የማር ምርት መጠንን ለማሳደግ የንብ አነባብ ሥራን ማዘመን ዋነኛው መፍትሔ ነው

Home Forums Semonegna Stories የማር ምርት መጠንን ለማሳደግ የንብ አነባብ ሥራን ማዘመን ዋነኛው መፍትሔ ነው

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #8770
    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ኢዜአ)– በኢትዮጵያ ንብን በዘመናዊ መንገድ በማነብ የአገሪቱን የማር ምርት ለማሳደግ ከተለያዩ ተቋማት ጋር በቅንጅት እንደሚሠራ የግብርና ሚኒስቴር ገለጸ። በአገሪቱ ማርን በብዛትና በጥራት ለማምረት የንብ እርባታ ኢንዱስትሪ መቋቋም ይኖርበታል ተብሏል።

    በኢትዮጵያ ከመቶ ዓመት በላይ የንብ ማነብ ልምድ ቢኖርም አሠራሩ ዘመናዊ የንብ አነባብ ግብአቶችን መሠረት ያላደረገ፣ ይልቁንም ባህላዊ መንገድ የተከተለ በመሆኑ የሚፈለገውን ያህል የማር ምርት ማምረትና ለገበያ ማቅረብ አልቻለችም።

    በአገሪቱ ከ2 ሚሊየን በላይ ንብ አናቢዎች ያሉ ሲሆን በአሁኑ ወቅትም በዓመት እስከ 50 ሺህ ሜትሪክ ቶን ማር በመመረት ላይ ይገኛል። ያም ሆኖ ግን የአመራረት ስርዓቱ እንዲዘምን ቢደረግ በአገሪቱ ከዚህ የበለጠ መጠን ማር ማምረት እንደሚቻል ነው ህዳር 21 ቀን 2011 ዓ.ም. አዲስ አበባ በተጀመረውና በዓለም አቀፉ አናቢዎች ፌዴሬሽን (Apimondia) በተዘጋጀው ዓለም አቀፍ ጉባኤ ላይ የተመለከተው።

    Ahadu Beekeeping and Honey Processing Factory inaugurated in Tigray Region, Ethiopia

    “በምግብ ምርት ላይ የንቦች አስተዋጽኦ” በሚል ርዕስ እየተካሄደ ባለው ጉባኤ ላይ የተገኙት የግብርና ሚኒስትሩ አቶ ዑመር ሁሴን የንብ እርባታ ለዜጎች ተጨማሪ የገቢ ምንጭ ከመሆን ባለፈ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ዓይነተኛ ሚና እንዳለውም ገልፀዋል። ሆኖም በኢትዮጵያ በርካታ የንብ ዝርያዎችና በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ አናቢዎች ቢኖሩም በተለያዩ ችግሮች ሳቢያ አገሪቱ ከዘርፉ ማግኘት የሚገባትን እያገኘች እንዳልሆነ ነው የተናገሩት። በመሆኑም መንግስት ገበያ-ተኮር የማር ምርት ለማምረት በዘርፉ ከተሰማሩ ዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር በትብብር ለመሥራት ዝግጁ መሆኑን ገልጸዋል።

    ኢትዮጵያን ጨምሮ በዓለም የንቦች ቁጥር እየተመናመነ መምጣቱን የገለጹት ሚኒስትሩ፤ ችግሩን ለመከላከል ከዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር በትብብረ መሥራት የግድ መሆኑን አስረድተዋል።

    የአየር ንብረት መዛባት፣ በሽታና የተክሎች መጠን መመናመን ለንቦች ቁጥር እንዲቀንስ ካደረጉት ምክንያቶች መካከል የችግሩ መንስዔ በመሆኑ የጋራ መፍትሄ መፈለግ ይኖርብናል ብለዋል።

    ለንቦች ቁጥር መመናመን አንዱ ምክንያት የሆነው በአርሶ አደሩ ዘንድ በብዛት ጥቅም ላይ እየዋለ ላለው የጸረ-አረም ርጭት ዘላቂ መፍትሄ ሊሰጠው እንደሚገባ ገልጸዋል። በኢትዮጵያም ሆነ በአፍሪካ እድገት እያሳየ ያለውን የግብርና ዘርፍ ዘመናዊ ለማድረግ የሚደረገው ጥረት አነስተኛ እንደሆነም ሚኒስትሩ አክለዋል።

    Ethiopia’s apiculture and huge honey production potential need to look for modern techniques

    በኢትዮጵያ እየተካሄደ ያለው ዓለም አቀፍ ጉባኤም መንግስትን፣ በዘርፉ የተሰማሩ አናቢዎችን፣ ማኅበራትና ተቋማትን የሚያበረታታ ነው ብለዋል።

    የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኤጀንሲ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ካሊድ ቦምባ በኢትዮጵያ የማር ምርትን ለማሳደግ አሠራሩን ዘመናዊ ማድረግ ይገባል ብለዋል። በአገሪቱ ማርን በብዛትና በጥራት ለማምረት የንብ እርባታ ኢንዱስትሪ መቋቋም አንዳለበትም አሳስበዋል። ዘርፉን ማሳደግ አንዲቻል አዳዲስ ቴክኖሎጂ ማላመድ፣ ዛፎችን በብዛት መትከል፣ የገበያ ትሰስር መፍጠር፣ አመራረቱን ዘመናዊ ማድረግ እንደሚገባ ገልጸዋል።

    ዓለም አቀፉ አናቢዎች ፌዴሬሽን (Apimondia) ምክትል ፕሬዚዳንት ፒተር ኮዝሙስ ኢትዮጵያ ካላት የማምረት አቅም አኳያ አሁን ያለው ምርት ከ10 በመቶ እንደማይበልጥ ገልጸዋል። የአየር ንብረት ለወጥ፣ የንቦች በሽታ እና የዓለም ገበያ መለዋወጥ የዘርፉ ችግር በመሆን በዓለም አቀፍ ደረጃ ውይይት ማድረግ ተገቢ መሆኑን አስረድተዋል። “ንቦች ከሌሉ ህይወት የለም” የሚሉት ምክትል ፕሬዘዳንቱ ተመራማሪዎች፣ እውቀት ያላቸው ሰዎች ልምዳቸውን ማካፈል አለባቸው ብለዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    የማር ምርት

Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.