በየትኛውም ወገን የሚፈፀም፣ ሥርዓት አልበኝነት በቃ ለማለት ጊዜው አሁን ነው! ኢዜማ የሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ

Home Forums Semonegna Stories በየትኛውም ወገን የሚፈፀም፣ ሥርዓት አልበኝነት በቃ ለማለት ጊዜው አሁን ነው! ኢዜማ የሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #13489
    Anonymous
    Inactive

    በየትኛውም ወገን የሚፈፀም፣ ሥርዓት አልበኝነት በቃ ለማለት ጊዜው አሁን ነው!
    ከኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

    የኢትዮጵያውያን የፍትህ የእኩልነትና የዴሞክራሲ ጥያቄ በርካታ አስርት ዓመታትን ያስቆጠረ ብቻ ሳይሆን የአያሌ ዜጎችን ሁለንተናዊ መስዋዕትነት የወሰደ ረጅም ጉዞ ነው። በተለይ ባለፉት አምስት ዓመታት የሁሉንም ተሳትፎ ያማከለና አገዛዙ ከሚቋቋመው በላይ የሆነ ንቅናቄ የታየበት ትግል ተደርጓል። ውጤቱም የዛሬዋን ሁኔታ ወልዷል።

    ከበርካታ የዓለም ሀገራት ተሞክሮ እንዳየነው ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን ማዋለድ ከባድ ምጥ ያለበት የጭንቅ ጊዜ ማሳለፍ የግድ መሆኑን ነው። በኢትዮጵያችንም እያየን ያለነው ይህንኑ ነው። በእንደዚህ ዓይነት አስጨናቂ ወቅት ይህን ሂደት እንደአንድ ከባድ ታሪካዊ ኃላፊነት ወስደው የሚሠሩ የመኖራቸውን ያህል ግርግር ፈጥረውና የራሳቸውን ፍላጎት በኃይል ለመጫን የሚፍጨረጨሩ ቡድኖችና ግለሰቦች መኖራቸውን በየእለቱ በየቦታው የምናየው አሳዛኝ ክስተት ሆኗል።

    ፓርቲያችን ከተመሠረተ ጀምሮ ለሀገር ሠላምና ለሕዘብ መረጋጋት የራሱን ያልተቆጠበ አሥተዋፅዖ እያበረከተ ይገኛል። በእኛ ዕምነት የተያዘው የሽግግር ሂደት ለአንድ ወገን የማይተውና የሁሉንም ተሳትፎ የሚጠይቅ እንደሆነ እናምናለን። ያም ሆኖ በዚህ ፈታኝ ወቅት የመንግሥት ሚና ትልቅና ከፍተኛ እንደሚሆን እንገነዘባለን።

    ፓርቲያችን በሀገር አቀፍ ደረጃ የተከሠቱ ፈታኝ ሁኔታዎችንና የመንግሥትን ምላሽ በመገምገም በሚከተሉት ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ያለውን አቋም ይገልፃል።

    1. የየትኛውም በኢትዮጵያ ሀገረ-መንግሥት ግዛት ውስጥ የሚንቀሳቀስ ቡድንም ሆነ ግለሰብ ተግባር የሀገራችን ሕጎ እና ሀገራችን ያፀደቀቻቸውንና የተቀበለቻቸውን ድንጋጌዎች ባከበረ መልኩ ብቻ እንዲሆን ማድረግ የሚገባን ዛሬ ነው። ዜጎች በሕግ ጥበቃ እንደሚደረግላቸው ካልተረጋገጠላቸው እና ከሕግ በታች መሆናቸውን ካልተረዱ ማንም እየተነሳ የፈለገውን አድርጎ “አልጠየቅም” የሚል ማንአለብኝነት ከሠፈነ መቼም ማቆሚያ ወደማይኖረው የሁከት ዓለም ጅው ብሎ እንዳይገባ ያሠጋል።
    2. የሁሉም የፖለቲካ አስተሳሰቦችን በነፃነት እና በሠለጠነ መንገድ መግለፅ፣ በሥልጣን ላይ ያለውንም ሆነ ሌሎች ፓርቲዎችን መተቸት፣ ማጋለጥ አልፎም በምርጫ ከሥልጣን ማውረድ የተለመደና ተገቢም ሊሆን ይችላል። ሀገርን የሚያዋርድ ተግባር መፈፀም ግን ለማንም ያልተፈቀደ የሀገር ከህደት ወንጀል መሆኑ በግልፅ ሊታወቅ ይገባል። በሕዝብ፣ በሃይማኖቶች፣ በብሔረሰቦች፣ በሰንደቅ ዓለማና በመሳሰሉት የአገር መገለጫዎች ላይ የሚፈፀም ማንኛውም የነውር ተግባር አስተማሪ የሆነ ቅጣት የሚያስከትል መሆን አለበት።
    3. ለዩኒቨርስቲ ተማሪዎች የሚሠጠው ትኩረት ከዚህ በፊት ከነበረው የተለየና ከወቅቱ የፖለቲካ ትኩሳት የሚጠብቃቸው መሆን እደሚገባው እናምናለን። በሁሉም የሀገራችን ክፍሎች ባሉ ዩኒቨርስቲ ግቢዎች የተከሠቱ ችግሮች የሕዝባችንን ልብ ሰብረው ያለፉ ክስተቶች ናቸው። ከሁሉም በላይ በደንቢዶሎ ዩኒቨርሲቲ ይማሩ የነበሩ ተማሪዎች ላይ የተደረገው እገታ ውሉ የጠፋና የመንግሥትን የተማሪዎችን ህይወት የመጠበቅ ኃላፊነት አለመወጣት ያጋለጠ ነው። ከዚህ ቀደም መንግሥት ስለለተማሪዎቹ እገታ ወቅቱን የጠበቀ እና ትክክለኛ መረጃ ለተማሪዎቹ ቤተሰቦች እና ለሕዝብ እንዲሰጥ ኢዜማ መጠየቁ ይታወሳል። ሆኖም መንግሥት ትክክለኛ እና ወቅታዊ መረጃ የመስጠት ከፍተኛ ክፍተት ታይቶበታል። ከዚህ አንጻር መንግሥት ተማሪዎቹን ከእገታ የማስለቀቁን ኃላፊነት በአግባቡ እንዲወጣ እና የሕዝብን ልብ እንዲያሳርፍ አበክረን እንጠይቃለን።
    4. በየትኛውም አካባቢ የሚፈጸም ግፍ ለየትኛውም አካባቢ ለሚገኝ ሰላም ጠንቅ ነው” እንዲሉ፥ ለተማሪዎቻችን የመቆም ጉዳይ የአንድ ወገን ወይም የአንድ ክልል ጉዳይ ሊሆን አይገባውም። የሁላችንንም ተናብቦ መሥራት ግድ ይላል። ከዚህ አንጻር የታገቱ ልጆቻችንን በሰላም ለማስለቀቅ ሕግ እና ሥርዓትን በተከተለ መልኩ በሀገራችን በሁሉም አካባቢዎች በሕዝባችን የሚደረጉ ሀቀኛ ጥረቶችን እንደግፋለን።
    5. ሀገርን እና ሕዝብን የማወክ አንድ አካል የሆነው የሞጣ መስጂዶችን የማቃጠል ድርጊት በአጥፊዎቹ ላይ አስተማሪ ርምጃ ተወስዶ ለሕዝብ ይፋ እንዲደረግ፤ መስጂዶቹን አድሶና ምዕመናኑን ክሶ ወደቀድሞው ሰላማዊ አገልግሎት ለመመለስ የሚደረጉትን የአብሮነት እንቅስቃሴዎችን እንደግፋለን።
    6. በቅርቡ የጥምቀት በዓል አከባበር ወቅት በተወሰኑት አካባቢዎች በተለይም በአቦምሳ የከተራ በዓል ሳይከበር የቀረበትን ሁኔታ ታዝበናል። የጥምቀት በዓል ሃይማኖታዊ ይዘቱን ጠብቆ እንዳይከበር እንቅፋት የሆኑ አካላትም ለሕግ እንዲቀርቡና ተገቢ ቅጣት እንዲያገኙ እንጠይቃለን።
    7. ኢዜማ የምርጫ ወረዳዎችን አመራሮች፣ አባላትና ደጋፊዎች እንደዚሁም ሕዝባዊ ውይይቶች በሚያካሄድበት ጊዜ ጥቂት ሥርዓት አልበኞች የሚፈጥሩት ግርግር ሕዝብን የሚወክል እንዳልሆነ ብንረዳም በአጠቃላይ የፖለቲካ ድባቡ ላይ የሚፈጠረው የስሜት መሻከር ያሳስበናል። በተለይም ወደምርጫ ለመግባት ዝግጅት እያደረግን ነው በሚባልበት በዚህ ወቅት ሕዝቡ ሕገመንግሥታዊ የሆነውን የመሰብሰብ መብቱን መጠቀም የማይችልበት ሁኔታ ይታያል። ባሳለፍነው ሳምንት በተከሠቱ በተለይ የጎንደር እና የሸዋሮቢት ድርጊቶችን ተከታትሎ አጥፊዎችን እንዲቀጣ አቤቱታችንን ለመንግሥት አቅርበናል። ኢዜማ ላይ የሚከሠቱ ችግሮች ሁለት ገጽ አላቸው አንደኛው ከመንግስት መዋቅር የሚመጣ ሲሆን ሁለተኛው ከዚያ ውጭ የሆኑ ሥርዓት አልበኞች የሚፈጥሩት ነው። “ባለጌና ጨዋ በተጣሉ ጊዜ ለጊዜውም ቢሆን ባለጌ ያሸነፈ ይመስላል” የሚል የቆየ የሀገራችን ብሂል አለ። ይህም ጨዋው በሕግ ስለሚያምንና የሕግ አስከባሪ ባለጌውን ይቀጣል፤ ብሎ በማመን ነው። በእኛ መዋቅርም የሚታየው ይሄው ሕግን የማክበር ጉዳይ ነው፤ ይህም ቢሆን ልክ አለው፤ ከገደብ ያለፈ ነውር ሲፈፀም አመራሩም፣ አባሉም፣ ደጋፊውም ራሱን፣ ፓርቲውንና ሀገሩን የመጠበቅ ተፈጥሯዊ መብት አለው። ኢዜማ ሀገርንና ሕዝብን ለድርድር አያቀርብም። ይህንንም ደግመን ደጋግመን ተናግረናል! መንግሥት በራሱ ውስጥም ሆነ ከራሱ ውጭ ያሉትን ሥርዓት አልበኞች በሕግ ሊቀጣ ይገባል። ይህ ካልሆነ ግን ሕዝቡ ራሱን ወደመከላከልና ሰላሙን ወደ ማስጠበቅ ሊገፋ ይችላል። ይህም በየትኛውም መመዘኛ ስህተት ሊሆን አይችልም።

    በመጨረሻም የዴሞክራሲ ግንባታ ሂደቱን መጠበቅ ለሁላችንም የሚጠቅም ሀገር እና ሕዝብን የሚታደግ ብቸኛው መንገድ መሆኑን አውቀን እንድንጓዝበት መልዕክታችንን እያስተላለፍን ሥርዓት አልበኝነትን በጋራ በቃ የምንልበት ጊዜው ዛሬ መሆኑን በአፅንኦት እንገልፃለን።

    ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!
    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)
    ጥር 22 ቀን 2012 ዓ.ም
    አዲስ አበባ

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)

Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.