የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር በአዲስ አበባ የተለያዩ የጤና ተቋማትን ጎበኙ
—–
ኢትዮጵያ በጤናው ዘርፍ እያደረገች ያለችው እንቅስቃሴ ከጊዜ ወደ ጊዜ ከፍተኛ መሻሻሎችን እያሳየ መምጣቱ ተገለፀ፡፡
የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር የሆኑት ዶ/ር ቴዎድሮስ አድሀኖም በዛሬው እለት አዲስ አበባ የሚገኘውን የጃን ሜዳ ጤና ጣቢያ እና የቅዱስ ጴጥሮስ ሆስፒታልን ተዘዋውረው ጎብኝተዋል፡፡ ዋና ዳይሬክተሩ በጃን ሜዳ ጤና ጣቢያ በቤተሰብ ጤና ቡድን በጤና ጣቢያው ባለሙያዎች ቤት ለቤት እየተሰጡ ያሉ የጤና አገልግሎቶችንም በተገልጋዮቹ ቤተሰቦች ቤት በመገኘት ጎብኝተዋል፡፡
የጃንሜዳ ጤና ጣቢያ ዝቅተኛ ኢኮኖሚ ላላቸው ግለሰቦች ቤታቸው ድረስ በመሄድ በአይነቱ አዲስ የሆነ የህክምና ግልጋሎት የሚሰጥ ሲሆን ታካሚዎቹ ተጨማሪ ህክምና ካስፈለጋቸው ወደ ጤና ጣቢያው ሪፈር እንደሚያደርጋቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡
በቅዱስ ጴጥሮስ ሆስፒታል ጉብኝታቸው መደሰታቸውን የገለፁት ዶ/ር ቴዎድሮስ ሆስፒታሉ የልብ ቀዶ ህክምና መጀመሩና በመመረዝ ህክምና ዙሪያ እያደረገ ያለው እንቅስቃሴ የሆስፒታሉን እመርታ እንደሚያሳይ ተናግረዋል፡፡
“ጤና ለሁሉም” በሚለው የዓለም ጤና ድርጅት መርህ መሰረት የዓለም ጤና ድርጅት ከኢትዮጵያ ጋር በጋራ ለመስራት ስምምነት ላይ መድረሳቸውን ዋናው ዳይሬክተሩ የተናገሩ ሲሆን የሀገሪቷ ከፍተኛ የጤና አመራሮች ለጤናው ዘርፍ ስርዓት መጠናከር የሰጡትን ትኩረት አድንቀዋል፡፡
ምንጭ፦ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር