በቁጥጥር ስር የዋሉት አቶ በረከት ስምኦን እና አቶ ታደሰ ካሳ ጉዳያቸው በክልሉ መንግስት ባህር ዳር ውስጥ ይታያል

Home Forums Semonegna Stories በቁጥጥር ስር የዋሉት አቶ በረከት ስምኦን እና አቶ ታደሰ ካሳ ጉዳያቸው በክልሉ መንግስት ባህር ዳር ውስጥ ይታያል

Viewing 3 posts - 1 through 3 (of 3 total)
  • Author
    Posts
  • #9334
    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – አቶ በረከት ስምኦን እና አቶ ታደሰ ካሳ (ጥንቅሹ) የአማራ ክልል የልማትና ኢንቨስትመንት ድርጅት በሆነው ጥረት ኮርፖሬት ላይ ከደረሰ የሀብት ብክነት ወንጀል ጋር በተያያዘ ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የአማራ ክልላዊ መንግስት ፀረ ሙስና ኮሚሽን አስታወቀ።

    የአማራ ክልል ፀረ ሙስና ኮሚሽኑ ኮሚሽነር አቶ ዝግአለ ገበየሁ አቶ በረከት ስምኦን እና አቶ ታደሰ ካሳ (“ተጠርጣሪዎች”) በቁጥጥር ስር ውለው ወደ ባህር ዳር መወሰዳቸውን ለመገናኛ ብዙኃንና ለጋዜጠኞች አስታውቀዋል። እንደ አቶ ዝግአለ ገለጻ፥ ሁለቱ ተጠርጣሪዎች ከፍተኛ በሆነ የሀብት ብክነት ምክንያት ጥረት ኮርፖሬትን ለኪሳራ ዳርገዋል፤ ይህም በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ምክንያት እንደሆነና የተጠረጠሩበት ወንጀል የተፈፀመው በክልሉ በመሆኑ ጉዳያቸው በክልሉ ፍርድ ቤት የሚታይ ይሆናል።

    የክልሉ ፀረ ሙስና ኮሚሽን በእስካሁኑ የመረጃና ማስረጃ ማሰባሰብ ሂደት በሁለቱ ግለሰቦች ላይ ተገቢውን ክስ ለመመሥረት የሚያስችለውን በቂ መረጃ/ማስረጃ መሰበሰቡንም አስታውቋል።

    አባይ የህትመትና የወረቀት ፓኬጂን ፋብሪካ ባህር ዳር ከተማ ውስጥ ሥራ ጀመረ

    አቶ በረከት ስምኦን እና አቶ ታደሰ ካሳ (ጥንቅሹ) የቀድሞዉ የኢትዮጵያ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ኢሕድን)እና የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) መሥራቾች ከመሆናቸው በተጨማሪ በፌደራልና በክልል መንግስታዊ ቦታውች ለረዥም ጊዜ ሲያገለግሉ ቆይተዋል። በጥረት ኮርፖሬት ውስጥ ደግሞ አቶ ታደሰ ካሳ በዋና ሥራ አስፈፃሚነት አቶ በረከት ስምኦን ደግሞ በቦርድ ሰብሳቢነት ለበርካታ ዓመታት መሥራታቸው ተጠቁሟል።

    አቶ በረከት ስምኦን እና አቶ ታደሰ ካሳን በቁጥጥር ስር ለመዋል ያበቃቸውና ጥረት ኮርፖሬት ላይ የተፈጸመው የሀብት ብክነት ምንድን ነው?

    የጥረት ኮርፖሬት የሀብት፣ እንዲሁም በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ የገንዘብ ብክነት ተፈጽሞብኛል ያላቸው ዝርዝሮች፦

    • የኮርፖሬቱ ንብረት የሆኑ አምስት ኩባንያዎች ከ ክስዮን መሸጥ/ግዢ ጋር በተያያዘ ለሀብት ብክነት የዳረገ ብልሹ አሠራር በኦዲት ተደርሶበታል፤
    • ሌሎች ሁለት እህት ኩባንያዎች ላይ ተመሳሳይ የኦዲት ሥራ እየተሠራ ነው፤
    • ተጠርጣሪዎቹ በኮርፖሬቱ ውስጥ በስልጣን ላይ እያሉ የተመሠረቱ ስድስት እህት ኩባንያዎች፥ ከመመሥረታቸው በፊት አስፈላጊውን የአዋጭነት ጥናት ሳይደረግ ለእነዚህ ኩባንያዎች መመሠረቻ/ ግዢ ወደ ሚሊዮን ብር ወጪ ወጥቷል፤
    • እነዚህ ስድስት እህት ኩባንያዎች ከተመሠረቱ/ ከተገዙ በኋላ በጊዜው ወደሥራ ባለመግባታቸው ኮርፖሬቱን ለተጨማሪ ወጪ/ ኪሳራ ዳርገውታል፤
    • ጥረት ኮርፖሬሽን በአጋርነት ከሚሠራቸው ኩባንያዎች ጋርም ከኮርፖሬቱ የፋይናንስ አሠራርና ሕግ ውጪ 7 ሚሊየን ብር ለሁለት ኩባንያዎች ተሰጥቷል፤
    • በሦስት ግለሰቦች ለሚተዳደር አንድ የማዕድን ኩባንያ ላወጣው የእያንዳንዱ አክሲዮን ዋጋ 1,000 ብር ሲሆን፥ ጥረት ኮርፖሬት በአንጻሩ የእያንዳንዱን አክሲዮን ዋጋ በ2,200 ብር እንዲገዛ ተደርጓል። በዚህም ሦስቱ ባለሀብቶች የ4 ሚሊየን 320 ሺህ ብር ተጠቃሚ ያደረገ ሲሆኑ፥ ጥረት ኮርፖሬት ግን ለኪሳራ ተዳርጓል፤
    • ባለሙያን ያላካተተ የአክስዮን መግዛትና መሸጥ ሥራ በኮርፖሬቱ ውስጥ ይተገበር ነበር፤ ይህም ለሀብት ብክነት ተጨማሪ ምክንያት ሆኗል፤
    • ለካፒታል ዕድገት ለሀገር ውስጥ ገቢ መክፈል የነበረበትን 1 ሚሊዮን 296 ሺህ ብር ባለመክፈሉ ጥረት ኮርፖሬት ባለዕዳ አድርጎታል፤
    • ለፋብሪካ ይገነባል በሚል የ17 ሚሊየን ብር ግብዓት ተገዝቶ እስካሁን ምንም ዓይነት ሥራላ በለመዋሉ ኮርፖሬቱን ለሌላ የሀብት ብክነት ዳርጎታል።

    በስተመጨረሻም አቶ ዝግአለ እንዳስታወቁት የአቶ በረከት ስምኦን እና የአቶ ታደሰ ካሳ በቁጥጥር ስር መዋል መጀመሪያ እንደሆነና፥ ሌሎችም በእንዲህ ዓይነት ወንጀል የተጠረጠሩ ሰዎች በቁጥጥር ስር ይውላሉ።

    ቀድሞ የኢትዮጵያ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ኢሕዴን)፣ በመሀል ብሔረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ብአዴን)፣ አሁን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (አዴፓ) የተባለው የአማራ ሕዝብ ፓርቲ ያቋቋመው ጥረት ኮርፖሬት በአምራችነት ዘርፍ፣ በአገልግሎት መሰጠት ዘርፍ፣ በኮንስትራክሽን ዘርፍ እና በ አግሮ ፕሮሰሲንግ ዘርፍ ላይ የተሰማሩ የአስራ ዘጠኝ ኩባንያዎች ባለቤት መሆኑን የኮርፖሬቱ ድረ ገጽ ያሳያል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    አቶ በረከት ስምኦን እና አቶ ታደሰ ካሳ


    #9338
    Anonymous
    Inactive

    አቶ በረከት አቶ ታደሰ ባሕርዳር ይዳኛሉ
    የቀድሞዉ የኢትዮጵያ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ኢሕድን)ና የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) መሥራቾች አቶ በረከት ስሞዖንና አቶ ታደሰ ካሳ የታሰሩትም፣የሚዳኙትም አማራ ክልል እንደሆነ የክክሉ ባለሥልጣን አስታወቀ።የአማራ መስተዳድር የሥነ-ምግባርና የፀረ ሙስና ኮሚሽን ኃላፊ አቶ ዝግአለ ገበየሁ ለጋዜጠኞች እንደነገሩት ሁለቱ ከፍተኛ ባለሥልጣናት የታሰሩት ጥረት የተሰኘዉን የኩባንዮች ስብስብ በማክሰራቸዉ ነዉ።ድሮ ኢሕዴን፣ በመሐሉ ብአዴን፣ በቅርብ ደግሞ አዴፓ በሚሉ ምሕፃረ-ቃላት የሚጠራዉ የአማራ ክልክል ገዢ ፓርቲ የመሠረተዉና የሚቆጣጠረዉ ድርጅት የአስራ-ሠባት አምራችን ነጋዴ ኩባንዮች ባለቤት ነዉ።

    አውዲዮውን ያዳምጡ።
    Deutsche Welle

    #9339
    Anonymous
    Inactive

    የአቶ በረከት ስምኦን እና አቶ ታደሰ ካሳ በቁጥጥር ሥር መዋል

    ሁለቱ የቀድሞ የብአዴንና የኢህአዴግ ከፍተኛ አመራሮች በቁጥጥር ሥር የዋሉት በጥረት ኮርፕሬት ፈፅመዋል ተብለው በተጠረጠሩበት የኃብት ብክነት ወንጀል ነው።
    ባህር ዳር —

    ሁለቱ የቀድሞ የብአዴንና የኢህአዴግ ከፍተኛ አመራሮች በቁጥጥር ሥር የዋሉት በጥረት ኮርፕሬት ፈፅመዋል ተብለው በተጠረጠሩበት የኃብት ብክነት ወንጀል ነው።
    አቶ ታደሰ ካሳ በጥረት ኮርፕሬት በዋና ሥራ አስፈፃሚነት አቶ በረከት ስምኦን ደግሞ የጥረት ኮርፕሬት የቦርድ ሰብሳቢ ሆነው ለበርካታ ዓመታት ሰርተዋል። ሁለቱ የቀድሞ ከፍተኛ አመራሮች ዛሬ አዲስ አበባ በሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው ነው የተያዙት።
    ይህንን ተከትሎ የአማራ ክልል ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ዛሬ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል። አቶ በረከትና አቶ ታደሰ ዛሬ ጠዋት ባህር ዳር ከተማ የገቡ ሲሆን በጊዜያዊ ማረፊያ ቤት ውስጥ እንደሚገኙ ኮሚሽነር ዝግ አለ ገበየሁ ተናግረዋል።

    ለተጨማሪ የተያያዘውን የድምፅ ፋይል ያዳምጡ።
    VOA Amharic

Viewing 3 posts - 1 through 3 (of 3 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.