የምርምር ቴክኖሎጂ ውጤቶች ሚና በከተማ ግብርና – የኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት

Home Forums Semonegna Stories የምርምር ቴክኖሎጂ ውጤቶች ሚና በከተማ ግብርና – የኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #9579
    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (EIAR) – የኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የአርሶ አደሩን እንዲሁም አርብቶና ከፊል አርብቶ አደሩን የአገሪቱ ማህበረሰብ ኑሮ የተሻለ ለማድረግ ብሎም የግብርናው ዘርፍ ዘላቂ እድገት እንዲያስመዘግብ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል።

    ኢንስቲትዮቱ የገጠሩን ማህበረሰብ ምርታማነት ከማሣደግም ባለፈ በከተማ ዙሪያ የሚኖሩ የማህበረሰብ ክፍሎችን ዘመናዊ የግብርና ዘዴዎችን በማስተዋወቅ አምራች እንዲሆኑ ለማስቻል እየሠራ ይገኛል ። በዚህም በምርምር የሚያወጣቸውን ከአካባቢ ስነ ምህዳር እንዲሁም አየር ንብረት ጋር ተስማሚ የሆኑ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን ለከተማ አርሶና አርብቶ አደሮች የማስተዋወቅና የማስፋፋት ሥራ ሲሠራ ቆይቷል። ተቋሙ ይህንን እንቅስቃሴ አጀንዳው አድርጎ መሥራት የጀመረው በ2009ዓ.ም ሲሆን በኢንስቲትዩቱ የቴክኖሎጂ ስርፀትና ኮሜርሻላይዜሽን ምርምር ዳይሬክቶሬትም ይህንኑ ተግባር እያስተባበረ ይገኛል።

    ቪዲዮ፦ እየተገነቡ ያሉት የግብርና ማቀነባበሪያ የኢንዱስትሪ ፓርኮች ለሀገሪቱ የእርሻ ሴክተር እና ኢኮኖሚ የሚኖራቸው አስተዋጽኦ

    ከከተማ ግብርና የሚገኝ ምርት የምግብ ስርዓትን በማሳደግ ጤናማ ማህበረሰብ ለመገንባት አይነተኛ አስተዋጽኦ አለው። ለዚህም እንደ ማሳያ ማህበረሰቡ በአነስተኛ ቦታ ዘመናዊ የግብርና ዘዴዎችን በመጠቀም ለጤና ጠቃሚ የሆኑ የግብርና ምርቶችን በማምረት ለለት ተእለት ፍጆታው ማዋል ሲጀምር የምግብ ደህንነቱ ከመጠበቁም በተጨማሪ በምርቱ ጥራት ላይ የሚኖረው እምነት ይጨምራል። ከዚሁ ጋር በተያያዘም እንደ ትራንስፖርት፣ የዘመናዊ እህል ማከማቻ ቦታ እጥረት እንዲሁም የገበያ ችግርና የመሣሠሉ በተለያዩ ምክንያቶች የሚከሰቱ የድህረ ምርት ብክነት መንስኤዎችን ለመቀነስ ያስችላል። የከተማው ማህበረሰብ የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኝ በማድረግ ጤናማ ማህበረሰብ መፍጠር ያስችላል፤ በከተሞች የሚኖረው የምግብ ዋስትና ችግር ከእናቶችና ህፃናት ጤና ከፍተኛ የሆነ ትስስር ያለው በመሆኑ የስርዓተ-ምግብ ዋስትና ከማረጋገጥ አንጻር ከፍተኛ ፋይዳ አለው።

    ኢንስቲትዩቱ ለከተማ ግብርና ልማት ሥራ በሚረዱ ቴክኖሎጂዎች ላይ ምርምር እንደሚሠራና ከኢንስቲትዩቱ የወጡ ከነባር የዶሮ ዝርያዎች የተሻለ የምርት ልዩነት የሚሠጡ የዶሮ ዝሪያዎች፤ ከአንድ የወት ላም በቀን ውስጥ ሊገኝ የሚችለውን የወተት መጠን ማሣደግ የቻሉ የተሻሻሉ የላም ዝርያዎች ፤ እንዲሁም የተለያዩ የሠብል፣ የአትክልትና ፍራፍሬ ቴክኖሎጂዎችም ወደ ተጠቃሚ ተሸጋግረው ማህበረሰቡ ውጤታማ ምርት ማምረት የሚያስችለውን አሠራር በመዘርጋት የምግብ ደህንነትን ለማስጠበቅ እየሠራ ይገኛል ። በዚህም የማህበረሰቡ አካል የሆኑ በርካታ ሴቶችና ወጣቶች ተጠቃሚ የሚሆኑባቸው የሥራ እድሎችን ይፈጥራል። ይህንንም እንደ መነሻ በመውሠድ ተቋሙ እነዚህን የከተማ ግብርና ሥራዎች ለማስፋፋትና በምርምር ያወጣቸውን የሰብልና እንሠሣት ቴክኖሎጂዎች በስፋት ለተጠቃሚዎች ለማዳረስ ከፍተኛ እንቅስቀሴዎች ሲያካሂድ ቆይቷል።

    ቪዲዮ፦ የተሻሻሉ የአቦካዶ ምርቶች ለገበሬዎች መልካም ምርት እየሰጡ ነው

    ከኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት በምርምር የሚወጡ የሰብል፣ እንስሳትና ተፈጥሮ ሀብት ቴክኖሎጂዎች በመሠረታዊነት የገጠሩን ህዝብ ያማከሉ ቢሆኑም ቴክኖሎጂዎቹ ውጤታማ በመሆን ከፍተኛ ምርት መስጠት ከሚያስችላቸው አየር ንብረትና ሌሎች ተያያዥ ግብአቶች ጋር ተቀራራቢ ስነምህዳር ባላቸው ከተማዎች እንዲሁም ከተማ ቀመስ ለሆኑ አካባቢዎች በቀላሉ እንዲላመዱ በማድረግ የሚታሠበውን ውጤት ማምጣት ይቻላል ። በተለይም የተሻሻሉ የአትክልትና ፍራፍሬ ቴክኖሎጂዎች፣ የእንስሳት መኖ ቴክኖሎጂዎች፣ የመዓዛማና መድሀኒት ሠብሎች፣ የዶሮ ቴክኖሎጂዎች እንዲሁም ከተፈጥሮ ማዳበሪያና አካባቢ ጥበቃ ጋር የተያያዙ ምክረ ሃሳቦችን ለከተማ ግብርናም በቀላል ወጪ እንዲሁም አነስተኛ ቦታ ተግባራዊ መሆን የሚችሉ ናቸው።

    የኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ከኦሮሚያ ክልል ፊንፊኔ ልዩ ዞን በረህ ወረዳና በዚሁ ወረዳ የተለያዩ ማኅበራዊ እንቅስቃሴዎችን እያከናወነ የሚገኘው የልማትና የአቅም ግንባታ ማዕከል (Center for Development and Capacity Building – CDCB) ፕሮጀክት ጋር በመተባበር የአካባበቢውን ማህበረሰብ በማስተባበር አዳዲስ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን የማስተዋወቅና የማስፋት እንዲሁም የቴክኖሎጂ ዘር ብዜት ተግባራትን የማከናወን ኃላፊነት ወስዶ ሲሠራ ቆይቷል። በዚህም በበርህ ወረዳ ሮጌ ቀበሌ የሚገኙ ነዋሪዎችን በክላስተር በማቀናጀት የሰንዴ ቴክኖሎጂ የዘር ብዜት ሥራ ተካሂዷል። በተጨማሪም በአካባቢው የአርሶ አደር ማሳ ላይ የሽብምራ ቴክኖሎጂ ሠርቶ ማሳያ በማከናወን በሌሎች የአካባቢው ማኅበረሰቦች እንዲጎበኝ ተደርጓል። በተመሳሳይም በዚሁ ወረዳ ሞጎሮ ቀበሌ የሚኖሩ የአካባቢው አርሶአደሮችን በክላስተር በማደራጀት የስንዴ ዘር ብዜት ማከናወን የቻሉ ሲሆን፣ በቀበሌው የአርሶ አደር ማሰልጠኛ ማዕከል የተከናወኑ የተለያዩ የግብርና ቴክኖሎጂ ሙከራዎችም ተካሂደዋል። የሰንዴና የጤፍ ሠርቶ ማሳያዎችን፣ የአርሶ አደር ማሰልጠኛ እንዲሁም የዶሮ ምግብ ማቀነባበርያ ማዕከላትም በወረዳው በሚገኝ ለገቦሎ ቀበሌ የተከናወኑ ተግባራት ናቸው።

    በግብርናው ዘረፍ የሚሠሩ የተለያዩ የመንግስት ፓሊሲ አውጪዎችን ጨምሮ የግብርና ተመራማሪዎች፣ የዞንና የወረዳ የግብርና ሃላፊዎችና ባለሙያዎች፣ የአካባቢው አርሶ አደሮች እንዲሁም ሌሎች የሚመለከታቸውን አካላት በማሳተፍ በከተማ ግብርና ዙሪያ የተሠሩትን ውጤታማ የሆኑ የቴክኖሎጂ ሠርቶ ማሳያና የዘር ብዜት ሥራዎች በመጎብኘትና ውይይት በማድረግ ውጤታቸውን በጋራ ለመገምገምና ግብረመልስ ለማሰባሰብ እንዲሁም በኢንስቲትዩቱ፣ በወረዳውና በCDCB በቅንጅት የተሠሩትን የቴክኖሎጂ ማስተዋወቅና ማስፋት ሥራዎችን በማሳየትና ውይይት በማድረግ ቋሚ የሆነ ትስስር ለመፍጠር የሚረዳ የመስክ ቀን ህዳር 16 ቀን 2011 ዓ.ም. በኦሮሚያ ክልል ፊንፊኔ ልዩ ዞን በረህ ወረዳ ሮጌ፣ ሞጎሮና ለገቦሎ ቀበሌዎች ተካሂዷል።

    VIDEO: Making Ethiopians not only have food per se but nutritious and quality food – Bless Agri Food Lab

    የኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት በኦሮሚያ ክልል ፊንፊኔ ልዩ ዞን የከተማ አካባቢ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚነት ማዕከል በማድረግ በ2010/11 መኸር ወቅት የቴክኖሎጂ አቅርቦት፣ ማስተዋወቅ እና አቅም ግንባታ ስልጠናዎች ሲያከናውን ቆይቷል። እነዚህ ተግባራትም ከምርምር ማዕከል የሙከራ ጣቢያዎች ጀምሮ እስከ ቴክኖሎጂ ተጠቃሚዎች ድረስ በስፋት በማሳተፍ የተከናወኑ ሲሆን አላማውም አዳዲስና የተሻሻሉ ዝርያዎችን ለተጠቃሚዎች በማቅረብ፣ የመነሻ ቴክኖሎጂ ብዜት ሥራዎችን በማካሄድንና የአቅም ግንባታ ሥራዎችን በማከናወንን በአገሪቱ ውጤታማ የሆነ የከተማ ግብርና ማስፋፋት ነው። ኢንስትቲዩቱ በዘርፉ ውጤታማ ከሆኑ ሀገራት ቴክኖሎጂ፣ እውቀትና ልምድ በመውሰድ ለአገሪቱ ስነምህዳር ተስማሚና ኢኮኖሚያዊ እድገት አስተዋጽኦ ሊያበረክቱ የሚችሉና ለከተማ ግብርና አመቺ የሆኑ ቴክኖሎጂዎችን በመለየት የማላመድ ሥራ በመሥራት ጥቅም ላይ እያዋለ ይገኛል። ለውጤታማነቱም ተቋማዊ ድጋፍ በማድረግ፣ ለተጠቃሚዎች ስልጠና በመስጠት፣ ከስልጠናም በኋላ ተገቢው የቴክኖሎጂ አጠቃቀም በሥራ ላይ እንዲውል ክትትልና ድጋፍ በማድረግ እንዲሁም ከሌሎች የሚመለከታቸው አካላት ጋር በመተባበር የገበያ ትስስር በመፍጠር የበኩሉን አስተዋጽኦ እየተወጣ ይገኛል።

    ሆኖም የከተማ ግብርና ተግባራት ሂደት ከዚህ በተሻለ ፍጥነት ወደፊት እንዲራመድ ለማስቻል ዘርፉ በቴክኖሎጂና እውቀት ሊታገዝ የሚገባው ሲሆን ተግባራቱም በከተማ ውስጥ ባሉ አነስተኛ ቦታዎችና ተፈጥሮ ሃብት ሊተገበሩ የሚችሉ መሆን ይኖርባቸዋል ይላሉ በዘርፉ ለረጅም ጊዜያት ያገለገሉ የግብርና ባለሞያዎች። ከዚህ በተጨማሪም የህብረተሰብ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ በኢኮኖሚ ዝቅተኛ ደረጃ ላይ የሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎችን መሠረት ያደረገ ሊሆን እንደሚገባም ይጠቁማሉ። የተጠቃሚዎችን አቅም ሊገነቡ የሚችሉ የልምድ ልውውጥና የግንዛቤ መፍጠር ሥራን ማከናወን ለሥራው ዘለቄታዊነት መፍትሄ ሊሆን እንደሚገባም ይጠቅሳሉ።

    በተለይም በዝቅተኛ የእለት ገቢ ራሣቸውን የሚያስተዳድሩ በከተማ አካባቢ የሚኖሩ የህብረተሰብ ክፍሎች ጉዳዩ በቀጥታ በሚመለከታቸው አካላት ቀና ድጋፍ በአነስተኛ ቦታ ማምረትና ህይወታቸውን መቀየር የሚያስችላቸውን መንገድ መፍጠር፤ የተጀመሩትንም ሥራዎች አጠናክሮ መቀጠል ያስፈልጋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት (EIAR) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት


Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.