Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Home Forums Search Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Viewing 15 results - 586 through 600 (of 730 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    መቀዛቀዝ የታየበትን የህዝባዊ ተሣትፎ ለማነቃቃት የተለያዩ መድረኮችን በቀጣይነት እንደሚያዘጋጅ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ህዝባዊ ተሣትፎ ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ኃይሉ አብርሃም ገልጸዋል።

    አዲስ አበባ (ዋልታ)– የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ህዝባዊ ተሣትፎ ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ባለፉት 6 ወራት 484 ሚሊዮን ብር መሰብሰቡን አስታውቋል።

    ጽህፈት ቤቱ በበጀት ዓመቱ እስከ አንድ ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ አቅዶ እየሠራ ሲሆን በቀጣይ የተጠናከረ አፈጻጸም ለማስመዝገብ እንደሚንቀሳቀስ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ማኅበር እና የህዳሴው ግድብ ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ባዘጋጁት ጋዜጣዊ መግለጫ ገልጿል።

    መቀዛቀዝ የታየበትን የህዝባዊ ተሣትፎ ለማነቃቃት የተለያዩ መድረኮችን በቀጣይነት እንደሚያዘጋጅ የህዳሴው ግድብ ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ኃይሉ አብርሃም ገልጸዋል።

    ቪዲዮ፦ ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የግንባታ ድጋፍ ዙሪያ ከኢትዮጵያውያን የዳያስፖራ አባላት ጋር የተደረገው ውይይት

    ከዚሁ ጋር በተያያዘም ጥር 22 ቀን 2011 ዓ.ም. ከንቅናቄ መድረኮች አንዱ የሆነው ሁሉም የዳያስፖራ አካላት የሚገኙበት መድረክ በራስ ሆቴል መድረክ አዘጋጅቶ ከተለያዩ ሀገራት ከመጡ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ አባላት ጋር በቀጣይነት እና በተሻለ ሁኔታ ግድቡን ሊደግፉ በሚችሉበት መንገድ ላይ ውይይት አድርጓል።

    ዳያስፖራው ባለፉት ሰባት ዓመታት 46 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ማድረጉ የተገለጸ ሲሆን ሃገሪቱ ካላት ዲያስፖራ ቁጥር አንጻር ድጋፉ አነስተኛ መሆኑ ተጠቁሟል። በመሆኑም በተለይም በምዕራብ አውሮፓ የሚገኙ ዲያስፖራዎች የሚጠበቅባቸውን ያህል ድጋፍ ስላላደረጉ ትኩረት አድርጎ እንደሚሠራ የዳያስፖራ ማኅበሩ ዋና ዳይሬክተር አቶ አብርሃም ስዩም አስታውቋል።

    ለዚህም ዳያስፖራው ለህዳሴው ግድብ አዲስ የዳያስፖራ ተሳትፎ ንቅናቄ ለመፍጠር እና በዳያስፖራው ዘንድ በህዳሴ ግድቡ ዙሪያ ያለውን ብዥታ ለማጥራት መድረክ ፈጥሮ ውይይት ማድረግ አስፈላጊ እንደነበርና፣ የራስ ሆቴሉ ውይይትም የዚሁ ዋነኛ አካል እንደነበር ተገልጿል። በተመሳሳይ ሁኔታም በዕለቱ የተለያዩ የህዝብ አደረጃጀቶች የሚሳተፉበት የንቅናቄ መድረክ በካፒታል ሆቴል ተካሂዶ ነበር።

    ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ከሁለት ዓመት በኋላ ኃይል ማመንጨት እንደሚጀምር የተገለጸ ሲሆን ከአራት ዓመት በኋላ ተገንብቶ እንደሚጠናቀቅ ይጠበቃል።

    ምንጭ፦ ዋልታ ሚዲያ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦  

    ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– የአሜሪካ ኢምባሲ 2ኛውን ‹‹SolveIT›› የተሰኘ ሀገር አቀፍ የፈጠራ ውድድርን የኢዲስ አበባ ከተማን በይፋ አስጀመረ። ኢምባሲው ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር፣ ከጃፓን ዓለማቀፋዊ ኮኦፐሬቲቭ ኤጀንሲ (Japan International Cooperation Agency – JICA) እና ከአይኮግ ላብስ (iCog Labs) ጋር በመተባር ነው ውድድሩን ይፋ ያደረገው።

    ፕሮጀክቱ በመላ ሀገሪቱ በሚገኙ 15 ከተሞች የሚካሄድ ሲሆን ቴክኖሎጂ ነክ የፈጠራ ሥራዎች ላይ ትኩረቱን ያደረገ ነው።
    ችግር ፈቺ ቴክኖሎጂ ነክ የፈጠራ ሰራዎች ያሏቸው ወጣቶች የሚሳተፉበት ይህ ውድድር የፈጠራ ባላሙያዎቹ ሥራዎቻቸውን ሊያዳብር የሚችል ስልጠና በየከተሞቹ ይሰጣቸዋል።

    SolveIT ሀገር አቀፍ የቴክኖሎጂ ፈጠራ ውድድርን የአሜሪካ ኢምባሲና የጃፓን ዓለማቀፋዊ ኮኦፐሬቲቭ ኤጀንሲ ፕሮጀክቱን በገንዘብ ይደግፉታል። ተመሳሳይ ፕሮግራሞች በየከተሞቹ የሚዘጋጁ ሲሆን የተመረጡ ችግር ፈቺ የፈጠራ ሥራዎች ለሽልማት ይበቃሉ ተብሏል።

    VIDEO: These two Ethiopian students are working to launch their own rocket – the future Eng. Kitaw Ejigu

    የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የኢኖቬሽን ልማትና ምርምርና ዘርፍ ዳይሬክተር ጀነራል ካህሊድ አህመድ (ዶ/ር) በፕሮጀክቱ ተመርጠው የመጡ የፈጠራ ሥራዎች ገበያውን እንዲቀላቀሉ ሚኒስቴሩ አስፈላጊውን ሁሉ ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል።

    ተጨማሪ ስልጠና የሚያስፈልጋቸውን በቴክኖሎጂ ማበልፀጊያ ማዕከላት በማስገባትና የሥራ ማስጀመሪያ ገንዘብ በመደጎም ጭምር ድጋፍ እንደሚያደረግ አረጋግጠዋል።

    የአሜሪካ ኤምባሲ በኢትዮጵያ በዋናነት ስፖንሰር የሚያደርገው SolveIT ውድድር በወጣት ኢትዮጵያውያን ዘንድ የሳይንስ፣ የቴክኖሎጂ፣ የኢንጂነሪንግ፣ የአርት እና የሒሳብ (STEAM) በወጣቶች ዘንድ ይበልጥ እንዲጎለብቱ የሚያበረታታ ውድድር ሲሆን ፥ ኢትዮጵያውያን ወጣቶች ለሚኖሩበት ህብረተሰብ፣ ብሎም ለሀገራቸው ችግር ፈቺ የሆኑ የቴክኖሎጂ፣ የሶፍትዌርና የሀርድዌር ፈጠራዎችን በመፍጠር እንዲሳተፉ ያደርጋል።

    ዕድሜያቸው ከ18 እስከ 28 ዓመት የሆነ ኢትዮጵያውያን ወጣቶች በሚኖሩበት ከተማ ሆነው ህብረተሰባቸው የሚያጋጥመውን ችግር ሊፈታ የሚፍል ፈጠራ ለመፍጠር ለዘጠኝ ወራት ያህል ጊዜ ተሰጥቷቸው ይሠራሉ። በዚህም ጊዜ ከአወዳዳሪዎች በተመደቡላቸው ባለሙያዎች ስልጠና ይሰጣቸዋል። ፈጠራዎቻቸው ከሞባይ አፕ (mobile app) ጀምሮ እስከ ከፍ ያለ የኮምፒዩተር ሶፍትዌር ሊሆን ይችላል። በከተሞቻቸው (በክሎቻቸው) አሸናፊ የሆኑ ተወዳዳሪዎች ከፍ ወዳለው (የፌደራል) ውድድር ያልፋሉ፤ በዚያም ለሳምንት ያህል በዳኞች ና በከፈተኛ ኤክስፐሮች እየተዳኙ ይወዳደራሉ። በዚህም የመጨረሻዎቹ አሸናፊዎች ይለያሉ።

    በአሁኑ ጊዜ ተወዳዳሪዎችን እየተቀበለ ይገኛል። የበለጠ መረጃ የአይኮግ ላብስ (iCog Labs) ድረ ገጽ ላይ ማግኘት ሲችሉ (እዚህ ጋር ይጫኑ)፥ መመዝገቢያውን ደግሞ እዚህ ጋር ያገኙታል (Register)።

    ምንጭ፦ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    SolveIT ውድድር


    Semonegna
    Keymaster

    ባለቤት አልባ ውሾችን ከማስወገዱ ተግባር ጎን ለጎን በከተማዋ ያሉ ውሾችን የቤት ለቤት ምዝገባ በማከናወን የባለቤትነት ማረጋገጫ በየወረዳው እየተሰጠ እንደሚገኝ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ገልጿል። በዚህም፣ ህብረተሰቡ ለሚመለከተው አካል እያሳወቀ ችግሩን በጋራ መቅረፍ እንደሚገባም ጥሪ ቀርቧል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ባለፉት ስድስት ወራት ውስጥ 7ሺህ 8 መቶ ባለቤት አልባ ውሾችን ማስወገዱን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አስታወቀ።

    በከተማ አስተዳድሩ አስተዳደር የንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ የከተማ ግብርና ዘርፍ አስተባባሪ አቶ አሰግድ ኃ/ጊዮርጊስ ለኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ) እንደተናገሩት በከተማዋ እየተበራከቱ የመጡ ባለቤት አልባ ውሾችን ከህብረተሰቡ ጋር በመሆን ለማስወገድ በጋራ እየሠራ ነው። ባለቤት አልባ ውሾቹ በህብረተሰቡ ላይ የሚደርሱትን የጤና ስጋት ችግር ለመቅረፍ እየሠራ መሆኑንም አስተባባሪው አቶ አሰግድ ገልፀዋል።

    በበጀት ዓመቱ ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ ከከተማው ውበትና መናፈሻ፣ የጽዳት አስተዳደር፣ ጤና ቢሮ እንዲሁም ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሆን እስካሁን 7ሺህ 8 መቶ ውሾችን ማስወገድ መቻሉንም ተመልክቷል። በየቦታው ተንጠባጥበው የሚገኙ ባለቤት የሌላቸው ውሾችን የማስወገዱ ሥራው ተጠናክሮ መቀጠሉንም አቶ አሰግድ ተናግረዋል።

    ቪዲዮ፦ አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የተለያዩ የቆሻሻ መጣያ የነበሩ ቦታዎችን በማጽዳትና አረንጓዴ በማድረግ፣ እንዲሁም የተለያዩ አትክልቶችን አልምቶ በመሸጥ ራሳቸውን የሚያስተዳድሩ ወጣቶች

    በተጨማም በከተማዋ ያሉ ውሾችን የቤት ለቤት ምዝገባ በማከናወን የባለቤትነት ማረጋገጫ በየወረዳው እየተሰጠ እንደሚገኝ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ገልጿል። በዚህም፣ ህብረተሰቡ ለሚመለከተው አካል እያሳወቀ ችግሩን በጋራ መቅረፍ እንደሚገባም ጥሪ ቀርቧል።

    በአንፃሩ ባለቤት አልባ ውሾችን በማስወገዱ ሂደት ከአንድ ወር በላይ ጊዜ የመድሃኒት አቅርቦት እጥረት እንደገጠመውም አስተዳደሩ ገልጿል። በዚህም፣ በፌዴራል ደረጃ የመድሃኒት ፈንድ መድሃኒቱን እስኪያቀርብ እየተጠበቀ መሆኑንና አቅርቦቱ እንደተሟላ ባለቤት አልባ ውጮችን የማስውገዱ ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ተብሏል ሲል ዘግቧል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕረሽ ድርጅት / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    ባለቤት አልባ ውሾች - የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– ግዙፉ የመኪና አምራች የሆነው የጀርመኑ ኩባንያ ቮልስዋገን በኢትዮጵያ ኢንቨስት ለማድረግ የሚያስችለውን የመግባቢያ ስምምነት ፈረመ። ስምምነቱን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽነር አበባ አበባየሁ እና ከሰሃራ በታች የኩባንያው የአፍሪካ ቀጣና ሥራ አስፈጻሚ ቶማስ ሻፈር ተፈራርመዋል። በስምምነቱ መሠረትም ኩባንያው የመኪና መገጣጠሚያ ፋብሪካ መክፈት፣ የተሽከርካሪ መለዋወጫ ዕቃዎችን ማቅረብ፣ የስልጠና ማዕከል መክፈት እና ተጓዳኝ ሥራዎችን ይሠራል።

    በስምምነቱ ላይ በኢትዮጵያ የሥራ ጉብኝት ላይ የሚገኙት የጀርመኑ ፕሬዚዳንት ፍራንክ ዋልተር ስታይንማየር እና የኢፌዴሪ የገንዘብ ሚኒስትር አቶ አህመድ ሽዴ ተገኝተዋል።

    ቮልስዋገን ኩባንያ ከሰሃራ በታች ካሉ የአፍሪካ አገራት መካከል ኢትዮጵያን የማስፋፊያ ማዕከሉ አድርጎ ሲመርጥ፣ ከኩባንያው ጋር የመግባቢያ ስምምነት በመፈረም ከሰሃራ በታች ካሉ አገራት ኢትዮጵያ ሦስተኛዋ አገር (ከጋና እና ናይጄሪያ ቀጥሎ) ሆናለች።

    ◌ VIDEO: የጀርመኑ ግዙፍ የመኪና አምራች ኩባንያ ኢትዮጵያ ውስጥ ሰፊ ኢንቨስትመንት ለመጀመር እየተንቀሳቀሰ ነው

    ኩባንያው ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር ለመሥራት መስማማቱ በቀጥታ የእሴት ሰንሰለት የተቀናጀ የአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪ ክላስተር ለመፍጠር ወሳኝ ምዕራፍ ይከፍታል ነው የተባለው።

    ኮሚሽነር አበበ አበባየሁ በፊርማ ሥነ-ስርዓቱ ላይ እንዳሉት መንግሥት አገሪቷን ቀዳሚ የኢንቨስትመንት መዳረሻ ለማድረግ በቁርጠኝነት እየተንቀሳቀሰ ነው።

    ”በአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪው መስክ ልዩ ክላስተር እንዲመሠረት መንግሥት ያለሰለሰ ጥረት ያደርጋል” ያሉት ኮሚሽነሩ ይህን ተግባራዊ ለማድረግ ቮልስዋገንን ጨምሮ ፍላጎት ካላቸው ተቋማት ጋር በቅንጅት ለመሥራት ‘ዝግጁ ነው’ ብለዋል።

    ◌ VIDEO: German companies including Volkswagen and Siemens embarking to invest in Ethiopia

    የኩባንያው የአፍሪካ ቀጣና ሥራ አስፈጻሚ ቶማስ ሻፈር በበኩላቸው የኢትዮጵያ መንግሥት ለአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪው እድገት ትኩረት መስጠቱ ‘የሚደነቅ ነው’ ሲሉ ተናግረዋል። ከዚህ በተጨማሪ ቶማስ ሻፈር ‘ኢትዮጵያ ፈጣን እድገት በማስመዝገብ ላይ ያለች እና በሕዝብ ብዛትም ከ አህሪካ አገራት በሁለተኛ ደረጃ የተቀመጠች በመሆኗ፥ ከሰሃራ በታች ባሉ ሀገራት ለመስፋፋት በምናደርገው ጥረት ኢትዮጵያን ሁነኛ ተመራጭ አገር አድርገናታል፤ በተጨማሪም ቮልስዋገን ኩባንያ ሀገሪቱ ያላትን የስትራቴጂ ጥቅም ከግምት በማስገባት በ አውቶሞቲቭ ዘርፍ ከፍትኛ እድገት እንድታስመዘግብ ይተጋል’ ብለዋል።

    ከዚህ ጋር በተያያዘ የጀርመን የቢዝነስ ልኡካን ቡድን ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የሥራ ሃላፊዎችና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በኢትዮጵያ በኢንቨስትመንት መስክ በሚሰማሩበት ሁኔታ ላይ መክረዋል።

    ሲመንስ የተሰኘው በግዙግነቱ ከአውሮፓ ኩባንያዎች ቀዳሚውን ስፍራ የሚይዘው የጀርመን የቴክኖሎጂ ኩባንያ በኢትዮጵያ ከዚህ በፊት ሲሠራቸው ከነበሩ የቴክሎጂ ዘርፍ ሥራዎች በተጨማሪ በተጠናከረ መልኩ ለመሥራት ዝግጁ መሆኑን አሳውቋል።

    NEWS: German automaker Volkswagen develops automotive industry in Ethiopia

    የጀርመን የቴክኖሎጂ ጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ማኅበርም ቢሮውን አዲስ አበባ በመክፈት ወደ ሥራ ለመግባት ፍቃደኛ መሆኑን አሳውቋል። ማኅበሩ ጀርመን ውስጥ ያሉ የቴክኖሎጂ ድርጅቶች ማኅበር እንደመሆኑ ድርጅቶቹ በመስኩ ለመሰማራት የሚያስችላቸውን ሁኔታ ለማመቻቸት መልካም አጋጣሚን እንደሚፈጥር ይታመናል።

    በኢትዮጵያ መንግስት በኩል በጊዜያዊነት በነፃ ቢሮ በመስጠት ጭምር ማንኛውንም እገዛ ለማድረግ ቁርጠኛ መሆኑንም ተገልጿል።
    የልኡካን ቡድኑ አባላት በኢትዮጵያ ውስጥ በኢንቨስትመንት የተሰማሩ ድርጅቶች ከምንዛሬ እጥረት፣ በደላላ ምክንንያት ምርቶቻቸው ተጠቃሚው ጋር በተጋነነ ዋጋ መድረስ የመሳሰሉ ችግሮች እንደገጠሟቸው ተናግረዋል።

    የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ ጌታሁን መኩሪያ (ዶ/ር ኢንጂ.) የኤሌክትሮኒክስ ግብይት ለመጀመር ሥራዎች እየተሰሩ በመሆኑ ወደ ሥራ ሲገባ ችግሩ እንደሚቀረፍ ተናግረዋል።

    ምንጮች፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ቮልስዋገን


    Semonegna
    Keymaster

     

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– የኢትዮጵያ አየር መንገድ 65 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር በሚደርስ ወጪ ያስገነባውና ዓለምአቀፍ ደረጃውን የጠበቀው ስካይላይት ሆቴል እሁድ ጥር 19 ቀን 2011 ዓ.ም. ታላላቅ ባልስልጣናት እና የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት ተመረቀ።

    በአጠቃላይ 40 ሺህ ካሬ ሜትር ላይ ያረፈው ስካይላይት ሆቴል (መደበኛ ስሙ፦ የኢትዮጵያ ስካይላይት ሆቴል/ Ethiopian Skylight Hotel) ለሦስት ዓመታት ያህል የግንባታው ሥራ አቭዬሽን ኢንዱስትሪ ኮርፖሬሽን ኦፍ ቻይና (Aviation Industry Corporation of China) በተባለ ድርጅት ሲከናወን የቆየ ሲሆን፥ ሙሉ ለሙሉ አገልግሎት መስጠት ሲጀምር የባለ 5 ኮከብ ደረጃን ያገኛል ተብሎ ይጠበቃል።

    ሆቴሉ በመላው ዓለም የሚገኙ በኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ አዲስ አበባ የሚመጡና በአዲስ አበባ የሚያልፉ ትራንዚተሮችን ከማስተናገድ ረገድ ትልቁን ድርሻ እንደሚወጣ ተገልጿል።

    Ethiopian Skylight Hotel – A new entrant to Ethiopia’s ever-growing hotel and hospitality industry

    ስካይላይት ሆቴል ከመደበኛ የመኝታ ክፍሎች እስከ ፕሬዝዳንታዊ ክፍሎች (presidential suites) የሚደርሱ በአጠቃላይ 373 የማረፊያ ክፍሎች፣ አራት ደረጃቸውን የጠበቁ ምግብ ቤቶች ሬስቶራንቶች (የኢትዮጵያ ባህላዊ ምግብ ቤት፣ የቻይና ሬስቶራንት፣ ዓለምአቀፍ ሬስቶራንት፣ ወዘተ)፣ ደረጃውን የጠበቀየመዋኛ ገንዳ፣ 2000 ሰዎችን ማስተናገድ የሚችል ለስብሰባ ወይም ለተመሳሳይ አገልግሎቶች የሚውል የመሰብሰቢያ አዳራሽ፣ ሌሎች አነስተኛ የውይይት አዳራሾች እና ሌሎችም ዘርፈ-ብዙ የሆቴል አገልግሎቶችን ያሟላ ነው። ሆቴሉ ሀገሪቱ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ትኩረት ሰጥታ እየሠራችበት ያለውን የቱሪዝም ኢንዱስትሪን ይበልጥ እንደሚያግዝም ታምኖበታል።

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ እኤአ በ2025 በዓለምአቀፍ ደረጃ እጅግ ተወዳዳሪ አየር መንገድ ለማድረግ የሚያደርገውን ጥረት ለማሳካት መሰል የሆቴል ግንባታዎች ሚናቸው ከፍተኛ መሆኑን በአየር መንገዱ የመሠረተ ልማት ክፍል ኃላፊ አቶ አብርሃም ተስፋዬ ለዋልታ ሚዲያ ተናግረዋል።

    ጥር 19 ተመርቆ ወደ ሥራ የሚገባው የቱሪዝም ኮንፌረንሱን በማገዝም የጎላ አስተዋፅዖ አለው ተብሏል። ስካይላይት ሆቴልን መቀመጫነቱን ቻይና ውስጥ ሸንዘን ከተማ (Shenzhen) ያደረገው ግራንድ ስካይላይት ሆቴል ማኔጅመንት (Grand Skylight Hotel Management) የተባለ የሆቴልና ሆስፒታሊቲ ድርጅት እንደሚያስተዳድረው ተጠቁሟል።

    ከዚህ ጋር በተያያዘ በዚሁ ዕለት (ጥር 19) አየር መንገዱ የአዲስ አበባ ቦሌ አለም አቀፍ ኤርፖርት ላይ ሲያስገነባ የነበረው የማስፋፊያ ፕሮጀችትን እንደሚያስመረቅም አስታውቋል። እ.ኤ.አ. በ2018 መገባደጃ ላይ የዱባይ ኤርፖርትን በመብለጥ ወደ አፍሪካ ያለውን ከፍተኛ የመንገደኞች ፍሰት ያስተናገደው የአዲስ አበባ ቦሌ አለም አቀፍ አሁን የሚመረቀው ማስፋፊያ ሲታከልበት ለኢትዮጵያ ብሎም ለአፍሪካ አዲስ ምዕራፍ እንደሚከፍት እምነት ተጥሎበታል። አዲሱ ማስፋፊያ በ74,000 ስኩዌር ካሬ ሜትር ላይ ያረፈ ሲሆን አሁን ኤርፖርቱ ማስተናገድ የሚችለውን የመንገደኛ ብዛት ከ8.5 ሚሊዮን ወደ 22 ሚሊዮን ከፍ ያደርገዋል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ስካይላይት ሆቴል


    Semonegna
    Keymaster

    ዓባይ ኢንዱስትሪያል የልማት አክስዮን ማኅበር ደጀን ከተማ ውስጥ (አማራ ክልል) የሚያስገነባው ሲሚንቶ ፋብሪካ አጠቃላይ ወጪው 8.8 ቢልዮን ብር እንደሆነና ግንባታው በ24 ወራት ውስጥ እንደሚጠናቀቅ ተጠቁሟል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– ዓባይ ኢንዱስትሪያል የልማት አክስዮን ማኅበር በአማራ ክልል ደጀን ከተማ ላይ ሲሚንቶ ፋብሪካ ለመገንባት ከሁለት የውጭ ሀገር ድርጅቶች ጋር የሦስትዮሽ የሥራ ስምምነት ተፈራረመ።

    አክስዮን ማኅበሩ አክስዮን ማኅበሩ ስምምነቱን የተፈራረመው መቀመጫውን ኮፐንሃገን ከተማ (ዴንማር) ያደረገውና ዓለምአቀፍ የምህንድስና (ግሎባል ኢንጂነሪንግ) ኩባንያ ከሆነው “FLSmidth & Co. A/S” እና መቀመጫውን ያንግጆ ከተማ፣ ቻይና (Yangzhou, China) ያደረገው ሌላው ዓለምአቀፍ የምህንድስና ኩባንያ “Hengyuan Group” ጋር አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ሸራተን አዲስ ሆቴል ውስጥ ነው ነው። በስምምነቱ መሠረት “FLSmidth & Co. A/S” የግንባታ መሣሪያዎችን ሲያቀርብ፣ “Hengyuan Group” ደግሞ የግንባታውን ሥራ ያከናውናል። የፋብሪካው ግንባታ አጠቃላይ ወጪውም 8.8 ቢልዮን ብር እንደሆነና ግንባታው በ24 ወራት ውስጥ እንደሚጠናቀቅ ተጠቁሟል።

    ቪድዮ፦ በ8.8 ቢልዮን ብር በደጀን ከተማ (አማራ ክልል) የሲሚንቶ ፋብሪካ ሊገነባ ነው።

    የዓባይ ኢንዱስትሪያል የልማት አክስዮን ማኅበር ለሚገነባው ፋብሪካ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች መጠናቀቃቸውንም የአክስዮን ማኅበሩ የቦርድ ሰብሳቢ አቶ መላኩ አለበል ጠቁመዋል።

    በስምምነቱ ወቅት የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ፕሬዝደንት አቶ ገዱ አንዳርጋቸው፦ “ይሄ ፕሮጀክት ተጠናቆ ለክልሉ ልማት ትልቅ አጋዥ ይሆናል የሚል እምነት አለን፤ ስለዚህ ገንቢዎቹም፣ አቅራቢዎቹም፣ ሁላችሁም ደጀን ላይ ይህንን ሲሚንቶ ፋብሪካ ለማፋጠን በምታደርጉት ጥረት የአማራ ክልል ሕዝብና መንግስት ሁልጊዜም ቢሆን ከጎናችሁ ይሆናል” በማለት የክልሉን መንግስት ደጋፍ አረጋግጠዋል።

    የኢፌዴሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንንም በበኩላቸው የመሠረት ድንጋይ ማስቀመጥ ብቻ ትርጉም እንደሌለውና፣ ይልቁንም በፍጥነት ተገንብተው ወደማምረት ሥራና ለኅብረተሰቡ የሥራ ዕድል ፈጠራ መግባት እንዳለባቸው አሳስበዋል።

    የሲሚንቶ ፋብሪካው ወደ ሥራ ሲገባ በቀን 5 ሺህ ቶን ክሊንከር እና በዓመት 2.25 ሚሊዮን ቶን ሲሚንቶ እንዲያመርት፣ ለዚህም 655 ሰዎችን በቋሚነት የሚቀጥር ሲሆን፥ ፋብሪካው በሙሉ አቅሙ ሥራ ሲጀምር ደግሞ የሠራተኞቹን ቁጥር ወደ 1,500 ለማሳደግ ታቅዶ እንደሚገነባ ማብራሪያ ተሰጥቷል።

    ዓባይ ኢንዱስትሪያል የልማት አክስዮን ማኅበር በህዝብና በግል ባለሀብቶች ባለቤትነት በአክስዮን የተቋቋመ የንግድ ድርጅት ነው። ዋና መሥሪያ ቤቱም የአማራ ክልላዊ መንግስት ዋና ከተማ በሆነችው ባሕር ዳር ከተማ ውስጥ ነው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ተመሳሳይ ዜናዎች፦

    ዓባይ ኢንዱስትሪያል የልማት አክስዮን ማኅበር


    Anonymous
    Inactive

    አቶ በረከት አቶ ታደሰ ባሕርዳር ይዳኛሉ
    የቀድሞዉ የኢትዮጵያ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ኢሕድን)ና የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) መሥራቾች አቶ በረከት ስሞዖንና አቶ ታደሰ ካሳ የታሰሩትም፣የሚዳኙትም አማራ ክልል እንደሆነ የክክሉ ባለሥልጣን አስታወቀ።የአማራ መስተዳድር የሥነ-ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ኃላፊ አቶ ዝግአለ ገበየሁ ለጋዜጠኞች እንደነገሩት ሁለቱ ከፍተኛ ባለሥልጣናት የታሰሩት ጥረት የተሰኘዉን የኩባንዮች ስብስብ በማክሰራቸዉ ነዉ።ድሮ ኢሕዴን፣ በመሐሉ ብአዴን፣ በቅርብ ደግሞ አዴፓ በሚሉ ምሕፃረ-ቃላት የሚጠራዉ የአማራ ክልክል ገዢ ፓርቲ የመሠረተዉና የሚቆጣጠረዉ ድርጅት የአስራ-ሠባት አምራችን ነጋዴ ኩባንዮች ባለቤት ነዉ።

    አውዲዮውን ያዳምጡ።
    Deutsche Welle

    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – አቶ በረከት ስምኦን እና አቶ ታደሰ ካሳ (ጥንቅሹ) የአማራ ክልል የልማትና ኢንቨስትመንት ድርጅት በሆነው ጥረት ኮርፖሬት ላይ ከደረሰ የሀብት ብክነት ወንጀል ጋር በተያያዘ ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የአማራ ክልላዊ መንግስት ፀረ ሙስና ኮሚሽን አስታወቀ።

    የአማራ ክልል ፀረ ሙስና ኮሚሽኑ ኮሚሽነር አቶ ዝግአለ ገበየሁ አቶ በረከት ስምኦን እና አቶ ታደሰ ካሳ (“ተጠርጣሪዎች”) በቁጥጥር ስር ውለው ወደ ባህር ዳር መወሰዳቸውን ለመገናኛ ብዙኃንና ለጋዜጠኞች አስታውቀዋል። እንደ አቶ ዝግአለ ገለጻ፥ ሁለቱ ተጠርጣሪዎች ከፍተኛ በሆነ የሀብት ብክነት ምክንያት ጥረት ኮርፖሬትን ለኪሳራ ዳርገዋል፤ ይህም በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ምክንያት እንደሆነና የተጠረጠሩበት ወንጀል የተፈፀመው በክልሉ በመሆኑ ጉዳያቸው በክልሉ ፍርድ ቤት የሚታይ ይሆናል።

    የክልሉ ፀረ ሙስና ኮሚሽን በእስካሁኑ የመረጃና ማስረጃ ማሰባሰብ ሂደት በሁለቱ ግለሰቦች ላይ ተገቢውን ክስ ለመመሥረት የሚያስችለውን በቂ መረጃ/ማስረጃ መሰበሰቡንም አስታውቋል።

    አባይ የህትመትና የወረቀት ፓኬጂን ፋብሪካ ባህር ዳር ከተማ ውስጥ ሥራ ጀመረ

    አቶ በረከት ስምኦን እና አቶ ታደሰ ካሳ (ጥንቅሹ) የቀድሞዉ የኢትዮጵያ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ኢሕድን)እና የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) መሥራቾች ከመሆናቸው በተጨማሪ በፌደራልና በክልል መንግስታዊ ቦታውች ለረዥም ጊዜ ሲያገለግሉ ቆይተዋል። በጥረት ኮርፖሬት ውስጥ ደግሞ አቶ ታደሰ ካሳ በዋና ሥራ አስፈፃሚነት አቶ በረከት ስምኦን ደግሞ በቦርድ ሰብሳቢነት ለበርካታ ዓመታት መሥራታቸው ተጠቁሟል።

    አቶ በረከት ስምኦን እና አቶ ታደሰ ካሳን በቁጥጥር ስር ለመዋል ያበቃቸውና ጥረት ኮርፖሬት ላይ የተፈጸመው የሀብት ብክነት ምንድን ነው?

    የጥረት ኮርፖሬት የሀብት፣ እንዲሁም በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ የገንዘብ ብክነት ተፈጽሞብኛል ያላቸው ዝርዝሮች፦

    • የኮርፖሬቱ ንብረት የሆኑ አምስት ኩባንያዎች ከ ክስዮን መሸጥ/ግዢ ጋር በተያያዘ ለሀብት ብክነት የዳረገ ብልሹ አሠራር በኦዲት ተደርሶበታል፤
    • ሌሎች ሁለት እህት ኩባንያዎች ላይ ተመሳሳይ የኦዲት ሥራ እየተሠራ ነው፤
    • ተጠርጣሪዎቹ በኮርፖሬቱ ውስጥ በስልጣን ላይ እያሉ የተመሠረቱ ስድስት እህት ኩባንያዎች፥ ከመመሥረታቸው በፊት አስፈላጊውን የአዋጭነት ጥናት ሳይደረግ ለእነዚህ ኩባንያዎች መመሠረቻ/ ግዢ ወደ ሚሊዮን ብር ወጪ ወጥቷል፤
    • እነዚህ ስድስት እህት ኩባንያዎች ከተመሠረቱ/ ከተገዙ በኋላ በጊዜው ወደሥራ ባለመግባታቸው ኮርፖሬቱን ለተጨማሪ ወጪ/ ኪሳራ ዳርገውታል፤
    • ጥረት ኮርፖሬሽን በአጋርነት ከሚሠራቸው ኩባንያዎች ጋርም ከኮርፖሬቱ የፋይናንስ አሠራርና ሕግ ውጪ 7 ሚሊየን ብር ለሁለት ኩባንያዎች ተሰጥቷል፤
    • በሦስት ግለሰቦች ለሚተዳደር አንድ የማዕድን ኩባንያ ላወጣው የእያንዳንዱ አክሲዮን ዋጋ 1,000 ብር ሲሆን፥ ጥረት ኮርፖሬት በአንጻሩ የእያንዳንዱን አክሲዮን ዋጋ በ2,200 ብር እንዲገዛ ተደርጓል። በዚህም ሦስቱ ባለሀብቶች የ4 ሚሊየን 320 ሺህ ብር ተጠቃሚ ያደረገ ሲሆኑ፥ ጥረት ኮርፖሬት ግን ለኪሳራ ተዳርጓል፤
    • ባለሙያን ያላካተተ የአክስዮን መግዛትና መሸጥ ሥራ በኮርፖሬቱ ውስጥ ይተገበር ነበር፤ ይህም ለሀብት ብክነት ተጨማሪ ምክንያት ሆኗል፤
    • ለካፒታል ዕድገት ለሀገር ውስጥ ገቢ መክፈል የነበረበትን 1 ሚሊዮን 296 ሺህ ብር ባለመክፈሉ ጥረት ኮርፖሬት ባለዕዳ አድርጎታል፤
    • ለፋብሪካ ይገነባል በሚል የ17 ሚሊየን ብር ግብዓት ተገዝቶ እስካሁን ምንም ዓይነት ሥራላ በለመዋሉ ኮርፖሬቱን ለሌላ የሀብት ብክነት ዳርጎታል።

    በስተመጨረሻም አቶ ዝግአለ እንዳስታወቁት የአቶ በረከት ስምኦን እና የአቶ ታደሰ ካሳ በቁጥጥር ስር መዋል መጀመሪያ እንደሆነና፥ ሌሎችም በእንዲህ ዓይነት ወንጀል የተጠረጠሩ ሰዎች በቁጥጥር ስር ይውላሉ።

    ቀድሞ የኢትዮጵያ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ኢሕዴን)፣ በመሀል ብሔረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ብአዴን)፣ አሁን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (አዴፓ) የተባለው የአማራ ሕዝብ ፓርቲ ያቋቋመው ጥረት ኮርፖሬት በአምራችነት ዘርፍ፣ በአገልግሎት መሰጠት ዘርፍ፣ በኮንስትራክሽን ዘርፍ እና በ አግሮ ፕሮሰሲንግ ዘርፍ ላይ የተሰማሩ የአስራ ዘጠኝ ኩባንያዎች ባለቤት መሆኑን የኮርፖሬቱ ድረ ገጽ ያሳያል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    አቶ በረከት ስምኦን እና አቶ ታደሰ ካሳ


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ከፍተኛ ኃይል የሚጠቀሙ ደንበኞቹ የኤሌክትሪክ ፍጆታ ሂሳባቸው በባንክ እንዲከፍሉ የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር ጥር 13 ቀን 2011 ዓ.ም. ተፈራርሟል።

    ስምምነቱን የተፈፀመው በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ሽፈራው ተሊላ እና በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የባንክ አገልግሎት ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ደረጄ ፉፋ አማካኝነት ነው።

    ኢትዮ ቴሌኮም እና የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በኤሌክትሪክ ኃይል መስመር ተሸካሚ ላይ የተዘረጋውን ገመድ በጋራ ለመጠቀም ተስማሙ

    የመግባቢያ ስምምነቱ ዋና ዓላማ በመጀመሪያው ምእራፍ 27 ሺህ የሚሆኑ ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ኃይል የሚጠቀሙ እንዲሁም መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ደንበኞች የኤሌክትሪክ ፍጆታ ሂሳባቸውን በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በኩል እንዲከፍሉ ለማስቻል እና በቀጣይም በአፈጻጸም ሂደቱ የተገኙ ተሞክሮዎችን በማካተት በመላ ሀገሪቱ ያሉ ደንበኞች ላይም ተግባራዊ የሚደረግ መሆኑን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ሽፈራው ተሊላ በሥነ ሥርዓቱ ላይ ባደረጉት ንግግር አስታውቀዋል።

    ተቋሙ ቀድሞ ይጠቀምበት የነበርውን የፍጆታ ሂሳብ አሰባሰብ ስርዓት በመቀየር፣ ቀልጣፋና በዘመናዊ ቴክኖሎጅ የታገዘ አገልግሎት ለደንበኞቹ ለመስጠት እንደሚስያችለው አክለው ገልፀዋል። ይህም በመሆኑ ተቋሙ፣ ባንኩና ደንበኞች የፍጆታ ሂሳብ ለመክፍል ይፈጠር የነበረውን የገንዘብና የጉልበት ብክነት በከፍተኛ ደረጃ ስለሚቀንሰው፤ ሦስቱም አካላት ተጠቃሚ ይሆናሉ ሲሉ ነው ዋና ሥራ አስፈፃሚው የተናገሩት።

    አዳዲስ የቴክኖሎጂ ዕውቀቶችና ልምዶች የተገኙበትና በምስራቅ አፍሪካ በርዝመት ቀዳሚውን ስፍራ የያዘው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዋና መሥሪያ ቤት ህንጻ

    የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የባንክ አገልግሎት ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ደረጄ ፉፋ በበኩላቸው፥ ዘመናዊ የክፍያ ስርዓት መዘርጋቱ ደንበኞች ሳይጉላሉ ካሉበት ስፍራ ሆነው ክፍያ በባንኩ አማካኝነት በቀላሉ ለመክፍል እንደሚያስችላቸው ገልፀዋል። ሲያጋጥሙ የነበሩ የአከፋፈል ስርዓት ችግሮችን እንዲቀርፍ ያስችላል፤ ደንበኞችም ያጠፉት የነበረውን ጊዜና የሚያጋጥማቸው ውጣ ውረድ ይቀንስላቸዋል ሲሉ ነው አክለው የተናገሩት።

    በስምምነቱ መሠረት እነዚህ ደንበኞች በቂ ግንዛቤ በተለያዩ አማራጮች ካገኙ በኋላ በያዝነው ዓመት ከሚያዝያ ወር ጀምሮ ተግባራዊ እንደሚደረግ እንዲሁም የዚህን ጅምር ሥራ ውጤታማነት ከታየ በኋላ ሁሉም ደንበኞች በተመሳሳይ መልኩ ክፍያ እንዲፈፅሙ በቀጣይ አንደሚደረግ ተገልጿል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት


    Semonegna
    Keymaster

    አዳማ (ሰሞነኛ)– አዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ እየተስተጓገለ ያለውን የትምህርት ክፍለ ጊዜ ለማስተካከል ለጊዜው የመማር ማስተማሩ ሂደት ተቋርጦ ተማሪዎች ወደ የቤተሰቦቻቸው እንዲመለሱ መወሰኑን አስታወቀ።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ለሚ ጉታ (ዶ/ር) ጥር 13 ቀን 2011 ዓ.ም. ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) እንደገለጹት ተማሪዎች ትምህርታቸውን ካቋረጡ 31 ቀናት ሆናቸዋል።

    ይህንኑ ቀናት ሁሉ ባክኖ የመጀመሪያውን መንፈቀ ዓመት የመማር-ማስተማር ዕቅዱን ማሳካት ስለማይቻል እንደ አዲስ ትምህርቱን የካቲት 25 ቀን እንዲጀመር በሴኔቱ ተወስኗል።

    የባከነውን የትምህርት ክፍለጊዜ እንደ አዲስ አስተካክሎ ለመጀመርና ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሂደት ለማረጋገጥ ለጊዜው ተማሪዎች ወደ ቤተሰቦቻቸው እንዲመለሱ መወሰኑን ፕሬዚዳንቱ አስታውቀዋል። ተማሪዎቹ ከአንድ ወር በላይ ትምህርታቸውን ያቋረጡት አዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የገባልን ቃል አልፈፀመም በሚል ሰበብ እንደነበር አስታውሰዋል።

    የተማሪዎቹ ጥያቄ የሁለተኛና ሦስተኛ ዲግሪ የትምህርት ዕድል እንደሚመቻችላቸው እንዲሁም የሥራ ዕድል ትስስር ከኢንዱስትሪዎች ጋር እንደሚፈጠርላቸው ቃል ተገብቶልን ነበር የሚል ነው። በተጨማሪም ላፕቶፕ ኮምፒዩተር እንደሚሰጣቸው የዩኒቨርስቲው ፕሬዝዳንት የነበሩት የውጭ ዜጋ ቃል ገብቶልናል የሚል ጥያቄ እንደሚያነሱም ዶክተር ለሚ አመልክተዋል።

    ሰላሌ ዩኒቨርሲቲ አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት ካጠናቀቀ በኋላ ተማሪዎችን መቀበሉ አስታወቀ

    መንግስት ሁኔታዎችን አይቶና ገምግሞ የሀገሪቷን አቅም መሠረት ያደረገ መፍትሔ እንደሚፈልግ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሚኒስቴር የሥራ ኃላፊዎች፣ የቦርድና የዩኒቨርስቲው አመራሮች ባሉበት በተካሄደው ውይይት ቢገልፅም ተማሪዎቹ ለመቀበል ሳይፈልጉ ቀርተዋል።

    በዚህም ምክንያት ከአንድ ወር በላይ የመማር-ማስተማር ሂደቱን በማስተጓጎል አንዳንድ ተማሪዎች ከግቢ ወጥተው ለተለያዩ ሱሶችና አልባሌ ተግባራት እየተጋለጡ መሆኑን ጠቁመዋል።

    “በተቋሙ ውስጥ የምግብ፣ የመኝታና ተጓዳኝ አገልግሎት እያገኙና የሀገር ሀብት እየባከነ እንደፈለጉ መሆን ስለማይቻል ለጊዜው የመማር-ማስተማር ሂደት በማቋርጥ ተማሪዎች ወደየቤተሰቦቻቸው እንዲመለሱ ወስነናል” ብለዋል።

    አዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ከጥር 12 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ ተማሪዎች ቅጥር ጊቢውን ለቀው እንዲወጡና ወደየቤተሰቦቻቸው እንዲመለሱ ማድረጉን ጠቅሰው የተማሪ ወላጆች ልጆቻቸው ከነሱ የተለዩበትን ዓላማ ብቻ ከዳር እንዲያደርሱ የማድረግና የመምከር ቤተሰባዊ ኃላፊነት መወጣት እንደሚጠበቅባቸውም አሳስበዋል።

    በሴኔቱ ውሳኔ ተማሪዎቹ ወደ ዩኒቨርሲቲው የሚመለሱትና በአዲስ መልክ ተመዝግበው ትምህርታቸውን የሚጀምሩበት የካቲት 25 እና 26 ቀን 2011 ዓ.ም. እንደሆነ ያስታወሱት ዶ/ር ለሚ “ነገር ግን የባከነውን የትምህርት ክፍለጊዜ ለማካካስ በማሰብ አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ መልሰን ለመጥራት ርብርብ እያደረግን እንገኛለን” ብለዋል።

    ዩኒቨርሲቲው እየተስተጓጓለ ያለውን የመማር-ማስተማር ሂደት ለማስተካከል የወሰደው እርምጃ አግባብ መሆኑን የገለጸው ደግሞ በዩኒቨርሲቲው የኤሌክትሮንክስና ኮሙዩኒኬሽን ትምህርት ክፍል የአምስተኛ ዓመት ተማሪና የተማሪዎች ተወካይ ፍፁም ቱጁባ ነው።

    በ2007 ዓ.ም. በወቅቱ ተቋሙ ሲመሩ በነበረው የውጭ ዜጋ በአፍ ደረጃ የላፕቶፕ ኮምፒዩተሮችን ጨምሮ የሁለተኛና ሦስተኛ ዲግሪ እንደሚሰጣቸው የተገባውን ቃል አሁን ካልተፈፀመልን አንማርም ብሎ ትምህርት ማቋረጥ ትክክል እንዳልሆነ ጠቅሷል። አሁን ላይ ተማሪዎች ወደ ቤተሰቦቻቸው ተመልሰው ራሳቸውን እንዲያዩና እንዲፈትሹ የሚያደርግ የእርምት እርምጃ በመሆኑ እንደሚደግፈው ተናግሯል። “በተቋሙ ሰላማዊ የመማር-ማስተማር ሂደት እንዲረጋገጥ የተማሪ ቤተሰቦች ጭምር የድርሻቸውን መወጣት አለባቸው” ብሏል። ተማሪዎችም ቢሆኑ ከፖለቲካ ግፊትና አስተሳሰብ ወጥተው የመማር ግዴታቸውን እየተወጡ የወጡለትን ዓላማ ሳይጎዱ መብታቸውን መጠየቅ እንደሚገባቸውም ተማሪ ፍፁም መልዕክቱን አስተላልፏል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ 

    አዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– አዲስ አበባን ከኤርትራዋ ምጽዋ ጋር ለሚያገናኘው የባቡር መስመር ፕሮጀክት ጥናት ወጪ ለመሸፈን የጣሊያን መንግስት መስማማቱን ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ገለጹ።

    በጣሊያን ጉብኝት እያደረጉ ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከጣሊያን አቻቸው ጁሴፔ ኮንቴ ጋር ተወያይተዋል። መሪዎቹ ከውይይቱ በኋላ በጋራ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ በዚሁ ጊዜ እንደገለጹት ጣልያን አዲስ አበባን ከምፅዋ ለሚያገናኘው የባቡር መስመር ፕሮጀክት የመጀመሪያ ጥናት ወጪ ለመሸፈን ተስማምታለች።

    ከጥናቱም በኋላ በሚገኘው ውጤት በጋራ ለመሥራት ፍላጎት እንዳላት ጁሴፔ ኮንቴ እንደገለጹላቸውና ለዚህም የኢትዮጵያ መንግስት ምስጋናውን እንደሚያቀርብ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ተናግረዋል።

    አዲስ አበባ እንደ ስሟ እንድትሆንና ነዋሪዎች ወጥተው ሲገቡ የሚዝናኑበትን ቦታ ከመፈለግ አንጻር በአዲስ አበባ በሚገኙ ኤምባሲዎች የተወሰነ ቦታቸውን ለህዝብ መዝናኛ ፓርክ እንዲያውሉ ጥያቄ ቀርቧል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ የጣልያን መንግስትም ለዚህ ቅን ምላሽ መስጠቱን ተናግረዋል።

    ◌ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ከጣሊያን አቻቸው ጁሴፔ ኮንቴ የሰጡት የጋራ መግለጫ

    የኢትዮጵያ መንግስት የብሔራዊ ቤተ መንግስቱን ግማሽ የህዝብ መዝናኛ ፓርክ ለማድረግ እየሠራ መሆኑንም ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ጠቅሰዋል። በአዲስ አበባ ለተቸገሩ ወገኖች ምግብ ለማቅረብ በሚደረገው ጥረት ጣልያን በመዲናዋ የዳቦ መጋገሪያ ፋብሪካ ለመገንባት ፍላጎት እንዳላትም አንስተዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጣልያን ቆይታቸው ከዓለም አቀፍ ድርጅቶች ጋር በልማትና በሰላም ውይይቶች እንዳደረጉና ከአቻቸው ጁሴፔ ኮንቴ ጋር ያደረጉት ሁለገብ ምክክርም የሁለትዮሽ ግንኙነቱን ለማሳደግ ፈር ቀዳጅ እንደሆነ ተናግረዋል።

    በምስራቅ አፍሪካ ሰላም፣ ልማትና አንድነት እንዲረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የጣሊያን መንግስት ድጋፍ ለማድረግ ፍላጎት እንዳለው ዶ/ር አብይ አመልክተዋል።

    በኢትዮጵያና በጣልያን መካከል የተደረገው ውይይት ፍሬያማ እንዲሆን በተለያዩ አጋጣሚዎች በሚካሄዱ የሁለትዮሽ ውይይቶች አገራቱ በሰላም፣ በልማትና በቱሪዝም ያለውን ግንኙነት ማጠናከር እንደሚገባም አንስተዋል። አገራቱ ለጋራ እድገትና ሰላም በጋራ እንሥራ ሲሉም ጥሪ አቅርበዋል።

    በአጠቃላይ ከልዑካን ቡድኑ ጋር በጣልያን የነበራቸው ቆይታ ስኬታማ እንደነበረ ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ የገለፁት። “እንደ ወንድም አገርና እንደ ጠንካራ ወዳጅ ከምናያት ከጣልያን የምንፈልገውን ነገር አግኝተናል” ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ።

    የኮምቦልቻ ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካ ምርቱን ለመጨመር እና የኤክስፖርት መጠኑን ለማሳደግ እየሠራ ነው

    የጣልያን ጠቅላይ ሚኒስትር ጄሴፔ ኮንቴ በበኩላቸው ሁለቱ አገራት ታሪካዊ የሚባል ግንኙነት እንዳላቸውና በበርካታ ጉዳዮች ዙሪያ በጋራና በትብብር ለመሥራት መግባባታቸውን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለምታከናውናቸው የልማት ሥራዎች የጣሊያን መንግስት የሚሰጠውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ቃል ገብተዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በጣልያን ጉብኝት ያደረጉት የጣሊያኑ አቻቸው ጁሴፔ ኮንቴ በ2011 ዓ.ም መጀመሪያ በኢትዮጵያ ጉብኝት ባረደጉበት ወቅት ባቀረቡላቸው ግብዣ መሠረት ነው።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጣሊያን ቆይታቸው ከአገሪቱ ፕሬዚዳንት ሰርጂዮ ማታሬላ፣ ከዓለም የምግብ ድርጅት ዋና ዳሬክተር ዴቪድ ቤዝሊ፣ ከተባበሩት መንግስታት የምግብና የእርሻ ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ሆዜ ግራዚያኖ ዳ ሲልቫና ከግብርና ልማት ዓለም አቀፍ ፈንድ ፕሬዝዳንት ጊልበርት ሆዉንግቦ ጋር ተወያይተዋል።

    በሌላ በኩል ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር የተጓዘው የልዑካን ቡድን በሮም ከጣሊያን ባለሃብቶች ጋር ውይይት አካሂዷል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር)፣ አምባሳደር ፍጹም አረጋ እንዲሁም የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽነር አበበ አበባየሁን ያካተተው የልዑካን ቡድን ለባለሃብቶቹ ሃገሪቱ ስላላት የተለያዩ የኢንቨሰትመንት ዘርፎችና አማራጮች ማብራሪያ መስጠታቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል።

    በኮምቦልቻ ኢንዱስትሪ ፓርክ ውስጥ የሚገኙ የጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካዎች ምርታቸውን ወደውጭ ሀገራት መላክ ጀምረዋል

    ካርቪኮ ግሩፕ በአሁኑ ሰዓት በኮምቦልቻ ኢንዱስትሪ ፓርክ በ23 ነጥብ 5 ሄክታር መሬት ላይ ግንባታውን እያጠናቀቀ ሲሆን፥ በጣሊያንና በቬትናም በሚገኙ ፋብሪካዎች የሠራተኛ ስልጠና በማድረግ ዝግጅቱን ለመጀመር በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል።

    በውይይቱ የተገኙት ሌሎች ባለሀብቶች በኢትዮጵያ በመድኃኒት፣ በግንባታ፣ በግብርና ማቀነባበርያ እና አልባሳት ዘርፍ በስፋት ለመሰማራት ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል ተብሏል።

    በጠቅላይ ሚኒስትሩ የተመራው የልዑካን ቡድን ከጣልያን ቆይታው በኋላ በስዊዘርላንድ ዳቮስ ከተማ በሚካሄደው የዓለም ኢኮኖሚክ ፎረም ለመሳተፍ ወደ ስፍራው ያቀናል ተብሎ ይጠበቃል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ 

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ከጣሊያን አቻቸው ጁሴፔ ኮንቴ ጋር


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– በ2006 ዓ.ም. በሰባት የየመገናኛ ብዙሃን (ሚዲያ) እና ኪነ ጥበብ ባለሙያዎች የተቋቋመው ጉዞ ዓድዋ፥ አንድ ሺሕ አስር ኪሎሜትሮችን የሚሸፍን፣ ከኢትዮጵያ ዋና ከተማ አዲስ አበባ ተነስቶ መዳረሻውን የዓድዋ ድል አምባ ተራሮች ጫፍ ላይ የሚያደርግ ረዥም የእግር ጉዞ ነው። ላለፉት ስድስት ዓመታት ከጥር ወር ጀምሮ የዓድዋ ድል በዓል እስከ ሚከበርበት የካቲት 23 ቀን ድረስ ከስድስት ሳምንታት ላላነሰ በየዓመቱ ሳይቋረጥ የቆየው ጉዞ ዓድዋ፥ ዘንድሮ የኢትዮጵያዊነቱ ስሜት እጅግ ጎልቶ በጉዞው ላይ የሚሳተፉት ቁጥርም ጨምሯል። በዘንድሮው ጊዞ ዓድዋ 44 ተጋዦች ከአዲስ አበባ እና 4 ተጓዦች ከሐረር በአጠቃላይ 48 ተጓዦች ጥር 7 ቀን 2011 ዓ.ም. ቀን ከአዲስ አበባ ተነስተዋል።

    የመላው አፍሪቃውያን ድል እስከመባል የደረሰው ታላቁ የዓድዋ ድል፥ የግዝፈቱን ያህል ክብር እና መታወሻ ሥነሥርዐት ሳይኖረው እየተከታተለ ከመጣው ትውልድ ጋር የበዓሉ አከባበር ዐውድ እየወረደ ጭራሽ እየተዘነጋ እና እየደበዘዘ መሔድ ያሳሰባቸው የጉዞ ዓድዋ መሥራቾች ትውልዱ ትኩረት ሰጥቶ የድሉን መንፈስ እንዲጋራ ለማድረግ ይህንን የጉዞ ሐሳብ አመንጭተዋል።

    ◌ የጉዞ ዓድዋ ተጓዦችና የኢትዮጵያዊያን አስተያየት

    በዚህም የተነሣ ጉዞ ዓድዋ ባለፉት ስድስት ዓመታት ብቻ ከታለመው ዓላማ አንጻር ከፍተኛ የሆነ አመርቂ ውጤት በማስመዝገብ የዓድዋ ድል በዓል ቀድሞ ከነበረበት አከባበር የላቀ ተሳትፎ ያለው የድል በዓል እንዲሆን አስተዋጽዖ ለማድረግ ተችሏል።

    ጉዞውን ከማካሔድ በተጓዳኝ በየመንገዱ ተንቀሳቃሽ የመጻሕፍት ንባብ መሰናዶ በማካሔድ በየዓመቱ የሚጓዙ አባላትን በዓድዋ ጦርነት እና ድል ዙሪያ በቂ የሆነ ግንዛቤ እና ዕውቀት የማጋራት ዝግጅቶችን ሲያካሂድ ቆይቷል። ከአንድ ወር በላይ በተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን ሰፊ ሽፋን የሚሰጠው የጉዞው የዕለት ተእለት ውሎ፣ በዓሉ ከመድረሱ አስቀድሞ በበርካታው ሕዝባችን ላይ የካቲት 23 ዕለትን በጉጉት የመጠበቅ ስሜት እንዲፈጠር አድርጓል።

    ◌ የዓድዋ ድል በዓል በጎሰኞች ዓይን የዲያቆን ዳንኤል ክብረት መጣጥፍ

    ከዚህ ቀደም የድል በዓሉ በብቸኝነት ከሚከበርባቸው የአዲስ አበባ እና የዓድዋ ከተሞች በተጨማሪ ከ28 በላይየሚሆኑ የክልል ከተሞች እና በርካታ ሕዝብ የሚኖርባቸው የገጠር ወረዳዎች ተጓዥ ቡድኑ በየደረሰበት በሚኖሩ ደማቅ አቀባበሎች ላይ በሚሰጡ የግንዛቤ መስጫ መልዕክቶች ስለ ዓድዋ ድል ታሪክ ግንዛቤ በመሰጠቱ የበዓሉአከባበር ከፍተኛ ለውጥ በማምጣት ላይ ይገኛል። የጉዞ ዓድዋ ትሩፋቶች፦

    • በዓድዋ ከተማ ውስጥ በአምስት ዓመት አንድ ጊዜ ብቻ የነበረው የዓድዋ ድል በዓል አከባበር ሥነ ሥርዐትበየዓመቱ እንዲካሔድ አስችሏል።
    • የበዓሉ አከባበር በፌደራል መንግሥት ደረጃ እንዲከበር ልዩ ትኩረት እንዲሰጠው ከፍተኛ አስተዋጽዖ አድርጓል።
    • ከ120 ዓመታት በፊት መቀሌ ከተማ በሚገኘው የእንዳየሱስን ምሽግ ለማስለቀቅ ከጣሊያን ጦር ጋር ሲዋጉ ሕይወታቸው ያለፉ ጀግና ኢትዮጵያውያን አጽም የትም ተበታትኖ በመቅረቱ፥ ጉዞ ዓድዋ በአሁኑ ሰዓት የቦታው አስተዳዳሪ የሆነውን የመቀሌ ዩኒቨርሲቲ በማንቃት፤ የካቲት 26 ቀን 2008 ዓ. ም አጽማቸውን አሰባስቦ በክብር እንዲያርፍ ተደርጓል። ከዚህም ባሻገር በዓመቱ የካቲት 26 ቀን 2009 ዓ.ም በመቀሌ ዩኒቨርሲቲ ወጪ “የጀግኖች ኢትዮጵያዊያን መታሰቢያ ሙዚየም” የተሰኘ ጣራ አልባ ቤተ መዘክር በእንዳየሱስ ታሪካዊ ምሽግ ላይ ተገንብቶ ለመመረቅ በቅቷል።
    • የዓድዋ ጦርነት መንስዔ የሆነው የዉጫሌ ውል የተፈረመበት “ይስማ ንጉሥ” የተባለው ታሪካዊ ቦታ ተከልሎ ጥበቃ እንዲደረግለት በማድረግ ጉዞ ዓድዋ ቁልፍ ሚና ተጫውቷል። ከዚህም በተጨማሪ ውሉ በተፈረመበት ዕለት ሚያዝያ 25 ቀን በየዓመቱ፤ ምሁራዊ ተዋስዖ የሚደረግባቸው መድረኮች በመፍጠር፣ ላለፉት ስድስት ዓመታት ባበረከተው የላቀ አስተጽዖ የአምባሰል ወረዳ የዓድዋ ድልን ለመዘከርና ቦታውን የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ ያለመቋሚ ቤተ መዘክር በቦታው ላይ እንዲገነባ የሚያስችል የ19 ሚልዮን ብር የበጀት ድጋፍ ከአማራ ክልል መንግሥት እንዲያገኝ ጉዞ ዓድዋ ቁልፍ ሚና ተጫውቷል።
    • ለበርካታ ዓመታት አገልግሎቱ ተዘግቶ የቆየው በዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ የትውልድ መንደር “አንጎለላ” የሚገኘው የዳግማዊ ዐፄ ምኒልክ መታሰቢያ ክሊኒክ እንዲከፈት ከፍተኛ ቅስቀሳ በማድረግ፤ በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ድጋፍ ክሊኒኩ ታዳጊ የጤና ጣቢያ ሆኖ በድጋሚ አገልግሎት እንዲሰጥ ጉዞ ዓድዋ አስተዋጽዖ ካደረጉ መካከል ግንባር ቀደሙን ሚና ተጫውቷል።
    • የዓድዋ ጀግና የሆኑት ራስ አሉላ አባ ነጋ የቀብር ቦታ በሆነው የአባ ገሪማ ገዳም ውስጥ ለሁለቱም ጾታዎች ጉብኝት ምቹ በሆነ ቦታ ላይ ሐውልት እንዲቆምላቸው ጉዞ ዓድዋ ባመቻቸው ዕድል በአንድ ባለ ሀብት ሐውልታቸው ተሠርቶ ለምረቃ በቅቷል።
    • በየዓመቱ በሚካሔዱ ጉዞዎች ከዓድዋ ድል ጋር ግንኙነት ያላቸው ቦታዋችን እና ልዩ ታሪካዊ መረጃዎችን በምስል እና በጽሑፍ በመሰብሰብ ለጥናትና ምርምር አስተዋጽዖ ማበርከት የሚችሉ የታሪክ ግብዓቶችን በማደራጀት በተለያዩ የመገናኛ ዘዴዎች በተለይም የማኅበራዊ ድረ ገጽን በመጠቀም ቅርሶችን የማስተዋወቅና የመጠበቅ ሥራዎችንበ መሥራት ላይ ይገኛል።

    የጉዞ ዓድዋ ማኅበር የዓድዋ ድል በዓል በኢትዮጵያውያን እንዲሁም በጥቁር አፍሪካውያን ዘንድ የሚገባውን ክብር እንዲያገኝ ላደረገው ጥረት፣ ከላይ ለተጠቀሱት እና በየዓመቱ በሚያደርጋቸው እጅግ አመርቂ ክንዋኔዎች ምክንያት በ2009 ዓም በቅርስና ባሕል ዘርፍ የዓመቱ በጎ ሰው ተሸላሚ ሆኗል።

    ላይ የሚሳተፉ ተጓዦች በጉዞአቸው ላይ የሚያደርጓቸውን የተለያዩ ክንዋኔዎችና የሚዘግቧቸውን ታሪክ ተኮር ዘገባዎች ለመከታተል የማኅበሩን የፌስቦክ ገጽ ይጎብኙ።

    ◌ ዓፄ ዘርዓ ያዕቆብ እና ዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ በደብረ ብርሃን ከተማ ሃውልት ሊቆምላቸው ነው

    ምንጭ፦ በጎ ሰው ሽልማት / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ጉዞ ዓድዋ


    Semonegna
    Keymaster

    የኢትዮጵያ ጥራት ሽልማት ድርጅት የሚያዘጋጀው ሽልማት ዓላማ በኢትዮጵያ አምራቾችና አገልግሎት ሰጪዎች እንዲሁም በግንባታ ዘርፍ የተሰማሩ ድርጅቶች ለጥራት የሚያደርጉትን ሥራ ማበረታታት መሆኑ በሽልማቱ ሥነ-ሥርዓት ወቅት ተገልጿል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ጎንደር ዩኒቨርሲቲ ለሦስተኛ ጊዜ የአገር አቀፍ የጥራት ሽልማት ልዩ ተሸላሚ ሆነ። ዩኒቨርሲቲው ያገኘውን ሽልማት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንት ደሳለኝ መንገሻ (ዶ/ር) ከፕሬዝደንት ሳህለወርቅ ዘውዴ እጅ ተቀብለዋል።

    የኢትዮጵያ ጥራት ሽልማት ድርጅት ስድስተኛ ዙር የጥራት ሽልማት ጥር 2 ቀን 2011 ዓ.ም. ምሽት በብሔራዊ ቤተ-መንግስት ተካሂዷል። በሽልማትና ዕውቅና ሥነ-ሥርዓቱ ላይ 40 ድርጅቶችና ተቋማት የምስክር ወረቀትና የዋንጫ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል። በውድድሩ ላይ

    ጎንደር ዩኒቨርሲቲ፣ ሐረር ቢራ አክሲዮን ማኅበር እና አማራ መልሶ ማቋቋምና ልማት ድርጅት የአንደኛ ደረጃ ዋንጫ ተሸላሚ ሲሆኑ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ለተከታታይ ሦስት ዓመታት የጥራት ደረጃውን ጠብቆ አሸናፊ በመሆኑ የልዩ ዋንጫ ተሸላሚ ሆኗል።

    The Ethiopian Quality Award Organization

    ከ336 በላይ ድርጅቶች እንዲመዘገቡ ጥሪ የተደረገ ቢሆንም የተመዘገቡት 52 ነበሩ። ከነዚህ ውስጥ 21 በአምራች፣ አምስት በአገልግሎት፣ አራት በከፍተኛ ትምህርት፣ አምስት በጤና እና አምስት በግንባታ ዘርፍ የተሰማሩ፤ በድምሩ 40 ተቋማት እስከመጨረሻው በውድድሩ የዘለቁ ናቸው።

    የሽልማቱ ዋና ዓላማ በኢትዮጵያ አምራቾችና አገልግሎት ሰጪዎች እንዲሁም በግንባታ ዘርፍ የተሰማሩ ድርጅቶች ለጥራት የሚያደርጉትን ሥራ ማበረታታት መሆኑ በሥነ-ሥርዓቱ ወቅት ተገልጿል።

    የኢትዮጵያ ጥራት ሽልማት ድርጅት የበላይ ጠባቂ የሆኑት የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ የጥራት ጉዳይ የሥነ-ልቦናና የፈረጠመ የኢኮኖሚ የበላይነት እንዲሁም የበለፀገ ማኅበረሰብ መገለጫዎች ናቸው ብለዋል። የምርትና አገልግሎት ጥራትን ለማስጠበቅና ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ከደረሱበት የጥራት ደረጃ ለመድረስ ጠንክሮ መሥራት እንደሚገባም አሳስበዋል።

    የኢትዮጵያ ጥራት ሽልማት ድርጅት በ2000 ዓ.ም በዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከልና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ትብብር የተቋቋመ ነው። ድርጅቱ ሲመሠረት ዓላማውን መንግስት በጥራት ረገድ የሚያደርገውን ጥረት ለመደገፍና የጥራት ጽንሰ ሀሰብን በማኅበረሰቡ፣ በአምራቾች፣ በአገልግሎት ሰጪዎችና በግንባታ (ኮንስትራክሽን) ዘርፍ በተሰማሩ ድርጅቶችና ተቋማት ዘንድ እንዲሰርጽ ለማድረግ ነው። እስካሁን 49 ድርጅቶችና ተቋማት የድርጅቱን የልዕቀት ማዕረግ የዋንጫ ሽልማት አግኝተዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    የኢትዮጵያ ጥራት ሽልማት ድርጅት


    Semonegna
    Keymaster

    የከተማዋን የቱሪዝም ዕድገት ከፍ ለማድረግ የዓፄ ዘርዓ ያዕቆብ እና ዳግማዊ ምኒልክ ሃውልቶችን የከተማ አስተዳደሩ ኅብረተሰቡን በማሳተፍ ያስገነባል። ስለሆነም የሁለቱ ታላላቅ መሪዎች ሃውልት በከተማዋ እንዲቆም እንቅስቃሴ እየተደረገ ነው።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ከ6 መቶ ዓመታት በላይ ባስቆጠረችው የድሮዋ ደብረ ኤባ የዛሬዋ ደብረ ብርሃን ከተማ ለዓፄ ዘርዓ ያዕቆብ እና ዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ ሃውልት ሊቆምላቸው እንቅስቃሴ መጀመሩን ከተማ አስተዳደሩ አስታውቋል።

    የከተማዋ ምክትል ከንቲባ እና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ብርሃን ገብረሕይወት ጥር 9 ቀን 2011 ዓ.ም. አዲስ አበባ ላይ በሰጡት መግለጫ ደብረ ብርሃን ከተማን የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ የከተማ አስተዳደሩ እየሠራ ነው፤ ከተማዋን የኮንፈረንስ ቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግም ከተማ አስተዳደሩ ባዛሮችን በተለያዩ ጊዚያት እንደሚያካሂድ ተገልጿል።

    የከተማዋን የቱሪዝም ዕድገት ከፍ ለማድረግ የዓፄ ዘርዓ ያዕቆብ እና ዳግማዊ ምኒልክ ሃውልቶችን የከተማ አስተዳደሩ ኅብረተሰቡን በማሳተፍ ያስገነባል። ስለሆነም የሁለቱ ታላላቅ መሪዎች ሃውልት በከተማዋ እንዲቆም እንቅስቃሴ እየተደረገ ነውም ተብሏል።

    ደብረ ብርሃን ኢንዱስትሪ ፓርክ በከተማዋ ለሚኖሩ ዜጎች የተለያዩ የሥራ ዕድሎችን ፈጥሯል

    ከተማ አስተዳደሩ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ እየሠራ እንደሆነም አስታውቋል። ደብረ ብርሃን ከተማ በዓፄ ዘርዓ ያዕቆብ መመሥረቷ ይታወቃል።

    አጼ ዘርአ ያዕቆብ

    አጼ ዘርአ ያዕቆብ በዘውድ ስማቸው ቆስጠንጥንዮስ ከአባታቸው ቀዳማዊ ዳዊት እና ከእናታቸው ንግስትክብረ እግዚ እ.ኤ.አ. በ1399 ከአዋሽ ወንዝ አጠቀብ ትገኝ በነበረው ትልቅ ተብላ በምትጠራው መንደር የድሮው ፈታጃር ክፍለ ሀገር ተወለዱ። የነገሡበትም ዘመን እ.ኤ.አ. ከ 1434 እስከ 1468 (እስከሞቱበት ጊዜ) ነበር። ያረፉትም በደጋ ደሴት፣ ጣና ሃይቅ ነው።

    ዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ

    ዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ ከአባታችው ከሸዋው ንጉሥ ኃይለ መለኮት ሣህለ ሥላሴና ከእናታቸው ወይዘሮ እጅጋየሁ ለማ አድያም እ.ኤ.አ. ነሐሴ 17 ቀን 1844 ደብረ ብርሃን አካባቢ አንጎለላ ከሚባል ሥፍራ ተወልደው፤ በአንጎለላ መቅደላ ኪዳነ ምኅረት ቤተ ክርስቲያን ክርስትና ተነሱ። የነገሡበትም ዘመን እ.ኤ.አ. ከ 1889 እስከ 1913 (እስከሞቱበት ጊዜ) ነበር። ያረፉትም ተዓካ ነገሥት ለማርያም ወደብረ መንክራት ስዕል ቤት ኪዳነ ምኅረት ገዳም (አዲስ አበባ) ነው።

    ምንጭ፦ የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    ዓፄ ዘርዓ ያዕቆብ እና ዳግማዊ ዓፄ ምኒልክ ሃውልት


    Semonegna
    Keymaster

    የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጅክቶቹ በገንዘብ ሚኒስቴር የ100 ቀናት ዕቅድ ውስጥ የተካተቱ ሲሆን ፕሮጀክቶቹ ሲጠናቀቁ 798 ኪሎ ዋት የማመንጭት አቅም አላቸው። የፕሮጀክቶቹ ወጪ 795 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር እንደሚገመት በጥናቱ ላይ ተመላክቷል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – በኢትዮጵያ መንግስትና በግል ድርጅቶች (ኢንቨስተሮች) አጋርነት የሚሠሩ የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶች የኢፌዴሪ የገንዘብ ሚኒስቴር ይፋ አድርጓል።

    ጥር 9 ቀን 2011 ዓ.ም. በገንዘብ ሚኒስቴር በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ እንደተገለፀው ስድስቱ የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶች በአፋር፣ በሶማሌ፣ በኦሮሚያ እና በትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስታት ስር ይተገበራሉ ተብሏል።

    ስድስቱ የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጅክቶች በገንዘብ ሚኒስቴር የ100 ቀናት ዕቅድ ውስጥ የተካተቱ ሲሆን ፕሮጀክቶቹ ሲጠናቀቁ 798 ኪሎ ዋት የማመንጭት አቅም አላቸው። የፕሮጀክቶቹ ወጪ 795 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር እንደሚገመት በጥናቱ ላይ ተመላክቷል።

    የኮምቦልቻ ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ የውጪ ንግዱን ለማሳደግ እና የምርት መጠኑን ለመጨመር እየሠራ መሆኑን አስታወቀ

    የገንዘብ ሚኒስቴር ዴኤታ ተሾመ ታፈሰ (ዶ/ር) አገሪቱ መካከለኛ ገቢ ካላቸው አገሮች ተርታ ለመሰለፍ ያስቀመጠችውን ራዕይ ለማሳካት ከዚህም ጋር ተያይዞ በየጊዜው ሳያቋርጥ እያደገ የመጣውን የህዝብ የኃይል አገልግልት ፍላጎት ለማሟላት ከመንግስት የፋይናንስ ምንጮች በተጨማሪ ሌሎች አማራጮችን ማየት አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል ሲሉ ገልጸዋል።

    የመንግስትና የግል አጋርነት (መግአ) የመሠረተ-ልማት አቅርቦትን ለማሻሻል እንደ አንድ ስልት የሚወሰድ ነው ያሉት ዶ/ር ተሾመ በአግባቡ ሥራ ላይ ከዋለ የግሉን ዘርፍ የኢንቨስትመንት አቅም እንደ አስፈላጊነቱ ለመጠቀም እድል ይሳጣል ሲሉ ተናግረዋል።

    ምንጭ፦ የገንዘብ ሚኒስቴር/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጅክቶች


Viewing 15 results - 586 through 600 (of 730 total)