በሕክምና ባለሙያዎች የሚታዘዙላቸውን መድኃኒት ለመጠቀም የዋጋ ልዩነት እየተፈታተናቸው መሆኑን ነዋሪዎቹ ገለጹ
—–
በሕክምና ባለሙያዎች የሚታዘዙላቸውን መድኃኒት ለመጠቀም የዋጋ ልዩነት እየተፈታተናቸው መሆኑን የትግራይ ደቡባዊ ዞን ሦስት ከተሞች ነዋሪዎች ገለጹ፡፡
የትግራይ ክልል ጤና ቢሮ በበኩሉ በጤና ተቋማት የሚታየውን የመድኃኒት አያያዝና አጠቃቀም ሥርዓት ለማሻሻል እየሰራሁ ነው ብሏል፡፡
ከከተሞቹ ነዋሪዎች አንዳንዶቹ ለኢ ዜ አ እንዳስታወቁት በመንግሥት ሆስፒታሎች በተመጣጣኝ ዋጋ ይቀርቡላቸው የነበሩትን መድኃኒት ባለማግኘታቸው ከአቅማቸው በላይ ወጪ በማድረግ ለመግዛት ተገደዋል።
በአላማጣ ሆስፒታል በ200 ብር ይቀርብላቸው የነበረውን የስኳር በሽታ መድኃኒት ከግል መድኃኒት ቤት በ400 ብር በመግዛት እየተጠቀሙ መሆናቸውን የከተማው ነዋሪ አቶ መኮንን ይሄይስ ይገልጻሉ፡፡
የሚጥል በሽታ መድኃኒት በ150 ብር ይገዙ እንደነበር የሚናገሩት የመሆኒ ከተማ ነዋሪው አቶ ገብሩ ስዩም ከግል መድኃኒት መደብር በ350 መቶ ብር ገዝቼ እየተጠቀምኩ ነው ይላሉ።ዋጋውም ወርኃዊ ገቢያቸው እየተፈታተነ መጥቷል ይላሉ፡፡
ከኮረም ሆስፒታል በተመጣጣኝ ዋጋ ያገኙት የነበረው የስኳር በሽታ መድኃኒት በ200 ብር ጭማሪ በመግዛት ላይ መሆናቸውን የሚናገሩት ደግሞ የኮረም ከተማ ነዋሪ ሼክ ኢብራሂም ሰዒድ ናቸው፡፡
ለመድኃኒቱ በወር የሚያወጡት 450 ብር ወጪውን መቋቋም እንዳላስቻላቸው ተናግረዋል፡፡
የአላማጣ አጠቃላይ ሆሰፒታል ሥራ አስኪያጅ አቶ ሓዱሽ ኃይሉ ከክልሉ ጤና ቢሮ ለሆስፒታሉ የሚላከው መድኃኒት መቀነስ ለእጥረቱ ዋነኛ ምክንያት መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የማይጨው ሆስፒታል ሥራ አስኪያጅ አቶ ኪዱ ተክሉ ሆስፒታሉ ከቢሮው የሚላክለት መድኃኒት መጠን እያነሰ በመምጣቱ የተገልጋዩን ፍላጎት ማሟላት እንዳልቻለ ተናግረዋል፡፡
ሆስፒታሉ በውስጥ ገቢው ተጠቅሞ እጥረቱን ለማቃለል ቢጥርም፤ ተፈላጊው መድኃኒት በአገር ውስጥ ገበያ ለማግኘት ችግር እንደሚያጋጥም አስታውቀዋል፡፡
ሙሉውን ኢዜአ ላይ ያንብቡ