“ጀግኒት ዓለመች፣ አቀደች፣ አሳካች” በሚል መሪ ቃል አገር አቀፍ ጉባዔ ሊደረግ ነው ― ጀግኒት ንቅናቄ

Home Forums Semonegna Stories “ጀግኒት ዓለመች፣ አቀደች፣ አሳካች” በሚል መሪ ቃል አገር አቀፍ ጉባዔ ሊደረግ ነው ― ጀግኒት ንቅናቄ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #8328
    Semonegna
    Keymaster

    የኢ.ፌ.ዴ.ሪ የሴቶችና ሕፃናት ጉዳይ ሚኒስቴር በበጎ ፈቃደኛ ኢትዮጵያውያን ሴቶች የተቋቋመውን ጀግኒት የተሰኘ የማህበረሰብ ንቅናቄ በይፋ ለመመሥረት እና አገር አቀፍ የሴቶች የሰላም ጉባዔ ለማካሔድ ዝግጅት መጀመሩን አስታውቋል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – ጀግኒት ንቅናቄ ከኢ.ፌ.ዴ.ሪ የሴቶችና ሕፃናት ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር በመተባበር “ጀግኒት ዓለመች፣አቀደች፣ አሳካች” በሚል መሪ ቃል የሚያዘጋጁትን አገር አቀፍ ጉባዔ አስመልክቶ ዘጠኙ ሴት ሚኒስትሮች፣ እንዲሁም የሁለቱ ምክር ቤት አፈ-ጉባዔና ምክትል አፈ ጉባዔ በተገኙበት ጋዜጣዊ መግለጫ መሰጠቱን ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት (ኤፍ.ቢ.ሲ) ዘግቧል።

    ከዘጠኙ ክልሎች እና ከሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ ሴቶች የሚሳተፉበት አገር አቀፍ የሴቶች የሰላም ጉባዔ የፊታችን ጥቅምት 26 ቀን 2011 ዓ.ም እንደሚካሄድም በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ይፋ ተደርጓል።

    በመግለጫው ላይ ንግግር ያደረጉት የሴቶች፣ ህፃናትና ወጣቶች ሚኒስትር ወ/ሮ ያለም-ፀጋይ አስፋው፥ “ጅግኒት ዓለመች፣ አቀደች፣ አሳካች” በሚል መሪ ቃል የሚደረገው አገር አቀፍ ጉባዔ በሀገሪቱ ውስጥ ዘላቂ ሰላም በማረጋገጥ፤ የሴቶችና ሕፃናትን የአደጋ ተጋላጭነት በመቀነስ መብትና ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ እና ሴቶች ሰላም በአጠቃላይ መከበር ላይ ያላቸውን አስተዋጽዖና ግብዓት ለማሳደግ ነው ብለዋል። እንዲሁም የሴቶችና ሕፃናትን ደኅንነት በዘላቂነት ለማረጋገጥ በየአከባቢው ሴቶች ለሰላማቸው ጠንክረው እንዲሠሩ ለማድረግም ነው በማለት አክለዋል።

    ጀግኒት የተሰኘው የማህበረሰብ ንቅናቄ በአገሪቱ የሴቶችን ጥንካሬ ከተተኪነት በላይ ራሳቸው ለተሻለ ነገር የሚያበቁ እና ብቁ ትውልድ የሚያፈሩ መሆናቸውን ለማሳየት ያስችላል ተብሏል። በአሁን ሰዓት ሴቶች በአገሪቱ ልማትና እድገት ላይ በየደረጃው እየተወጡ ያለው ከፍተኛ አስተዋጽዖ ለሁሉም የኅብረተሰብ ክፍል በማሳወቅና በማሳየት ክብርና ዕውቅና ማግኘት እንዲችሉ ያደርጋል ተብሎ ተብራርቷል።

    ከንቅናቄው በኋላ የሴቶች የልማት ጥምረት ይመሰረታል የተባለ ሲሆን፥ ይህም በሴቶችና ህፃናት ዙሪያ የሚንቀሳቀሱ አካላት ለማጠናከር፣ በዘላቂ ሰላም ማረጋግጥና ሴቶች በልማቱ ያላቸው ተሳታፊነትና ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ዙሪያ የራሱ ድርሻ እንደሚኖረው ተጠቁሟል።

    ከዚህ ጋር በተያያዘ ኢትዮጵያ ውስጥ ከጾታ እኩልነት ጀምሮ እስከ አጠቃላይ ዲሞክራሲ እንዲሰፍን፥ ከቅርብ ወራት ወዲህ በአገሪቱ የተጀመረውን ለውጥ ለማፋጠንም ንቅናቄው አስተዋፅኦው የጎላ ይሆናል ተብሏል።

    በጋዜጣዊ መግለጫው ወቅት ለሚኒስትሮቹ አሁን ያለውን የሴት ሚኒስትሮች ቁጥር ለማስቀጠልም ሆነ በአጠቃላይ በፖለቲካ ውስጥ የሴቶችን ተሳትፎ ለማጎልበት ምን ታስቧል ተብሎ ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ የሰጡት የሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል፥ ብዙ አቅም ያላቸው ሴቶች እንዳሉና ንቅናቄው እስከ ወረዳ ድረስ የሚካሄድ በመሆኑ አቅም ያላቸውን ሴቶች ወደ ከፍተኛ የስልጣን እርከኖች ማምጣት ይቻላል ብለዋል።

    ጀግኒት ንቅናቄን ለመቀላቀል ወይም ደግሞ ስለንቅናቄው የበለጠ ለመረዳት በፌስቡክ ገጻቸው (Jegnit) ወይም በትዊተር አድራሻቸው (@jegnit) ያግኟቸው።

    ምንጭ፦ ኤፍ.ቢ.ሲ እና የጀግኒት ንቅናቄ ማኅበራዊ ገጾች

    ጀግኒት ንቅናቄ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.