የፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ የስልጣን መልቀቂያ ማቅረብ ― አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ ማን ናቸው?

Home Forums Semonegna Stories የፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ የስልጣን መልቀቂያ ማቅረብ ― አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ ማን ናቸው?

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #8231
    Semonegna
    Keymaster

    የኢፌዴሪ መንግስት የፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመን የመልቀቂያ ጥያቄ ከተቀበለ ከሀያ ዓመታት በላይ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ስር በአምባሳደርነትና የኢትዮጵያ ተጠሪነት ያገለገሉት አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ ፕሬዝዳንት ሆነው እንደሚሾሙ የተለያዩ የዜና ምንጮች ዘግበዋል።

    አዲስ አባባ – ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ (ዶ/ር) ሀሙስ ጥቅምት 15 ቀን 2011 ዓ.ም. በሚውለው የሕዝብ ተወካዮችና የፌዴሬሽን ምክር ቤቶች 2ኛ አስቸኳይ መደበኛ ስብሰባ የሥራ መልቀቂያ እንደሚያቀርቡ ይጠበቃል። የአስቸኳይ ስብሰባው ዋና አጀንዳ የፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመን የሥራ መልቀቂያ መቀበልና አዲስ ፕሬዚዳንት መምረጥ እንደሚሆን ተገልጿል።

    ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ (ዶ/ር) የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ሆነው የተመረጡት መስከረም 27 ቀን 2006 ዓ.ም ሲሆን ሶስተኛው ፕሬዚዳንትም (ከዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ እና አቶ ግርማ ወልደጊዮርጊስ ቀጥሎ) ናቸው።

    ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ ወለጋ አርጆ ከተማ በ1949 ዓ.ም ነው የተወለዱት፤ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን በቻይና የፖለቲካ ኢኮኖሚ ፍልስፍና፣ ሁለተኛውን በህግና ዲፕሎማሲ ከአሜሪካ፣ 3ኛ ዲግሪያቸውን ከቻይና ቤጂንግ ዩኒቨርስቲ በህግ አግኝተዋል።

    ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ በጃፓንና በቻይና የኢትዮጵያ ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ሆነው ያገለገሉ ሲሆን፤ ከ1993-1994 ዓ.ም የግብርና ሚኒስትር፣ ከጥቅምት 1994-1998 ዓ.ም የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ሆነውም አገልግለዋል። በፕሬዝዳንትነት እስከተመረጡበት ጊዜም በቱርክ የኢትዮጵያ ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ነበሩ።

    ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ የተለያዩ የምርምር ሥራዎችን በተለያዩ መስኮች ያከናወኑና በመምህርነትም ያገለገሉ ሲሆን ከአገር ውስጥ አማርኛና ኦሮምኛ ከውጭ ደግሞ እንግሊዝኛ፣ ቻይንኛና ፈረንሳይኛ ቋንቋዎችን መናገርና መጻፍ ይችላሉ።

    በኢፌዴሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 70 ንዑስ አንቀጽ 4 መሰረት የአንድ ፕሬዝዳንት አገልግሎት ጊዜ ስድስት ዓመት ሲሆን፥ አንድ ግለሰብ ከሁለት ጊዜ በላይ በርዕሰ ብሔርነት ሊመረጥ እንደማይችል ይደነግጋል። ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ የመጀመሪያ ቨፕሬዝዳትነት አምስተኛ ዓመታቸው ነው።

    ከዚህ ጋር በተያያዘ የተለያዩ የሀገር ውስጥ ሚዲያዎች ኢትዮጵያን ከሀያ ዓመታት በላይ በሚኒስቴርነትና በአምባሳደርነት ያጋለገሉት አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ ቀጣዩ የኢትዮጵያ ርዕሰ ብሔር (ፕሬዝዳንት) ይሆናሉ ብለው ቅድመ ግምታቸውን እየሰጡ ነው። በዚህም አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ ፕሬዝዳንት ሆነው ከተመረጡ በኢትዮጵያ ታሪክ የመጀመሪያዋ እንስት ፕሬዝዳንት ይሆናሉ ማለት ነው።

    ለመሆኑ አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ ማን ናቸው?

    ተወልደው ያደጉት አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ሲሆን የመጀመሪያና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን የተከታተሉት በሊሴ ገብረማርያም ትምህርት ቤት ነው። አራት ሴት ልጆች ለነበሯቸው ወላጆቻቸው የመጀመሪያ ልጅ የሆኑት ሳህለወርቅ ዘውዴ ገና በ17 ዓመታቸው ነጻ የትምህርት ዕደል አግኝትው ወደ ፈረንሳይ በማቅናት ሞንትፔልየር (Montpellier) በምትባለው የፈረንሳይ ከተማ በሚገኘው ዮኒቨርሲቲ ኦፍ ሞንትፔልየር (University of Montpellier) የተፈጥሮ ሳይንስን አጥንተዋል። በሀገረ ፈረንሳይ ለዘጠኝ ዓመታት ከቆዩ በኋላ ወደ ኢትዮጵይ በመመለስ በትምህርት ሚኒስቴር ውስጥ የሕዝብ ግንኙነት ክፍልን ማገልገል ጀመሩ። ቆይተውም የሕዝብ ግንኙነት ክፍሉን በበላይነት መርተዋል። ከዚያም ወደ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በመዘዋወር በተለያዩ የሥራ ኃላፊነቶች አገልግለዋል።

    ወሮ ሳህለወርቅ ዘውዴ በአምባሳደርነት ለመሾም ከአምባሳደር ዮዲት እምሩ ቀጥሎ ሁለተኛዋ እንስት ናቸው። በመጀመሪያ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሆነው የተሾሙትም ሴኔጋል ሲሆን የአምባሳደርነት ስልጣናቸውም ሴኔጋልን ጨምሮ ማሊን፣ ኬፕ ቨርዴን፣ ጊዚ ቢሳውን፣ ጋምብያን እና ጊኒን (እ.ኤ.አ 1989–1993) ያጠቃልል ነበር። ቀጥሎም እ.ኤ.አ 1983–2002 በጅቡቲ የኢትዮጵያ አምባሳደርና በኢጋድ (IGAD) የኢትዮጵያ ተጠሪ ሆነው አገልግለዋል። እ.ኤ.አ ከ2002 ጀምሮ እስከ 2006 ድረሰ በፈረንሳይ (ሞሮኮን ጨምሮ) የኢትዮጵያ አምባሳደርና በዩኔስኮ (UNESCO) የኢትዮጵያ ተጠሪ ሆነው አገልግለዋል። እ.ኤ.አ ከ2006 ጀምሮ እስከ 2009 ድረስ በአፍሪካ ህብረት (AU) እና በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (UNECA) የኢትዮጵያ ተጠሪ ሆነው ሀገራቸውን አገልግለዋል።

    ከሀያ ዓመታት በላይ በተለያዩ ሀገራትና ዓለማቀፋዊ ድርጅቶች የኢትዮጵያ አምባሳደርና ተጠሪ በመሆን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤትን ያገለገሉት አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ እ.ኤ.አ በ2009 የተበባሩት መንግስታት ድርጅትን (ተመድ) በመቀላቀል የድርጅቱ በመካከለኛው አፍሪካ ሪፑብሊክ የተቀናጀ ሰላም ግንባታ መሪ (Head BINUCA) በመሆን ማገልገል ጀመሩ። ይህ አገልግሎታቸውም ወደ ሚቀጥለው ኃላፊነት አሸጋግሯቸው እ.ኤ.አ በ2011 ዓም የዚያን ጊዜ የተመድ ጠቅላይ-ጸሀፊ ባን ኪ-ሙን (Ban Ki-moon) አዲስ ለተቋቃመው በናይሮቢ የተመድ ጽህፈት ቤት (UNON) የመጀመሪያዋ ጠቅላይ-መሪ አድርገው ሾማቸው። በዚያም ለሰባት ዓመታት ካገለገሉ በኋላ እ.ኤ.አ በሰኔ ወር 2010 የአሁኑ የተመድ ጠቅላይ-ጸሀፊ አንቶንዮ ጉቴሬስ (António Guterres) አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴን በተመድ ጠቅላይ-መሪ ስር (Under-Secretary-General) የአፍሪካ ህብረት ልዩ ተጠሪ (UN’s Special Representative to the AU) እና በአፍሪካ ህብረት ውስጥ የተመድ ጽህፈት ቤት ዋና ኃላፊ (Head of UNOAU) አድርገው ሾሟቸው እስካሁን ድረስ በዚሁ ሹመታቸው እያገለገሉ ይገኛሉ።

    አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ ባለትዳርና የሁለት ወንድ ልጆች እናት ናቸው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ሳህለወርቅ ዘውዴ


Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.