ሀገር በቀል የመድኃኒት አምራቾች መሠረታዊ ችግሮች በጥናት ሊለዩ ይገባል ― የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅርቦት ኤጀንሲ

Home Forums Semonegna Stories ሀገር በቀል የመድኃኒት አምራቾች መሠረታዊ ችግሮች በጥናት ሊለዩ ይገባል ― የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅርቦት ኤጀንሲ

Viewing 3 posts - 1 through 3 (of 3 total)
  • Author
    Posts
  • #9645
    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦትና የውጪ ምንዛሬ እጥረት ለሀገር በቀል የመድኃኒት እና የሕክምና መገልገያ አምራቾች እውነተኛ ፈተና መሆን አለመሆናቸው በገለልተኛ አካል ሊጠና ይገባል ሲሉ የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅርቦት ኤጀንሲ ባለድርሻ አካላት ተናገሩ።

    ጥር 24 ቀን 2011 ዓ.ም ከሀገር ውስጥ አምራቾች በተደረገው ውይይት የ6 ወር የመድኃኒት አቅርቦት አፈፃፀም 25% መሆኑን ተከትሎ ለአቅርቦቱ ዝቅተኛ አፈፃፀም በተደጋጋሚ በምክንያትነት የሚሰጡት የውጭ ምንዛሪ እጥረትና የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ በገለልተኛ አካል ተጠንቶ ድጋፍ የሚያስፈልገውን በመደገፍ የሚያጭበረብረውን በማጣራት እርምጃ ሊወሰድበት ይገባል ሲሉ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ገልፀዋል።

    ኤጀንሲው ለሀገር ውስጥ አምራቾች በቅድሚያ ክፍያ እንዲሁም 25 በመቶ ጨረታ ላይ እንዲወዳደሩ እንደሚደግፉ የተጠቀሱት አስተያየት ሰጪዎቹ አሁንም አምራቾች መድኃኒቶችን በበቂ መጠን ጥራት ማቅረብ አለመቻላቸው አጠራጣሪ ነው ሲሉ ተናግረዋል።

    ◌ News: Humanwell Healthcare Group inaugurates Humanwell Pharmaceutical Ethiopia PLC in Chacha town

    እንደአስተያት ሰጪዎች ገለጻ ሀገር በቀል አምራቾች ኤጀንሲው የሚሰጣቸው የቅድሚያ ክፍያ ሒሳብ በአግባቡ ቃላቸውን ለመተግበር እያዋሉት መሆኑ ወይም ሌላ ዓላማ መዋሉ ሊጠና ይገባል ብለዋል። አክለውም የሚሰጠውን ገንዘብ ለሌላ የግል ንግድ እየተጠቀሙበት መሆኑን ጥርጣሬ እንዳላቸው ገልጸዋል።

    በተያያዘ ዜና የቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊዎች በአዳማ ከተማ የግማሽ ዓመት አቅድ አፈጻጸም ላይ እንዳሉት ሀገር በቀል የመድኃኒት አምራቾች ኤጀንሲው በሚያቀርበው ገንዝብ ለግል አቅራቢዎች ትርፍ ለማሳደድ እንደሚያውሉት መረጃ አለ ሲሉ ተናግረዋል። ከዚህ በተጨማሪም የሚደረገው ድጋፍ በአግባቡ የመያጠቀሙበት ከሆነ በሂደት እየለዩ እርምጃ ለወሰድ ይገባል ሲሉ ተናግረዋል።

    ከዚሁ ውይይት በተጨማሪ የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅርቦት ኤጀንሲ የጀመረውን ለውጥ ለማስቀጠል አቅርቦቱን የበለጠ ለማሻሻል ብቻውን መስራቱ ውጤታማ ሊያደርገው እንደማይችል የኤጀንሲው የግዥ ትንበያና ገበያ ጥናት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ አብይ ክፍሎም አብራርተው የሀገር ውስጥ አምራቾቹ ሊያስቡበት እንደሚገባም አቶ አብይ አክለው ገልፀዋል።

    ◌ News: SanSheng Pharmaceutical PLC inaugurated in the Eastern Industry Zone in Dukem, Ethiopia

    የአገር ውስጥ አምራቾች አፈፃፀማቸውን መፈተሽ እንዳለባቸውና አፈፃፀማቸው ዝቅ ባለ ቁጥር በመድኃኒት እጦት የሚያልፈውን የሰው ሕይወት ሊያስቡ እንደሚገባ የመድኃኒትና የህክምና መሣርያዎች ግዢ ም/ዋና ዳይሬክተር አቶ ጎይቶም ጊጋር ገልፀዋል።

    የድሬዳዋ ቅርንጫፍ ስራ አስኪያጅ አቶ ሣሙኤል ኃይሉ በበኩላቸው በአሁኑ ሠዓት የመድኃኒት እጥረት እንደ ቀልድ የሚታይ ጉዳይ አይደለም ብለዋል።

    አቅርቦቱ ዝቅ እንዲል ካደረጉ ምክንያቶች መካከል የውጭ ምንዛሬና የመብራት መቆራረጥ በዋናነት በውይይቱ የተጠቀሱ ሲሆን ኤጀንሲው ይህን ለማስተካከል አፈፃፀማቸውን ለመለካት የሚያስችል ነጥቦችን የያዘ ረቂቅ ሰነድ (KPI) ቀርቦ የጋራ ማድረግ ተችሏል።

    በመጨረሻም ከጤና ጥበቃ ሚኒስቴር፣ ከብሔራዊ ባንክ፣ የኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት እና ሌሎች የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት መገኘታቸው በቀጣይ ችግሩን በመቅረፍ የሕብረተሠቡን የመድኃኒት ፍላጎት ለማሟላት ያስችላል ብለዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅርቦት ኤጀንሲ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ 

    የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅርቦት ኤጀንሲ


    #9806
    Anonymous
    Inactive

    በሕክምና ባለሙያዎች የሚታዘዙላቸውን መድኃኒት ለመጠቀም የዋጋ ልዩነት እየተፈታተናቸው መሆኑን ነዋሪዎቹ ገለጹ
    —–

    በሕክምና ባለሙያዎች የሚታዘዙላቸውን መድኃኒት ለመጠቀም የዋጋ ልዩነት እየተፈታተናቸው መሆኑን የትግራይ ደቡባዊ ዞን ሦስት ከተሞች ነዋሪዎች ገለጹ፡፡

    የትግራይ ክልል ጤና ቢሮ በበኩሉ በጤና ተቋማት የሚታየውን የመድኃኒት አያያዝና አጠቃቀም ሥርዓት ለማሻሻል እየሰራሁ ነው ብሏል፡፡

    ከከተሞቹ ነዋሪዎች አንዳንዶቹ ለኢ ዜ አ እንዳስታወቁት በመንግሥት ሆስፒታሎች በተመጣጣኝ ዋጋ ይቀርቡላቸው የነበሩትን መድኃኒት ባለማግኘታቸው ከአቅማቸው በላይ ወጪ በማድረግ ለመግዛት ተገደዋል።

    በአላማጣ ሆስፒታል በ200 ብር ይቀርብላቸው የነበረውን የስኳር በሽታ መድኃኒት ከግል መድኃኒት ቤት በ400 ብር በመግዛት እየተጠቀሙ መሆናቸውን የከተማው ነዋሪ አቶ መኮንን ይሄይስ ይገልጻሉ፡፡

    የሚጥል በሽታ መድኃኒት በ150 ብር ይገዙ እንደነበር የሚናገሩት የመሆኒ ከተማ ነዋሪው አቶ ገብሩ ስዩም ከግል መድኃኒት መደብር በ350 መቶ ብር ገዝቼ እየተጠቀምኩ ነው ይላሉ።ዋጋውም ወርኃዊ ገቢያቸው እየተፈታተነ መጥቷል ይላሉ፡፡

    ከኮረም ሆስፒታል በተመጣጣኝ ዋጋ ያገኙት የነበረው የስኳር በሽታ መድኃኒት በ200 ብር ጭማሪ በመግዛት ላይ መሆናቸውን የሚናገሩት ደግሞ የኮረም ከተማ ነዋሪ ሼክ ኢብራሂም ሰዒድ ናቸው፡፡

    ለመድኃኒቱ በወር የሚያወጡት 450 ብር ወጪውን መቋቋም እንዳላስቻላቸው ተናግረዋል፡፡

    የአላማጣ አጠቃላይ ሆሰፒታል ሥራ አስኪያጅ አቶ ሓዱሽ ኃይሉ ከክልሉ ጤና ቢሮ ለሆስፒታሉ የሚላከው መድኃኒት መቀነስ ለእጥረቱ ዋነኛ ምክንያት መሆኑን ገልጸዋል፡፡

    የማይጨው ሆስፒታል ሥራ አስኪያጅ አቶ ኪዱ ተክሉ ሆስፒታሉ ከቢሮው የሚላክለት መድኃኒት መጠን እያነሰ በመምጣቱ የተገልጋዩን ፍላጎት ማሟላት እንዳልቻለ ተናግረዋል፡፡

    ሆስፒታሉ በውስጥ ገቢው ተጠቅሞ እጥረቱን ለማቃለል ቢጥርም፤ ተፈላጊው መድኃኒት በአገር ውስጥ ገበያ ለማግኘት ችግር እንደሚያጋጥም አስታውቀዋል፡፡

    ሙሉውን ኢዜአ ላይ ያንብቡ

    #10320
    Semonegna
    Keymaster

    የሕክምና መሣሪያዎችን በሀገር ውስጥ ለማምረት የሚያስችል ስምምነት ተፈረመ
    —–

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– የሕክምና መሣሪያዎችን በሀገር ውስጥ ለማምረት የሚያስችል ስምምነት መጋቢት 10 ቀን 2011 ዓ.ም. ተፈረመ።
    ስምምነቱ በቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ሚኒስቴር፣ በንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ፥ በጤና ሚኒስቴር እና በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን መካከል ነው የተፈረመው።
    ስምምነቱ በሀገሪቱ ያለውን የሕክምና መሳሪዎችን ፍላጎት ለማሟላትና ለግዢ የሚወጣውን የውጪ ምንዛሪ ለመቀነስ ያስችላል።

    ምንጭ፦ የጤና ሚኒስቴር / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

Viewing 3 posts - 1 through 3 (of 3 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.