አቶ ታዬ ዳንደአ ― የሞኝ ለቅሶ መልሶ መላልሶ! ኦሪት ዘህወሓት!

Home Forums Semonegna Stories ነፃ አስተያየት (ስለኢትዮጵያ በኢትዮጵያውያን) አቶ ታዬ ዳንደአ ― የሞኝ ለቅሶ መልሶ መላልሶ! ኦሪት ዘህወሓት!

#16193
Anonymous
Inactive

የሞኝ ለቅሶ መልሶ መላልሶ! ኦሪት ዘህወሓት!
(ታዬ ዳንደአ)

የግራ አስተሳሰብ ሁሌ ግራ ተጋብቶ ግራ ያጋባል። ህወሓት የግራ ጁንታ መሆኑ ይታወቃል። የግራ ፖለቲካ ደግሞ ውሸት ሲደጋገም እውነት እንደሚሆን ያምናል። “መስከረም 25/30” የሚደጋገመዉ ለዚህ ይመስላል። ህወሓት ከፈረሶቹ ጋር ብቅ ጥልቅ እያለ ይፎክራል። በሕገ-መንግሥት እና በፌዴራሊዝም ስም ያለቃቅሳል። ከመስከረም 25/30 በኋላ መንግሥት ስለማይኖር “ባለአደራ መንግሥት ከሰማይ ይዉረድልኝ” ይላል። ኢትዮጵያን ወደ ሊቢያ ለመቀየር አቅዶ በሙሉ ኃይሉ ይንደፋደፋል! በእርግጥ ዋነኛ እቅዱ ሰኔ 2012 ዓ.ም. መጨረሻ ላይ ተሞክሮ በኢትዮጵያዊያን የተባበረ ክንድ ከሽፏል! አሁን ቅዠትን እዉነት ለማድረግ በህወሓት አሻንጉሊቶች በከንቱ ዳንኪራ ይመታል። ይህ በአማርኛ ‘የሞኝ ለቅሶ መልሶ መላልሶ’ ይባላል!

የህወሓት ህልም ሩቅ ኖሯል። ኢትዮጵያዊያንን ከፋፍሎ እየገዛ ለመቶ ዓመታት ኢትዮጵያን የመጋጥ ግልፅ ዕቅድ እንደነበረዉ ይታወቃል። በዚሁ አግባብ ለ27 ዓመታት በኢትዮጵያዊያን ሰቆቃ ውስኪ እየተራጬ ሲንደላቀቅ ኖሯል። ያ ሁኔታ መጋቢት 2010 ዓ.ም. ላይ አክትሟል። በኢትዮጵያ ሕዝብ የዘመናት ትግልና በለውጥ አመራሩ ቆራጥ ውሳኔ የህወሓት ጉልበት ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ ተንኮታኩቷል፤ ነገር ግን እዉነታዉ አልዋጥ ብሎታል። የቀን ቅዠት እዉን እየመሰለዉ አስቸግሮታል! ሁሌ ድምፂ ወያኔ ላይ ወጥቶ “ከመስከረም በኋላ ከኔ ውጭ ሌላ የለም” ይላል። “የለም! የለም!” እያለ ግልፅና ተጨባጭ እዉነታን መሰረዝ ይፈልጋል። መቼስ ከዚህ በላይ የሚገርም በዓለም ላይ ምን ይኖራል? ህወሓት ከነሙሉ ጥርሱና ጥፍሩ በነበረበት ወቅት ታግሎት ያቃተዉን ለዉጥ ከሬሳ ሳጥን ደጃፍ ሆኖ “የለም!” በማለት ብቻ ለመቀልበስ ይሞክራል!

ዘንድሮ ‘ሰይጣን ለተንኮሉ ቅዱሳን መጽሐፍትን ይጠቅሳል’ የሚባለዉ በግልፅ መታየት ጀምሯል። ህወሓት በምክንያት የኢሬቻ 2013 ዋነኛ አቀንቃኝ ሆኖ ብቅ ብሏል። በኢሬቻ አስታኮ አዲስ አበባ ላይ ተጀምሮ አዲስ አበባ ላይ እንዲያልቅ ታቅዶ የከሸፈዉን ጦርነት ዳግም ለማወጅ ፈልጓል! ፍላጎቱን ለማሳካት ደግሞ በኦሮሞ ስም የሚነግዱ አሉላ የሚቀልባቸዉን ፈረሶች አዘጋጅቷል! በፈረሶቹ በኩል የኦሮሞ ወጣት ኢሬቻን አሳቦ በነቂስ በመዉጣት ሸገር ላይ እንዲረብሽ ይቀሰቅሳል። በዲጂታል ወያኔ ደግሞ “ኢሬቻ የሰይጠን አምልኮ ነዉ” እያለ በአማራ ስም ያሰራጫል። የኦሮሞን ሕዝብ ‘ጋኔን’ ያለዉ ህወሓት መሆኑ ግን ይታወቃል። በተጨማሪም “ኢሬቻ አዲስ አበባ ላይ መከበር የለበትም!” እያለ በሌላዉ አሻንጉሊቱ በኩል የሸገር ወጣቶችን ይቀሰቅሳል። ኢሬቻ 2009ን የዘነጋነዉ መስሎታል። ያኔ ቢሾፍቱ ላይ በአንድ ቀን ብቻ ከ700 በላይ የኢሬቻ ታዳሚ ኦሮሞዎች በወያኔ አግዓዚ ገደል ውስጥ ተጥለዉ ሞቷል። በዚያ ወሳኝ ወቅት “የኦሮሞ ደም ደሜ ነዉ” ያሉትን የጎንደር ወጣቶች ታሪክ መዝግቧል። ኢሬቻን መደገፍ እና ማሞገስ ከቁርጥ ቀን ወገኖች ያምራል! ዛሬ ወያኔ በግራና በቀኝ የሚያጫውታቸዉን አሻንጉሊቶች ማን ይሰማል?

ታዲያ በመጨረሻ ምን ይሆናል? ውሾቹ እየጮሁ ግመሉ ይጓዛል! ባቡሩ ፍጥነቱን እና አቅጣጫዉን ጠብቆ ወደፊት ይገሰግሳል። ኢትዮጵያዊያን ለዘመናት በከፈሉት ውድ ዋጋ የመጣዉ ለውጥ ከመስከረም 25/30 በኋላም ተጠናክሮ ይቀጥላል! የተቋማት ግንባታ እና ብሔራዊ ውይይት መሠረት ይይዛል። በዋና ዋና ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ መግባባት ይፈጠራል። ህወሓት ሲያበላሸዉ የነበረዉ ብሔራዊ ምርጫም በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ግልፅ፣ አሳታፊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ ይከወናል። የማይኖረዉ ህወሓት እና ተፅዕኖዉ ብቻ ይሆናል። ጓድ ህወሓት ቀስ እያለ ወደ መቃብሩ ጠጋ ጠጋ ይላል! በትግራይ ላይ ጠባሳ ሳይጥል፤ ማንም ሳይነካዉ ራሱን ችሎ ይሞታታል! የትግራይ ሕዝብም እንደወገኖች የነፃነትን አየር ይተነፍሳል! አሉላ ፈረሶቹን የሚቀልብበት መኖ ያጣል። በዚያዉ ጋብቻዉ ለአንዴና ለመጨረሻ ግዜ ይፈርሳል። አሻንጉሊትም አስታዋሽና አጫዋች ያጣል! የሴራና የሸር ሥራ ብኩን ይሆናል። የሌብነት፣ የውሸት፣ የፅንፈኝነት እና የክፋት ዘመን ያበቃል! እዉነት እና ዕዉቀት መርህና መመሪያ ይሆናል! የኢትዮጵያ ኅብረ-ብሔራዊ አንድነት እና ብልጽግና ደግሞ እየጎለበተ ይሄዳል! የኢትዮጵያ ሕዝብ ወንድማማችነትን መሠረታዊ መርሁ አድርጎ በድል ላይ ድል ይጎናጸፋል! ይህ ቃል ነዉ! ቃል ይነቅላል! ቃል ይተክላል! አሜን!!

ታዬ ዳንደአ

አቶ ታዬ ዳንደአ የኦሮሚያ ብልፅግና ፓርቲ ቃል አቀባይ ናቸው።

ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

አቶ ታዬ ዳንደአ