በአዲስ አበባ የትምህርት ጥራት ደረጃን ያላሟሉ 52 ትምህርት ቤቶች ተዘጉ

Home Forums Semonegna Stories በአዲስ አበባ የትምህርት ጥራት ደረጃን ያላሟሉ 52 ትምህርት ቤቶች ተዘጉ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #8551
    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ኢ.ፕ.ድ) በአዲስ አበባ በ2010 ዓ.ም የትምህርት ጥራት ደረጃን ያላሟሉ 52 የቅድመ መደበኛ፣ የአንደኛ ደረጃና የሁለተኛ ደረጃ መሰናዶ ትምህርት ቤቶች መዘጋታቸውን የአዲስ አበባ አጠቃላይ ትምህርት ጥራትና አግባብነት ተቆጣጣሪ ባለስልጣን አስታወቀ።

    የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ ብሩክነሽ አርጋው ኅዳር 7 ቀን 2011 ዓ.ም ለብዙኃን መገናኛ በሰጡት መግለጫ እንደተናገሩት፤ በ2010 ዓ.ም በአጠቃላይ ትምህርት ጥራትና አግባብነት ተቆጣጣሪ ባለስልጣን አማካኝነት ቁጥጥር ከተደረገባቸው 1 ሺህ 407 ትምህርት ቤቶች ውስጥ በቅድመ መደበኛ 26፣ በመጀመሪያ ደረጃ 22፣ በሁለተኛ ደረጃና መሰናዶ አራት ትምህርት ቤቶች ከደረጃ በታች በመሆናቸው ተዘግተዋል።

    እንደ ወ/ሮ ብሩክነሽ ገለጻ፥ በቅድመ መደበኛ ትምህርት ከደረጃ በታች ሆነው የተዘጉ ትምህርት ቤቶች የቅድመ መደበኛ ትምህርት ተቋም ሊኖሩት የሚገባ የአገልግሎት መስጫ ክፍሎች ማሟላት አልቻሉም፤ ተመጣጣኝ የሆነ የመምህራንና የሠራተኞች የትምህርት ደረጃም የላቸውም፤ የመምህራንና ሠራተኞች ብዛት አነስተኛ ነው፤ የሕፃናት ማሸለቢያ ክፍልና የመምህራን ማረፊያ ክፍል ውስጥ ሊኖሩ የሚገባቸው ቁሳቁሶች አልተሟሉም፤ ቋሚ የውጭ መጫወቻ መሳሪያዎች የሏቸውም። የትምህርት ማበልፀጊያ ማዕከል እጥረት፣ በቂ የሰው ኃይልና ለሰውነት ማጎልመሻ ትምህርት የሚያስፈልጉ የትምህርት መሳሪያዎችና የአገልግሎት መስጫ ክፍሎች አለመኖርም ለትምህር ቤቶቹ መዘጋት ዋነኛ ምክንያቶች ናቸው።

    ወ/ሮ ብሩክነሽ፥ የተዘጉ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች 3በ1 የሆነ ቤተ ሙከራና የማዕከል ቁሳቁስ ግብአት በተገቢው ያልተሟላላቸው፣ 3በ1 የሆነ የስፖርት ሜዳ ያላሟሉና የሰለጠነ መምህር የሌላቸው እንዲሁም የመምህራን ማረፊያ ክፍል ውስጥ ሊኖሩ የሚገባቸው ቁሳቁሶችን እንዳላሟሉ ገልጸዋል። የሁለተኛና መሰናዶ ትምህርት ቤቶችም በተመሳሳይ ለትምህርት ጥራት የተሰጠውን የመመዘኛ መስፈርት ባለማሟላታቸው እንደተዘጉ ተናግረዋል።

    These two Ethiopian students are working to launch their own rocket – the future Eng. Kitaw Ejigu

    በቅድመ መደበኛ ከተዘጉ ትምህርት ቤቶች መካከል ቦሌ ቡልቡላ፣ ሳሊተ ምህረት፣ ቶምናጄሪ፣ ገነተ ኢየሱስ፣ አዲስ ሰው፣ ኤሎን፣ ሀመር፣ ሙሴ፣ ሜሲ ሚዶ፣ ብራስ ዩዝ፣ ንጋት፣ አሀዱ ቤተሰብ፣ ደብል፣ አፍሪካስ ድሪም፣ ባቤጅ፣ ብሪሊያንት፣ አልአፊያ ቁጥር 1፣ ጂ. ኤች፣ ኢስት አፍሪካ፣ ቅዱስ ዮሃንስ፣ አጼ ተክለጊዮርጊስ፣ ሳም ፋሚሊ፣ ኒው ዩኒክ፣ ብራይት የሚጠቀሱ ሲሆን፥ ማራናታ፣ ቦሌ ካውንት፣ ማይ ፊውቸር፣ ሰብለ መታሰቢያ፣ ጎል፣ አካዳሚ ፎር ኤክሰለንስ፣ ፎንት፣ ሰለሞን፣ አፍሪካስ ድሪም፣ ቤተሰብ፣ ቅዱስ ገብርኤል፣ ብሪሊያንት፣ እየሩሳሌም፣ ስሪ ኤስ ሜርሲ ከተዘጉ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ውስጥ ናቸው።

    ከዚህ በተጨማሪ እንጦጦ ወንጌላዊት፣ ማርክ፣ አዲስ አበባ ሉተራንና መካነ ኢየሱስ የሁለተኛ ደረጃ መሰናዶ ትምህርት ቤቶች የተዘጉ መሆናቸውንም ዳይሬክተሯ አስታውቀዋል። ከኤጀንሲው የተገኘ መረጃ እንደሚያመለክተው፤ በከተማዋ በ2011 ዓ.ም ፈቃድ ያገኙ 101 አዲስ ት/ቤቶች የመማር ማስተማር ሥራቸውን ጀምረዋል።

    የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የአጠቃላይ ጥራትና አግባብነት ተቆጣጣሪ ባለስልጣን (ሬጉላቶሪ ኤጀንሲ) የሰጠው መግለጫ

    የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የአጠቃላይ ጥራትና አግባብነት ሬጉላቶሪ ኤጀንሲ የ2010 ዓ.ም የትምህርት ተቋማት የኢንስፔክሽን እና የእውቅና ፍቃድ እድሳት ሪፖርትን በተመለከተ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ

    • የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የአጠቃላይ ትምህርት ጥራትና አግባብነት ሬጉላቶሪ ኤጀንሲ ዳይሬክተር ወ/ሪት ብሩክነሽ አረጋው በ2010 ዓ.ም ከቅድመ መደበኛ እስከ መሰናዶ ድረስ ባሉ የመንግስትና የግል ትምህርት ተቋማት በተካሄደ የኢንስፔክሽን መረጃ መሠረት ተቋማቱ ያሉበትን ደረጃ በዝርዝር አቅርበዋል። በዚሁ መሠረት በቅድመ መደበኛ ትምህርት አገልግሎት ከሚሰጡ ተቋማት መካከል 41 ተቋማቱ ደረጃ 1፣ 560 ደረጃ 2 እንዲሁም 108 ተቋማት ደረጃ 3 እና 1 ተቋም ደረጃ 4 ላይ መሆናቸው ገልፀዋል።
    • በመጀመሪያ ደረጃ በሚገኙ የትምህርት ተቋማት በተደረገ ኢንስፔክሽን 10 ተቋማት በደረጃ 1፣ 409 ተቋማት ደረጃ 2፣ 125 ደረጃ 3፣ እና 1 ተቋም ብቻ ደረጃ 4 ላይ እንደሚገኝ የተጠቆመ ሲሆን በሁለተኛና መሰናዶ ተቋማት ላይ በተካሄደ ኢንስፔክሽን ደግሞ 6 ተቋማት ደረጃ 1፣ 80 ተቋማት ደረጃ 2፣ 66 ተቋማት ደረጃ 3 ላይ ሲገኙ አንድም ተቋም ደረጃ 4 ላይ አለመገኘቱን ነው ዳይሬክተሯ ገልፀዋል።
    • በሌላ በኩል ባለስልጣኑ ከኮተቤ ሜትሮፖሊታን ዩኒቨርሲቲ ጋር በጋራ በመሆን በአዲስ አበባ ደረጃ የ8ኛ ክፍል ክልላዊ ፈተና የተማሪዎች ውጤት ዝቅተኛ የሚሆንበትን ምክንያት በተለመከተ ጥናት ማድረጉ በመግለጫው ከመገለፁ ባሻገር የጥናቱን ውጤትም የኮተቤ ሜትፖሊታን ዩኒቨርሲቲ ምክትል ፕሬዘዳንት ዶ/ር ኤላዛር ታደሰ ያቀረቡ ሲሆን ለ8ኛ ክፍል ውጤት ማሽቆልቆል በዋናነት ከተለዩ ምክንያቶች መካከል ተማሪዎች ለትምህርት ያላቸው አሉታዊ አመለካከት፣ የመምህራን ለደረጃው ብቁ አለመሆን እንዲሁም በየትምህርት ተቋማቱ የሚደረገው (የማስተባበርና መቆጣጠር (የሱፐርቪዥንና ኢንስፔክሽን) አሠራር በቂ አለመሆን እንደምክንያት ተጠቁሟል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እና የአዲስ አበባ ከተማ ትምህርት ቢሮ
    ትምህርት ቤቶች

Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.