዓም ሲሆን በ1982 የአሜሪካ ድምጽን በሲኒየር ኤዲተርነት ተቀላቅሏል። ቀጠሎም የአሜሪካ ድምጽ የመካከለኛው አፍሪካ ሰርቪስ ቺፍ (Service Chief)፣ የአፍሪካ ዲቪዥን ፕሮግራም ማናጀር (Africa Division Program Manager)፣ አሁን ደግሞ ሆኖ የአፍሪካ ዲቪዥን ዳይሬክተር አገልግሏል/እያገለገለ ይገኛል።

    ጋዜጠኛ ትዝታ በላቸው
    በ ኤሉባቡር ዞን (የቀድሞው ኤሉባቡር ክፍለሀገር) ያዮ ወረዳ ውስጥ የተወለደችው ጋዜጠኛ ትዝታ በላቸው ወደ አሜሪካ የመጣችው እ.ኤ.አ በ1973 ሲሆን፥ ትምህርቷን ዋሽንግተን ዲሲ በሚገኘው ሐዋርድ ዩኒቨርሲቲ (Howard University) ተከታትላ የአሜሪካ ድምጽን የተቀላቀለችው የአማርኛ ዝግጅት ክፍሉ በተመሠረተ በሁለት ዓመቱ (እ.ኤ.አ በ1984) ነበር። በአሜሪካ ድምጽ (የአማርኛ ዝግጅት ክፍሉን ጨምሮ) በተለያዩ የጋዜጠኝነት ሙያ እርከኖች ያገለገለች ሲሆን በአሁኑ ወቅት የአፍሪካ ቀንድ ማኔጂንግ ኤዲተር (Horn of Africa Managing Director) ሆና እየሠራች ነው።

    የአሜሪካ ድምፅ

    Semonegna
    Keymaster

    ኢታካ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካ የተለያዩ የሴት አልባሳት በማምረት ወደ ተለያዩ የአውሮፓ አገራት መላክ መጀመሩን የፋብሪካው ዋና ሥራ አስኪያጅ ሚስተር ቴድርኮ ፍራንቦኒ (Federico Fraboni) ተናግረዋል።

    መቀሌ (ኢዜአ)–በጣልያኑ ግዙፍ ኩባንያ ካልዜዶንያ ግሩፕ በ15 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ወጪ የተገነባው ኢታካ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካ ተመረቀ።

    በመቀሌ ልዩ ስሙ አሸጎዳ በተባለ አካባቢ የተገነባው ፋብሪካ በወር 22 ሚሊዮን ብር ዋጋ ያላቸው አልባሳትን ለዓለም ገበያ የማቅረብ አቅም እንዳለው በምረቃ ሥነ ስርዓቱ ላይ ተመልክቷል።

    ፋብሪካውን መርቀው የከፈቱት የንግድና ኢንዱስቱሪ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር መብራህቱ መለሰ በክልሉ ከተማ ልማት ንግድና ኢንዳስትሪ ቢሮ የኢንቨስትመንት ጽህፈት ቤት ዳይሬክተር አቶ ሃፍቶም ፋንታሁነኝ እና በኢትዮጵያ የጣሊያን ኤምባሲ ተወካይ ሚስተር ፕትሮ ፓናሮላ ናቸው።




    የንግድና ኢንዱስቱሪ ሚኒስትር ዴኤታው ዶ/ር መብራህቱ በዚህ ወቅት እንዳሉት በጣሊያን ባለሃብቶች ተገንብቶ ለምረቃ የበቃው ኢታካ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካ አገሪቱን ከማልማት አልፎ የኢትዮጵያዊያንን ትክክለኛ ምስል ለዓለም ያስተዋውቃል፤ ፋብሪካው ለዜጎች የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ ለአገሪቱ የኢኮኖሚ እድገት ፋይዳው የጎላ መሆኑንም ተናግረዋል።

    ለሀገሪቱ እድገት ትልቅ ድርሻ ያለውን የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ለማበረታታት ከሁሉም የመንግስት አካላት ትኩረት ሰጥቶ መሥራት እንደሚገባም ዶ/ር መብራህቱ ገልጸዋል።

    ኢታካ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካ የተለያዩ የሴት አልባሳት በማምረት ወደ ተለያዩ የአውሮፓ አገራት መላክ መጀመሩን የተናገሩት ደግሞ የፋብሪካው ዋና ሥራ አስኪያጅ ሚስተር ቴድርኮ ፍራንቦኒ (Federico Fraboni) ናቸው።

    ፋብሪካ በወር 22 ሚሊዮን ብር ዋጋ ያላቸው አልባሳት ለውጭ ገበያ እንደሚያቀርብ እና ቀደም ሲል ለሙከራ ሲያመርት መቆየቱን ገልጻው የመጀመሪያ ምርቱንም በቅርቡ ለውጭ ገበያ መላኩን ጠቁመዋል።

    ———————————————-

    ———————————————-

    በክልሉ ከተማ ልማት ንግድና ኢንዳስትሪ ቢሮ የኢንቨስትመንት ጽህፈት ቤት ዳሬክተር አቶ ሀፍቶም ፋንታሁነኝ በበኩላቸው ፋብሪካው ለአንድ ሺህ ወገኖች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ገልጸዋል።

    በመቀሌ አካባቢ ኢታካ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካን ጨምሮ ባለቤትነታቸው የውጭ ባለሀብቶች የሆኑ ሦስት የጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካዎች ግንባታቸው ተጠናቅቆ ወደ ምርት መሸጋገራቸውንም አቶ ሀፍቶም ተናግረዋል።

    ሌሎች አስር የአገር ውስጥ ባለሀብቶችም በዘርፉ ለመሰመራት የኢንቨስትመንት ፍቃድ ወስደው በተለያዩ የግንባታ ሂደት ላይ ይገኛሉ።

    በክልሉ የኢንዱስቱሪ ዘርፍ እንቅስቃሴ ከዚህም በላይ እንዲያደግ የመንግስት ጥረት ሊጠናከር እንደሚገባም አቶ ሀፍቶም ተናግረዋል።

    በፋብሪካው ምረቃ ላይ የተገኙት በኢትዮጵያ የጣሊያን ኤምባሲ ተወካይ ሚስተር ፕትሮ ፓናሮላ ክልሉ ሰላም የሰፈነበትና ለሥራ የተነሳሳ የሰው ኃይል ያለው መሆኑ በጣሊያን ባለሀብቶች ተመራጭ እንዲሆን አድርጎታል።

    “በኢትዮጵያና በኢጣሊያ የቆየውን የሁለቱን አገራት ታሪካዊና ልማታዊ ግንኙነት በሁሉም ዘርፍ ለማጠናከር በጋራ እንሠራለን” ብለዋል።

    በፋብሪካው የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው ዜጎች መካከል ከመቀሌ ዩኒቨርሲቲ በኢንዱስትሪያል ኢንጂነሪንግ የተመረቀው ወጣት ልኡል ኃይሉ አንዱ ነው።

    ፋብሪካው በአካባቢው በመከፈቱ እሱን ጨምሮ በርካታ ወጣት ምሩቃንን የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ማድረጉን ተናግሯል።

    “ኢታካ የጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካ ወደምርት ሥራ በመግባቱ የሥራ እድል አግኝቺያለሁ” ያለው ደግሞ ወጣት አወጣሀኝ አለነ ነው።

    በምረቃ ስነ ስርዓቱ ላይ ከጣሊያን አገርና ከኢትዮጵያ የመጡ ባለሀብቶችና ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    ኢታካ

    Semonegna
    Keymaster

    “ለኢንቨስትመንት በሚል ሰበብ አርሶ አደሩን በማደህየት ኢንቨስትመንቱን ማሳደግ አይቻልም፤ መሬታቸው የሚወሰድባቸው አርሶ አደሮች ተመጣጣኝ ካሳ ማግኘት አለባቸው።” ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው

    ዘጋቢ፡-ደጀኔ በቀለ (አብመድ)

    ባሕር ዳር – የገጠር መሬት አስተዳደርና አጠቃቀም ቢሮ በ2011 ዓ.ም በጀት ዓመት ዕቅድ ትውውቅ፣ በሕግ ማዕቀፎች እና አሠራሮች ላይ ሲሰጥ የነበረውን ክልላዊ የምክክር መድረክ ዛሬ አጠናቅቋል።

    የአማራ ክልላዊ መንግስት ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ለኢንቨስትመንት በሚል ሰበብ ብዙ አርሶ አደሮች መብታቸው ተጥሶ እንደነበር በመጥቀስ አርሶ አደሩን በማደህየት ኢንቨስትመንቱን ማሳደግ አይቻልም፤ መሬት የሚወሰድባቸው አርሶ አደሮች ተመጣጣኝ ካሳ ማግኘት አለባቸው ሲሉ አስገንዝበዋል። ቀደም ሲል ካሳ የማያገኙበት ሕግ የነበረ ቢሆንም ሕጉን የማስተካከል እርምጃ መወሰዱንም አስታውቀዋል።

    አርሶ አደሮች እና የነባር ይዞታ ባለቤቶች መሬታቸውን ሕጋዊ በሆነ መንገድ እንዲጠቀሙ መደረጉ ጥያቄ በሚያነሱበት ጊዜ በመረጃ ላይ የተመሠረተ ምላሽ ለመስጠት ከማገዙም በላይ ህብረተሰቡ ተረጋግቶ እንዲሠራ ያደርገዋል። በመሆኑም አርሶ አደሩን ከአላስፈላጊ እንግልት የምናድንበት በመሆኑ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ርዕሰ መስተዳድሩ አሳስበዋል።

    አርሶ አደሮች በጉልበተኛ ጥቅማቸውን የሚያጡበት ፍትሃዊ ያልሆነ አሠራር ካለ የገጠር መሬት አስተዳደር እና አጠቃቀም ቢሮ ህዝባዊ ኃላፊነቱን ለመወጣት ጠንክሮ መሥራት እና የፍትህ ስርዓቱን ማስከበር ይጠበቅበታልም ነው ያሉት አቶ ገዱ አንዳርጋቸው።

    ሕገ-ወጥ የመሬት ወረራን በተመለከተ ትኩረት ተሰጥቶት እንዲሠራ ርዕሰ መስተዳድሩ በጥብቅ አሳስበዋል። በተለይ የወል መሬቶች በሕገ-ወጥ መንገድ ወደ ግለሰቦች ይዞታ ስር እየገቡ በመሆኑ በፍጥነት መግታት ካልተቻለ ስር እየሰደደ ሄዶ ግለሰቦች ላይ ጫና ማሳደሩ እንደማይቀር አስገንዝበዋል።

    በመድረኩ የተሳተፉ አካላት በባለቤትነት ይዞ በመንቀሳቀስ ከሚመለከተው ባለድርሻ አካላት ጋር ትኩረት ሰጥተው ሊሠሩ እንደሚገባም አፅንዖት ሰጥተው ተናግረዋል።

    ለተከታታይ አምስት ቀናት የቆየውን የምክክር መድረክ የተካፈሉ አስተያየት ሰጪዎች በበኩላቸው በሚችሉት አቅም ሁሉ ህብረተሰቡን ለማገልገል ፍቃደኛ መሆናቸውን ተናግረዋል።

    ተጨማሪ ዜና፦ ኢትዮጵያዊው ባለሃብት አቶ በላይነህ ክንዴ እያስገነቡ ያሉት የምግብ ዘይት ፋብሪካ በቅርቡ ሥራ ይጀምራል

    አቶ ወዳጅ ምስክር ከሰሜን ወሎ ዞን፣ ወይዘሮ በላይነሽ አሻግሬ ደግሞ ከደቡብ ጎንደር ፋርጣ ወረዳ በምክክር መድረኩ የተገኙ ተሳታፊዎች ናቸው። ከውይይቱ በቂ ግብዓት እንዳገኙ ነግረውናል። ተሳታፊዎቹ እንደተናገሩት ወቅቱን መሰረት ያደረገ የገጠር መሬት አጠቃቀም ስልጠና መውሰዳቸው ለቀጣይ የተጣለባቸውን የሕዝብ ኃላፊነት በብቃት ለመወጣት ዝግጁ እንደሚያደርጋቸው ለአብመድ ጋዜጠኞች አረጋግጠዋል።

    በመዝጊያ ሥነ-ስርዓቱ ላይ የተገኙት ርዕሰ መስተዳድር ገዱ አንዳርጋቸው የገጠር መሬት አስተዳደር እና አጠቃቀም ቢሮ ከወረዳ እስከ ክልል ድረስ ተቋማዊ በሆነ መንገድ ሥራውን በአግባቡ ለመወጣት ጥረት እያደረገ ያለ ተቋም መሆኑን አውስተው፥ መሬት ሀብት እና የማንነት መገለጫ መሆኑን በመረዳት የኃላፊነት ስሜት በተሞላበት መንገድ ሲንቀሳቀስ ለቆየው ለተቋሙ ምስጋናቸውን አቅርበዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ ሥራው አድካሚ መሆኑን በመጥቀስ ወደ ዘመናዊ የመረጃ ቋት ለማስገባት ተቋሙ እያደረገ ያለው ጥረት የሚበረታታ ነው ብለዋል።

    ከገጠር መሬት ጋር በተያያዘ ለሚከሰቱ ማንኛውም ጥያቄዎች ምላሽ መስጠት የሚችለው በመድረኩ ላይ የተሳተፈው ባለሙያ ነው፤ በተለይ በምዕራብ ቆላማው የክልሉ አካባቢዎች ለበርካታ ዘመናት ጥሩ አሠራር ያልነበረባቸውን ቦታዎች በዚሁ ተቋም ውስጥ በተሰማሩ ሙያተኞች እና አመራሮች አማካኝነት ውጤታማ በሆነ መንገድ ማስተካከል ተችሏል ብለዋል።

    በከተሞች ዙሪያ የሚኖሩና ትኩረት የማያገኙ አርሶ አደሮች ጥቅማቸው እና መብታቸው እንዲከበር በማድረግ በኩል ትልቅ ሥራ ተሰርቷል፤ ተገፍተው ለነበሩ አርሶ አደሮች በተገቢው መንገድ ካሳ እንዲያገኙ ተደርጓል ብለዋል።

    ምንጭ፦ የአማራ መገናኛ ብዙሀን ድርጅት (አብመድ)

    ገዱ አንዳርጋቸው

    Semonegna
    Keymaster

    ኢትዮጵያውያን የፋሽን ዲዛይነሮች ለዓለም ገበያ የኢትዮጵያን ምርት ይዘው ሲወጡ ምርቱን ብቻ ሳይሆን ሜድ ኢን ኢትዮጵያ በሚለው ሳያሜ ኢትዮጵያዊነትንም በማስተዋወቅ ደረጃ ጉልህ አስተዋጽዖ አያደረጉ እንደሆነ እንደሚሰማቸው ይናገራሉ።

    አዲስ አበባ (ኢዜአ)– ኢትዮጵያውያን ዲዛይነሮች በኢትዮጵያ የተመረተ ሜድ ኢን ኢትዮጵያ በተሰኘው መለያ አገራቸውን ለማስተዋወቅ ተስፋ ሰንቀዋል።

    ዲዛይነር ሳምራዊት መርሲኤሓዘን ኢትዮጵያ ውሰጥ የተሰራ ሜድ ኢን ኢትዮጵያ የተሰኘ መለያን የያዙ ቦርሳዎችና ሌሎች የቆዳ ውጤቶችን በማምረት አገሯን የማስተዋወቅ ራዕይ ይዛ እየሰራች ትገኛለች።

    በእንስሳት ሃብት ከአፍሪካ ቀዳሚ እየተባለች ለዘመናት የምትታወቀው ኢትዮጵያ ከቆዳ ውጤቶች እምብዛም አለመጠቀሟ ዲዛይነር ሳምራዊትን ያስቆጫታል። እንደ እርሷ አገላለጽ አሁንም ቢሆን በቁጭት ከተሠራ በእንስሳት ሃብት ብቻ ሳይሆን በኢትዮጵያ በተመረቱ የቆዳ ውጤቶች አገርን ለማስጠራት ጊዜው አልረፈደም።

    ለዚህ የእርሷ የቆዳ ቦርሳ፣ ምንጣፍና ሌሎች ምርቶች ተደራሽ በሆኑባቸው አገራት ያለውን ተቀባይነት በማንሳት ታብራራለች። ለዓለም ገበያ የኢትዮጵያን ምርት ይዛ ስትወጣ ምርቱን ብቻ ሳይሆን ሜድ ኢን ኢትዮጵያ በሚለው ሳያሜ ኢትዮጵያዊነትንም እየሸጠች መሆኑን እንደሚሰማት ነው የተናገረችው።

    ሥራዋን ከጀመረች ስድስት አመታትን ያስቆጠረችው ዲዛይነሯ፤ ጀርመን፣ ጃፓንና ሆላንድ ምርቷን ከምታቀርብባቸው አገሮች መካከል ሲሆኑ በቀጣይም የዱባይና እንግሊዝ ገበያን ለመድረስ ዕቅድ አላት።

    የውጭ ገበያን ሰብሮ ለመግባት መጀመሪያ የራሳችንን መቀበልና የራሳችንን ማድነቅ መጀመር አለብን የሚል ሃሳብም አንስታለች።

    በቆዳ ምርቶች ያደጉ አገሮች ለዲዛይን፣ ለአሠራርና አጨራረስ የሚጠቀሙበትን ዘዴ ልምድ በመውሰድ መወዳደር አለብን የሚል እሳቤም አላት ዲዛይነር ሳምራዊት።

    “በውጭ ባህል ጥገኛ ከመሆን የብሔር ብሔረሰቦችን የአለባበስ ስርዓት ከዓለም አቀፍ ፍላጎት ጋር በማመጣጠን መለያ በማድረግ ልንታወቅበት የምንችል የገበያ ዘርፍ ነውም” ስትል ትገልጻለች።

    የቀደምት ኢትዮጵያውያን እናቶች መገለጫ ከሆነው “ፈትል” በተሠሩ የአገር ባህል ልብሶችም ኢትዮጵያን ለዓለም ለማስተዋወቅ ተስፋ ማድረጋቸውን “የፈትል ዲዛይነር” ሽያጭ ሠራተኛ ወጣት ፌቨን ተስፋዬ ትናገራለች።

    የኢትዮጵያ ፈትል በማንኛውም ሰዓት ሊለበስ በሚችል መልኩ በማምረት አሜሪካን ጨምሮ ሌሎች አገሮች ምርቱን ካገኙ በጉጉት እንደሚወስዱ ታዝባለች። ልብሱ የተሠራበት ጥሬ እቃ ከፈትል መሆኑ በተለያዩ አገራት አድናቆትን እያገኘና ባህልን እያስተዋወቀ መሆኑንም ፌቨን ትናገራለች።

    ሌላዋ አስተያየት ሰጪ ዲዛይነር ቁንጅና ተስፋዬ ዘወትር የሚለበሱ የኢትዮጵያን ባህል የሚገልጹ ልብሶችን በመሥራት ለአገር ውስጥና ለውጪ ገበያ በማቅረብ ላይ ትገኛለች።

    ቪድዮ፦ የኢትዮጵያ አልባሳትና ባህላዊ ዲዛይኖች የዓለም ገበያን ሰብረው እንዲገቡ ለማድረግ ብዙ መሠራት አለበት

    የምትሠራቸው አልባሳት የኢትዮጵያን አንዱን ብሔረሰብ አለባበስ በሚገልጽ መልኩ በመሆናቸውም በእያንዳንዱ ልብስ የኢትዮጵያ ብሔረሰቦችን ባህል እያስተዋወቀች መሆኗን ተናግራለች።

    ከዚህ በፊት በዓለም ላይ የተሰሩት የአለባበስ ዲዛይኖች እየተደጋገሙ በመሆናቸውና አሁን አሁን እነሱ በሠሩት ዲዛይን መሠረት ዓለም ወደ አፍሪካ ፊቱን እያዞረ መሆኑን በመግለጽ ይህን ዕድል አገራችንን ለማስተዋወቅ መጠቀም አለብን የሚል አስተያየትም ሰጥታለች።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    ሜድ ኢን ኢትዮጵያ

    Semonegna
    Keymaster

    የወሎ ዩኒቨርሲቲ የሚጀምረው የግዕዝ ቋንቋ ትምህርት በቋንቋው የተጻፉ ሥራዎችን ወደ ሌሎች አገርኛ ቋንቋዎች በመተርጎም ጥቅም ላይ ለማዋል እንደሚያስችል በዩኒቨርሲቲው የማኅበራዊና ሥነ ሰብእ ኮሌጅ የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ ጽሁፍ ትምህርት ክፍል ተጠሪ ተናግረዋል።

    ደሴ (ኢዜአ) – የወሎ ዩኒቨርሲቲ ከያዝነው የትምህርት ዘመን ጀምሮ የግዕዝ ቋንቋን በመጀመሪያ ዲግሪ ለማስተማር ዝግጅቱን ማጠናቀቁን አስታወቀ።

    ዩኒቨርሲቲው ትምህርቱን ለመጀመር በቀረጸው ሥርዓተ ትምህርት (curriculum) ዙሪያ ከምሁራንና ባለድርሻ አካላት ጋር መስከረም 29 ቀን 2011 ዓ.ም ተወያይቷል።

    በዩኒቨርሲቲው የማኅበራዊና ሥነ ሰብእ ኮሌጅ የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ ጽሁፍ ትምህርት ክፍል ተጠሪ ዶክተር እንድሪስ አብይ እንዳስረዱት ግዕዝ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የላቀ ሥፍራ አለው።

    ትምህርቱን ለማስጀመር አራት መምህራን የተቀጠሩ ሲሆን፣ እስከ 18 ተማሪዎችን ለመቀበል ዝግጅት ማድረጉን ገልጸዋል።

    ሥርዓተ ትምህርቱ ጋዜጠኝነትን ጨምሮ አገር በቀል ህክምናና መድኃኒት፣ የሥነ ከዋክብት ቀመርና የቀን አቆጣጠር፣ የባህልና የህግ ሥርዓቶች ተካተውበታል።

    ትምህርቱ በቋንቋው የተጻፉ ሥራዎችን ወደ ሌሎች አገርኛ ቋንቋዎች በመተርጎም ጥቅም ላይ ለማዋል እንደሚያስችል ዶክተር እንድሪስ ተናግረዋል።

    በቋንቋው በፍልስፍና፣ በህክምና፣ በሥነ ከዋክብትና በመሳሰሉት የዕውቀት ዘርፎች በርካታ ጽሁፎች ቢጻፉም፤ ህዝቡንም ሆነ አገሪቱን መጠቀም የሚገባቸውን ያህል አልተጠቀሙበትም። ዕውቀቱም ለሌሎች ሳይተላለፍ ለረጅም ዓመታት መቆየቱን ተጠሪው ገልጸዋል።

    በዩኒቨርሲቲው የታሪክና ቅርስ ጥናትና ጥበቃ ትምህርት ክፍል አስተባባሪና መምህር አቶ ዘላለም ጌትነት በበኩላቸው የመጥፋት አደጋ ላይ የሚገኘውንና የዕውቀት ምንጭ የሆነውን ቋንቋ በዩኒቨርሲቲ ደረጃ መስጠቱ ታሪክን ከማቆየትና እውቀትን ከማጋራት አንጻር ጠቀሜታው ጉልህ ነው ብለዋል።

    ሥርዓተ ትምህርቱ በተለይ ቋንቋው ከኢትዮጵያ ታሪክ ጋር ያለውን ቁርኝት በሚያሳይ መልኩ ቢቀረጽ የተሻለ እንደሚሆን አመልክተዋል።

    በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቲያትር ጥበባት ትምህርት ክፍል መምህርና የሥነ ጥበባት ኮሌጅ የድህረ ምረቃ ተባባሪ ዲን ረዳት ፕሮፌሰር አሰፋ ወርቁ ”ዩኒቨርሲቲው የአገር ሃብት የሆነውን የግዕዝ ቋንቋ ለማስተማር መወሰኑ የሚያስመሰግነውና ሌሎችም ዩኒቨርሲቲዎች ተመሳሳይ ኃላፊነት እንዲወስዱ መነቃቃትን የሚፈጥርላቸው ነው” ብለዋል።

    ግዕዝ ኢትዮጵያን የምናውቅበት የዕውቀት ምንጭ መሆኑን አስታውሰው፣ ይህንን መገናኛ ብዙኃን አገራዊ ፋይዳ ያለውን የዕውቀት ዘርፍ በማስተዋወቅ ድርሻቸውን እንዲወጡ ጠይቀዋል።

    የወሎ ዩንቨርሲቲም ተማሪዎችን ካስመረቀ በኋላ የሥራ ዕድል እንዲያገኙ ከባለድርሻ አካላት ጋር መምከር እንዳለበትም አቶ አሰፋ አሳስበዋል።

    በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የደቡብ ወሎ አገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ መአምራን ብርሃነሕይወት እውነቱ ቋንቋው በዩኒቨርሲቲው መሰጠቱ በርካታ አገራዊ ታሪኮች፣ ቅርሶች፣ መንፈሳዊና ዓለማዊ ሥራዎች፣ ምርምርን የሚጋብዙ ሥራዎች ለማወቅና ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን በአዲስ መንፈስ ለማስቀጠል ጠቀሜታ እንዳለው አስረድተዋል።
    የአብነት ተማሪዎች እንቅስቃሴ መዳከም ቋንቋውን እንዳዳከመው አውስተው፣ የወሎ ዩንቨርሲቲ የጀመረው ጥረት እንዲሳካ ቤተክርስቲያኗ ድርሻዋን ለመወጣት ዝግጁ መሆኗን አስታውቀዋል።

    ከዚህ ጋር በተያያዘ በ1999 ዓ.ም. የተመሠረተው የወሎ ዩኒቨርሲቲ ዓመታዊ የቅበላ አቅም ዘንድሮ ከ20 ሺህ በላይ ደርሷል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    የወሎ ዩኒቨርሲቲ

Viewing 15 results - 106 through 120 (of 124 total)