የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ያስገነባው ጥበበ ግዮን ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በልዩ መርሀ ግብር ይመረቃል

Home Forums Semonegna Stories የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ያስገነባው ጥበበ ግዮን ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በልዩ መርሀ ግብር ይመረቃል

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #8462
    Semonegna
    Keymaster

    ግንባታው ስድስት ዓመታትን የፈጀው የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ጥበበ ግዮን ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በቀን 2000 የሚሆኑ ታካሚዎችን ሊያስተናግድ የሚችል፣ 11 የቀዶ ሕክምና ክፍሎች እና 500 አልጋዎች አንዳሉት ተገልጿል።

    ባሕር ዳር (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ በ207 ሚሊዮን ብር ወጪ ያስገነባው ጥበበ ግዮን ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ነገ በሦስት አገሮች መሪዎች ይመረቃል።

    የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ፍሬው ተገኘ እና የሕክምና ኮሌጅ የሥራ አፈጻጸም ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር የሺጌታ ገላው በጋራ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ዩኒቨርሲቲው የግንባታ ወጪው 207 ሚሊዮን ብር የፈጀውና ተጠናቆ ለአገልግሎት ዝግጁ የሆነውን ጥበበ ግዮን ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል የፌደራልና የክልል ባለስልጣናት በተገኙበት ህዳር 1 ቀን 2011 ዓ.ም. በድምቀት እንደሚያስመርቅ ገልጸዋል።

    በምረቃ ሥነ ስርዓቱ ላይ ከሦስቱ መሪዎች በተጨማሪ የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸውና ሌሎችም ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ ባለስልጣናትና ጥር የተደረገላቸው እንግዶች ይገኛሉ ፕሮፌሰር የሺጌታ ተናግረዋል።

    ከዚሁ መግለጫ ጋር አብሮ እንደተጠቀሰው በዩኒቨርሲቲው የሕክምና ኮሌጅ ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የነበሩ 148 የህክምና ተማሪዎችም ከኮሌጁ ለስድስተኛ ጊዜ ይመረቃሉ።

    በእነዚህ የሆስፒታሉ እና የተማሪዎቹ ምረቃ መርሀ ግብር ላይ የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢፌዴሪ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ (ዶ/ር)፣ የኤርትራ ሀገረ ግዛት ፕሬዚዳንት ኢሳያስ አፈወርቂና የሱማልያ ፌደራላዊ ሪፐብሊክ ፕሬዚዳንት መሐመድ አብዱላሂ መሐመድ በተገኙበት ይከናወናሉ።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንቱ ዶክተር ፍሬው ተገኘ እንደገለጹት በመሪዎቹ የሚመረቀው ሆስፒታሉ የቀዶ ህክምና የሚጠይቁና ወደ ክፍተኛ ሕክምና መስጫ ቦታ የተላኩ (referral) በሽታዎችን የሚያክምና በተለያዩ የትምህርት ክፍሎች (ዲፓርትመንቶች) ውስጥ በሕክምና እና በጤና ባለሙያነት ተማሪዎችን የሚያሰለጥን ነው።

    Ethiopia: Are Ethiopian hospitals constructed in environment-suitable and climate-friendly way?

    ግንባታው ስድስት ዓመታትን የፈጀው ጥበበ ግዮን ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በቀን 2000 የሚሆኑ ታካሚዎችን ሊያስተናግድ የሚችል፣ 11 የቀዶ ሕክምና ክፍሎች ያሉት፣ 500 አልጋዎችን መያዝ የሚችል መሆኑን ፕሮፌሰር የሺጌታ አብራርተዋል። በክልሉ ካሉት ስፔሻላይዝድ ሆስፒታሎች በጥራትም ሆነ በአገልግሎት የተሻለ ሆኖ ለመገኘት መዘጋጀቱንም ገልጸዋል።

    ሀምሌ 7 ቀን 2006 ዓ.ም. ከተመረቀው የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ሪፈራል ሆስፒታል በመቀጠል በክልሉ ስድስተኛ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል እንደሚሆን አስታውቀዋል። አያይዘውም ሆስፒታሉ ለምርቃቱ ቀን ይብቃ እንጅ እጅግ ዘመናዊ የሆኑ የህክምና ቁሳቁሶችና ሌሎች መሟላት ያለባቸው ነገሮች ስላሉ ከመንግስት በተጨማሪ ለጋሽ አካላትና በዚህ ዙሪያ የሚሠሩ ወገኖችን ትብብር የሚጠይቅ መሆኑን ገልጸዋል።

    ሚያዝያ 28 ቀን 1992 ዓ.ም በኢፌዴሪ የትምህርት ሚኒስቴር ስር በሙሉ ዩኒቨርሲቲነት የተመረቀው የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ሀገሪቱ ውስጥ ካሉት ግዙፍ ዩኒቨርሲቲዎች አንዱ ሲሆን፥ በ2010 ዓ.ም  52,830 ተማሪችዎችን፣  219 የትምህርት  ዘርፎች (69 በመጀመሪያ/ባችለር ዲግሪ፣ 118  በሁለተኛ/ማስተር  እና 32 በሶስተኛ/ዶክትሬት ዲግሪዎች) ተቀብሎ ያስተምራል። ዩኒቨርሲቲው ስምንት ካምፓሶች ሲኖሩት፥ በውስጣቸውም አምስት ኮሌጆች፣ አራት ተቋማት (institutes)፣  ሁለት ፋኩልቲዎችና አንድ የሕግ ትምህርት ቤት (School of Law)  አሉት።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ጥበበ ግዮን ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል

Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.