ብርሃን ኢንሹራንስ ከ20 ሚሊዮን ብር በላይ የተጣራ ትርፍ አስመዘገበ
ኩባንያው ይፋ ባደረገው መረጃ መሠረት በዕቅድ ከተያዘው 17 ሚሊዮን ብር የትርፍ መጠን አንፃር ሲታይ ከዕቅድ በላይ ትርፍ አስመዝግቧል፡፡ ኩባንያው በ2009 ዓ.ም. 9.6 ሚሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ አስመዝግቦ ነበር፡፡ የ2010 ዓ.ም. ትርፉ ከካቻምናው ሲነፃፀር የ115 በመቶ ዕድገት እንደታየበት አስታውቋል፡፡
በ2010 ዓ.ም. የኩባንያው ዓመታዊ የተመዘገበ የገቢ መጠንም ወደ 104.3 ሚሊዮን ብር ከፍ በማለቱ ከካቻምናው አኳያ መጠነኛ ለውጥ በማሳየት የአምስት በመቶ ጭማሪ አስተናግዷል፡፡ ከጠቅላላው የዓረቦን መጠን ውስጥ የተሽከርካሪ ኢንሹራንስ የአንበሳውን ድርሻ በመያዝ 59 በመቶ፣ በገንዘብ ሲሰላም የ61.3 ሚሊዮን ብር ድርሻ ይዟል፡፡ የገንዘብ ነክ ኢንሹራንስ 16 በመቶ ወይም 16.4 ሚሊዮን ብር በማስመዝገብ በሁለተኛ ደረጃ ይከተላል፡፡
በሒሳብ ዓመቱ የቀረቡ የጉዳት ካሳ ጥያቄዎችን በተመለከተ ኩባንያው 66.6 ሚሊዮን ብር የነበረ ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥም 50.1 በመቶ የሚሆነው ክፍያ ተፈጽሟል፡፡ ከአጠቃላይ የካሳ ክፍያ ጥያቄዎች ውስጥ 43.5 ሚሊዮን ብር ወይም 65 በመቶ የሚሆነው የተመዘገበው በተሽከርካሪ ኢንሹራንስ እንደነበር ያመለክታል፡፡
Read more: https://bit.ly/2PXgDuf