ከ7ሺህ 800 በላይ አዳዲስ አነስተኛና መካከለኛ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎች በመላው አገሪቱ ሊቋቋሙ ነው

Home Forums Semonegna Stories ከ7ሺህ 800 በላይ አዳዲስ አነስተኛና መካከለኛ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎች በመላው አገሪቱ ሊቋቋሙ ነው

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #8283
    Semonegna
    Keymaster

    በአገሪቱ ከ7 ሺህ 800 በላይ አዳዲስ አነስተኛና መካከለኛ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎች እንደሚቋቋሙ የፌዴራል አነስተኛና መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ልማት ኤጀንሲ አስታወቀ።

    አዳማ (ኢዜአ)– በመላ አገሪቱ በዚህ አመት ከ7 ሺህ 800 በላይ አዳዲስ አነስተኛና መካከለኛ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎች እንደሚቋቋሙ በኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ስር የሚገኘው የፌዴራል አነስተኛና መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ልማት ኤጀንሲ (Federal Small and Medium Manufacturing Industry Development Agency) አስታወቀ።

    አዳዲስ ኢንዱስትሪዎቹን ለማቋቋም፣ ነባሮችን ለማጠናከርና በቁሳቁስ ለማደራጀት 14 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር እንደሚያስፈልግ ኤጀንሲው አስታውቋል።

    የአነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዝ ፋይናንስ ፕሮጀክት የ2010 በጀት ዓመት የሥራ ዕቅድ አፈጻጸምን የሚገመግምና በ2011 ዕቅድ ላይ የሚመክር የሁለት ቀን መድረክ ጥቅምት 17 ቀን 2011 ዓም በአዳማ ከተማ ተጀምሯል።

    በኤጀንሲው የፖሊሲ ዕቅድና ፕሮጀክት ዝግጅትና ክትትል ዳይሬክተር ወ/ሮ ገነት አረጋዊ በወቅቱ እንደገለጹት ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ መር ኢኮኖሚ ለሚደረገው መዋቅራዊ ሽግግር አዳዲስ አነስተኛና መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎችን መገንባት አስፈልጓል። ነባሮችንም የማጠናከር ሥራ የትኩረት አቅጣጫ መሆኑን ነው የገለጹት።

    ለእዚህም በበጀት ዓመቱ 7 ሺህ 860 አዳዲስ አነስተኛና መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎችን የማቋቋምና 2 ሺህ 924 ነባር ኢንዱስትሪዎች የማጠናከር ሥራ እንደሚከናወን አመልክተዋል።

    “አዳዲስ ኢንዱስትሪዎቹን ለማቋቋም፣ ነባሮቹን ለማጠናከርና ለእቃ አቅርቦት የሚያስፈልገው 14 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ለሁሉም ክልሎች፣ ለአዲስ አበባና ድሬዳዋ ከተማ መስተዳድሮች በብድር ይቀርባል” ብለዋል ወ/ሮ ገነት።

    የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ወ/ሮ መሰንበት ሸንቁጥን ፕሬዝደንት አድርጎ መርጧል

    አዲስ ከሚቋቋሙት የማምረቻ ኢንዱስትሪዎች መካከል የብረታ ብረትና እንጨት ሥራ፣ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት፣ ቆዳና የቆዳ ውጤቶች፣ የግብርና ምርት ማቀነባበሪያዎች፣ የኮንስትራክሽን ግብዓቶችና ጌጣ ጌጥ ማምረቻዎች እንደሚገኙበት ጠቅሰዋል።

    ዳይሬክተሯ እንዳሉት በሚቋቋሙት ኢንዲስትሪዎች ከ195 ሺህ ለሚበልጡ ዜጎች ቋሚ የሥራ እድል ይፈጠራል ተብሎ ይጠበቃል። አያይዘውም “ኢንዱስትሪዎቹን ውጤታማ ለማድረግ በሀገር ውስጥ የ2 ቢሊዮን ብርና በውጭ አገራት የ194 ነጠብ 5 ሚሊዮን ዶላር የገበያ ትስስር ይመቻቻል” ብለዋል።

    ዘርፉን ለማሳደግ ለባለሀብቶች፣ ለዩኒቨርሲቲ ምሩቃን፣ ለሞዴል አርሶ አደሮችና አርብቶ አደሮች እንዲሁም ለሌሎችም የኅብረተሰብ ክፍሎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና እንደሚሰጥ ዳይሬክተሯ አስታውቀዋል ።

    የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር አቶ አስፋው አበበ በበኩላቸው “የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ልማት የትራንስፎርሜሽኑ መሰረት ስለሆነ በእያንዳንዱ ወረዳ ሊቋቋም ይገባል” ብለዋል።

    ባለድርሻ አካላትን በልዩ ትኩረት በመሳተፍ ዕቅዱን እውን ለማድረግ ኤጀንሲው ከሁሉም ክልሎችና ከሁለት የከተማ መስተዳድሮች ጋር ጥቅምት 17 ቀን 2011 ዓ.ም የስምምነት ሰነድ መፈራረሙንም አቶ አስፋው አመልክተዋል።

    የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ለውጥና ብልጽግና እንዲሁም የቴክኖሎጂ ሽግግር ያለማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪው ዕድገትና ተወዳዳሪነት ሊመጣ ስለማይችል ሁሉም አካላት ለተፈጻሚነቱ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ዋና ዳይሬክተሩ አሳስበዋል ።

    የቀረበው አመላካች ዕቅድ ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ-መር ኢኮኖሚ ለመሸጋገር የሚደረገውን ግብ ለማሳካት ወሳኝ ስለመሆኑ ከመድረኩ ተሳታፊዎች ተገልጿል።

    ለኢንዱስትሪው ልማት ማነቆ የሆኑ በሊዝ፣ በብድር ገንዘብና በኤሌክትሪክ አቅርቦት የሚስተዋሉ እጥረቶችና የተንዛዙ አሠራሮች ሊፈቱ እንደሚገባም በተሳታፊዎቹ ጥያቄ ቀርቧል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    መካከለኛ የማኑፋክቸሪንግ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.