ኢትዮጵያ ውስጥ የደረስንበትን የሞራል ድቀት፣ የዕውቀት ውድቀት እና የሰብዓዊነት ውርደት የሰሞኑ ሞት ፍንትው አድርጎ አሳይቷል

Home Forums Semonegna Stories ኢትዮጵያ ውስጥ የደረስንበትን የሞራል ድቀት፣ የዕውቀት ውድቀት እና የሰብዓዊነት ውርደት የሰሞኑ ሞት ፍንትው አድርጎ አሳይቷል

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #11241
    Anonymous
    Inactive

    ኢትዮጵያ ውስጥ የደረስንበትን የሞራል ድቀት፣ የዕውቀት ውድቀት እና የሰብዓዊነት ውርደት የሰሞኑ ሞት ፍንትው አድርጎ አሳይቷል
    (ሙሉዓለም ጌታቸው)

    የሞራል ድቀት

    • ገዳይ እና ሟች እኩል ጀግና የሚባልበት አገር ሆናለች ኢትዮጵያ። ዳቦ ስለራበኝ በዘላቂነት ዳቦ ለመብላት የዳቦ ቤቱን ባለቤት ገድዬ ዳቦውን ሁሉ ልውረስ የሚል ሌባ ወንጀለኛ ተብሎ ሀገር ካላወገዘው ወንጀለኛ ማን ሊባል ነው? ከእስር አስፈትተው ሹመት በሰጡ፣ 27 ዓመት ቃል ሳይተነፍሱ፥ ትላንት በተፈጠረ ዕድል ‘አማራ አማራ’ ብለው እንደ ጀግና ሲታዩ ዝም ባሏቸው በጥይት አረር ጨረሷቸው። እነዚህን የ21ኛው ዘመን አውሬዎችን በክብር መቅበር እና ጀግና ማለት ካላስነወረ ምን ሊያስነውር ነው? ‘የትም ፍጭው ዱቄቱን አምጭው፣’ ያነገብከው ዓላማ እንጂ ዓላማህን የምትፈጽምበት መንገድ ግድ አይሰጠኝም እንደሚል ሰው በዚህ ምድር ላይ አረመኔ የለም። ኦሳማ ቢን ላደን ያነገበውን ዓላማ ምናልባት ሁላችን የምንደግፈው እና በሞራልም ደረጃ ልክ የሆነ ነው። ያን ለመፈጸም የሄደበት መንገድ፣ የተጠቀመበት መሣሪያ ግን ርኩስ እና አረመኔ አስብሎታል። ሰብዓዊ የሆነ ሁሉ ሰው ይሄን ያምናል። ባዶ እጃቸውን የነበሩ፣ ለአገር ለወገን እረፍት አጥተው የሠሩ ግለሰቦችን አረመኔያዊ በሆነ መልኩ መግደል ሰይጣንነት ነው። የትኛውም ዓይነት ዓላማ ይሄን ግፍ ጽድቅ አያደርገውም። አሳምነው ጽጌን እንደ ጀግና የቆጠሩ ለእኔ ክርስቶስን እንደሰቀሉ መንጎች ናቸው። ክርስቶስን የሰቀሉ ግብዝ አይሁዶች እግዚአብሔርን እያገለገሉ ያሉ ይመስላቸው ነበር። ለዛ ግፋቸው መበተን እጣ ፈንታቸው ሆነ። ዛሬ ከእነዚህ ግፈኞች ጋር መተባበር የደም ዋጋን በራስ ላይ መሳብ ነው። ገዳይም ተገዳይም ጀግና ሊሆን አይችልም፤ ካልዞረብን በቀር።

    የዕውቀት እጥረት

    • የኢትዮጵያ መሪዎች በ21ኛው ክፈለ ዘመን ሀገርን የሚያክል ነገር በ“try and error” እየመሩ ነው። የእነሱን ነፍስ ብቻ ሳይሆን በፍጥነት አገሪቷን ገደል እየከተቱ ነው። 8 እና 9 ዓመት ከጨለማ በቀር ሌላ ነገር ያላዩን ግለሰቦች እና ከመንግስት ቢሮክራሲ ተለያይተው የነበሩ ሰዎችን በግዙፍ ስልጣን ላይ አሰቀመጡ። በሰለጠነው ዓለም ቢሆን ከፍተኛ የህክምና እርዳታ የሚደረግላቸውን ግለሰቦች በጡዘት ላይ ያለ አገርን እንዲመሩ ስልጣን አንበሻበሿቸው። ኤርትራ በርሀ ሊታገል የሄደን ወጣት ጉርጓድ ቆፍረው የሚቀብሩ ግለሰቦችን ሽግግር ምሩ ብለው ስልጣን ሰጡ። የቀደመው መንግስት ካጠፋው ይልቅ ይሄን ጥፋት ልናርም እየሄድንበት ያለው መንገድ የበለጠ ጥፋት እየከሰተ ነው።
    • ዲሞክራሲ ባህል ነው። ይሄ ባህል ፈጽሞ ባልገባው ማኅበረሰብ ፊት ሰው ሆኖ መታየት የደካማነት መገለጫ ነው። መሪዎቻችን ሆይ ዲሞክራሲ ያለንን ነገር እንዲያሳጣን ሳይሆን ባለን ነገር ላይ እንዲጨምርልን ተደርጎ መተግበር ካልቻለ፥ ዲሞክራሲ ለእኛ የሞት የሽረት ጉዳይ አይደለም። እባካችሁ በዲሞክራሲ ሳይሆን በዕውቀት ይሄን ሕዝብ ምሩት።

    የሰብዓዊነት ውርደት

    • ዘረኞች ስለሰው አንዳች ክብር እንደሌላቸው ድጋሚ ያየንበት ወቅት ነው። ጄነራል ሰዓረ መኮንን ድንቅ ኢትዮጵያዊ ነው። የሞተው ለኢትዮጵያዊነት በመቆሙ ነው። እንደነ አሳምነው ባለማበዱ ነው። እንደነሱ በዘር ልክፍት ገምቶ ዙሪያውን በራሱ ወገን እና ዘሮቼ በሚላቸው ሰዎች ተከቦ ቢሆን ኖር ዛሬ የተከሰተው ባልደረሰበት ነበር። አንዳንዶች ግን ዛሬም በሱ ሞት ፖለቲካ በመሥራት የእሱን ድንቅ ሰብዓዊነት ሊያራክሱ ይሞክራሉ። ምናለ ሞቱን እንኳ ቢያከብሩለት? ምናለ ለጥቂት ጊዜ እንኳ የሞተለትን ኢትዮጵያዊነት እና ሰብዓዊነት ከፍ ቢያደርጉ?
    • አንድ ቀን መንገድ ላይ የፈሰሰውን የአማራ የኔቢጤ እና መስኪን ለመርዳት፣ በየጎዳናው የወደቀውን የአማራን ተወላጅ ረሃብ ለመቅረፍ ገንዘብ አወጥቶ የማያቅ ሁላ ‘አማራ አማራ’ እያለ በውንድማማቾች መካከል ጥላቻን እየዘራ ያለ፥ ለሞታቸው ከቶ ደንታ የሌለው፣ በምዕራብ አገራት ሸሽቶ ተሰዶ እነሱ የከፈሉትን መስዋዕትነት በጣቱ ለመንካት አቅም የሌለው ሰው ‘ዘሬ!’ ሲል መስማት እጅግ ያማል። የግብዞች መዓት ኢትዮጵያን እያወካት ነው።

    ሙሉዓለም ጌታቸው

    የሞራል ድቀት፣ የዕውቀት ውድቀት እና የሰብዓዊነት ውርደት የሰሞኑ ሞት ፍንትው አድርጎ አሳይቷል


     

Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.