አዲስ አበባ ውስጥ የተካሄደው የሕዳሴ ግድብ ድርድር ኢትዮጵያና ግብፅ በመቃረናቸው ስምምነት ላይ ሳይደረስ ተጠናቀቀ

Home Forums Semonegna Stories አዲስ አበባ ውስጥ የተካሄደው የሕዳሴ ግድብ ድርድር ኢትዮጵያና ግብፅ በመቃረናቸው ስምምነት ላይ ሳይደረስ ተጠናቀቀ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #13229
    Anonymous
    Inactive

    አዲስ አበባ (ኢቢሲ) በሕዳሴው ግድብ ዙሪያ እየተካሄደ በነበረው ድርድር ግብጽ አዳዲስ ሀሳቦችን በማምጣቷ ኢትዮጵያ ሳትቀበል ቀርታለች። ድርድሩ ለአራተኛ እና ለመጨረሻ ጊዜ የተካሄደ በመሆኑ ስምምነት ላይ ይደረሳል ተብሎ ተጠብቆ ነበር።

    ግብፅ ያቀረበችው ዋነኛው የማያግባባ ሀሳብ የሙሌት ሰንጠረዡ ከ12 ዓመት እስከ 21 ዓመት ይሁን ብላ እንደ አዲስ ማቅረቧ ነው። ግብፅ እስካሁን ወደ መስማማቱ ስትቃረብ ቆይቷ ነው በዛሬው ዕለት (ታህሳስ 30 ቀን 2012 ዓ.ም.) በተደረገው ድርድር አዲሱን ሀሳብ ያነሳችው። ኢትዮጵያ በበኩሏ የሙሌት ጊዜው ከ4 ዓመት እስከ 7 ዓመት የሚል ሀሳብ አቅርባ ስትደራደር ቆይታለች።

    በድርቅ ጊዜ የውሃ አለቃቀቅ እና አሞላል ሂደቱ ምን ይምሰል የሚለው ጉዳይም ኢትዮጵያን እና ግብፅን ያላግባባ ሆኗል። የድርቅ ብያኔ /definition/ ላይም ስምምነት ላይ አልተደረሰም። ግብፅ “የውሃ መጠኑ ከ40 ቢሊዮን ሜትር ኪዩብ በታች ሲሆን ‘ድርቅ ነው’ ተብሎ የተሻለ ውሃ ይለቀቅልኝ” የሚል ሀሳብ ያቀረበች ሲሆን፥ ኢትዮጵያ በበኩሏ “‘ድርቅ’ የሚለው ብያኔ መሰጠት ያለበት የውሃ መጠኑ ከ35 ቢሊዮን ሜትሪክ ኪዩብ በታች ሲሆን ነው” በሚል መከራከሪያ ሀሳብ አቅርባለች። በድርድሩ ላይ እነዚህ ሀሳቦች የማይታረቁ ሆነው ቀርተዋል።

    የኢትዮጵያ ውሃ፣ መስኖ እና ኢነርጂ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶ/ር ኢንጂነር ስለሺ በቀለ በጉዳዩ ላይ በሰጡት አስተያየት “የግብፅ ተደራዳሪዎች ካቀረቡት ሀሳብ አንፃር በአዲስ አበባው ድርድር ላለመስማማት የመጡ ይመስላል” ብለዋል። ከዚህ በፊት የነበረውን መቀራረብ በዚህ ድርድር እንደገና እንዲራራቅ ማድረጋቸውንም ነው ያከሉት ሚኒስትሩ።

    በድርቅ ጊዜ የውሃ አሞላል ሂደት ምን ይምሰል የሚለውም በኢትዮጵያ በኩል ግድቡ ከፍተኛ የውሃ መጠን ከያዘ በኋላ ወደ ግድቡ የሚገባው ውሃ በቀጥታ የማመንጫ ተርባይኑን እየመታ እንዲሄድ እና እንዲለቀቅ እንደሚደረግ ኢትዮጵያ አቋሟን ገልጻለች። ግብፅ ግን ይህ ተቀባይነት የለውም ብላለች። በከፍተኛ ድርቅ ወቅት ደግሞ እስከ 13 ነጥብ 5 ቢሊዮን ሜትሪክ ኪዩብ ውሃ ይለቀቃል የሚል ሀሳብም ከኢትዮጵያ በኩል ቀርቧል። ግብፅ በበኩሏ ወደ 14 ነጥብ 5 ቢሊዮን ሜትሪክ ኪዩብ ከፍ ሊል ይገባል ስትል ተከራክራለች።

    የቴክኒክ ኮሚቴው ውጤት ሪፖርት በሚቀጥለው ሰኞ (ጥር 4 ቀን 2012 ዓ.ም.) ዋሽንግተን ዲሲ ውስጥ በሚካሄድ ስብሰባ ላይ ይፋ ይደረጋል። ይህንን ተከትለሎም የየሀገራቱ መሪዎች የሚወስኑት ውሳኔ በሀገራቱ መካከል ቀጣይ ምን ዓይነት ድርድር ሊካሄድ ይችላል የሚለውን የሚወስን ይሆናል።

    ኢትዮጵያ በዚህ የቴክኒክ ኮሚቴ ላይ በመመሥረት ቀጣይ ድርድሮችን ለማድረግ እንደምትፈልግ ዶ/ር ኢንጂነር ስለሺ ተናግረዋል። በአዲስ አበባው ድርድር መግባባት ላይ ይደረሳል የሚል እሳቤ የነበረ ቢሆንም ተፈላጊው ውጤት አለመገኘቱን ነው ሚኒስትሩ የገለጹት።

    የሆነው ሆኖ የግድቡ ሂደት የማይቋረጥ መሆኑን እና ኢትዮጵያ ከሚቀጥለው ሐምሌ ወር ጀምሮ ግድቡን ውሃ የመሙላት ሂደት እንደምትጀምር ተገልጿል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ)/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ 

    የሕዳሴ ግድብ ድርድር ስምምነት ላይ ሳይደረስ ተጠናቀቀ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.