ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ <ሌሎችን ለመርዳት ሮጣለሁ> እርዳታ ማሰባሰብያ ፕሮግራም እና ለልጆች ሩጫ ምዝገባ ተዘጋጅቷል

Home Forums Semonegna Stories ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ <ሌሎችን ለመርዳት ሮጣለሁ> እርዳታ ማሰባሰብያ ፕሮግራም እና ለልጆች ሩጫ ምዝገባ ተዘጋጅቷል

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #12164
    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – በዓለም ምርጡ ተብሎ በይፋ የተሰየመውን እና በህዳር ወር የሚካሄደውን 45,000 ህዝብ የሚሳተፍበት የ2012 ዓ.ም. ቶታል ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ 10 ኪ.ሜ. ውድድር የሚያዘጋጀው ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከዚህ ጎን ለጎን የሚያካሂደውን “ሌሎችን ለመርዳት ሮጣለሁ” የእርዳታ ማሰባሰቢያ ሥራ እንዲሁም የዘንድሮውን ሩጫ መሪ ቃል “ሴቶች ልጆች በእኩል ሚዛን መታየት፤ መደመጥ እና ተቀባይነት ሊኖራቸው ይገባል” በመለየት መሰናዶውን በተቀላጠፈ መልኩ በማካሄድ ላይ ሲሆን ውድድሩ ከዛሬ 45 ቀን በኋላ እሁድ ህዳር 07 እንደሚካሄድ ተገልጿል።

    በጎ አድራጎ ሥራ ከተጀመረበት ከ1998 ዓ.ም. ጀምሮ ከ13.5 ሚሊዮን ብር በላይ ሰላሳ (30) ለሚሆኑ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች የተሰባሰበበት “ሌሎችን ለመርዳት ሮጣለሁ” መርሀ ግብር 9 ሚሊዮን ብሩ ባለፉት ስድስት ዓመታት የተሰባሰበ ሲሆን ዘንድሮ 1.9 ሚሊዮን ብርለማግኘት ታቅዶበታል። ይሄም ገንዘብ በዋግህምራ ዞን ትምህርት ቤት ለማስገንባት የሚውል ሲሆን የፕሮጀክቱ መነሻ ጀግናው አትሌት ሀይሌ ገብረሥላሴ በቅርቡ በአካባቢው አንድ ትምህርት ቤት ማሠራቱን ተከትሎ የመጣ ነው።

    ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ዘንድሮ በውድድር ዝግጅት ረጅም እድሜ ካስቆጠሩ አንጋፋ ዓለም አቀፍ ውድድሮች ጋር ተፎካክሮ ያገኘው ትልቅ ዕውቅና እና ሽልማት ለሀገራችን የቱሪዝም ዘርፍ የሚኖረው ጉልህ አስተዋጽኦ ቀላል የሚባል አይደለም። ስኬቱ የኢትዮጵያን ቱሪዝም ይበልጥ ለማስተዋወቅ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያን እንደ አንድ መስህብ መጠቀም የሚያስችል ሲሆን በተለይም ከቱሪዝም ኢትዮጵያከኢትዮጵያ አየር መንገድ እንዲሁም ሌሎች የውድድሩ አጋሮች ጋር አብሮ በመሥራት የአገሪቷን ቱሪዝም ለማሳደግ ካለው አላማ ጋር አብሮ የሚሄድ ነው።

    በሌላ በኩል ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከውድድር ስያሜ ስፖንሰሩ ቶታል ጋር ያለውን ኮንትራት ለተጨማሪ ሶስት ዓመታት አድሷል። ከዚህ በተጨማሪ የ2012 ዓ.ም. ቶታል ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የምዝገባ ሰኔ ላይ የተጠናቀቀ ሲሆን የተቀሩት ጥቂት ለበጎ አድራጎት የሚውሉ ቦታዎች ለማቀላጠፍ ከአሞሌ የዲጂታል መገበያያ ቴክኖሎጂ ጋር በአጋርነት መሥራት ጀምሯል። ማንኛውም ለበጎ አድራጎት የሚውለውን የሩጫ ቲሸርት የሚፈልግ ግለሰብ አሞሌን በመጠቀም መግዛት የሚችል ሲሆን አሞሌን ለማይጠቀሙ ግለሰቦች ደግሞ በማንኛውም የዳሽን ባንክ በመሄድ 600ብር በመክፈል መመዝገብ የሚችሉበትን መንገድ አመቻችቷል። የመወዳደሪያው ቲሸርት ለሁሉም ተሳታፊዎች ከጥቅምት 28-30 ቀን ከውድድሩ 1 ሳምንት ቀድሞ በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል በታላቁ ሩጫ የስፖርት ኤክስፖ ላይ ይሰጣል።

    ዘንድሮ ታላቁ ሩጫ አዳዲስ አጋሮችን ይዞ መቷል። “ከሥራዎች ሁሉ ውድ ÷ ክፍያ የማይፈፀምላቸው የቤት ውስጥ ሥራዎች እና ክብካቤዎች ናቸው!”) የሚል መልዕክት ይዞ የመጣው አክሽን ኤይድ ኢትዮጵያ (ActionAid Ethiopia)፤ ቴክኖሎጂ ላይ የሚሰራው ኤች ፒ (HP) እና ዘመናዊው ሃየት ሬጀንሲ ሆቴል (Hyatt Regency Addis Ababa) ናቸው።

    ከ2012 ቶታል ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ጋር ተያይዞ በሩጫው ዋዜማ በድምቀት የሚካሄደውና በአጠቃላይ 3,500 ልጆች የሚሳታፉበት የሕፃናት ውድድር ከአዋቂዎቹ ሩጫ ጋር በተመሳሳይ “ሴቶች ልጆች በእኩል ሊታዩ፤ ሊደመጡ እና ቦታ ሊሠጣቸው ይገባል” በሚል መሪ ቃል ይደረጋል። የልጆች ሩጫ ከሚያስተላለፈው መልዕክት በተጨማሪ ሕፃናት ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ገና በለጋ እድሜያቸው እንዲለምዱ እድል ሲሰጥ በተጨማሪም ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ በሁሉም የእድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ሰዎችን ተሳትፎ የሚያሰፋበት መንገድ ነው።

    የ14ኛው የፕላን ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ (Plan International Ethiopia) የሕፃናት ሩጫ ምዝገባ ሰኞ መስከረም 26 ቀን 2012 ዓ.ም. ቦሌ መንገድ ዓለም ህንጻ በሚገኘው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ቢሮ ይጀመራል ።

    የ19ኛው ዙር የ2012 ዓ.ም. ቶታል ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከፊታችን እሁድ 6 ሳምንታት በኋላ የሚካሄድ ሲሆን በቀጣይ ያሉት 6 ሳምንታት የተለያዩ 6 አንኳር ህሳቦች ላይ እንዲያጠነጥኑ የታቀደ ሲሆን እነሱም፡

    1. ዱበ ዱብ፡ ተሳታፊዎች ለሩጫው ዝግጅታቸውን የሚጀምሩበት ሳምንት ሲሆን ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የ6 ሳምንት የልምምድ ምክር ከሻለቃ ሀይሌ ገብረሥላሴ እንዲያገኙ ያመቻቻል።
    2. ጥንቃቄ፡ ይህ ተሳታፊዎች ጤናቸውን የሚያረጋግጡበት (ቼክ የሚያደርጉበት) ሳምንት ሲሆን አዘጋጆች ደግሞ ከኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር እንዲሁም ከጠብታ አምቡላንስ እና ከውድድሩ ሜዲካል ዳይሬክተር የተጠናከረ ዝግጅት የሚደረግበት ነው።
    3. ምንጭ፡ አርንጓዴ ምንጭ በመባል የሚታወቀው የኢትዮጵያ ብሄራዊ የአትሌቲክስ ቡድን ሲሆን የዚህ ምንጭ የሆኑት ታዳጊ እና አዳዲሰ አትሌቶች በቃታቸውን የሚያሳዩበት የምርጫ ውድድር የምናደርግበት ሲሆን፣ ጥቅምት 9 ቀን 300 የሚሆኑ ታዳጊ አትሌቶች በውድድሩ ይሳተፋሉ ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን ወድድሩ በኢትዮጵያ ወጣቶች ስፖርት አካዳሜ የሚካሄድ ይሆናል።
    4. በጎ ፈቃደኛ፡ ለውድድራችን በየአመቱ መሳካት ትልቅ ድጋፍ ለሚያደርጉልን በጎ ፈቃደኞቻችን እውቅና የምንሰጥበት ሳምንት ነው።
    5. ጽዱ፡ የሩጫችን መንገድ ንጹህ ሆኖ እንዲዘጋጅ የሙከራ የጽዳት ፕሮግራም የምናደርግበትና በዋናነት ከቂቆስ ክ/ከተማ ጽዳት ቢሮ ጋር የሚሰራ ሲሆን ውድድሩ የሚንካቸውን ሌሎች ክ/ከተማዎችን ጨምሮ የሚካሄድ ሲሆን ከውድድሩም በኋላ ከተማችን ጽድ እንድትሆን ከአጋሮቻችን አርኪ ውሃ እንዲሁም ዳይናሚክ የጽዳት ድርጅት ጋር አብረን እንሰራለን።
    6. ስፖርት ኤክስፖ፡ ለተሳታፊዎቻችን የሩጫ ቲ-ሸርት የሚሰጥበት ሳምንት ሲሆን በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል ከጥቅምት 27-30 ቀን 2012 ዓ.ም. የሚካሄድ ሲሆን ተሳታፊዎች ልዩ ልዩ የስፖርት ትጥቅ የሚያገኙበት እንዲሁም የተለያዩ ስፖርቶችን የሚሞክሩበት እና የሚዝናኑበት ነው።

    ለበለጠ መረጃ የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የማርኬቲንግ እና ኮሚኒኬሽን ሃላፊ መርከብ መንግስቱን በስ.ቁ. 0911-671002/0116-635757 ኢሜይል፡ merkeb@ethiopianrun.org ማግኘት ይችላሉ።

    ምንጭ፦ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ


Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.