Search Results for 'ከኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት'

Home Forums Search Search Results for 'ከኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት'

Viewing 11 results - 16 through 26 (of 26 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    እ.ኤ.አ ከ2019 እስከ 2023 ለሚተገበረው አገራዊ የጤና ደህንነት የትግበራ ዕቅድ 10 ቢሊዮን ብር የሚያስፈልግ ሲሆን፥ ወጪው ከኢትዮጵያ መንግሥት፣ ከልማት አጋሮችና ባለድርሻ አካላት እንደሚሰባሰብ ለማወቅ ተችሏል።

    አዲስ አበባ (ኢዜአ) – በኢትዮጵያ ለሚቀጥሉት አምስት ዓመታት ተግባራዊ የሚሆን አገራዊ የጤና ደህንነት የትግበራ ዕቅድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ጨምሮ ዓለም አቀፍ ድርጅቶችና የልማት አጋሮች በተገኙበት ዛሬ ይፋ ሆነ።

    በዚህ ወቅት እንደተገለጸው፥ አገሪቷ መከላከልን መሠረት ያደረገ ስልት ቀይሳ የምታደርገውን ጥረት በጉልህ ይደግፋል። በተለይም በአሁኑ ወቅት በተለያዩ አካባቢዎች በተፈጠሩ አለመረጋጋት ከቀያቸው የተፈናቀሉ ዜጎች ተላላፊ ለሆኑ በሽታዎች እንዳይጋለጡ አስቀድሞ ለመከላከል የሚያስችል ነው።

    እ.ኤ.አ ከ2019 እስከ 2023 ለሚተገበረው አገራዊ የጤና ደህንነት የትግበራ ዕቅድ 10 ቢሊዮን ብር የሚያስፈልግ ሲሆን፥ ወጪው ከኢትዮጵያ መንግሥት፣ ከልማት አጋሮችና ባለድርሻ አካላት እንደሚሰባሰብ ለማወቅ ተችሏል።

    የጤና ሚኒስትሩ ዶ/ር አሚር አማን እንደተናገሩት፥ በዕቅድ ዝግጅቱ የሚመለከታቸው መሥሪያ ቤቶች ተሳትፎ አድርገዋል።

    አገራዊ የጤና ደህንነት የትግበራ ዕቅድ ችገሮች ከመከሰታቸው በፊት አስቀድሞ በመለየት መከላከል፣ ችግሮች ሲከሰቱ ፈጣን ምላሽ መስጠት በኅብረተሰቡ ላይ በህመምና በሞት የከፋ ጉዳት ሳይደርስ ምላሽ ለመስጠት የሚያስችል ስትራቴጂ ነው።

    ◌ SEMONEGNA on Social Media: FacebookTwitterInstagramPinterest

    ባለፉት ሁለት ዓመታት የጤና ሚኒስቴር ከኢትዮጵይ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት (EPHI) ጋር በመሆን ዕቅዱን ዝግጅት ሲደረግ እንደነበረ ዶ/ር አሚር ገልጸው፥ አገሪቷ በዘርፉ ምን ክፍተት አለባት? የሚለውን በጥናት ላይ የተመሰረተ ሥራ መከናወኑን አስረድተዋል። እንደ ሚኒስትሩ ገለጻ፥ ዕቅዱ ከመዘጋጀቱ በፊት አገር አቀፍ የዳሰሳ ጥናት ተካሂዷል።

    ዶ/ር አሚር እንደሚሉት፥ በጥናቱ መሠረት ዝቅተኛ አፈጻጸም የታየበት አደጋ ሲከሰት ፈጣን ምላሽ መስጠት መሆኑ የተለየ ሲሆን ችግሩን ለመፍታት በሁለቱ ከተማ መስተዳደሮችና በዘጠኙ ክልሎች ማዕከላት ተቋቁሟል።

    ከኬሚካልና ጨረር ጋር በተያያዘ አደጋ ቢያጋጥም ምላሽ ለመስጠት በቂ ዝግጅት እንደሌለ በጥናት የተለየ ሌላው ችግር መሆኑን ጠቁመው በዚህም ላይ የማስተካከያ እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን አብራርተዋል።

    በዕቅዱ ላይ እንደ ክፍተት የተቀመጡ ችግሮችን ለመፍታት መንግሥት 25 ሚሊዮን ዶላር በመመደብ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ገልጸዋል።

    የኢትዮጵይ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ኤባ አባተ በበኩላቸው፥ አገራዊ የጤና ደህንነት የትግበራ ዕቅዱ በአገሪቷ ተላላፊ በሽታዎችና ወረርሽኝን አስቀድሞ ለመግታት ወሳኝ ሚና እንዳለው ተናግረዋል።

    ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን በዚሁ ወቅት እንደገለጹትዕ አገራዊ የጤና ደህንነት የትግበራ ዕቅዱ ወቅታዊና አስፈላጊ ነው። አደጋዎችን ቀድሞ የመከላከል፣ ብዙ ጉዳት ሳያደርሱ የመቆጣጠርና መልሶ የማገገምና እንዳይደገም የማድረግን አቅምን መገንባት እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    አገራዊ የጤና ደህንነት የትግበራ ዕቅድ


    Semonegna
    Keymaster

    የአድዋ ድል ለኢትዮጵያ ነጻነትና ኩራትን፣ በዓለም ዙሪያ በተለይ በአሜሪካዎቹ ሰፋፊ እርሻዎች ለ500 አመታት በባርነት ለተጋዙ ጥቁር ሕዝቦች ደግሞ፥ የማንነት ማረጋገጫ፣ የዘመናት ጭቆናና የስነ-ልቦና ቁስልን አውልቆ የመጣያ የተስፋ ትንሳኤ ሆኖ ነበር።

    ሰለሞን ተሰራ (ኢዜአ)

    በርሊን ከተማ ውስጥ የጀርመን ግዛት አስተዳዳሪ (ቻንስለር)በነበረው ኦቶ ቫን ቢስማርክ (Otto von Bismarck) መኖርያ ሳሎን ፌሽታ በፌሽታ ሆኗል። እለቱ እንደ አውሮጳውያን አቆጣጠር (እ.አ.አ) የካቲት 16 ቀን 1885 ሶስት ወር ሙሉ አሰልቺ ውይይት የተደረገበትና ዋና ዋናዎቹ የአውሮፓ ቅኝ ገዢዎች ተሰብስበው ”አንተ ይሄን ያዝ አንተ ያንን ያዝ” ተባብለው ከወታደራዊ ዘመቻ በፊት አፍሪካን የተቃረጡት።

    በስብሰባው ከ80 በመቶ በላይ የሚሆነውን የአፍሪካ መሬት የሃሳብ መስመር እያሰመሩ ያለከልካይ ተከፋፈሉት። ከሦስት ወራት በላይ (እ.አ.አ ከኅዳር 15 ቀን 1884 እስከ የካቲት 26 ቀን 1885) ሲካሄድ የነበረው የበርሊን ጉባዔ (Berlin Conference) መደምደሚያ የነበረው ‘የበርሊን ጉባዔ ጠቅላላ ግብአተ ሰንድ’ (በእንግሊዝኛው፥ General Act of Berlin conference) በታሪክ አጥኚዎችና ፖለቲካ ተመራማሪዎች ዘንድ በ አብዛኛው “አፍሪካን የመቀራመት ጉባዔ” (“The Division of Africa” ወይም “Scramble of Africa”) ተብሎ ይታወቃል። በጉባዔው ላይ የጀርመን፣ ኦስትሮ-ሀንጋሪ፣ ቤልጅየም፣ ዴንማርክ፣ ፈረንሳይ፣ ብሪታንያ፣ ጣልያን፣ ኔዘርላንድስና ፖርቱጋል ተወካዮች ተገኝተዋል።

    አውሮፓውያን አፍሪካን ለመቀራመት በበርሊን ስምምነት ሲያደርጉ፤ አፍሪካዊያን ደግሞ የውጭ ወራሪዎችን ለመከላከል ከዚህ አለፍ ሲልም እርስ-በርሳቸው መተነኳኮስ የጀመሩበት ጊዜ እንደነበር ታሪክ ያስረዳል። ወቅቱ በአራቱም የአህጉሪቷ አቅጣጫዎች የሚገኙ ነገስታት እና የጭፍራ አለቆች በተናጠል ከአውሮፓውያኑ ጋር በገጠሟቸው ውጊያዎች ትርጉም ያለው ስኬት ሳያገኙ፤ አፍሪካውያን በቅኝ ግዛት መውደቅ የጀመሩበት ነው።

    ይህን ተከትሎ ጣልያንም ኢትዮጵያን በቁጥጥሯ ስር ለማድረግ ብትነሳም እምቢተኛው ጥቁር ሕዝብ ማንነቱንና ክብሩን አሳልፎ ላለመስጠት በመወሰኑ ያልተመጣጠነ ውጊያ ቢገጥሙም አሳፍሮ መልሷታል። ዘመናዊ የጦር መሣሪያ የታጠቀው የጣልያን ጦር የቅኝ ግዛት ተልእኮውን እውን ለማድረግ የተመመው በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ በአግባቡ የሰለጠኑ ወታደሮችን ይዞ ነው። ነገሩ እንደታቀደው ሳይሆን ቀርቶ የጣልያን ጦር በአድዋ ድል ተነሳ። ታሪክም ይህን ጦርነት <የአድዋ ጦርነት> (The Battle of Adwa) በማለት፣ ለጥቁር ሕዝቦች ታላቅ መነቃቃትና ተስፋ የሰጠውን የጦርነቱን ድል ደግሞ <የአድዋ ድል> (The Victory of Adwa) ብሎ ሲገዝበው ይኖራል።

    የታሪክ ሊቃውንት እንደሚያስቀምጡት የአድዋ ጦርነት በአፍሪካ ምድርና ታሪክ ከተከናወኑት ጦርነቶች ከፍተኛውን የዋጋና የክብር ስፍራ ይዟል። የሰሜን አፍሪካን በስፋት ይገዛ የነበረው አኒባል የአልፕን ተራሮች ዞሮ የአውሮፓን ኃያል መንግሥት ካሸነፈ ወዲህ (Hannibal’s crossing of the Alps)፣ አንድ አውሮፓዊ ጦር በአፍሪካውያን ጦር ሲሸነፍ ለመጀመሪያ ጊዜ ነበር። ስለሆነም፣ ጦርነቱ ብዙ መልክና ብዙ ቅጽል ተሰጥቶታል።

    የአድዋ ድል ለኢትዮጵያ ነጻነትና ኩራትን፣ በዓለም ዙሪያ በተለይ በአሜሪካዎቹ ሰፋፊ እርሻዎች ለ500 አመታት በባርነት ለተጋዙ ጥቁር ሕዝቦች ደግሞ፥ የማንነት ማረጋገጫ፣ የዘመናት ጭቆናና የስነ-ልቦና ቁስልን አውልቆ የመጣያ የተስፋ ትንሳኤ ሆኖም ነበር።

    የታሪክ ተመራማሪና ደራሲውፖል ሄንዝ በጻፉት ንብረ ጊዜ፥ የኢትዮጵያ ታሪክ (Layers of Time: A History of Ethiopia, by Paul B. Henze) በተሰኘው የታሪክ ድርሳናቸው “አውሮፓውያን የፈለጉትን ገድለዋል፣ ባሪያ ፈንግለዋል፣ አካባቢን፣ ሀብትን፣ ጉልበትን መዝብረዋል፤ ምክንያቱ በግልጽ ባይታወቅም ‘ኢትዮጵያን በጦር ከማስገበር ይልቅ እንቃረጣት ብለው’ ብሪታኒያ፣ ፈረንሳይና ጣልያን የሦስትዮሽ ስምምነት (Tripartite Agreement) ተፈራርመው አጼ ምኒልክን ‘እወቁልን’ ብለው ጦማር ሰደዋል። አጼ ምኒልክም ‘ስለነገራችሁኝ አመሰግናለሁ፣ ነገር ግን እኔ በሌለሁበት የተወሰነውን አላውቅም’ በማለታቸው ጣልያን ኢትዮጵያን በወረራ ያዘች።

    ወረራውን ለመቀልበስ በአጼ ምኒልክ የሚመራው የኢትዮጵያ መንግስት ሰላማዊ ትግል ቢያደርግም የወራሪዎቹ ብልጣብልጥነት ጦርነቱን አይቀሬ አደረገው። ወደ ጦርነት ተገዶ የገባው የኢትዮጵያ የጦር ኃይል በአምባላጌ፣ በመቀሌና በአድዋ በተከታታይ ባደረገው ጦርነት የበላይነት ወስዶ የካቲት 23 ቀን 1988 ዓ.ም. ላይ በአድዋ የድል ባለቤት መሆኑ ተበሰረ። የድሉ ዜና እንደናኘ በአፍሪካ ተስፋ፣ በአውሮፓ ድንጋጤ ፈጠረ። የኢትዮጵያ ድል አውሮፓውያን በዓለም የነበራቸውን ልዕለ ኃያልነት ለመጀመሪያው ጊዜ ጥያቄ ውስጥ ከቷል። ፖል ሄንዝ ”ዛሬ ላይ ሆነን ስናየው” የኢትዮጵያ ድል የአውሮፓ ተሰሚነት የቁልቁለት ጉዞ መነሻ ነበር” ሲሉ በጽሁፍ አስፍረዋል።

    ድሉ ታላቋ ብሪታንያን ኢትዮጵያን በእኩል ዓይን ዓይታ ”የምስራቁን የደቡቡን የምእራቡን ድንበራችንን እንካለል” ብላ በፊርማ እንድታጸድቅ አስገድዷታል። ከዚህ በተጨማሪ በአውሮፓ ቅኝ ግዛት መዳፍ ስር ሲማቅቁ የነበሩትን አፍሪካውያን እና ካሪቢያን ጥቁሮች ለነፃነታቸው እንዲታገሉ ብርታት እና ምሳሌ ሆኗቸዋል። ለጥቁር አሜሪካውያን ምሁራን ከፍተኛ የመንፈስ መነቃቃት እንዲያገኙ አድርጓል።

    የአድዋ ድል (ማለትም፥ በአውሮፓውያን ዘንድ የአድዋ ጦርነት ሽንፈት) በተሸናፊ የአውሮፓ ገዢዎች ዘንድ ቁጭት ፈጥሮ ከ30 ዓመት በኋላ ፋሺዝም በጣልያን ውስጥ ስር እንዲሰድ እና መሪ የፖለቲካ ርዕዮተ ዓለም (አይዲዮሎጂ) እንዲሆን ምክንያት ሆኗል። ለኢትዮጵያ ደግሞ የተረጋጋ መንግስታዊ አስተዳደር አስገኝቷል። በዚህ የከሸፈ የቅኝ-ግዛት ዕቅድና የአውሮፓውያን ተስፋፊነት የተደሰቱ ሶሻሊስት አመለካከት ያላቸው ወገኖች በጣልያን፣ በብሪታንያና በፈረንሣይም ነበሩ።

    ዕውቁ የታሪክ ተመራማሪና የአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ ፕሮፌሰር የነበሩት ሪቻርድ ፓንክረስት እና ሌላው ኢትዮጵያዊ የታሪክ ተማራማሪ ዶ/ር አብዱልሳማድ አህመድ በጋራ በጻፉት ስለ አድዋ ድል በጻፉት መጽሐፍ (Adwa Victory Centenary Conference, 26 February – 2 March 1996) ውስጥ እንዳሰፈሩት የኢጣሊያኑ ክሪቲካ ሶሻሌ (Critica Sociale) ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ፊሊፖ ቱራቲ (Filippo Turati) በወኔና በምልዓት ለእውነት ስለእውነት ጻፈ። “ጣልያን ወደ አድዋና ወደ ሌሎችም ከኢትዮጵያ ጋር ወደ ተደረጉት ጦርነቶች የገባችው፣ ለእንግሊዛውያን አገልጋይና አሽከር ሆና ነው። በዚህም የተነሳ የጣሊያናውያን ሀብትና ደም ያላግባብ ፈሰሰ” ሲል ወረራውን በማውገዝ ድፍረት የተሞላበት ጽሁፉን ማስነበቡን ይገልጻሉ።

    ጋዜጠኛው በጽሁፉ “የጣልያንና የእንግሊዝ መንግሥታት በአፍሪካ ስለተቀዳጁት የቅኝ-ግዛትና የተስፋፊነት ድል እንደጽጌረዳ የፈካ ውሸት እየፈበረኩ ይመጻደቁ እንጂ፣ በእርግጥ ኢትዮጵያ ድል አድርጋለች… ቪቫ ምኒልክ! ቪቫ ኢትዮጵያ!” ሲል አወድሷል።

    በአጼ ምኒልክ መሪነት የኢትዮጵያ ኃይል በጣልያን ወራሪ ኃይል ላይ በአድዋ የተቀዳጀው ድል ድልድይ ሆኖ የጥንታዊቷን ኢትዮጵያ የታላቅነት ክብር ከዘመናዊ ዓለም ጋር ያገናኘ ድልድይ ሆኗል። ታዲያ ይህ ድልድይ በ1890ዎቹ ግንባታው የተጀመረው የተቀረው የአፍሪካ ክፍል በውጭ ኃይሎች አገዛዝ ቀንበር ስር ሲወድቅ ኢትዮጵያውያን ብቻ በተከታታይ የተሰነዘረባቸውን ወረራ በድል ሲመልሱ ነበር።

    በዚያው ክፍለ ዘመን ኢትዮጵያውያን ለውጭ ወራሪዎች የማይንበረከኩ መሆናቸውን ማሳየታቸውን ማስታወስ ይቻላል። በ1870ዎቹ የግብፃውያንን፣ በ1880ዎቹ የመሃዲስቶችን ተደጋጋሚ ጥቃቶች መክተው መልሰዋል። የአድዋ ድል ደግሞ ይህን የነፃነት ቀናዒነት ይበልጥ ከማድመቅ አልፎ የዓለምን ትኩረት ስቧል።

    የአውሮፓ መንግሥታት ዲፕሎማቶቻቸውን ወደአዲስ አበባ እንዲልኩ፣ ከኢትዮጵያ ጋር 19 ድንበርን የሚመለከቱ ስምምነቶችን እንዲፈራረሙ አደረጋቸው ። በአርነት ትግሉ መስክ በቅኝ ግዛት ሥር ለነበሩት እህት የአፍሪካ አገሮች ታጋዮችም ኢትዮጵያ ፋና ወጊ መብራታቸውና የራዕይ ምንጫቸው ነበረች።

    የአድዋ ድል የፓን አፍሪካን ንቅናቄ መሠረት መሆኑን የኢትዮጵያውያንን የአድዋ ውሎ ከዘከሩ የታሪክ ጠበብት መካከል የዋሽንግተኑ የታሪክ ሊቅ ፕሮፌሰር ራየሞንድ ጆናስ፥ “የአድዋ ጦርነት – የአፍሪካውያን ድል በዘመነ ግዛት” (The Battle of Adwa: African Victory in the Age of Empire, by Raymond Jonas” በሚለው መጽሐፋቸው አስፍረዋል፡፡ በዚህ ጽሁፋቸው “የአድዋ ድል ለአፍሪካውያን ቅኝ አገዛዝን ታግሎ መጣል እንደሚቻል ያሳየ፣ የኢትዮጵያንም ታላቅነት ያስመሰከረ” ስለመሆኑ ደጋግመው አውስተዋል።

    ለዚህም ነው የናይጄሪያ ድኀረ ነፃነት የመጀመሪያ ፕሬዚዳንት የነበሩት ዶ/ር ናምዲ አዚኪዊ (Nnamdi Azikiwe) “ኢትዮጵያ ጥቁር ራሱን በራሱ የሚያስተዳድርባት አገር ነች። በዚህ ክፍለ አህጉር ላይ የአፍሪካ ቀደምት አባቶች የመሠረቱት መንግሥት የታሪክ ዋቢ ነች። ኢትዮጵያ ከዘመን ወደ ዘመን እየተሸጋገረች ህልውናዋን ጠብቃ መኖሯ የሚደነቅና መደነቅም ያለበት ነው” በማለት የተናገሩት።

    ከአድዋው ድል አርባ ዓመት በኋላ ጣልያን ቂሟን ልትወጣ ወረራ ስታካሂድ በግልጽም ይሁን በተዘዋዋሪ የአውሮፓና የአሜሪካ መንግሥታት ከእሷ ጎን ቆመዋል። በተቃራኒው ድሉ በአፍሪካም ይሁን በተቀረው ዓለም የተቀጣጠለውን የአፍሪካዊነት የትግል ስሜት አነሳስቷል፤ እልህ አጭሯል። በአጠቃላይ መላው ጥቁር ሕዝብ፣ በቁጥር አነስተኛ ቢሆኑም ለፍትህ የታመኑ አውሮፓዊያን ነጮችም ለኢትዮጵያ ያላቸውን ወገናዊነት እንዲያጠናክሩ ጥርጊያውን አመቻችቷል። የነኝህም ጥረት በውጭ የነበረውን ሕዝባዊ ድጋፍ ወደ ኢትዮጵያ ያደላ እንዲሆን አድርጎታል። ባህላዊ እሴቶቻቸውን ያልጣሉ የአፍሪካ ምሁራን ከነበሩባቸው የአህጉሩ ከተሞች፣ ከካርቢያን ደሴቶች፣ ከጥቁር አሜሪካዊያን በኩል ተሰባስበው ወረራው ያጫረባቸውን የመጠቃት ስሜት በይፋ አንጸባርቀዋል።

    ደቡብ አፍሪካ ውስጥ ለነበሩት የአፍቃሪ ኢትዮጵያዊነት እንቅስቃሴ መሪዎችም የአድዋው ድል የሞራል እርሾ ሆኗቸዋል። ከእንቅስቃሴው ግንባር ቀደም መሪዎች አንዱ ጀምስ ድዋኔ (James Mata Dwane) ግብጽና ሱዳን ውስጥ ያሉትን ክርስቲያን አፍሪካዊያን ሁኔታ ትኩረት ሰጥተው መፍትሄ ይፈልጉለት ዘንድ ለአጼ ምኒልክ ደብዳቤ የፃፉት የአድዋውን ድል ተከትሎ ነበር።

    ስለአድዋ ድል የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት ዊንስተን ቸርችል “የካቲት 23 ቀን 1888 የአድዋ ጦርነት ተካሂዶ፥ ጣልያን በኢትዮጵያውያን የደረሰባት ሽንፈት ደረሰባት። (ይህም) ሌሎች ሕዝቦችን የሚነካ ሁለት ውጤቶች አስከተለ፤ አንደኛ፥ ሰሜን አፍሪካ ላይ አውሮፓዊ ክብርን ትልቅ ምች መታው። ሁለተኛ፥ በአውሮፓ ፖለቲካ ማንነት ረገድ የኢጣልያ ዋጋ ወደታች ወረደ” ብለው ጽፈዋል።

    ዊንስተን ቸርችል ስለ ኢጣልያ ሽንፈትና ውጤቱ ከመጻፍ ይልቅ ስለ ኢትዮጵያ ድልና በአፍሪካና በሌሎቹ ጭቁን አገሮች ዘንድ የኢትዮጵያን ማንነት ሽቅብ መናሩን መግለጽ አልፈለጉም። ይህ ሊሆን የቻለው ምናልባትም አድዋ ላይ የተገኘው ድል ለጥቁር ሕዝቦች ከነጻነት ለመውጣት የተስፋ እርሹ በመሆኑ፣ ለአውሮፓውያኑ የቅኝ ግዛቶቻቸውን ሊያጡ የሚችሉበት ጅምር በመሆኑ ሊሆን ይችላል።

    የሆነ ሆኖ አድዋ ላይ የተለኮሰው የድል ችቦ በቅኝ ግዛት ስር ለነበሩት የአፍሪካ አገሮች ቀንዲል ሆኗል። ለዚህም ክብር ለመስጠት 17 የአፍሪካ አገሮች የሰንደቅ ዓላማ ቀለማቸውን ከኢትዮጵያ ወስደዋል። አረንጓዴ፣ ቢጫና ቀይ የሆነው የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ቀለም ማሊ፣ ጋና፣ ካሜሩን … አገሮች በተለያየ ቅርጽ የአገራቸው መለያ ሰንደቅ አላማ እንዲሆን አድርገዋል።

    Pankhurst, Richard. “”Viva Menelik!”: The Reactions of Critica Sociale to the Battle and to Italian Colonialism” In Adwa Victory Centenary Conference, 26 February – 2 March 1996, edited by Abdussamad Ahmad and Richard Pankhurst, 517-548. Addis Ababa: Institute of Ethiopian Studies, Addis Ababa University, 1998.

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የአድዋ ድል


    Semonegna
    Keymaster

    መቀዛቀዝ የታየበትን የህዝባዊ ተሣትፎ ለማነቃቃት የተለያዩ መድረኮችን በቀጣይነት እንደሚያዘጋጅ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ህዝባዊ ተሣትፎ ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ኃይሉ አብርሃም ገልጸዋል።

    አዲስ አበባ (ዋልታ)– የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ህዝባዊ ተሣትፎ ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ባለፉት 6 ወራት 484 ሚሊዮን ብር መሰብሰቡን አስታውቋል።

    ጽህፈት ቤቱ በበጀት ዓመቱ እስከ አንድ ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ አቅዶ እየሠራ ሲሆን በቀጣይ የተጠናከረ አፈጻጸም ለማስመዝገብ እንደሚንቀሳቀስ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ማኅበር እና የህዳሴው ግድብ ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ባዘጋጁት ጋዜጣዊ መግለጫ ገልጿል።

    መቀዛቀዝ የታየበትን የህዝባዊ ተሣትፎ ለማነቃቃት የተለያዩ መድረኮችን በቀጣይነት እንደሚያዘጋጅ የህዳሴው ግድብ ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ኃይሉ አብርሃም ገልጸዋል።

    ቪዲዮ፦ ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የግንባታ ድጋፍ ዙሪያ ከኢትዮጵያውያን የዳያስፖራ አባላት ጋር የተደረገው ውይይት

    ከዚሁ ጋር በተያያዘም ጥር 22 ቀን 2011 ዓ.ም. ከንቅናቄ መድረኮች አንዱ የሆነው ሁሉም የዳያስፖራ አካላት የሚገኙበት መድረክ በራስ ሆቴል መድረክ አዘጋጅቶ ከተለያዩ ሀገራት ከመጡ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ አባላት ጋር በቀጣይነት እና በተሻለ ሁኔታ ግድቡን ሊደግፉ በሚችሉበት መንገድ ላይ ውይይት አድርጓል።

    ዳያስፖራው ባለፉት ሰባት ዓመታት 46 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ማድረጉ የተገለጸ ሲሆን ሃገሪቱ ካላት ዲያስፖራ ቁጥር አንጻር ድጋፉ አነስተኛ መሆኑ ተጠቁሟል። በመሆኑም በተለይም በምዕራብ አውሮፓ የሚገኙ ዲያስፖራዎች የሚጠበቅባቸውን ያህል ድጋፍ ስላላደረጉ ትኩረት አድርጎ እንደሚሠራ የዳያስፖራ ማኅበሩ ዋና ዳይሬክተር አቶ አብርሃም ስዩም አስታውቋል።

    ለዚህም ዳያስፖራው ለህዳሴው ግድብ አዲስ የዳያስፖራ ተሳትፎ ንቅናቄ ለመፍጠር እና በዳያስፖራው ዘንድ በህዳሴ ግድቡ ዙሪያ ያለውን ብዥታ ለማጥራት መድረክ ፈጥሮ ውይይት ማድረግ አስፈላጊ እንደነበርና፣ የራስ ሆቴሉ ውይይትም የዚሁ ዋነኛ አካል እንደነበር ተገልጿል። በተመሳሳይ ሁኔታም በዕለቱ የተለያዩ የህዝብ አደረጃጀቶች የሚሳተፉበት የንቅናቄ መድረክ በካፒታል ሆቴል ተካሂዶ ነበር።

    ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ከሁለት ዓመት በኋላ ኃይል ማመንጨት እንደሚጀምር የተገለጸ ሲሆን ከአራት ዓመት በኋላ ተገንብቶ እንደሚጠናቀቅ ይጠበቃል።

    ምንጭ፦ ዋልታ ሚዲያ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦  

    ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– ግዙፉ የመኪና አምራች የሆነው የጀርመኑ ኩባንያ ቮልስዋገን በኢትዮጵያ ኢንቨስት ለማድረግ የሚያስችለውን የመግባቢያ ስምምነት ፈረመ። ስምምነቱን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽነር አበባ አበባየሁ እና ከሰሃራ በታች የኩባንያው የአፍሪካ ቀጣና ሥራ አስፈጻሚ ቶማስ ሻፈር ተፈራርመዋል። በስምምነቱ መሠረትም ኩባንያው የመኪና መገጣጠሚያ ፋብሪካ መክፈት፣ የተሽከርካሪ መለዋወጫ ዕቃዎችን ማቅረብ፣ የስልጠና ማዕከል መክፈት እና ተጓዳኝ ሥራዎችን ይሠራል።

    በስምምነቱ ላይ በኢትዮጵያ የሥራ ጉብኝት ላይ የሚገኙት የጀርመኑ ፕሬዚዳንት ፍራንክ ዋልተር ስታይንማየር እና የኢፌዴሪ የገንዘብ ሚኒስትር አቶ አህመድ ሽዴ ተገኝተዋል።

    ቮልስዋገን ኩባንያ ከሰሃራ በታች ካሉ የአፍሪካ አገራት መካከል ኢትዮጵያን የማስፋፊያ ማዕከሉ አድርጎ ሲመርጥ፣ ከኩባንያው ጋር የመግባቢያ ስምምነት በመፈረም ከሰሃራ በታች ካሉ አገራት ኢትዮጵያ ሦስተኛዋ አገር (ከጋና እና ናይጄሪያ ቀጥሎ) ሆናለች።

    ◌ VIDEO: የጀርመኑ ግዙፍ የመኪና አምራች ኩባንያ ኢትዮጵያ ውስጥ ሰፊ ኢንቨስትመንት ለመጀመር እየተንቀሳቀሰ ነው

    ኩባንያው ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር ለመሥራት መስማማቱ በቀጥታ የእሴት ሰንሰለት የተቀናጀ የአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪ ክላስተር ለመፍጠር ወሳኝ ምዕራፍ ይከፍታል ነው የተባለው።

    ኮሚሽነር አበበ አበባየሁ በፊርማ ሥነ-ስርዓቱ ላይ እንዳሉት መንግሥት አገሪቷን ቀዳሚ የኢንቨስትመንት መዳረሻ ለማድረግ በቁርጠኝነት እየተንቀሳቀሰ ነው።

    ”በአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪው መስክ ልዩ ክላስተር እንዲመሠረት መንግሥት ያለሰለሰ ጥረት ያደርጋል” ያሉት ኮሚሽነሩ ይህን ተግባራዊ ለማድረግ ቮልስዋገንን ጨምሮ ፍላጎት ካላቸው ተቋማት ጋር በቅንጅት ለመሥራት ‘ዝግጁ ነው’ ብለዋል።

    ◌ VIDEO: German companies including Volkswagen and Siemens embarking to invest in Ethiopia

    የኩባንያው የአፍሪካ ቀጣና ሥራ አስፈጻሚ ቶማስ ሻፈር በበኩላቸው የኢትዮጵያ መንግሥት ለአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪው እድገት ትኩረት መስጠቱ ‘የሚደነቅ ነው’ ሲሉ ተናግረዋል። ከዚህ በተጨማሪ ቶማስ ሻፈር ‘ኢትዮጵያ ፈጣን እድገት በማስመዝገብ ላይ ያለች እና በሕዝብ ብዛትም ከ አህሪካ አገራት በሁለተኛ ደረጃ የተቀመጠች በመሆኗ፥ ከሰሃራ በታች ባሉ ሀገራት ለመስፋፋት በምናደርገው ጥረት ኢትዮጵያን ሁነኛ ተመራጭ አገር አድርገናታል፤ በተጨማሪም ቮልስዋገን ኩባንያ ሀገሪቱ ያላትን የስትራቴጂ ጥቅም ከግምት በማስገባት በ አውቶሞቲቭ ዘርፍ ከፍትኛ እድገት እንድታስመዘግብ ይተጋል’ ብለዋል።

    ከዚህ ጋር በተያያዘ የጀርመን የቢዝነስ ልኡካን ቡድን ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የሥራ ሃላፊዎችና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በኢትዮጵያ በኢንቨስትመንት መስክ በሚሰማሩበት ሁኔታ ላይ መክረዋል።

    ሲመንስ የተሰኘው በግዙግነቱ ከአውሮፓ ኩባንያዎች ቀዳሚውን ስፍራ የሚይዘው የጀርመን የቴክኖሎጂ ኩባንያ በኢትዮጵያ ከዚህ በፊት ሲሠራቸው ከነበሩ የቴክሎጂ ዘርፍ ሥራዎች በተጨማሪ በተጠናከረ መልኩ ለመሥራት ዝግጁ መሆኑን አሳውቋል።

    NEWS: German automaker Volkswagen develops automotive industry in Ethiopia

    የጀርመን የቴክኖሎጂ ጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ማኅበርም ቢሮውን አዲስ አበባ በመክፈት ወደ ሥራ ለመግባት ፍቃደኛ መሆኑን አሳውቋል። ማኅበሩ ጀርመን ውስጥ ያሉ የቴክኖሎጂ ድርጅቶች ማኅበር እንደመሆኑ ድርጅቶቹ በመስኩ ለመሰማራት የሚያስችላቸውን ሁኔታ ለማመቻቸት መልካም አጋጣሚን እንደሚፈጥር ይታመናል።

    በኢትዮጵያ መንግስት በኩል በጊዜያዊነት በነፃ ቢሮ በመስጠት ጭምር ማንኛውንም እገዛ ለማድረግ ቁርጠኛ መሆኑንም ተገልጿል።
    የልኡካን ቡድኑ አባላት በኢትዮጵያ ውስጥ በኢንቨስትመንት የተሰማሩ ድርጅቶች ከምንዛሬ እጥረት፣ በደላላ ምክንንያት ምርቶቻቸው ተጠቃሚው ጋር በተጋነነ ዋጋ መድረስ የመሳሰሉ ችግሮች እንደገጠሟቸው ተናግረዋል።

    የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ ጌታሁን መኩሪያ (ዶ/ር ኢንጂ.) የኤሌክትሮኒክስ ግብይት ለመጀመር ሥራዎች እየተሰሩ በመሆኑ ወደ ሥራ ሲገባ ችግሩ እንደሚቀረፍ ተናግረዋል።

    ምንጮች፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ቮልስዋገን


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ከፍተኛ ኃይል የሚጠቀሙ ደንበኞቹ የኤሌክትሪክ ፍጆታ ሂሳባቸው በባንክ እንዲከፍሉ የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር ጥር 13 ቀን 2011 ዓ.ም. ተፈራርሟል።

    ስምምነቱን የተፈፀመው በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ሽፈራው ተሊላ እና በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የባንክ አገልግሎት ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ደረጄ ፉፋ አማካኝነት ነው።

    ኢትዮ ቴሌኮም እና የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በኤሌክትሪክ ኃይል መስመር ተሸካሚ ላይ የተዘረጋውን ገመድ በጋራ ለመጠቀም ተስማሙ

    የመግባቢያ ስምምነቱ ዋና ዓላማ በመጀመሪያው ምእራፍ 27 ሺህ የሚሆኑ ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ኃይል የሚጠቀሙ እንዲሁም መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ደንበኞች የኤሌክትሪክ ፍጆታ ሂሳባቸውን በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በኩል እንዲከፍሉ ለማስቻል እና በቀጣይም በአፈጻጸም ሂደቱ የተገኙ ተሞክሮዎችን በማካተት በመላ ሀገሪቱ ያሉ ደንበኞች ላይም ተግባራዊ የሚደረግ መሆኑን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ሽፈራው ተሊላ በሥነ ሥርዓቱ ላይ ባደረጉት ንግግር አስታውቀዋል።

    ተቋሙ ቀድሞ ይጠቀምበት የነበርውን የፍጆታ ሂሳብ አሰባሰብ ስርዓት በመቀየር፣ ቀልጣፋና በዘመናዊ ቴክኖሎጅ የታገዘ አገልግሎት ለደንበኞቹ ለመስጠት እንደሚስያችለው አክለው ገልፀዋል። ይህም በመሆኑ ተቋሙ፣ ባንኩና ደንበኞች የፍጆታ ሂሳብ ለመክፍል ይፈጠር የነበረውን የገንዘብና የጉልበት ብክነት በከፍተኛ ደረጃ ስለሚቀንሰው፤ ሦስቱም አካላት ተጠቃሚ ይሆናሉ ሲሉ ነው ዋና ሥራ አስፈፃሚው የተናገሩት።

    አዳዲስ የቴክኖሎጂ ዕውቀቶችና ልምዶች የተገኙበትና በምስራቅ አፍሪካ በርዝመት ቀዳሚውን ስፍራ የያዘው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዋና መሥሪያ ቤት ህንጻ

    የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የባንክ አገልግሎት ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ደረጄ ፉፋ በበኩላቸው፥ ዘመናዊ የክፍያ ስርዓት መዘርጋቱ ደንበኞች ሳይጉላሉ ካሉበት ስፍራ ሆነው ክፍያ በባንኩ አማካኝነት በቀላሉ ለመክፍል እንደሚያስችላቸው ገልፀዋል። ሲያጋጥሙ የነበሩ የአከፋፈል ስርዓት ችግሮችን እንዲቀርፍ ያስችላል፤ ደንበኞችም ያጠፉት የነበረውን ጊዜና የሚያጋጥማቸው ውጣ ውረድ ይቀንስላቸዋል ሲሉ ነው አክለው የተናገሩት።

    በስምምነቱ መሠረት እነዚህ ደንበኞች በቂ ግንዛቤ በተለያዩ አማራጮች ካገኙ በኋላ በያዝነው ዓመት ከሚያዝያ ወር ጀምሮ ተግባራዊ እንደሚደረግ እንዲሁም የዚህን ጅምር ሥራ ውጤታማነት ከታየ በኋላ ሁሉም ደንበኞች በተመሳሳይ መልኩ ክፍያ እንዲፈፅሙ በቀጣይ አንደሚደረግ ተገልጿል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት


    Semonegna
    Keymaster

    ቤልካሽ ኢትዮጵያ የሚያስጀምራቸው ሄሎማርኬት እና ሄሎሾፕ የተሰኙ ሁለት የኤሌክትሮኒክስ መገበያያ ገፆች በኢትዮጵያ ውስጥ እና ከኢትዮጵያ ውጪ ለሚገኙ ተገልጋዮች ኢንተርኔት አማካኝነት ግብይት መፈም የሚችሉባቸው ናቸው።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ቤልካሽ ኢትዮጵያ ተጠቃሚዎች በበይነመረብ (ኢንተርኔት) አማካኝነት ግብይት መፈም የሚችሉባቸው ሁለት የኤሌክትሮኒክስ መገበያያ ገፆችን በቅርቡ እንደሚያስጀምር አስታወቀ።

    ሄሎማርኬት (Hellomarket) የተሰኘው ገፅ በዋነኛነት በኢትዮጵያ ውስጥ ለሚገኙ ተገልጋዮቹ ብቻ ካሉበት ቦታ ሆነው ቁሳቁሶችን የሚሸምቱበት አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን በበይነመረብ አማካኝነት የግዥ ትዕዛዝ እና ክፍያ የተፈፀመባቸው ቁሳቁሶቹን ወደ ደምበኞች ለማጓጓዝም ከ ዓለምአቀፉ ዲኤችኤል (DHL) ጋር ስምምነት ተፈራርሟል።

    The dispute between RIDE Taxi, Ethiopian-kind of Uber, and Addis Ababa Transport Authority continues

    ተቋሙ በመጀመርያው ምዕራፍ ወደ 2,500 የሚጠጉ ሴት ኢትዮጵያውያን በባለቤትነት በሚያስተዳድሩዋቸው የተለያዩ ድርጅቶች የተመረቱ ምርቶችን ለማሻሻጥ ቅድመ ዝግጅቱን አጠናቋል።

    በተመሳሰይ ቤልካሽ ከኢትዮጵያ ውጭ ሆነው የኤሌክትሮኒክ ግብይት መፈፀም ለሚፈልጉ ደንበኞቹ አገልግሎት የሚሰጥ ሄሎሾፕ (Helloshop) የተሰኘ ሌላ ገፅ ያዘጋጀ ሲሆን የክፍያ ስርዓቱም በማስተር ካርድ አማካኝነት አንደሚከወን ለማወቅ ተችሏል።

    Ethiopia – blueMoon Incubator and Addis Garage co-working space for startups in Ethiopia

    ቤልካሽ ኢትዮጵያ መቀመጫውን ኔዘርላንድ ባደረገው እና ቤልካሽ ቴክኖሎጂ ሶሉሽን (Belcash Technology Solutions) የተሰኘ በኤሌክትሮኒክ ክፍያ ቴክኖሎጂ ዘርፍ ላይ የተሰማራ ድርጅት እህት ኩባንያ ሲሆን እ.ኤ.አ ከ2011 ጀምሮ በኢትዮጵያ በተለይም በሞባይል ክፍያ እና የገንዘብ ማስተላለፍ ዘርፎች ላይ የተለያዩ ሥራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ ከኩባንያው ድረገፅ የተገኘ መረጃ ያመላክታል።

    የኤሌክትሮኒክስ ክፍያ ሥርዓት በተገቢው አለመስፋፋት እና በዚህ ዘርፍ ላይ ግልፅ የሆኑ ፖሊሲዎችን አለመኖራቸው በኢትዮጵያ መሰል የኤሌክተሮኒክ ግብይት ተቋማት እንዳይስፋፉ እንቅፋት መሆኑን ባለሞያተኞች ይገልፃሉ።

    ከዚህ ዜና ጋር በተመሳሳይ የቻይናው ግዙፉ የኤሌክትሮኒክስ መገበያያ (e-commerce) አሊባባ ኢትዮጵያ ውስጥ ገብቶ ለመሥራት ፍላጎት እንዳለውና ከኢትዮጵያ ባላስልጣናት ጋር (የቀድሞ የኢፌዴሪ ፕሬዝደንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመን ጨምሮ) መወያየቱን የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ዘግቦ ነበር

    ምንጭ፦ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ / አዲስ ፎርቹን
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    ቤልካሽ ኢትዮጵያ


    Semonegna
    Keymaster

    ኢታካ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካ የተለያዩ የሴት አልባሳት በማምረት ወደ ተለያዩ የአውሮፓ አገራት መላክ መጀመሩን የፋብሪካው ዋና ሥራ አስኪያጅ ሚስተር ቴድርኮ ፍራንቦኒ (Federico Fraboni) ተናግረዋል።

    መቀሌ (ኢዜአ)–በጣልያኑ ግዙፍ ኩባንያ ካልዜዶንያ ግሩፕ በ15 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ወጪ የተገነባው ኢታካ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካ ተመረቀ።

    በመቀሌ ልዩ ስሙ አሸጎዳ በተባለ አካባቢ የተገነባው ፋብሪካ በወር 22 ሚሊዮን ብር ዋጋ ያላቸው አልባሳትን ለዓለም ገበያ የማቅረብ አቅም እንዳለው በምረቃ ሥነ ስርዓቱ ላይ ተመልክቷል።

    ፋብሪካውን መርቀው የከፈቱት የንግድና ኢንዱስቱሪ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር መብራህቱ መለሰ በክልሉ ከተማ ልማት ንግድና ኢንዳስትሪ ቢሮ የኢንቨስትመንት ጽህፈት ቤት ዳይሬክተር አቶ ሃፍቶም ፋንታሁነኝ እና በኢትዮጵያ የጣሊያን ኤምባሲ ተወካይ ሚስተር ፕትሮ ፓናሮላ ናቸው።




    የንግድና ኢንዱስቱሪ ሚኒስትር ዴኤታው ዶ/ር መብራህቱ በዚህ ወቅት እንዳሉት በጣሊያን ባለሃብቶች ተገንብቶ ለምረቃ የበቃው ኢታካ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካ አገሪቱን ከማልማት አልፎ የኢትዮጵያዊያንን ትክክለኛ ምስል ለዓለም ያስተዋውቃል፤ ፋብሪካው ለዜጎች የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ ለአገሪቱ የኢኮኖሚ እድገት ፋይዳው የጎላ መሆኑንም ተናግረዋል።

    ለሀገሪቱ እድገት ትልቅ ድርሻ ያለውን የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ለማበረታታት ከሁሉም የመንግስት አካላት ትኩረት ሰጥቶ መሥራት እንደሚገባም ዶ/ር መብራህቱ ገልጸዋል።

    ኢታካ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካ የተለያዩ የሴት አልባሳት በማምረት ወደ ተለያዩ የአውሮፓ አገራት መላክ መጀመሩን የተናገሩት ደግሞ የፋብሪካው ዋና ሥራ አስኪያጅ ሚስተር ቴድርኮ ፍራንቦኒ (Federico Fraboni) ናቸው።

    ፋብሪካ በወር 22 ሚሊዮን ብር ዋጋ ያላቸው አልባሳት ለውጭ ገበያ እንደሚያቀርብ እና ቀደም ሲል ለሙከራ ሲያመርት መቆየቱን ገልጻው የመጀመሪያ ምርቱንም በቅርቡ ለውጭ ገበያ መላኩን ጠቁመዋል።

    ———————————————-

    ———————————————-

    በክልሉ ከተማ ልማት ንግድና ኢንዳስትሪ ቢሮ የኢንቨስትመንት ጽህፈት ቤት ዳሬክተር አቶ ሀፍቶም ፋንታሁነኝ በበኩላቸው ፋብሪካው ለአንድ ሺህ ወገኖች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ገልጸዋል።

    በመቀሌ አካባቢ ኢታካ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካን ጨምሮ ባለቤትነታቸው የውጭ ባለሀብቶች የሆኑ ሦስት የጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካዎች ግንባታቸው ተጠናቅቆ ወደ ምርት መሸጋገራቸውንም አቶ ሀፍቶም ተናግረዋል።

    ሌሎች አስር የአገር ውስጥ ባለሀብቶችም በዘርፉ ለመሰመራት የኢንቨስትመንት ፍቃድ ወስደው በተለያዩ የግንባታ ሂደት ላይ ይገኛሉ።

    በክልሉ የኢንዱስቱሪ ዘርፍ እንቅስቃሴ ከዚህም በላይ እንዲያደግ የመንግስት ጥረት ሊጠናከር እንደሚገባም አቶ ሀፍቶም ተናግረዋል።

    በፋብሪካው ምረቃ ላይ የተገኙት በኢትዮጵያ የጣሊያን ኤምባሲ ተወካይ ሚስተር ፕትሮ ፓናሮላ ክልሉ ሰላም የሰፈነበትና ለሥራ የተነሳሳ የሰው ኃይል ያለው መሆኑ በጣሊያን ባለሀብቶች ተመራጭ እንዲሆን አድርጎታል።

    “በኢትዮጵያና በኢጣሊያ የቆየውን የሁለቱን አገራት ታሪካዊና ልማታዊ ግንኙነት በሁሉም ዘርፍ ለማጠናከር በጋራ እንሠራለን” ብለዋል።

    በፋብሪካው የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው ዜጎች መካከል ከመቀሌ ዩኒቨርሲቲ በኢንዱስትሪያል ኢንጂነሪንግ የተመረቀው ወጣት ልኡል ኃይሉ አንዱ ነው።

    ፋብሪካው በአካባቢው በመከፈቱ እሱን ጨምሮ በርካታ ወጣት ምሩቃንን የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ማድረጉን ተናግሯል።

    “ኢታካ የጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካ ወደምርት ሥራ በመግባቱ የሥራ እድል አግኝቺያለሁ” ያለው ደግሞ ወጣት አወጣሀኝ አለነ ነው።

    በምረቃ ስነ ስርዓቱ ላይ ከጣሊያን አገርና ከኢትዮጵያ የመጡ ባለሀብቶችና ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    ኢታካ

    Semonegna
    Keymaster

    የኦሞ ኩራዝ ቁጥር 3 የስኳር ፋብሪካ የምረቃ ሥነ ስርዓት ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ እና የኤርትራው ፕሬዝዳንት ኢሳይያስ አፈወርቂ ጨምሮ የተለያዩ የክልል፣ የፌደራል እና የውጭ ሀገር ባለስልጣናት ተገኝተዋል።

    አዲስ አበባ (ኢዜአ) – ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድና የኤርትራው ፕሬዝዳንት ኢሳይያስ አፈወርቂ የኦሞ ኩራዝ ቁጥር 3 የስኳር ፋብሪካ መርቀው ከፈቱ።

    በኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን ንብረትነት በተገነባው በዚሁ ፋብሪካ የምረቃ ሥነ ስርዓት ላይ የኤርትራው ፕሬዝዳንት አማካሪ የማነህ ገብረአብ፣ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ወርቅነህ ገበየሁየቻይና ልማት ባንክ ዋና ሥራ አስኪያጅ ሚስተር ቡ ዪ እንዲሁም የደቡብ ክልል ርዕስ መስተዳደር አቶ ሚሊዮን ማቲዮስን ጨምሮ ሌሎች የመንግስት ባለስልጣናትም ተገኝተዋል።

    ከቻይና ልማት ባንክ በተገኘው 8 ቢሊዮን ብር ብድር የተገነባው ይህ ፋብሪካ በቻይናው ቻይና ኮምፕላንት ግሩፕ ተቋራጭነት የተገነባ ሲሆን የሙከራ ምርቱን ዛሬ ይጀምራል። ፋብሪካው የሙከራ ሥራውን የሚጀምረው ከ2ሺህ እስከ 3ሺህ ቶን ሸንኮራ አገዳ በመፍጨት ነው።

    ፋብሪካው በሙሉ አቅሙ መሥራት ሲጀምር በቀን ከ8 ሺህ እስከ 10 ሺህ ኩንታል ስኳር የማምረት አቅም የሚኖረው ሲሆን የዓለም ገበያን ፍላጎት መሠረት በማድረግም ጥሬ ስኳር (raw sugar)፣ ነጭ ስኳር (plantation white sugar) እና የተጣራ ስኳር (refined sugar) ማምረት ይችላል። ከሁለት ወር በፊት በተደረገው ፍተሻ የፋብሪካው ማምረቻ ማሽኖች ወደ ምርት ለመሸጋገር ዝግጁ መሆናቸው ተረጋግጠዋል።

    በኦሞ ኩራዝ ስኳር ልማት ፕሮጀክት ስር በሚገኙ አራቱም ፋብሪካዎች በ100 ሺህ ሄክታር በላይ የሸንኮራ አገዳ ለማልማት የመስኖ መሠረተ ልማት ተከናውኗል፤ እስካሁንም ባለው ሂደት 30ሺህ ሄክታር መሬት የመስኖ ውሃ እንዲያገኝ ማድረግ ተችሏል። የመስኖ ውሃ ካገኘው መሬት ውስጥም 16ሺህ ሄክታር በሚሆነው መሬት ላይ ሸንኮራ አገዳ መተከሉም ተገልጿል።

    ዜና፦ ቬሎሲቲ አፓረልዝ ኩባንያ ኢትዮጵያ ውስጥ የመጀመርያ የሆነውን የግል የኢንዱስትሪ ፓርክ ሊገነባ ነው።

    የአሞ ኩራዝ ቁጥር ሁለት ስኳር ፋብሪካ ወደ ምርት በተሸጋገረበት በመጋቢት ወር 2008 ዓ.ም የኦሞ ኩራዝ ቁጥር 3 ፋብሪካ ግንባታ በይፋ መጀመሩ ይታወሳል። ግንባታውም የተከናወነው ከቻይና ልማት ባንክ በተገኘ ከ8 ቢሊዮን ብር በላይ ብድር ነው።

    ፕሮጀክቱ ወደ አገልግሎት መግባቱ በአገሪቱ ስኳር ወደ ማምረት የተሸጋገሩ ፋብሪካዎችን ቁጥር ወደ ስምንት (ወንጂ ሸዋ፣ መተሐራ፣ ፊንጫአ፣ ከሰም፣ ተንዳሆ፣ አርጆ ዲዴሳ፣ ኦሞ ኩራዝ ቁጥር 2 እና 3) ያደርሰዋል።

    በኦሞ ኩራዝ ስኳር ልማት ፕሮጀክት ስር ከሚገነቡት አራት የስኳር ፋብሪካዎች አንዱ የሆነው ይህ ፋብሪካ፤ በደቡብ ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች ክልል የኦሞ ወንዝን በሚያዋስኑት በከፋና ቤንች ማጂ ዞኖች መሃል ይገኛል።

    ኦሞ ኩራዝ ስኳር ልማት ፕሮጀክት ከተቋቋመ ከ2003 ዓ.ም ጀምሮ ከ110 ሺህ በላይ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ከኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    የኦሞ ኩራዝ ቁጥር 3 የስኳር ፋብሪካ ተመረቀ

     

    Semonegna
    Keymaster

    በመቀሌ ከተማ በ147 ሚሊዮን ብር ካፒታል ሙሉ ብርሃን ኢንዱስቱሪና ንግድ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ያቋቋመው ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ምሶሶ ማምረቻ ፋብሪካ ከ200 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል ፈጥሯል።

    መቀሌ (ኢዜአ) – በ147 ሚሊዮን ብር ካፒታል የተቋቋመው ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ገመድ ተሸካሚ የኮንክሪት ምሶሶ ማምረቻ ፋብሪካ ምርት ማከፋፈል መጀመሩን አስታወቀ።

    “ሙሉ ብርሃን ኢንዱስቱሪና ንግድ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር” በሚል የተቋቋመው ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ምሶሶ ማምረቻ ፋብሪካ ከ200 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል ፈጥሯል።

    የፋብሪካው ሥራ አስኪያጅ አቶ እሥራኤል ብርሃኑ ለኢዜአ እንደገለጹት ፋብሪካው በአገር አቀፍ ደራጃ ያለውን የኮንክሪት ምሶሶ ችግር ለመፍታት ታሳቢ ተደርጎ የተቋቋመ ነው።

    ፋብሪካው በአሁኑ ወቅት በቀን እስከ 90 የሚደርስ ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ኃይል ተሸካሚ ምሶሶዎችን በማምረት ላይ ሲሆን በሙሉ አቅሙ ሥራ ሲጀምር በቀን እስከ 300 የተለያዩ ደረጃ ያላቸው ምሶሶዎችን የማምረት አቅም እንደሚኖረው ሥራ አስኪያጁ ተናግረዋል።

    ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ጋር በመነጋገር ፋብሪካው ምርቶቹን ለትግራይአማራአፋር ክልሎች ማከፋፈል መጀመሩን አቶ እሥራኤል አስታውቀዋል።

    ፋብሪካው ከአገር ውስጥ ስሚንቶ፣ አሸዋና ጠጠር የሚጠቀም ሲሆን ለምሶሶው መሥሪያ የሚውሉ ብረቶችን ከውጭ በማስገባት ለአገልግሎት ያውላል።

    ፋብሪካው በሚያመርተው ምርት መንግስት በከተማና በገጠር የኤሌክትሪክ ሽፋን ለማዳረስ እያከናወነ ላለው ሥራ አጋዥ መሆኑን ሥራ አስኪያጁ ተናግረዋል።

    የክልሉ መንግስት በቦታ አቅርቦትና ብድር በማመቻቸት እገዛ እንዳደረገላቸው የገለጹት አቶ እሥራኤል ፋብሪካው በሙሉ አቅሙ ማምረት እንዲችል ከውጭ ለሚመጡ ጥሬ ዕቃዎች መግዣ የውጭ ምንዛሬ አቅርቦት እንዲመቻችላቸው ጠይቀዋል።

    በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የትግራይ ቅርንጫፍ ሥራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ገብረመድህን የኮንክሪት ምሶሶ ማምረቻ ፋብሪካው ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ምርቶች ማምረት መጀመሩን ተናግረዋል።

    የኮንክሪት ምሶሶ ማምረቻ ፋብሪካው በመቀሌ ማምረት መጀመሩ ከአሁን ቀደም ከአዲስ አበባ ለማጓጓዝ ለትራንስፖርት ይወጣ የነበረውን ወጪ ይቀንሳል ብለዋል።

    ከፍትኛ የኤሌክትሪክ ምሶሶዎች ለ20 ዓመታት ዋስትና ያላቸው መሆኑን የገለጹት ሥራ አስፈፃሚው ካሁን በፊት ለአገልግሎት ይውሉ የነበሩ የባህርዛፍ ምሶሶዎች በጉዳት ምክንያት ያደርሱ የነበሩትን አደጋና የኤሌክትሪክ መቆራረጥ የሚቀንስ ነው።

    የትግራይ ክልል ኢንቨስትመንት ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሃፍቶም ፋንታሁን እንደገለጹት የምሶሶ ማምረቻ ፋብሪካው በመቀሌ ከተማ ለተለያዩ የኢንቨስትመንት ሥራዎች ቦታ ከተሰጣቸው ባለሀብቶች መካከል በፍጥነት ወደ ማምረት ሥራ መሸጋገር መቻሉ በአርያነቱ እንዲቀመጥ የሚያደርገው ነው።

    የትግራይ ክልል የተረጋጋ ሰላም ያለው በመሆኑ በርካታ የውጭና የአገር ውስጥ ባለሀብቶች በተለያዩ የኢንቨስትመንት ሥራዎች እየተሳተፉ መሆናቸውን የጽህፈት ቤት ኃላፊው ገልጸዋል።

    በመካኒካል ምህንድስና የተመረቀው ወጣት አማኑኤል ሀይሉ በፋብሪካው በመቀጠር በወር 6ሺህ ብር የወር ደሞዝ እየተከፈለው ይሠራል። በፋብሪካው የሥራ እድል በማግኘቱ ደስተኛ መሆኑን የሚናገረው ወጣት አማኑኤል ገቢ ማግኘት መጀመሩ ከቤተሰብ ጥገኝነት ወጥቶ የራሱን ቤተሰብ ለመመስረት መቻሉን ገልጿል።

    ወጣት ዙፋን ኪዳኑ በበኩሏ “ማኅበሩ በዘርፉ ኢንቨስት በማድረጉ የአካባቢውን ወጣቶች የሥራ አድል ተጠቃሚ አድርጎናል” ብላለች።

    በትግራይ ክልል በ2010 ዓ.ም 24 ቢልዮን ብር ካፒታል ያስመዘገቡ 1ሺህ 328 ባለሀብቶች በሥራ እንዳሉ ከክልሉ ኢንቨስትመንት ጽህፈት ቤት የተገኘ መረጃ ያመልክታል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    የኤሌክትሪክ ምሶሶ

    Semonegna
    Keymaster

    የወሎ ዩኒቨርሲቲ የሚጀምረው የግዕዝ ቋንቋ ትምህርት በቋንቋው የተጻፉ ሥራዎችን ወደ ሌሎች አገርኛ ቋንቋዎች በመተርጎም ጥቅም ላይ ለማዋል እንደሚያስችል በዩኒቨርሲቲው የማኅበራዊና ሥነ ሰብእ ኮሌጅ የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ ጽሁፍ ትምህርት ክፍል ተጠሪ ተናግረዋል።

    ደሴ (ኢዜአ) – የወሎ ዩኒቨርሲቲ ከያዝነው የትምህርት ዘመን ጀምሮ የግዕዝ ቋንቋን በመጀመሪያ ዲግሪ ለማስተማር ዝግጅቱን ማጠናቀቁን አስታወቀ።

    ዩኒቨርሲቲው ትምህርቱን ለመጀመር በቀረጸው ሥርዓተ ትምህርት (curriculum) ዙሪያ ከምሁራንና ባለድርሻ አካላት ጋር መስከረም 29 ቀን 2011 ዓ.ም ተወያይቷል።

    በዩኒቨርሲቲው የማኅበራዊና ሥነ ሰብእ ኮሌጅ የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ ጽሁፍ ትምህርት ክፍል ተጠሪ ዶክተር እንድሪስ አብይ እንዳስረዱት ግዕዝ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የላቀ ሥፍራ አለው።

    ትምህርቱን ለማስጀመር አራት መምህራን የተቀጠሩ ሲሆን፣ እስከ 18 ተማሪዎችን ለመቀበል ዝግጅት ማድረጉን ገልጸዋል።

    ሥርዓተ ትምህርቱ ጋዜጠኝነትን ጨምሮ አገር በቀል ህክምናና መድኃኒት፣ የሥነ ከዋክብት ቀመርና የቀን አቆጣጠር፣ የባህልና የህግ ሥርዓቶች ተካተውበታል።

    ትምህርቱ በቋንቋው የተጻፉ ሥራዎችን ወደ ሌሎች አገርኛ ቋንቋዎች በመተርጎም ጥቅም ላይ ለማዋል እንደሚያስችል ዶክተር እንድሪስ ተናግረዋል።

    በቋንቋው በፍልስፍና፣ በህክምና፣ በሥነ ከዋክብትና በመሳሰሉት የዕውቀት ዘርፎች በርካታ ጽሁፎች ቢጻፉም፤ ህዝቡንም ሆነ አገሪቱን መጠቀም የሚገባቸውን ያህል አልተጠቀሙበትም። ዕውቀቱም ለሌሎች ሳይተላለፍ ለረጅም ዓመታት መቆየቱን ተጠሪው ገልጸዋል።

    በዩኒቨርሲቲው የታሪክና ቅርስ ጥናትና ጥበቃ ትምህርት ክፍል አስተባባሪና መምህር አቶ ዘላለም ጌትነት በበኩላቸው የመጥፋት አደጋ ላይ የሚገኘውንና የዕውቀት ምንጭ የሆነውን ቋንቋ በዩኒቨርሲቲ ደረጃ መስጠቱ ታሪክን ከማቆየትና እውቀትን ከማጋራት አንጻር ጠቀሜታው ጉልህ ነው ብለዋል።

    ሥርዓተ ትምህርቱ በተለይ ቋንቋው ከኢትዮጵያ ታሪክ ጋር ያለውን ቁርኝት በሚያሳይ መልኩ ቢቀረጽ የተሻለ እንደሚሆን አመልክተዋል።

    በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቲያትር ጥበባት ትምህርት ክፍል መምህርና የሥነ ጥበባት ኮሌጅ የድህረ ምረቃ ተባባሪ ዲን ረዳት ፕሮፌሰር አሰፋ ወርቁ ”ዩኒቨርሲቲው የአገር ሃብት የሆነውን የግዕዝ ቋንቋ ለማስተማር መወሰኑ የሚያስመሰግነውና ሌሎችም ዩኒቨርሲቲዎች ተመሳሳይ ኃላፊነት እንዲወስዱ መነቃቃትን የሚፈጥርላቸው ነው” ብለዋል።

    ግዕዝ ኢትዮጵያን የምናውቅበት የዕውቀት ምንጭ መሆኑን አስታውሰው፣ ይህንን መገናኛ ብዙኃን አገራዊ ፋይዳ ያለውን የዕውቀት ዘርፍ በማስተዋወቅ ድርሻቸውን እንዲወጡ ጠይቀዋል።

    የወሎ ዩንቨርሲቲም ተማሪዎችን ካስመረቀ በኋላ የሥራ ዕድል እንዲያገኙ ከባለድርሻ አካላት ጋር መምከር እንዳለበትም አቶ አሰፋ አሳስበዋል።

    በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የደቡብ ወሎ አገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ መአምራን ብርሃነሕይወት እውነቱ ቋንቋው በዩኒቨርሲቲው መሰጠቱ በርካታ አገራዊ ታሪኮች፣ ቅርሶች፣ መንፈሳዊና ዓለማዊ ሥራዎች፣ ምርምርን የሚጋብዙ ሥራዎች ለማወቅና ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን በአዲስ መንፈስ ለማስቀጠል ጠቀሜታ እንዳለው አስረድተዋል።
    የአብነት ተማሪዎች እንቅስቃሴ መዳከም ቋንቋውን እንዳዳከመው አውስተው፣ የወሎ ዩንቨርሲቲ የጀመረው ጥረት እንዲሳካ ቤተክርስቲያኗ ድርሻዋን ለመወጣት ዝግጁ መሆኗን አስታውቀዋል።

    ከዚህ ጋር በተያያዘ በ1999 ዓ.ም. የተመሠረተው የወሎ ዩኒቨርሲቲ ዓመታዊ የቅበላ አቅም ዘንድሮ ከ20 ሺህ በላይ ደርሷል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    የወሎ ዩኒቨርሲቲ

    Semonegna
    Keymaster

    በ2010 ዓ.ም ወደ ከፍትኛ ትምህርት ተቋማት የሚገቡ 280 ኤርትራውያን ስደተኞች የመግቢያ ፈተና እንዲወስዱ መደረጉንና በአሁኑ ወቅት ፈተናውን ያለፉ 150 ተማሪዎች መለየታቸውን አስረድተዋል።

    አዲስ አበባ (ኢዜአ/UNHCR)፦ በኢትዮጵያ በስደት ላይ ከሚኖሩ ኤርትራውያን መካከል 150 ተማሪዎች በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ገብተው የመማር ዕድል እንደሚያገኙ በኢትዮጵያ የስደተኞችና ከስደት ተመላሾች ጉዳይ አስተዳደር አስታወቀ።

    በተያዘው ዓመት ሌሎች ቁጥራቸው ከ11ሺህ በላይ የሆኑ ህጻናት (የስደተኛ ኤርትራውያን ልጆች የሆኑ) የቅድመ መደበኛ ትምህርት ዕድል ማግኘታቸውም ተመልክቷል።

    በኢትዮጵያ የስደተኞችና ከስደት ተመላሾች ጉዳይ አስተዳደር (Ethiopia Administration for Refugee and Returnee Affairs/ ARRA) የሰሜን ጽህፈት ቤት የትምህርት ኦፊሰር አቶ ኤፍሬም ሀጎስ ለኢዜአ እንደገለጹት ከ180 ሺህ የሚበልጡ ኤርትራውያን ስደተኞች በተለያዩ መጠለያ ጣቢያዎች ይገኛሉ፡፡

    የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ ኤርትራውያን ስደተኞች መካከል 150 ተማሪዎች ዘንድሮ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በነጻ ለመማር እድል እንደሚሰጣቸውም ተናግረዋል።

    ወደ ከፍትኛ ትምህርት ተቋማት የሚገቡ 280 ስደተኞች የመግቢያ ፈተና እንዲወስዱ መደረጉንና በአሁኑ ወቅት ፈተናውን ያለፉ 150 ተማሪዎች መለየታቸውን አስረድተዋል።

    ፈተናውን ያለፉ 150 ስደተኞችም በተለያዩ የኢትዮጵያ መንግስት ዩኒቨርሲቲዎች ትምህርታቸውን እንደሚከታተሉም ነው አቶ ኤፍሬም የገለጹት።

    ኤርትራውያን ስደተኛ ተማሪዎች በኢትዮጵያ ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ መደረጉ በሁለቱ አገራት መካከል አሁን የተጀመረውን ሰላማዊ ግንኙነት ይበልጥ እንደሚያጠናክረውም ተናግረዋል።

    ◌ ቪድዮ፦ ኢትዮጵያ የቀይ ባህር እና የምጽዋ ወደቦችን ለመጠቀም ቅድመ ዝግጅቶችን እያጠናቀቀች ነው

    የኢትዮጵያ መንግስት ለኤርትራውያን ስደተኞች የትምህርት ዕድል ሲሰጥ የአሁኑ ለሰባተኛ ጊዜ ሲሆን በየዓመቱ ከ100 ያላነሱ ተማሪዎችም የዕድሉ ተጠቃሚ ሆነዋል።

    በተመሳሳይ በትግራይ ክልል በሚገኙ አራት የኤርትራውያን ስደተኞች መጠለያ ጣቢያዎች የሚገኙ 11ሺህ 87 ኤርትራውያን በቅድመና በመደባኛ ትምህርት እንዲሁም በሙያ ክህሎት ማበልጸጊያ እንዲማሩ መደረጉን አቶ ኤፍሬም አክለው ተናግረዋል።

    በተለያዩ ምክንያቶች ከአገራቸው ተሰደው ወደኢትዮጵያ ቢመጡም ልጆቻው እዚህ የትምህርት ዕድል በማግኘታቸው መደበኛ ትምህርታቸውን መቀጠላቸውን የተናገሩት ደግሞ በማይዓይኒ የስደተኞች መጠለያ ጣቢያ የሚገኙት አቶ ተስፋልደት ይህደጎ የተባሉ ስደተኛ ናቸው።

    በአዲ ሓሩሽ መጠለያ ጣቢያ የሚገኙ ሌላው ስደተኛዋ ወይዘሮ ለምለም ዘካሪያስ እንደተናገሩት በአካባቢያችን የሚገኙ ትምህርትቤቶች ለኤርትራውያን ተማሪዎች በራቸው ክፍት መሆኑ ትልቅ እድል መሆኑን ገልጸዋል።

    “ልጆቻቸው ከኢትዮጵያውያን ወንደሞቻቸው ጋር በአንድ ክፍል ውስጥ እንዲማሩ መደረጉ በሁለቱ አገራት ህዝቦች መካከል ጠንካራ ግንኙነት ለመፍጠር ለሚደረገው ጥረት የላቀ አስተዋፅኦ አለው” ብለዋል።

    የኢትዮጵያ መንግስት ለኤርትራውያን ስደተኞች እየሰጠ ያለው የከፍተኛ የትምህርት እድል ለሌሎች አገራት በመልካም አርአያነት የሚጠቀስ መሆኑን የገለጸው ደግሞ ወደ ዩኒቨርሲቲ ለማግባት የመግቢያ ፈተና የወሰደው ተማሪ ዓንዶም ፍሳሃየ ነው።

    እስከ ግንቦት ወር 2010 ዓ.ም ባለው ጊዜ ውስጥ በአጠቃላይ 71,833 ኤርትራውያን ስደተኞች ትግራይ ክልል ውስጥ በሚገኙ አራት መጠለያ ጣብያዎችና አፋር ክልል ውስጥ በሚገኙ ሁለት መጠለያ ጣብያዎች ውስጥ እንደሚገኙ የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች መርጃ ድርጅት (UNHCR) ዘግቧል።

    ምንጮች፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) እና የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች መርጃ ድርጅት (UNHCR)

    ኤርትራውያን

Viewing 11 results - 16 through 26 (of 26 total)