ጉራጌ በክልል የመደራጀት ሕገ መንግሥታዊ ጥያቄ አፋጣኝ ምላሽ እንዲሰጠው የብሔሩ ተወላጆች ጠየቁ

Home Forums Semonegna Stories ጉራጌ በክልል የመደራጀት ሕገ መንግሥታዊ ጥያቄ አፋጣኝ ምላሽ እንዲሰጠው የብሔሩ ተወላጆች ጠየቁ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #13138
    Semonegna
    Keymaster

    ጉራጌ በክልል የመደራጀት ሕገ መንግሥታዊ ጥያቄ የክልሉ መንግሥት በሰላማዊና በሰለጠነ መንገድ አፋጣኝ ምላሽ እንዲሰጠው የብሔሩ ተወላጆች ጠየቁ።

    ኧዣ ወረዳ ፥ጉራጌ ዞን (ሰሞነኛ) – የደቡብ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ክቡር አቶ ርስቱ ይርዳው ከጉራጌ ማኅበረሰብ ጋር በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ በጉራጌ ዞን ኧዣ ወረዳ በደሳለኝ ሎጅ ውይይት አካሄዱ። የውይይቱ ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት ጉራጌ በክልል የመደራጀት ሕገ መንግሥታዊ መብቱ በሰላማዊና በሰለጠነ መልኩ የክልሉ መንግሥት አፋጣኝ ምላሽ ሊሰጠው እንደሚገባ ጥሪ አቀረቡ።

    በጠንካራ የሥራ ባህሉና ከየትኛውም ብሔር ብሔረሰቦች ጋር ተግባብቶ፣ ተቻችሎና ተከባብሮ የመኖር የቆየ ልማድ ያለው የጉራጌ ብሔር ባለፋት 27 ዓመታት በማኅበራዊ፣ በፓለቲካዊና በኢኮኖሚው ከፍተኛ በደልና ጭቆና ሲደርስበት እንደነበር ያስታወሱት አስተያየት ሰጪዎቹ፥ አሁን በመጣው የሀገሪቱ ለውጥ ፍትሃዊ የኢኮኖሚና የፓለቲካ ተጠቃሚነቱ ሊረጋገጥለት እንደሚገባ ተናግረዋል።

    አክለውም ብዙ ጊዜ በክልል የመደራጀት ጥያቄ ሲነሳ ጉራጌ ክልል አያስፈልገውም የሚል አስተያየት የሚሰጥ መሆኑን የገለጹት ተሳታፊዎቹ፥ ክልል የማያስፈልግ ከሆነ አሁን ያለው የዞን አስተዳደር ለምን ያስፈልጋል፣ ጉራጌ በክልል ቢደራጅ ስጋቱ ምንድን ነው የሚል ጥያቄዎች ተነስተው በመድረክ አወያዮቹ ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል።

    የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ መሀመድ ጀማል እንደገለጹት፥ ዞኑ የብዙ ብሔር ብሔረሰቦች መኖሪያ ስትሆን መንግሥት እንኳ ባይኖር ሕዝቡ ራስ በራሱ መምራት የሚችልበት ቱባ ባህል፣ እሴትና እምነት እንዲሁም ባህላዊ የዳኝነት ሥርዓት ያለው ነው ብለዋል።

    የዞኑ ሰላም ለማስጠበቅ የሀይማኖት አባቶችና ሽማግሌዎች እየሠሩት ያለው ሥራ የሚበረታታ መሆኑን የገለጹት አቶ መሀመድ፥ በቀጣይም የሕዝቦች አንድነት ለማጠናከር በትኩረት ይሠራል ብለዋል። ጉራጌ በክልል የመደራጀት ጥያቄ የሚጠይቀው ለቅንጦት ሳይሆን ሕገ መንግሥታዊ መብቱ ስለሆነ መንግሥት አፈጣኝ ምላሽ እንዲሰጥ አቶ መሀመድ ጠይቀዋል።

    በክብር እግድነት የዞኑ ማኅበረሰብ ለማወያየት የመጡት የደቡብ ክልል የብልጽግና ፓርቲ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሞገስ ባልቻ እንደተናገሩት፥ የጉራጌ ብሔር ለሥራ እንጂ ለግጭትና ለንትርክ ጊዜ የሌለው ከየትኛውም ብሔር ብሔረሰብ ጋር ተከባብሮና ተዋዶ በፍቅር የሚኖር ነው ብለዋል። ጉራጌ በክልል እንዲደራጅ ለተጠየቀው ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት አሁን አዎንታዊም ሆነ አሉታዊ መልስ መስጠት እንደማይችሉና በቀጣይ በመመካከር ለህብረተሰቡ ምላሽ እንደሚሰጠው አቶ ሞገስ ተናግረዋል።

    የደቡብ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ክቡር አቶ ርስቱ ይርዳው ከውይይቱ ተሳታፊዎች ለተነሳላቸው ጥያቄዎች መልስ ሲሰጡ እንደተናገሩት፥ በመስቃን ቤተ ጉራጌና በማረቆ መካከል የተፈጠረው ግጭት ለመፍታት ከሀይማኖት አባቶች፣ ከሀገር ሽማግሌዎች እና ከሌሎችም የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር በመሆን ጥረት እየተደረገ መሆኑንና በአጭር ጊዜ መፍትሄ ያገኛል ብለዋል።

    ክቡር ርዕሰ መስተዳድሩ የሕዝቡ በክልል የመደራጀት ጥያቄ ሲመልሱ እንደተናገሩት፥ ጉራጌ በክልል የመደራጀት መብት እንዳለው ጠቁመው ጥያቄው የሀገሪቱ የለውጥ ጉዞ በማያደናቅፍ መልኩ መሆን አለበት በማለት አቋማቸውን ተናግረዋል።

    በመድረኩ የደቡብ ክልል የካቢኔ አባላት፣ ከአዲስ አበባ የመጡ አመራሮችና ተወላጆች፣ ባለሀብቶች፣ የዞን፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር አመራሮች ፣ የሀገር ሽማግሌዎች እንዲሁም ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳታፊ ነበሩ ሲል የዘገበው የጉራጌ ዞን አስተዳደር ሕዝብ ግንኙነት ጽህፈት ቤት ነው።

    ምንጭ፦ የጉራጌ ዞን አስተዳደር ሕዝብ ግንኙነት ጽህፈት ቤት / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ጉራጌ በክልል የመደራጀት

Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.