የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ዶ/ር አምባቸው መኮንን መገደላቸው ተረጋገጠ
—–
የአማራ ክልል ፕሬዝደንት ዶ/ር አምባቸው መኮንን ትላንት (ሐምሌ 15 ቀን 2011 ዓ.ም.) በነበረው የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ተከትሎ መገደላቸውን የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን አስታውቋል።
አቶ አምባቸውን ጨምሮ የርዕሰ መስተዳድሩ አደረጃጀት ዘርፍ አማካሪ የሆኑት አቶ እዘዝ ዋሴም በደረሰው ጥቃት ሕይወታቸውን ማጣታቸው ታውቋል። ጥቃቱ የተፈፀመው ግለሰቦቹ ስብሰባ ላይ ባሉበት ወቅት እንደሆነ ኢቲቪ አስታውቋል።
አቶ አምባቸው መኮንን የቀድሞውን የክልሉን ፕሬዝደንት አቶ ገዱ አንዳርጋቸውን በመተካት የተሾሙት የካቲት 29 ቀን 2011 ዓ.ም. ነበር።
የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (አዴፓ) ሐምሌ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ተፈፀመ በተባለው የመንፈቅለ መንግሥት ሙከራ እጃቸው አለበት የተባሉ ሰዎችን በቁጥጥር ሥር ማዋሉም ተሰምቷል።
የክልሉ ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ ብርጋዴር ጀኔራል አሳምነው ፅጌ መንፈቅለ መንግሥቱን አቀነባብረዋል ተብለው በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ፓርቲው አስታውቋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ትላንት ከእኩለ ለሊት በኋላ በብሔራዊው ቴሌቪዥን ቀርበው በሰጡት መግለጫ የአማራ ክልል ባለስልጣናት የተገደሉት እና የቆሰሉት በስብሰባ ላይ እያሉ እንደነበር መናገራቸው አይዘነጋም።