የጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ ለሰላማዊ የመማር ማስተማር ሒደት ትኩረት መስጠቱን አስታወቀ
—–
የጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሒደቱን ለማስቀጠልና መልካም ስነ-ምግባር የተላበሰ ምሁር ላማፍራት እየሰራ መሆኑን አስታወቀ።
በተለያየ አጋጣሚ ሰላምን ሊያውክ የሚችል የስነ-ምግባር ችግር በታየባቸው ተማሪዎች ላይም አስተዳደራዊ እርምጃ መውሰዱን ጨምሮ ገልጿል።
የዩኒቨርሲቲው ፕሬዘዳንት ዶክትር ኡጁሉ ኡኮክ ዛሬ ለኢዜአ እንደገለጹት መደበኛውን የመማር ማስተማር ሒደት ሰላማዊ ለማድረግ ሁሉንም ያሳተፈ እንቅስቃሴ እየተደረገ ነው።
በግቢው የሚካሔደው የትምህርት አሰጣጥ ውጤታማ እንዲሆንም የማሪዎችን ስነምግባር ከመከታተል ጀምሮ አስፈላጊው ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።
በቅርቡም በዩኒቨርሲቲው ቅጥር ግቢ ውስጥ ተገቢ ያልሆነ ተግባር የተፈጸመ በማስመሰል ተማሪዎችን ለሁከት ለማነሰሳት ሲሰሩ የተደረሰባቸው 30 ተማሪዎች ላይ አስተዳደራዊ እርምጃ መወሰዱን ተናግረዋል።።
“ከነዚህ ውስጥም 13ቱ የስንብት፣ 10 ተማሪዎች ከአንድ እስከ ሁለት ዓመት ከዩኒቨርሲቲው የታገዱ ሲሆን ሰባት ተማሪዎች ላይ ደግሞ የመጨረሻ የጹሁፍ ማስጠንቀቂያ እርምጃ ተወሰዷል” ብለዋል።
ዩኒቨርሲተው እርምጃውን ለመውሰድ የተገደደው የተቋሙን ስርዓትና ደህንነት ለማከበር መሆኑን ተናግረዋል።
ተማሪዎች የተወሰደባቸው እርምጃ ተገቢ አደለም በሚል ቅሬታ ማቅረባቸውንና ጉዳያቸውም በቅሬታ ሰሚ ኮሚቴ እንደገና እየታየላቸው እንደሚገኝ ገልጸዋል።
“በቀጣይም የዩኒቨርሲቲውን ህግና ደንብ የሚጥስ ተማሪ ከተገኘ ተመሳሳይ እርምጃ የመውሰዱ ተግባር ተጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል” ብለዋል።
የጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ በ2006 ዓ.ም. የተቋቋመ ሲሆን ይዞታው ያልታጠረ በመሆኑ ለጸጥታ ችግር የተጋለጠ መሆኑን የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ አባላት ይገልጻሉ።
ምንጭ፦ ኢዜአ