የኤሌክትሪክ መሠረተ ልማት አዉታሮች ስርቆትና የተጠቃሚ ደንበኞች ሰቆቃ

Home Forums Semonegna Stories የኤሌክትሪክ መሠረተ ልማት አዉታሮች ስርቆትና የተጠቃሚ ደንበኞች ሰቆቃ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #11718
    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት) – ኤሌክትሪክ ለአንድ ሃገር ሁለንተናዊ የዕድገት እንቅስቃሴ የማይተካ ሚና ያለው መሆኑ የሚያጠያይቅ አይደለም። ይሁን እንጂ ይህንን መሠረታዊ የሆነውን ዘርፍ ለሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች ለማዳረስና ተጠቃሚ ለማድረግ እየተደረገ ባለው ጥረት፤ በኤሌክትሪክ መሠረተ-ልማቱ ላይ የሚደረሱ አደጋዎችና ስርቆቶች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተበራከቱ መጥተዋል።

    የኤሌክትሪክ መሠረተ-ልማት አውታሮች የኤሌክትሪክ ኃይል ተጓጉዞ ደንበኞች ጋር የሚደርስበትና ደንበኛው የኤሌክትሪክ ተጠቃሚ እንዲሆን ለማድረግ የሚረዱ ግብዓቶች ቢሆኑም፤ በሚደርስባቸው ጉዳትና ስርቆት የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ድርጅት (ተቋም) የተጠቃሚውን የኃይል ፍላጎት ለሟሟላት እያደረገ ያለውን ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ አድረጎታል።

    ትራንስፎርመር ደግሞ ከእነዚህ ግብዓቶች አንዱና መሠረታዊ ነው። ለደንበኞች የኤሌክትሪክ ኃይል ለማሰራጨት ሚናው ከፍተኛ ሲሆን፤ የኃይል ፍላጎት ሲጨምር የትራንስፎርመሩን አቅም ለማሳደግ ካልሆነ በስተቀር መነካካት፣ ለማንሳት ወይም ለማንቀሳቀስ መሞከር እጅግ አደገኛ ከመሆኑ በላይ ለንብረትና ህይወት መጥፋት መንስዔ ይሆናል። ነገር ግን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ይህንን ችላ በማለት የስርጭት ትራንስፎርመር ስርቆት በስፋት እየተከናወነ መጥቷል። በዚህም በተቋሙ ላይ ከፍተኛ ኪሳራ እያደረሰና የአብዛኛው ደንበኞች የኤሌክትሪክ ተጠቃሚነት እያስተጓጎለ ይገኛል። ለዚህ ማሳያ ሰሞኑን በአንዳንድ የአዲስ አበባ አካባቢዎች የኤሌክትሪክ መሠረተ-ልማት ላይ እየደረሰ ያለውን ጉዳትና ስርቆት መጥቀስ ይቻላል።

    በአዲስ አበባ ከተማ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ስር በሚገኙት አራት ዲስትሪክቶች መካከል በደቡብ አዲስ አበባ ዲስትሪክት ሁለት ትራንስፎርመሮች እንዲሁም በምስራቅ አዲስ አበባ ዲስትሪክት 3 ትራንስፎርመርመሮች እና ሌሎችም በርካታ ንብረትነታቸው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የሆኑ እና ለሰፊው የህብረተሰብ ክፍል የኤሌክትሪክ አገልግሎት ይሰጡ የነበሩ ንብረቶችን ኃላፊነት በጎደላቸው እና የራሳቸውን ኪስ ከመሙላት ባለፈ ለሀገራቸው በማያስቡ ጥቂት ግለሰቦች ተዘርፈዋል።

    ዝርፈያው የተፈፀመው ጨለማን ተገን በማድረግና በመስመሩ ላይ ኃይል በማይኖርበት ወቅት በመጠቀም ነው። ይህ በተቋምና ህዝብ ንብረት ላይ ከፍተኛ ኪሳራ የሚያደርስ ህገወጥ ተግባር ሲሆን፤ ህብተረሰቡ የኤሌክትሪክ ኃይል በአግባቡ እንዳያገኝም የሚያደረግ ነው። በመሆኑም ህብረተሰቡ ይህንን አውቆ በአካባቢው የሚገኙ የተቋሙ ብሎም የሀገር ንብረቶች የሆኑቱን የኤሌክትሪክ መሠረተ ልማት አውታሮች እንደራሱ ንብረት ሁልጊዜ በንቃት እንዲጠብቅ ተቋሙ ይጠይቃል።

    ጥገና የሚያከናውኑ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ተቋም ባለሞያዎች በመምሰል ንብረቱን የሚነካኩ፣ የሚበጥሱ፣ የሚቀይሩ እና ሌሎች ሕገ-ወጥ ተግባሮችን የሚፈፅሙ ግለሰቦች ሲመለከት ህብረተሰቡ ሊከላከላቸው ይገባል።

    የተቋሙ ሠራተኞች ቢሆኑም እንኳን ሕጋዊ መታወቂያ መያዛቸውን፣ መለያ ባጅ (badge) ማድረጋቸውንና የደንብ ልብስ መልበሳቸውን ማረጋገጥ፣ ክትትልና ቁጥጥር ማድረግም ያስፈልጋል። እንዲሁም የሚያጠራጥር ሁኔታ ካለ በተቋሙ 905 ነፃ የጥሪ ማዕከል በማሳወቅ፣ በአካባቢው በሚገኝ የተቋሙ የአገልግሎት መስጫ ማዕከል በመጠቆምና ከሚመለከተው የህግ አካላት ጋር በጋር በመተበባር ማስቆም እንደሚገባ ተቋሙ ያሳስባል።

    የኤሌክትሪክ መሠረተ ልማት በከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ የሚገዙና የህዝብ ሃብት የፈሰሰባቸው በመሆናቸው፣ ሁሉም ህብረተሰብ እንደራሱ ንብረት ሊጠብቃቸው ይገባል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ 

    የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት


Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.