ኢትዮጵያን ለ52 ዓመታት በዲፕሎማትነት ያገለገሉት አምባሳደር ቆንጂት ሥነጊዮርጊስ እውቅና ተሰጣቸው

Home Forums Semonegna Stories ኢትዮጵያን ለ52 ዓመታት በዲፕሎማትነት ያገለገሉት አምባሳደር ቆንጂት ሥነጊዮርጊስ እውቅና ተሰጣቸው

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #9207
    Semonegna
    Keymaster

    አምባሳደር ቆንጂት ሥነጊዮርጊስ ከኢትዮጵያም አልፈው በአፍሪካ አህጉር ለረዥም ዓመታት በዲፕሎማትነት ያገለገሉ ግለሰብ ሲሆኑ፥ ለዚህም አገልግሎታቸው እ.ኤ.አ በኅዳር ወር 2015 የአፍሪካ ህብረት የክብር ሽልማት ሸልሟቸዋል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ለ52 ዓመታት በተለያዩ ሀገራትና ተቋማት ኢትዮጵያን በመወከል በዲፕሎማትነት ያገለገሉት አምባሳደር ቆንጂት ሥነጊዮርጊስ ላባረከቱት አገልግሎት ከኢፌደሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ዕውቅና ተሰጣቸው።

    አምባሳደር ቆንጂት ሥነጊዮርጊስ የአገልግሎት የክብር እውቅናው በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) የተሰጣቸው ጥር 07 ቀን 2011 ዓ.ም. ነው።

    ይህ ሽልማት አምባሳደሯ ለረጅም ዓመታት በተለያዩ የዓለም ሀገራት፣ በአህጉር አቀፍ እና ዓለም አቀፍ ተቋማት ለኢትዮጵያ ተወካይና ዲፕሎማት በመሆን ላበረከቱት ስኬታማ አገልግሎት እንደተበረከተላቸው የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት (ኤፍ.ቢ.ሲ.) ዘግቧል።

    አምባሳደር ቆንጂት በግብፅ ፣ በእስራኤል፣ በአፍሪካ ህብረትና በተባበሩት መንግስታት ድርጅት (ተመድ) ሀገራቸውን በዲፕሎማትነት በመወከል ውጤታማ ስራ ማስመዝገባቸው ተገልጿል።

    አምባሳደሯ ከምንም በላይ ሀገራቸውን በማስቀደም በዲፕሎማሲው ዘርፍ ያበረከቱት አስተዋጽዖም ለሌሎቸ ዲፕሎማቶች አርዓያ የሚሆን ነው ተብሏል።

    ለአምባሳደሯ የተሰጣቸውን የክብር እውቅና ተገቢ እንደሆነ በመደገፍ የኢፌዴሪ ፕሬዝደንት ወ/ሮ ሳህለወርቅ ዘውዴ በትዊተር ገጻቸው ላይ እንዲህ ብለው ጽፈዋል

    እህቴ፣ ባልንጀራዬ ክብርት አምባሳደር ቆንጂት ሥነጊዮርጊስ በኢትዮጵያና በአፍሪካ ረዥሙን የአገልግሎት ዘመን የያዙ ዲፕሎማት በዛሬው ዕለት ከክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር የሚገባቸውን ሽልማትና እውቅና በማግኘታቸው እንኳን ደስ አላቸው! ደስ አለን! አገርን በጨዋነት፣ በታማኝነት፣ በታታሪነት የማገልገል ዋጋ ነው። ለሁሉም በተለይ በዛሬ ጊዜ ትልቅ ትምህርት ልንወስድበት ይገባል።

    አምባሳደር ቆንጂት ሥነጊዮርጊስ ለተደረገላቸው እውቅና ምስጋና ያቀረቡ ሲሆን፥ በቅርቡ የመጣውን ለውጥ ተከትሎ በሀገሪቱ ትልልቅ ቦታዎች ላይ ሴቶች ሹመት እንዲያገኙ መደረጉንም አድንቀዋል።

    በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያን በመወከል የሚሠሩ ዲፕሎምቶችና አምባሳደሮችም ለሀገራቸው ጥቅም ቅድሚያ በመስጠት ሊሠሩ እንደሚገባ አሳስበዋል።

    አምባሳደር ቆንጂት ሥነጊዮርጊስ የተወለዱት በሐረር ከተማ እ.ኤ.አ. በ1940 ሲሆን፥ በእንግሊዝ ሀገር ለንደን ከተማ ከሚገኘው ለንደን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ እ.ኤ.አ በ1954 ዓለም አቀፍ ግንኙነት (International Relations) በዲግሪ ተመርቀዋል። እ.ኤ.አ በ1963 ኒው ዮርክ ከተማ፣ አሜሪካ ከሚገኘው የኮለምብያ ዩኒቨርሲቲ የካርኒጌ ፌሎውሺፕ (Carnegie Fellowship) አግኝተዋል። ኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተቀጥረው መሥራት የጀመሩት እ.ኤ.አ በ1962፥ ይህም የአፍሪካ አንድነ ድርጅት (የአሁኑ የአፍሪካ ህብረት) ከመቋቋሙ ከአንድ ዓመት በፊት ነው።

    አምባሳደር ቆንጂት ሥነጊዮርጊስ ከኢትዮጵያም አልፈው በአፍሪካ አህጉር ለረዥም ዓመታት በዲፕሎማትነት ያገለገሉ ግለሰብ ሲሆኑ፥ ለዚህም አገልግሎታቸው እ.ኤ.አ በኅዳር ወር 2015 የአፍሪካ ህብረት የክብር እውቅና ሰጥቷቸዋል

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከአምባሳደር ቆንጂት በተጨማሪም በተለያዩ ሀገራት በአምባሳደርነት ሲሠሩ ቆይተው በጡረታ ለተሰናበቱ ቀደምት ዲፕሎማቶች የዕውቅና ምስክር ወረቀት ሰጥቷል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    አምባሳደር ቆንጂት ሥነጊዮርጊስ


Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.