በወቅታዊ ሀገራዊ ሁኔታዎች ላይ የተሰጠ የአቋም መግለጫ ― ኢሕአፓ

Home Forums Semonegna Stories የፖለቲካ ፓርቲዎች ድምጽ (ኢትዮጵያ ውስጥ የሚነቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች) በወቅታዊ ሀገራዊ ሁኔታዎች ላይ የተሰጠ የአቋም መግለጫ ― ኢሕአፓ

#15528
Anonymous
Inactive

በወቅታዊ ሀገራዊ ሁኔታዎች ላይ የተሰጠ የአቋም መግለጫ ― ኢሕአፓ

በጀግኖች ሰማዕታት ብርቱ ተጋድሎና ክቡር መስዋዕትነት የተገነባዉ የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢ.ሕ.አ.ፓ)፥ በታሕሳስ 4 እና 5 ቀን 2012 ዓ.ም. 9ኛ ጉባኤውን በተሳካ ሁኔታ አድርጎ አመራሮቹን መምረጡ ይታወቃል። የኢሕአፓ ቋሚ ኮሚቴ በሀገራዊና ድርጅታዊ አጅንዳዎቸ ላይ ከነሐሴ 2 እስከ ነሐሴ 8 ቀን 2012 ዓ.ም. ድረስ በወቅታዊ የኢትዮጵያ የፖለቲካ-ኢኮኖሚ ሁኔታዎች ላይ፣ በኢትዮጵያ ስላለው የሰላም፣ የዲሞክራሲና የልማት ክንዉን ሂደቶች በስፋት መክሯል። ፓርቲው የ2012 ዓ.ም. የ6 ወራት የዕቅድ አፈጻጸሙን ግምግሞ የ2013 ዓ.ም. የበጀት ዓመት የፓርቲዉ ዕቅድ ላይ ከፍተኛ ዉይይት አድርጓል። በተጨማሪም፥ የፓርቲው አባላትና ደጋፊዎች የሰላማዊ ትግል መርሆዎችና ስልቶችን ተግባራዊ በሚያደርግ፣ የትግል ቁርጠኝነታቸውን ጠብቀው ለማይቀረው ድል እንዲሰለፉና ሀገራቸውንና ሕዝባቸውን ካንዣበበባቸው አደጋ እንዲከላከሉ ጥሪውን አቅርቧል።

የኢሕአፓ ቋሚ ኮሚቴም የሚከተሉትን ዉሳኔዎችና የአቋም መግለጫዎችን በሰፊው ከተወያየ በኋላ አዉጥቷል።

1ኛ. መንግሥት የሕግ የበላይነትን ለማስከበርና በቅርቡ የጀመረውን ለሰላም፣ ለልማትና ለዲሞክራሲ እውን መሆን የሚያደርገዉን ጥረት እያደነቅን፥ ይህን መሰሉ ሕግን የማስከበር ጉዳይ አስቀድሞ ተከናውኖ ቢሆን ኖሮ ዜጎች በጠራራ ጸሐይ ከመገደልና ሃብት ንብረታቸውም ከመውደም መታደግ ይቻል እንደነበር ኢሕአፓ እምነቱን እየገለጸ፥ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ግጭት፣ ሁከትና ብጥብጥ በመፍጠር ለንጹሀን ዜጎች ሞት፣ ስደት፣ እንግልትና መፈናቀል ምክንያት የሆኑ፣ ንብረት ያወደሙና የዘረፉ ወንጀለኞችን ለሕግ በማቅረብ ተጠያቂ የማድረገረ ሂደቱን አጠናክሮ እንዲቀጥል፤ እና ተጠርጣሪዎችና ከሁከቶች ጋር ግንኙነት ያላቸው ሁሉ አፋጣኝ የፍርድ ሂደት እንዲያገኙ ኢሕአፓ መንግሥትን ይጠይቃል።

2ኛ. የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የመጀመሪያ ዙር የውሃ ሙሌት በታቀደለት ጊዜ በመጠናቀቁ ኢሕአፓ የተሰማውን ልባዊ ደስታ እየገለጸ፥ መንግሥት በጣና ሐይቅ ዙሪያ የተከሰተውን የእንቦጭ አረም ችግርና በወንዞቻችን፣ ሐይቆቻችንና በተፈጥሮ ሀብቶቻችን ላይ እየደረሰ ያለውን ብሔራዊ አደጋ ለማስቀረት ሕዝባዊ ንቅናቄ አስፈላጊ በመሆኑ፥ የኢሕአፓ አባላትና ደጋፊዎች የተፈጥሮ ሃብት እንክብካቤንና ጥበቃን ለማጎልበት በንቃት እንዲሳትፉ ጥሪውን ያስተላልፋል።

3ኛ. በደቡብ ክልል እየተከሰቱ ያሉት ግጭቶችና ሰሞኑን በወላይታ ዞን የተፈጸመው ሁከትና ብጥብጥ ወደከፋ ሁኔታ ከመቀየሩ በፊት መንግሥት የ’ክልል እንሁን’ ጥያቄዎችና የአከላልለ ጉዳይን በተመለከተም በተጠናና በማያዳግም ሁኔታ እንዲፈታው እየጠየቅን፥ ችግሮችን በክልሉ በሚኖሩት ሕዝቦች ፍላጎትና ውይይት መሠረት አድርጎ መፍታት አለበት። የአስተዳደር በደል ጥያቄዎቹንና አለመረጋጋቱን ተገን አድርገዉ በሚቀሰቀሱ ግጭቶች ተከትሎ የሚጠፋዉ የሰዉ ሕይወትና የሀገር ሀብት ውድመት በአስቸኳይ እንዲያቆምና ችግሮችም በሰላማዊና ሕጋዊ መንገድ እንዲፈቱ ኢሕአፓ በአንክሮ ይጠይቃል። በግጭቱ ሰበብ ለሞቱት ወገኖች የተሰማንን ጥልቅ ሃዘን እየገለጽን፥ በየትኛውም የፌዴራሉ ክልሎች ውስጥ ለዘመናት ተዋዶና ተከባብሮ የሚኖረውን ሕዝብ እርስ በርስ ለማጋጨትና ሀገራችንን ወደ አልተፈለገ የእርስ በርስ ግጭት ለመክተት የሚሯሯጡ ቡድኖችና ኃይሎችን ለፍርድ ለማቅረብ መንግሥት እየወሰደ ያለውን ርምጃ ኢሕአፓ ይደግፋል።

4ኛ. የኮቪድ-19 ወረርሽኝኝ በሀገራችን ከተከሰተ ጊዜ ጀምሮ፣ በመላው ኢትዮጵያ ከፍተኛ የሆነ የኑሮ ውድነትና ሥራ አጥነት፣ የኢኮኖሚ ጫና በመላው ሕዝባችን ላይ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ በመሆኑና የዕለት-ተዕለት የምግብና ሸቀጣ ሸቀጦችም ላይ ከፍተኛ የሆነ የዋጋ ንረት እየተከሰተ ስለሆነ፥ የዋጋ ንረቱም የሀገራዊ ምርት እጥረት ሳይሆን የአቅርቦት ውሱንነት ያስከተለው በመሆኑ፣ መንግሥት በአፋጣኝ ገበያውን በመቆጣጠርና ሕዝቡን ካልተገባ የኢኮኖሚ ምዝበራ እንዲታደገው እንጠይቃለን። ከዚህ በተጨማሪ በአዲስ አበባ ከተማ ያለዉ ከፍተኛ የሕዝብ ትራንስፖርት እጥረት ረጃጅም ሰልፎችን እየፈጠረ ሕብረተሰቡን ለቫይረሱ ተጋላጭ እንዲሆን እያደረገዉ ስለሆነ አፋጣኝ መፍትሄ እንዲፈለግለት አሕአፓ በአጽንኦት ያሳስባል።

5ኛ. በተለያዩ የሀገራችን ክልሎች በሰላምና መረጋጋት እጦት ምክንያት አካላቸው ለጎደለባቸው፣ ንብረታቸው ለወደመባቸው፣ ከመኖሪያ ቀያቸው ለተፈናቀሉና ለችግር ተጋላጭ ለሆኑ ዜጎች መንግሥት ወደ ሰላማዊ ኑሮአቸው መመለስ የሚችሉበትን ካሳ እንዲከፍልና ዜጎች በብሔራቸዉና በማንነታቸዉ እየተለዩ የሚደርስባቸዉን ጥቃት እንዲከላከል ኢሕአፓ ጥሪዉን ያቀርባል።

6ኛ. የተለያዩ ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣናትና የብልጽግና ከፍተኛ አመራሮች በተለያዩ ሕዝባዊ መድረኮች ስብሰባዎችና ብዙሃን መገናኛ ድርጅቶች ላይ የሚያደርጉት ከፋፋይና በተወሰኑ ብሄሮች ላይ የሚያነጣጥር ንግግር በኢትዮጵያዉያን ዜጎች መካከል ለብዙ ዘመናት አብሮ የኖረዉን የመቻቻልና የመከባበር እሴት የሚሸረሽርና ለጥላቻ፣ ለግጭትና እርስ በርስ በጥርጣሬ ዓይን ለመተያየት በር የሚከፍት አደገኛ ተግባር ስለሆነ፥ ኢሕአፓ እንደዚህ ዓይነት ንግግሮች እንዲታረሙ በጥብቅ ያሳስባል፤ ለአብነትም፥ ሰሞኑን የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝደንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ ብልጽግናን በተመለከተ ያደረጉት ንግግር በኢትዮጵያዉያን መካከል የነበረዉን የእርስ በርስ ግንኙነትና ዉሁድ ኢትዮጵያዊነትን የሚሸረሽር፣ አደገኛና ዘረኛ ሀሳብ መሆኑ ግልጽ ነዉ፤ ይህ ሀሳብ እዉን የብልጽግና ፓርቲ ሀሳብ ከሆነ የተረኝነት ጉዳይ እንጂ የለዉጥ ጉዳይ ሊሆን ስለማይችል ሀሳቡ የግለሰብ ወይም የፓርቲዉ ሀሳብ መሆን አለመሆኑን መንግሥት ግልጽ እንዲያደረግ እንጠይቃለን።

7ኛ. በፌደራል መንግሥትና አምባገነኑ ህወሓት በሚመራዉ በትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት መካካል ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተካረረ የመጣዉ ዉዝግብና አለመግባባት በንጹሃን የአማርኛና የትግርኛ ቋንቋ ተናጋሪ ማኅበረሰቦች የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴና ኑባሬ ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ እየፈጠረ መሆኑ እሙን ነዉ። ስለዚህ መንግሥት ለንጹሃን ዜጎች ሲል የሕግ የበላይነትን በማስከበር በኩል ጥብቅ እርምጃ በመዉሰድ ስርዓት አልበኞችንና አምባገነኖችን ለሕግ እንዲያቀርብ እየጠየቅን፥ ያለምርጫ ቦርድ ፈቃድና ዕዉቅና ሁሉም ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ሳያካትት ህወሓቶች በተናጠል የፊታችን ጳጉሜ 4 ቀን 2012 ዓ.ም. ሊያደርጉት ያቀዱትን ምርጫም ጣልቃ ገብቶ እንዲያስቆም ኢሕአፓ በአጽንኦት ይጠይቀል።

8ኛ. ፓርቲያችን ኢሕአፓ ባለፉት 6 (ስድስት) ወራት ውስጥ ያከናወናቸዉን ዋና ዋና ተግባራት በጥልቀት የገመገመ ሲሆን፥ በኢትዮጵያ የዘመናዊ የፖለቲካ ታሪክ ውስጥ ደማቅና ጉልህ ስፍራ ያለውና ዘመን ተሻጋሪ የሆነዉ የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) የኢትዮጵያን ሕዝብ ታግሎ-በማታገል መርሆውና አይበገሬነቱ ጸንቶ የሚገኝ ድርጅት መሆኑን ለመላው አባላቱና ደጋፊዎቹ እየገለጸ፥ ከርዕዮት-ዓለማችን ከማኅበራዊ ዲሞክራሲ (social democracy) ጋር ተመሳሳይነትና ተቀራራቢነት ያላቸውንና በኢትዮጵያ ሕዝብ አንድነትና እኩልነት ላይ ጽኑ እምነት ያላቸውን ፓርቲዎችና የፖለቲካ ኃይሎች ሁሉ የትብብርና የአጋርነት ጥሪ ያቀርብላችኋል።

ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!!

ኢ.ሕ.አ.ፓ ለተሻለ ነገ!!

የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ)