የማህፀን በር ካንሰር መከላከያ ክትባት የሚሰጥበት ጊዜ ተራዘመ
የማህፀን በር ካንሰር መከላከያ ክትባት የሚሰጥበት ቀን መራዘሙን የአማራ ክልል ጤና ጥበቃ ቢሮ አስታወቀ።
ክትባቱ በኢትዮጵያ በሁሉም ክልሎች በጥቅምት ወር እና ከስድስት ወራት በኋላ ደግሞ ለሁለተኛ ዙር ሊሰጥ ታቅዶ ነበር። በቢሮው የክትባት መርሃ ግብር የቴክኒክ አማካሪ አቶ ሙሉጌታ አድማሱ እንደገለፁት ለክትባት የሚሆነው መድሃኒት በመዘግየቱ ምክንያት ክትባት የሚሰጥበት ቀን ወደ ህዳር 5/2011 ዓ.ም ተራዝሟል።
በሀገር አቀፍ ደረጃ ለሚሰጠው የማህፀን በር ካንሰር መከላከያ ክትባት ዉጤታማነት በአማራ ክልል በሁሉም ዞኖች እና ወረዳዎች ለጤና ባለሙያዎች ስልጠና መሰጠቱንም አቶ ሙሉጌታ ነግረውናል። ከጤና ጥበቃ ቢሮ ያገኘነው መረጃ እንደሚያሳየው በክልሉ ከ4 መቶ 50 ሺህ በላይ ልጃገረዶች ክትባቱን ይወስዳሉ። እድሜያቸው 14 ዓመት የሆናቸው ልጃገረዶች ብቻ የክትባቱ ተጠቃሚ እንደሚሆኑም ለማወቅ ተችሏል።
የማህፀን በር ካንሰር መከላከያ ክትባት እድሜያቸው ከ9 እስከ 14 ዓመት የሆናቸው ልጃገረዶችን የግብረ ስጋ ግንኙነት ከመፈጸማቸው በፊት ከበሽታው ለመከላከል ሲባል በዓለማቀፍ ደረጃ ይሰጣል። ይሁን እንጅ በኢትዮጵያ ደረጃ ለሁሉም ልጃገረዶች የሚበቃ መድኃኒት ገዝቶ ማቅረብ ባለመቻሉ ለበሽታው ይበልጥ ተጋላጭ የሆኑት ላይ ክትባቱ እንደሚሰጥ ጤና ጥበቃ ቢሮው ገልጿል።