ጎንደር ዩኒቨርሲቲ ለሦስተኛ ጊዜ የአገር አቀፍ ጥራት ልዩ ተሸላሚ ሆነ

Home Forums Semonegna Stories ጎንደር ዩኒቨርሲቲ ለሦስተኛ ጊዜ የአገር አቀፍ ጥራት ልዩ ተሸላሚ ሆነ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #9280
    Semonegna
    Keymaster

    የኢትዮጵያ ጥራት ሽልማት ድርጅት የሚያዘጋጀው ሽልማት ዓላማ በኢትዮጵያ አምራቾችና አገልግሎት ሰጪዎች እንዲሁም በግንባታ ዘርፍ የተሰማሩ ድርጅቶች ለጥራት የሚያደርጉትን ሥራ ማበረታታት መሆኑ በሽልማቱ ሥነ-ሥርዓት ወቅት ተገልጿል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ጎንደር ዩኒቨርሲቲ ለሦስተኛ ጊዜ የአገር አቀፍ የጥራት ሽልማት ልዩ ተሸላሚ ሆነ። ዩኒቨርሲቲው ያገኘውን ሽልማት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንት ደሳለኝ መንገሻ (ዶ/ር) ከፕሬዝደንት ሳህለወርቅ ዘውዴ እጅ ተቀብለዋል።

    የኢትዮጵያ ጥራት ሽልማት ድርጅት ስድስተኛ ዙር የጥራት ሽልማት ጥር 2 ቀን 2011 ዓ.ም. ምሽት በብሔራዊ ቤተ-መንግስት ተካሂዷል። በሽልማትና ዕውቅና ሥነ-ሥርዓቱ ላይ 40 ድርጅቶችና ተቋማት የምስክር ወረቀትና የዋንጫ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል። በውድድሩ ላይ

    ጎንደር ዩኒቨርሲቲ፣ ሐረር ቢራ አክሲዮን ማኅበር እና አማራ መልሶ ማቋቋምና ልማት ድርጅት የአንደኛ ደረጃ ዋንጫ ተሸላሚ ሲሆኑ የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ለተከታታይ ሦስት ዓመታት የጥራት ደረጃውን ጠብቆ አሸናፊ በመሆኑ የልዩ ዋንጫ ተሸላሚ ሆኗል።

    The Ethiopian Quality Award Organization

    ከ336 በላይ ድርጅቶች እንዲመዘገቡ ጥሪ የተደረገ ቢሆንም የተመዘገቡት 52 ነበሩ። ከነዚህ ውስጥ 21 በአምራች፣ አምስት በአገልግሎት፣ አራት በከፍተኛ ትምህርት፣ አምስት በጤና እና አምስት በግንባታ ዘርፍ የተሰማሩ፤ በድምሩ 40 ተቋማት እስከመጨረሻው በውድድሩ የዘለቁ ናቸው።

    የሽልማቱ ዋና ዓላማ በኢትዮጵያ አምራቾችና አገልግሎት ሰጪዎች እንዲሁም በግንባታ ዘርፍ የተሰማሩ ድርጅቶች ለጥራት የሚያደርጉትን ሥራ ማበረታታት መሆኑ በሥነ-ሥርዓቱ ወቅት ተገልጿል።

    የኢትዮጵያ ጥራት ሽልማት ድርጅት የበላይ ጠባቂ የሆኑት የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ የጥራት ጉዳይ የሥነ-ልቦናና የፈረጠመ የኢኮኖሚ የበላይነት እንዲሁም የበለፀገ ማኅበረሰብ መገለጫዎች ናቸው ብለዋል። የምርትና አገልግሎት ጥራትን ለማስጠበቅና ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ከደረሱበት የጥራት ደረጃ ለመድረስ ጠንክሮ መሥራት እንደሚገባም አሳስበዋል።

    የኢትዮጵያ ጥራት ሽልማት ድርጅት በ2000 ዓ.ም በዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከልና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ትብብር የተቋቋመ ነው። ድርጅቱ ሲመሠረት ዓላማውን መንግስት በጥራት ረገድ የሚያደርገውን ጥረት ለመደገፍና የጥራት ጽንሰ ሀሰብን በማኅበረሰቡ፣ በአምራቾች፣ በአገልግሎት ሰጪዎችና በግንባታ (ኮንስትራክሽን) ዘርፍ በተሰማሩ ድርጅቶችና ተቋማት ዘንድ እንዲሰርጽ ለማድረግ ነው። እስካሁን 49 ድርጅቶችና ተቋማት የድርጅቱን የልዕቀት ማዕረግ የዋንጫ ሽልማት አግኝተዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    የኢትዮጵያ ጥራት ሽልማት ድርጅት


Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.