ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ በሰብዓዊ መብት ጥሰት፣ በሰኔ 16ቱ የቦንብ ጥቃት፣ በሜቴክ አመራሮች የተፈፀመው ሙስና የሰጠው መግለጫ

Home Forums Semonegna Stories ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ በሰብዓዊ መብት ጥሰት፣ በሰኔ 16ቱ የቦንብ ጥቃት፣ በሜቴክ አመራሮች የተፈፀመው ሙስና የሰጠው መግለጫ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #8489
    Semonegna
    Keymaster

    ጠቅላይ ዐቃቤ ሕጉ አቶ ብርሀኑ ጸጋዬ በሰጡት መግለጫ፥ እስካሁን ድረስ በጥቅሉ 63 የሚደርሱ ግለሰቦች በቁጥጥር ስር የዋሉ ሲሆን፥ ከእነዚህም 27 ግለሰቦች በሙስና፣ 36 ደግሞ በሰብዓዊ መብት ጥሰት ምክንያት በቁጥጥር ስር የዋሉ ናቸው።

    አዲስ አበባ – ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ህዳር 3 ቀን 2011 ዓ.ም በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ በተለያዩ ቦታዎች የተፈጸሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰት፣ ሰኔ 16 ቀን 2010 ዓ.ም በተከሰተው የቦምብ ጥቃት እንዲሁም በሜቴክ አመራሮች በተፈፀመው የሙስና ወንጀል በተመለከተ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጠ።

    ጠቅላይ ዐቃቤ ሕጉ በሰጡት መግለጫ መሰረት እስካሁን በቁጥጥር ስር የዋሉት በጥቅሉ 63 የሚደርሱ ናቸው። ከእነዚህም 27 በሙስና፣ 36 ደግሞ በሰብዓዊ መብት ጥሰት ናቸው። በሙስና ወንጀል የተጠረተሩትን ግለሰቦች በቁጥጥር ስር ከማዋላችን በፊት ማስረጃዎችን በማሰባሰብ ሂደት ላይ እያለን እንዚህን ማስርጃዎች ማለትም ሊብሬ፣ የአክስዮን ደብተር፣ የቤት ካርታዎች ፣ የባንክ ደብተር የቤት ሽያጭ ውሎች፣ ጦር መሣሪያዎች ማግኘትት ተችሏ በኤግዚብትነትም ተይዘዋል ብለዋል።

    ጠቅላይ አቃቤ ሕጉ አሁንም የምንጠረጥራቸው ነገር ግን በአገር ውስጥና በውጪ ተሸሽገው ያሉ አሉ። በውጪ ያሉትን መንግስታቶቹ አሳልፈው እንዲሰጡን ተንጋግረር አገራቱ አሳልፈው እንደሚሰጡን ቃል ገብተውልናል ሲሉ ሀገር ውስጥ ያሉት ደግሞ ራሳቸውን ወደ ሕግ እንዲያቀርቡ እንዲሁም ህብረተሰቡ በመተባበር ጥቆማ እንዲሰጥ እና ሰላማዊ በሆነ መልኩ የፍትህ ሂደታቸውን እንዲከታተሉ ጥሪ እናቀርባለን ብለዋል።

    በቁጥጥር ስር ስለ ዋሉ ግለሰቦች አቃቤ ሕጉ በመግለጫው ካነሷቸው አንኳር ነጥቦች መካከል ምርመራው ከ5 ወር በላይ የፈጀ ሲሆን የዚህ ምክንያቱም በቁጥጥር ስር የዋሉ ግለሰቦችን አስረን ከማጣራት አጣርተን ለማሰር ስለሞከርን ነው። ማንንም ተጠርጣሪ ሳንይዝ ነው ያጣራንው። በቁጥጥር ስር ከዋሉ ግለሰቦች መሀል የተሰጣቸውን ኃላፊነት ወደ ጎን በመተው ያለአግባብ ሀብት ያከማቹ፣ ሀብት ያሸሹ፣ በሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ላይ የተሳተፉ፣ በሀገሪቱ በተለያዩ አካባቢዎች ላይ የተከሰቱ ብጥብጦች ያስተባበሩ ይገኙበታል ተብሏል።

    በሌላ በኩል ደግሞ በብሔራዊ መረጃ እና ደኅንነት አባላት መካከል በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች በስውር እስር ቤት ግለሰቦችን በማሰር እና በማሰቃየት ተጠርጥረው የተያዙ አሉ። በአዲስ አበባ ብቻ ከሰባት በላይ እስር ቤቶች ተገኝተዋል። እንዲሁም በሰብዓዊ መብት ጥሰት ተጠርጥረው ከተያዙ ግለሰቦች መሀል ግለሰቦችን ከፖለቲካ ፓርቲ አባልነት እራሳቸውን እንዲያገሉ ማድረግ እና ማሰቃየት፣ በአንቡላንስ እያፈኑ ሰዎችን መሰወር፣ ሕገ-ወጥ መሣሪያዎችን የራሴ ነው ብሎ እንዲፈርሙ ማድረግ፣ የብልት ቆዳዎችን በፒንሳ መሳብ፣ ጫካ ማሳደር፣ ከአውሬ ጋር ማሰር፣ አፍንጫ ውስጥ እስክርቢቶ መክተት፣ ግብረሰዶማዊ ጥቃት መፈፀም፣ ሴቶችን መድፈር የመሳሰሉ አረመኔያዊ ድርጊቶችን ፈፅመዋል።

    የሰኔ 16ቱ የቦንብ ጥቃት በተመለከተ በዋናነት የተቀነባበረው የብሔራዊ መረጃ እና ደኅንነት አባል በሆኑ ግለሰብ ነው። ኬንያ ከምትገኝ ገነት ቶሎሺ ከተባለች ግለሰብ ጋር በመሆን ነበር።

    የብረታብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን (ሜቴክ) ድርጅትን በተመለከተ የውጪ ሀገር ግዥዎችን ያለጨረታ መስጠት፣ ግዥ አፈፃፀሙ ከኮርፖሬሽኑ የበላይ አመራሮች ጋር የጥቅም ትስስር እና ዝምድና ያላቸው ሰዎች የድለላ ሥራ ሠርተው የሚከፈላቸውና እነዚህ የውጪ ኩባንያዎችን የሚያመጡት ደላሎች ለአመራሩ ቅርብ የሆኑ ናቸው። እነዚህ በድለላ ያሉ ሰዎች በሀገር ውስጥ ካካበቱት ሃብት በላይ ወደ ዉጪ ሃብት አሽሸዋል። ከመደበኛው ዋጋ እስከ 400% ተጨማሪ ዋጋ እየተጨመሪ ግዢ ይፈፀም ነበር ተብሏል። ከዚህም ጉዳይ የሀገር ውስጥ ግዢም በግልፅ ጨረታ መፈፀም ሲገባው እስካሁን በዚህ መልኩ የተፈፀመ የለም። ከኮርፓሬሽኑ አመራሮች ጋር የዝምድናና የጥቅም ትስስር ካላቸው ሰዎች በብዙ እጥፍ በተጋነነ ዋጋ ይገዛ ነበር። ከአንድ ድርጅት 21 ጊዜ፣ ከሌላው ደግሞ 15 ጊዜ ግዥ ተፈፅሟል። ለአብነት ያህል ከአንድ ድርጅት በአንድ ጊዜ ብቻ የ205 ሚሊዮን ብር ግዢ ያለጨረታ ተፈፅሟል በማለት አቶ ብርሀኑ ጸጋዬ ጠቅሰዋል። ከተቋሙ ተልዕኮ ውጪ የተፈፀሙ ግዥዎችም አሉ። ከዚህም ውስጥ የመርከብ ግዢ ይገኝበታል። በማይመለከተውም ሥራ ገብቶ ወደ ንግድ ሥራ አስገብቷቸዋል ሲሉ ጠቅላይ አቃቤ ሕጉ አቶ ብርሀኑ ጸጋዬ ገልጸዋል።

    ምንጭ፦ የፌዴራል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ | ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    አቶ ብርሀኑ ጸጋዬ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.