ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ምርጥ የአዝዕርት ዝርያዎችን ለአርሶ አደሩ በማከፋፈል ምርትን በማሳደግ አመርቂ ውጤት ተገኝቷል

Home Forums Semonegna Stories ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ምርጥ የአዝዕርት ዝርያዎችን ለአርሶ አደሩ በማከፋፈል ምርትን በማሳደግ አመርቂ ውጤት ተገኝቷል

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #8321
    Semonegna
    Keymaster

    ሐረማያ (ሐዩ) – ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ የምርምር ተቋም የተገኙ 78 ምርጥ የአዝዕርት ዝርያዎችን ከአርሶ አደሩ ጋር በማብዛት እንዲሰራጭ እያደረገ መሆኑን ዩኒቨርሲቲው ገለጸ።

    በዞኑ በማኅበር የተደራጁ አርሶ አደሮች ከዩኒቨርሲቲው የግብርና እና አካባቢ ሳይንስ ኮሌጅ ጋር በመሆን ምርጥ ዘር የማባዛት ሥራ ላይ ተሰማርተው ውጤታማ እየሆንን እንገኛለን ሲሉ ተናግረዋል።

    የዩኒቨርሲቲው የተቀናጀ የዘር ዘርፍ ልማት ፕሮጀክት ሥራ አስኪያጅ አቶ ደንደና ገልሜሳ “ከሐረማያ ዩኒቨርሲቲና ከአገሪቱ የተለያዩ የምርምር ተቋማት የተገኙ ምርጥ ዘሮችን በማሳ የተግባር ሥራ በማከናወን የመምረጥና የማባዛት ሥራ ከአርሶ አደሩ ጋር እየተከናወነ ይገኛል” በማለት ገልጸዋል።

    በምዕራብና ምሥራቅ ሐረርጌ ዞን በስምንት ወረዳ 38 ቀበሌ ገበራት ውስጥ ማኅበር በሚከናወነው ሥራ 3ሺህ አርሶ አደሮች በማኅበር ተደራጅተው በስንዴ፣ በቆሎ፣ ማሽላ፣ ቦሎቄ እና ሌሎች ሰብሎች ላይ የዘር መረጣና ብዜት ሥራ ላይ ተሳታፊ መሆናቸውን አቶ ደንደና ተናግረዋል፤ ከነዚህ ውስጥም 1ሺ 200 ሴት አርሶ አደሮች መሆናቸውን ጠቁመዋል።

    ሰብሎቹም የዝናብ እጥረትን እና በሽታን ተቋቁመው ምርት የሚሰጡ መሆናቸውን ጠቁመው በአሁኑ ወቅትም አርሶ አደሩ የሚስማማውን የአዝዕርት ዓይነት እየለየ እና ለሌሎች አርሶ አደሮች ዘሩን እያሰራጨ እንደሚገኝ ጠቁመው በዚህም 23 በዘር ብዜት የተሰማሩ የአርሶ አደር ማህበራት ከፍተኛውን ሚና እያበረከቱ እንደሚገኙ ተናግረዋል።

    ባለፉት ጊዜያት ምርጥ ዘሩን ያለምንም የሙከራ ሥራ ለአርሶ አደሩ ይሰራጭ ነበር ያሉት አቶ ደንደና የአሁኑ ቴክኖሎጂ ግን አርሶ አደሩ በማሳው ላይ ሰብሉን አብቅሎ ውጤቱን በመመልከት የሚበጀውን ለይቶ እንዲመርጥ እየተደረገ በመሆኑ ቴክኖሎጂው ለየት እንደሚያደርገው አስረድተዋል። በዚህም በዞኖቹ የሚገኙ የዘር አቅራቢ ማህበራት፣ ምርጥ ዘር አቅራቢ ድርጅቶች የግብርና ቢሮዎችና ባለሞያዎች ከዩኒቨርሲቲው ተመራማሪዎችና ከቴክኖሎጂው ልምድ እንዲቀስሙ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል።

     

    በምሥራቅ ሐረርጌ ዞን የኩርፋ ጨሌ ወረዳ የግብርና ባለሞያ የሆኑት አቶ ግዛው ልኬለው እንደሚገልጸው ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ በወረዳው ህዳሴ፣ ኪንግ በርድና ኦበራ የተባሉ ሶስት የስንዴ ዝርያዎቸ እንዲሁም ከደቡብ ጬንቻ የመጣውን አፕል ዝርያዎችን ከአርሶ አደሩና ከግብርና ባለሞያ ጋር በተግባር ሥራ እየመረጥን እንገኛለን ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

    ተመራማሪው፣ የግብርና ባለሞያና አርሶ አደሩ በጋራ እየሠራን በሚገኘው ተግባር ተኮር የዘር መረጣ የአካባቢውን የዝናብ እጥረት እጥረትን እና በሽታ ተቋቁሞ ምርት የሚሰጠውን ህዳሴ የተባለውን ዝርያ አርሶ አደሩ መርጧል እኛም እንዳየነው ትክክል ሆኖ አግኝተነዋል በማለት አቶ ግዛው ስለተገኘው ውጤት ያስረዳሉ። የአፕል ዝርያም ለ16 አርሶ አደሮች ተሰጥቶ ሙከራ እየተደረገ መሆኑን ጠቁመው እንዲህ ዓይነቱ ተግባር ተኮር ቴክኖሎጂ አርሶ አደሩን እያነሳሳ ስለሚገኝ መበረታታት አለበት ብለዋል።

    ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ በተለይ ከሴት አርሶ አደሮች ጋር በሚሠራው ተግባር ተኮር የዘር መረጣ እኛ ሴቶች ተጠቃሚ ሆነናል፤ በአንድ ዓመትም 25 ኩንታል ምርጥ የስንዴ ዘር በማምረት ለአካባቢው አርሶ አደሮች አንዱን ኩንታል በ4ሺ ብር ሸጠናል ያለችው በሜታ ወረዳ ዱርሲቱ ቢሊሱማ ቀበሌ ገበሬ ማኅበር በዘር ብዜት ሥራ በማኅበር የተደራጀችው ሴት አርሶ አደር ሚሥራ አደም ናት።

    በቀርሳ ወረዳ ወተር ቀበሌ ገበሬ ማኅበር በዘር ብዜት ሥራ የተሰማራው ሌላው አርሶ አደር ሸረፍ ኡመሬ ከዩኒቨርሲቲው ጋር በቦሎቄ፣ ስንዴ፣ ድንች እና ሌሎች ምርጥ የሰብል ዝርያዎችን በተግባር የምርምር እያመረቱ እና ለአካባቢው ተስማሚ የሆነውን ዝርያ ለሌሎች እያሰራጨን እንገኛለን፤ በዚህም ቀደም ሲል ይጠቀሙት የነበረው የድንችና የስንዴ በክረምት ወቅት ብቻ የሚበቅል እና በሽታን የመቋቋም አቅሙ ደካማ እንደነበር ገልጸው በአሁኑ ወቅት ግን በተግባር የሰሩት ኪንግ በርድ የተባለው የስንዴና ቡቡ የተሰኘው የድንች ዝርያ በሽታን ተቋቁሞ የተሻለ ምርት የሚሰጥ በመሆኑ መምረጣቸውን ተናግረዋል።

    ምንጭ፦ የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ

    ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.