የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ የተቀናጀ የግብርና ምርምር ፕሮጀክት ተመረቀ

Home Forums Semonegna Stories የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ የተቀናጀ የግብርና ምርምር ፕሮጀክት ተመረቀ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #9878
    Semonegna
    Keymaster

    የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ የጥናትና ምርምር ማኅበረሰብ አገልግሎት ም/ፕሬዚዳንት ዶ/ር አልማዝ አፈራ በዚህ ፕሮጀክት የተሳተፉ ተመራማሪዎችን ያሉትን ተግዳሮቶች ተቋቁመው ለዚህ በመብቃታቸው ምስጋና ቸረዋቸዋል።

    ደብረ ብርሃን (ሰሞነኛ)– የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ የጥናትና ምርምር ማኅበረሰብ አገልግሎት ምክትል ፕሬዚዳንት ጽሕፈት ቤት ከኢፌዴሪ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ባገኘው የገንዘብ ድጋፍ በሰሜን ሸዋ ዞን ኤፍራታና ግድም ወረዳ ይምሎ ቀበሌ በተቀናጀ የአሳ፣ የዶሮ፣ የአትክልትና ፍራፍሬ ምርቶች ላይ ሲያካሂድ የቆየውን የምርምር ፕሮጀክት አጠናቆ ለዞኑ አስተዳደርና ለአካበቢው ማኅበረሰብ አስረከበ።

    በርክክብ ሥነ-ስርዓቱ ወቅት የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ መምህርና መሪ ተመራማሪ ዶ/ር ገዛኸኝ ደግፌ እንደተናገሩት ምርምሩ በትንሽ ቦታ አሳን፣ ዶሮንና አትክልትን አቀናጅቶ ማልማት የሚያስችል የቴክኖሎጅ ዕውቀትን በመጠቀም የአሳ፣ የዶሮና የአትክልት ልማቱን አቀናጅቶ መሥራት እንደሚቻል ነው ብለዋል። በዚህም የዶሮ ኩስን ለአሳዎች ምግብ እንዲውል እንዲሁም “vermicompost” ቆሻሻን ወደ ጠቃሚ ነገርነትና ማዳበሪያነት የሚቀይሩ ትሎችን ለዶሮዎችና ለአሳ ምግብነት እንዲውል የሚያስችል እንደሆነ አብራርተዋል።

    በምስራቅ ጎጃም ዞን ስንዴ አምራች ወረዳዎች ለገበሬዎች የቀረቡላቸው ኮምባይነሮች በምርታቸው ላይ ጉልህ አስተዋጽዖ እያደረጉ ነው

    አቶ ተፈራ ወንድማገኘሁ የሰሜን ሸዋ ዞን ዋና አስተዳደሪ እንዳሉት ይህ ለምርቃት የበቃው የምርምር ሥራ የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ በዞኑ ከሚያከናውናቸው ምርምሮች አንዱ ሲሆን ፣ በደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ ፈጻሚነትና በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የገንዘብ ድጋፍ የተሠራ መሆኑን ተናግረዋል። ዋና አስተዳዳሪው አክለው እንዳስታወቁት ይህንን ምርምር በዞኑ በሚገኙ ወረዳዎችና ቀበሌዎች ለማስፋፋት ትልቅ ኃላፊነትና አደራ የተጣለባቸው መሆኑን አውስተው ለተግባራዊነቱም እንደሚሠሩ ተናግረዋል።

    የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶ/ር ኢንጅነር ጌታሁን መኩሪያ ባደረጉት ንግግር ሚኒስቴር መሥሪያ ቤታቸው ከሚደግፋቸው በሁሉም ዩኒቨርሲቲዎች በሚባል ደረጃ ከ60 በላይ ምርምሮች መካከል የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ አንዱና ውጤታማው በመሆኑ ደስተኛ መሆናቸውን ተናግረዋል። የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ በሚችሉ ትናንሽ ፕሮጀክቶች በመደገፍ የሀገራችንን ልማት ማረጋገጥ ይኖርብናል ብለዋል። ይህን ፕሮጀከት የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ለሁሉም ዞኖችና ወረዳዎች እንዲተላለፍ ማኑዋልና ስታንዳርድ ተዘጋጅቷል። የሰሜን ሸዋ ዞን አስተዳደርም በአማራ ክልል ለሚገኙ ሁሉም ዞኖች እንዲያደርስ ኃላፊነት የተሰጣቸው ሲሆን በቀጣይ በሀገር አቀፍ ደረጃ እንዲሰራጭ አናደርጋለን ብለዋል።

    ዶ/ር አልማዝ አፈራ የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ የጥናትና ምርምር ማኅበረሰብ አገልግሎት ም/ፕሬዚዳንት በበኩላቸው በዚህ ፕሮጀክት የተሳተፉ ተመራማሪዎችን ያሉትን ተግዳሮቶች ተቋቁመው ለዚህ በመብቃታቸው ምስጋና ቸረዋቸዋል። እንደ ፕሬዚዳንቷ ገለፃ፥ በሀገራችን እስከ ሁለት ሚሊዮን የሚደርሱ ሥራ-አጥ ወጣቶች መኖራቸው የሚታወቅ ሲሆን እንደነዚህ ዓይነት የምርምር ሥራዎች ደግሞ ወጣቶችን የኢኮኖሚ ተጠቃሚ በማድረግ ሚናቸው የጎላ ነው ብለዋል። ደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲም ብዙ የምርምር ውጤቶች ያሉት ሲሆን እነዚህን ምርምሮች ወደ ፕሮጀክት መቀየር የሚያስችል ተሞክሮ ስለሆነ ይህ ትልቅ ማሳያ ይሆነናል ብለዋል። በመጨረሻም የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴርንና የኤፍራታና ግድም ወረዳ አስተዳደርን ላደረጉት ድጋፍና ትብብር ምስጋና አቅርበዋል።

    ምንጭ፦ ደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ የተቀናጀ የግብርና ምርምር ፕሮጀክት


Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.