የፖለቲካ ፓርቲዎች ድምጽ (ኢትዮጵያ ውስጥ የሚነቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች)

Home Forums Semonegna Stories የፖለቲካ ፓርቲዎች ድምጽ (ኢትዮጵያ ውስጥ የሚነቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች)

Viewing 15 posts - 1 through 15 (of 54 total)
  • Author
    Posts
  • #12409
    Semonegna
    Keymaster

    ሀገር የማዳን ጥሪ
    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ሕዝብ ግንኙነት

    ባለፉት ሁለት ቀናት ውስጥ በሥርዓት አልበኞች በተወሰደ የጥፋት እርምጃ የማይተካ የዜጎቻችንን ሕይወት አጥተናል፣ የብዙዎች አካል ጎድሏል፣ ዜጎች ለፍተው ያፈሩት ንብረት ወድሟል እዲሁም በተዘጉ መንገዶች ምክንያት ዜጎች ተንገላተዋል፤ የሀገሪቷ የኢኮኖሚ እቅስቃሴም ተስተጓጉሏል።

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) በዜጎች ሕይወት ላይ በደረሰው ጥፋት የተሰማውን ጥልቅ ሐዘን ይገልጻል። ሕይወታቸውን ላጡ ዜጎች ቤተሰቦች እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ መጽናናትን ይመኛል። የተፈጸመውን ሕገ ወጥ እና አሳፋሪ ተግባር አጥብቆ ያወግዛል!

    የፖለቲካ ፍላጎትን በኃይል ለመጫን የሚደረጉ የሥርዓት አልበኞች ሙከራዎች ከጊዜ ወደጊዜ እየተባባሱ መጥቷል። የመንግሥት እነዚህን ሙከራዎች አስቀድሞ የመተንበይ፣ ሲከሰቱም አፋጣኝ እና ተገቢውን ምላሽ የመስጠት አቅሙ ከጊዜ ወደጊዜ መሻሻል እየታየበት አይደለም። በዚህም ምክንያት የዜጎች ሕይወት በተደጋጋሚ አደጋ ላይ ወድቋል፤ አሁንም እየወደቀ ይገኛል። በቁጥር ቀላል የማይባሉ ዜጎች በሀገራቸው ደኅንነታቸው ተጠብቆ በነጻነት የመንቀሳቀስ፣ የመሥራት እና የመኖር መብታቸውን መጠቀም የማይችሉበት ብቻ ሳይሆን በማያቋርጥ ስጋት እና ጭንቀት ውስጥ ሕይወታቸውን እንዲመሩ የተገደዱበት ደረጃ ላይ ደርሰናል። ከዚህም አልፎ በዕምነት ተቋማት እና ማንነት ላይ ያነጣጠሩ ጥቃቶች ደግሞ በማኅበረሰቡ ውስጥ ያለመተማመን ክፍተት እንዲፈጠር ምክንያት እየሆነ ነው። ይህ ጉዳይ በአስቸኳይ የማይታረም ከሆነ የሽግግር ሂደቱ ተጨናግፎ ወደማንወጣው ቀውስ ውስጥ ሊከተን ይችላል።

    መንግሥት የችግሩን ጥልቀት እና ሕግ የማስከበር ድክመቱን በሚገባ ፈትሾ በአስቸኳይ ክፍተቶቹን እንዲያስተካክል እና የዜጎችን ሰላም እና ደኅንነት የማስጠበቅ እና ጥፋተኞችን ሕግ ፊት የማቅረብ ኃላፊነቱን በአግባቡ እንዲወጣ ከመቼውም ጊዜ በላይ አጥብቀን እናሳስባለን።

    መላው ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያዊያን ከመቼውም ጊዜ በላይ የጋራ ሀገራችንን ከጥፋት አፋፍ ለማዳን የምንችለውን ሁሉ ማድረግ የሚገባን ወቅት ላይ መሆናችንን ተገንዝበን ልዩነቶቻችንን አቻችለን በአንድነት እንድንቆም እና ሀገራችን ከተደቀነባት ከባድ አደጋ እንድንታደግ ከአደራ ጭምር ጥሪ እናስተላልፋለን።

    የኢዜማ ሕዝብ ግንኙነት

    ምንጭ፦ ኢዜማ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    —–
    ተመሳሳይ ዜናዎች፦

    ሀገር የማዳን ጥሪ

    #15134
    Anonymous
    Inactive

    ሂሩት ክፍሌ ማን ናቸው?

    አዲስ አበባ (ኢዜማ) – ሂሩት ክፍሌ በ1967 ዓ.ም. በጎንደር ከተማ ነው የተወለዱት። ትውልዳችው ጎንደር ቢሆንም እድገታቸው ግን በአዲስ አበባ ከተማ ነው። የመጀመሪያ ደረጃ እና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በአዲስ አበባ ከተማ በቀድሞ እቴጌ መነን የአሁኑ የካቲት 12 ትምህርት ቤት ተከታትለዋል።

    ሂሩት የፖለቲካ ተሳትፎ አሀዱ ብለው የጀመሩት በአስራት ወልደየስ (ፕሮፌሰር) አማካኝነት በተመሠረተው የመላው አማራ ሕዝብ ድርጅት (መአህድ) መሥራች አባል በመሆን ነበር። ይህ የፖለቲካ ተሳፏቸው መአህድ ወደ መላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ከተለወጠ በኋላ የቀጠለ ሲሆን መኢአድ ቅንጅት ለአንድነት እና ለዴሞክራሲ (ቅንጅት) ጋር ከተጣመረ በኋላ በቅንጅት ውስጥም በአባልነት ተሳትፎ አድርገዋል። በ1998 ዓ.ም. የቅንጅቱ አመራሮች ወደ ወህኒ ሲጋዙ ከቅንጅት አመራሮች ጋር ወደ ወህኒ ከወረዱት አባላት መካከል አንዷ የነበሩ ሲሆን ‹‹ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በኃይል ለመናድ›› የሚል ክስ ቀርቦባቸው 18 ዓመት ተፈርዶባቸው ነበር። ሁለት ዓመት ለተጠጋ ጊዜ ከሌሎች የቅንጅት አመራር እና አባላት ጋር ከታሰሩ በኋላ ‹‹በምኅረት›› በሚል በ2000 ዓ.ም. የአዲስ ዓመት ዋዜማ ከእስር ተለቀው ነበር። ከቅንጅቱ እስር ከተለቀቁ በኋላ ብዙም ሳይቆይ በ2003 ዓ.ም. በድጋሚ በእነ ኤልያስ ክፍሌ መዝገብ ‹‹በሽብር›› ተከሰው 19 ዓመታት ተፈርዶባቸው ነበር። በዚህ ክስ 6 ዓመታት ከታሰሩ በኋላም በ2009 ዓ.ም. ከእስር ‹‹በምኅረት›› ሊለቀቁ ችለው ነበር።

    ሂሩት ከእስር ከተለቀቁ በኋላ በ2011 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) ሲመሠረት መሥራች አባል ከመሆናቸውም በተጨማሪ የፓርቲው ብሔራዊ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባልና የሙያ ማኅበራት ተጠሪ ሆነው እያገለገሉ ይገኛሉ።

    ሂሩት ክፍሌ ኢትዮጵያ ውስጥ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እንዲገነባ፣ ለውጥ እንዲመጣና አምባገነኑ የህወሓት/ኢሕአዴግ አገዛዝ ከፌደራል መንግሥትነት ሥልጣኑ እንዲወገድ ከፍተኛ ዋጋ ከከፈሉ ዜጎች መካከል በግምባር ቀደምነት የሚነሱ ኢትዮጵያዊት ናቸው። እጅግ በጣም ጥቂት እንስቶች በሚሳተፉበት የኢትዮጵያ ተቃውሞ ፖለቲካ ውስጥ በመሳተፍም የፅናት ምሳሌ የሆኑ ዜጋ ናቸው። በሥልጣን ላይ የነበረው የህወሓት/ኢሕአዴግ አገዛዝም ለሁለት ጊዜያት ያህል አስሯቸው በድምሩ ለ9 ዓመታት በፖለቲካ እስረኝነት አሳልፈዋል። ለውጥ መጣ በሚባልበት ጊዜም የበኩሌን አስተዋፅኦ ልወጣ በማለት ኢዜማን በመመሥረት ፓርቲውን በከፍተኛ ኃላፊነት እያገለገሉ ይገኛሉ።

    መረጃ ― የመሥራች አባል ሂሩት ክፍሌ መታሰር እና አሁን ያሉበት ሁኔታ

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የሥራ አስፈጻሚ አባል እና የሙያ ማኅበራት ተጠሪ ሂሩት ክፍሌ ማክሰኞ ሐምሌ 7 ቀን 2012 ዓ.ም. ከመኖሪያ ቤታቸው በፖሊስ ተወስደው መታሰራቸው ይታወሳል። በተመሳሳይ ቀን ፖሊስ የፍርድቤት ማዘዣ በመያዝ መኖሪያ ቤታቸውን የፈተሸ ሲሆን ሦስት የተንቀሳቃሽ ስልክ ቀፎዎች፣ ልጃቸው የሚገለገልበት ከሚሠራበት ድርጅት የተሰጠው ላፕቶፕ ኮምፒውተር እና የቤተሰብ ዝግጅት የተቀዳበት የቪዲዮ ካሴት ከመኖሪያ ቤታቸው ተወስዷል።

    ሐምሌ 8 ቀን 2012 ዓ.ም. ከሰዓት የኢዜማ ጠበቃ ሂሩትን አግኝተው የተያዙበትን ሁኔታ እና የተጠረጠሩበት ጉዳይ ላይ ተወያይተዋል። ሐሙስ ሐምሌ 9 ቀን 2012 ዓ.ም. ፍርድ ቤት ከጠበቃቸው ጋር የቀረቡ ሲሆን ፖሊስ «ሰኔ 23 ቀን 2012 ዓ.ም. አዲስ አበባ ውስጥ ሁከት እንዲነሳ አስተባብረዋል» ብዬ ጠርጥሬያቸዋለሁ ብሏል። ፖሊስ ተጨማሪ ምርመራ ለማድረግ 14 ቀን ጠይቆ የነበረ ቢሆንም ፍርድ ቤቱ 10 ቀን ፈቅዷል። ፍርድ ቤቱ በቤተሰብ የመጎብኘት ሕገ መንግሥታዊ መብታቸው እንዲከበር ሂሩት ያቀረቡትን አቤቱታ ተንተርሶ በቤተሰብ እንዲጎበኙ እንዲሁም አልባሳት እና ምግብ እንዲገባላቸው ለፖሊስ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር። ፖሊስ ትዕዛዙን እስከ አርብ ሐምሌ 10 ቀን 2012 ዓ.ም. ከሰዓት ድረስ ሳያከብር የቆየ ቢሆንም ከአርብ ከሰዓት በኋላ የፍርድ ቤቱን ትዕዛዝ በመቀበል ለሂሩት አልባሳት እና ምግብ እንዲገባላቸው ፈቅዷል።

    ኢዜማ ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር ያሉት የሥራ አስፈጻሚ አባል ሂሩት ክፍሌ እና ሌሎችም ዜጎች በሕገ መንግሥት እውቅና የተሰጠው የሰብዓዊ እና የተያዙ ዜጎች መብቶቻቸው ምንም ሳይሸራረፍ እንዲከበርላቸው እና የተፋጠነ ፍትህ እንዲያገኙ ባሳለፍነው ሳምንት በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ማሳሰቡ ይታወሳል።

    ምንጭ፦ ኢዜማ

    ሂሩት ክፍሌ

    #15339
    Anonymous
    Inactive

    ፖሊስ የሕግ የበላይነትን ለማስከበር ቀድሞ የሕግ የበላይነትን እራሱ ሊያከብር ይገባል!
    ከኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የተሰጠ መግለጫ

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ሕዝብ ለዘመናት የታገለለትን የፍትሃዊ እና ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ምሥረታ ግቡን እንዲመታ ለማገዝ ከየትኛውም በሀገራችን ካለ የፖለቲካ ፓርቲ በላይ እራሱን በማደራጀት እያዘጋጀ የሚገኝ የፖለቲካ ፓርቲ ነው።

    የፓለቲካዊ ለውጥ ወይንም ሽግግር አስተማማኝ ዋስትና ተቋማት ብቁ፣ ነፃ እና ገለልተኛ ሆነው መቆም መጀመራቸው እና መቀጠላቸው ትልቁን ድርሻ እንደሚይዝ አያጠራጥርም። እነዚህ ለአንድ ሀገር ሕዝብ በሰላም እና በአንድነት የመኖር ዋስትናን የሚያረጋግጡ ተቋማት ከየትኛውም የግለስብም ሆነ የፓርቲ ፍላጎት ራሳቸውን በማላቀቅ በሂደት በሕግና በሕግ ብቻ የሚሠሩበት ሁኔታ እየፈጠሩ መሄድ እንዳለባቸው ኢዜማ ያምናል፤ ለሂደቱም ውጤታማነት በፅናት ይታገላል። በተለይም የሕግ የበላይነትን ማስከበር ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ፤ የዜጎችን ደህንነት ለማስጠበቅ እና የሀገር አንድነትን ለማረጋገጥ ዋነኛው ግብዓት ነው። በዚህ ደረጃ የሚሠሩ ተቋሞችን መገንባት የረጅም ጊዜ ሥራ እንደሚፈልጉ ብንረዳም ሕግን ማስከበር የሚገባቸው ተቋማት የሕግ የበላይነትን የሚሸረሽር ተግባር ላይ ሲሳተፉ መመልከት ደግሞ አሰዛኝ ክስተት ይሆናል፡፡

    ባለፉት ሁለት ዓመታት ከአንባገነናዊ ሥልጣኑ የተባረረው እና ለውጡ የመጣባቸው ኃይሎች እንዲሁም ለውጡን ራሳቸው በቆፈሩት ቦይ ብቻ እንዲፈስ የፈለጉ ቡድኖች በጋራም ሆነ በተናጥል በፈጠሯቸው ትርምሶች ክቡር የሆነው የዜጎች ሕይወት ጠፍቷል፤ አካል ጎድሏል፤ ንብረት ጠፍቷል። በእነዚህ ግዚያት ውስጥ የክልልም ሆነ የፌደራል መንግሥት አስተዳደሮች እንዲሁም የፀጥታ እና የፍትህ አካላት ባሳዩት ከፍተኛ የዝግጅትና የአፈፃፀም አቅም ውሱንነት ለደረሰው ከፍተኛ ጉዳት በግልፅ ይቅርታ ሊጠይቁና አስፈላጊውን ካሳ ሊከፍሉ እንደሚገባ ማሳሰባችን ይታወሳል።

    ሕዝብ ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እስክንሻገር ድረስ ከቀጥተኛ ውክልና ፍጹም ባነሰ ስምምነት ሥልጣን ላይ እንዲቆይ ፈቅዶ ከለውጡ በፊት ያጠፋውን ጥፋት ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የምናደርገውን ሽግግር አግዞ እንዲክስ ሌላ ዕድል የተሰጠው ገዢው ፓርቲ እንዲሁም ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች (እኛንም ጨምሮ) ከዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ሊያዘገዮን ከሚችሉ እንቅስቃሴዎች ሁሉ መታቀብ የሚገባን ወቅት ላይ ደርሰናል። በተለይ ገዢው ፓርቲ ከመቼውም ጊዜ በላይ የያዘው ሥልጣን የሰጠውን የሕግ የበላይነትን የማስከበር ዋነኛ ኃላፊነት እና ታሪካዊ አደራ አሁን የደረስንበት ወቅት ግድ የሚለውን ከፍተኛ ጥንቃቄ እና ብስለት ጋር መወጣት ይገባዋል። የሕግ የበላይነትን ማክበር በጣም አስፈላጊው ግን ደግሞ በጣም ትንሹ ግዴታው ነው ብለን እናምናለን።

    በሀገራችን ያሉ የፍትህ ተቋማት በተግባር የሚፈተኑበት ወቅት አሁን ነው። ከየትኛውም አካል የተፈጠርን ወይምን ሊፈጠር ይችላል ከሚሉት ሥጋት ወይንም ከግለሰብም ሆነ ከየትኛውም የፓለቲካ ፓርቲ ከሚመጣ ሙገሳም ሆነ ወቀሳ በራቀ መልኩ ፓሊስ በቁጥጥር ስር ያዋላቸው ዜጎች የተቀላጠፈ እና እውነተኛ ፍትህ የማግኘት ሕገ መንግሥታዊ መብት የሚከበርበትን መንገድ በማረጋገጥ ማኅበረሰቡ በፍትህ ተቋማት እና ሥርዓቱ ላይ ለረጅም ጊዜ ያጣውን ዕምነት መልሶ መገንባት የሚጀምሩበት ወቅት መሆን ይገባዋል።

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ሥራ እስፈፃሚ አባል እና የሙያ ማኅበራት ተጠሪ ሂሩት ክፍሌ ከሐምሌ 7 ቀን 2012 ዓ.ም ጀምሮ ለ22 ቀናት በፓሊስ ቁጥጥር ሥር ቆይተው ሐምሌ 29 ቀን በ6,000 ብር ዋስ ከእስር ተለቀዋል። ሂሩት በቁጥጥር ስር ከዋሉበት ቀን ጀምሮ «ለምን ታሰሩ?» ወይንም «ይፈቱ!» የሚል ጥያቄ ከማቅረብ ይልቅ ጉዳዩን በቅርበት ስንከታተል እና ሁሉም ተጠርጣሪዎች ሰብዓዊ መብታቸው ተጠብቆ የተፋጠነ ፍትህ እንዲያገኙ ስንጠይቅ ቆይተናል።

    ፓሊስ የዜጎችን መብት ለማስከበር እና አጥፊዎችን ለመለየት የሚረዳው ዜጎችን ከማሰሩ በፊት ከጥርጣሬ በላይ በወንጀል መሳተፋቸውን የሚያስረዳ ማስረጃ እንዲኖረው የሚያስገድደውን መሠረታዊ መርህ በመተው ሂሩት በወንጀል ድርጊት ተሳታፊነት ጠርጥሬያቸዋለው በማለት ለሁለት ግዜ የምርመራ ጊዜ ጠይቆ ተፈቅዶለታል። ለሁለተኛ ጊዜ ተጨማሪ የምርመራ ቀን ለፖሊስ የፈቀደው ፍርድ ቤት በተጨማሪው ቀናት ፖሊስ ምርመራውን አጠናቆ እንዲቀርብ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር። ፖሊስ የተሰጠውን ትዕዛዝ ሳያከብር ተፈጽሟል ያለው ወንጀል 35 ቀን ካለፈው በኋላ ሐምሌ 28 ቀን 2012 ዓ.ም. ለሦስተኛ ጊዜ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ጠይቋል። የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ 2ኛ ወንጀል ችሎት የፖሊስ ጥያቄን ውድቅ አድርጎ ሂሩት በ6,000 ብር ዋስ ከእስር እንዲለቀቁ ትዕዛዝ ሰጥቷል። ፖሊስ ፍርድ ቤቱ በግልጽ የሰጠውን ትዕዛዝ የመፈቻ ወረቀቱን አልቀበልም በማለት ጥሷል። ሂሩትንም ያለምንም ምክንያት በእስር እንዲቆዩ በማድረግ መሠረታዊ መብታቸውን ረግጧል። ይህ ድርጊት በምንም ዓይነት ተቀባይነት የሌለው እና ሕግን አስከብራለው ከሚል ተቋም በፍጹም የማይጠበቅ እንዲሁም አልፈነዋል ያልነውን የፖሊስ እራሱን ከሕግ በላይ አድርጎ የመቁጠር ፍጹም የሆነ የማን አለብኝነት ትዕቢት አሁንም እንዳለ የሚያረጋግጥ ተግባር ሆኖ አግኝተነዋል። ፖሊስ ተመሳሳይ ድርጊት ሌሎች ዜጎች ላይ በተከታታይ ይህ ድርጊት ለሕግ ግድ የማይሰጠው አንድ ፖሊስ ወይንም ጥቂት ፖሊሶች ያደረጉት ሳይሆን እጅግ አሳሳቢ የሆነ ተቋማዊ ችግር እንደሆነ ተገንዝበናል።

    አሁንም ፖሊስ የፍርድ ቤት ትዕዛዝን ያለመቀበል መደበኛ ተግባር እንዳያደርገው ስጋት ያለን ሲሆን፥ ፖሊሶች በመንገድ ላይ ዜጎችን ሰብዓዊ እና ዴሞክራሲያዊ መብት እንዲሁም ዜጎች ሃሳባቸውን በሚመቻቸው መንገድ የመግለፅ መብትን ለማፈን የሚያደርጉት እንቅስቃሴ፥ ተቋሙ ለለውጥ ሩቅ መሆኑን የሚያመላክት ሆኖ አግኝተነዋል። መንግሥት ይህን ተቋም በማረም ማስተካከያ የማያድረግ ከሆነ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ጅምሮቻችን አደጋ ላይ እንደሚወድቁ ሊታወቅ ይገባል፡፡

    ፖሊስ በሕብረተሰቡ ዘንድ ያለውን አመኔታ መልሶ መገንባት ትልቁ የቤት ሥራው መሆኑን የሚገነዘብ እና ቅንጣት ታክል የሚያሳስበው ጉዳይ ከሆነ፥ ይህንን ድርጊት የፈጸሙ አባላቱ ላይ የማያዳግም እርምጃ ወስዶ ለሕዝብ ይፋ እንዲያደርግ፣ ለሂሩት እና ተመሳሳይ ድርጊት ለፈጸመባቸው ዜጎች ሁሉ በይፋ ይቅርታ እንዲጠይቅ እንዲሁም ከእንደዚህ ዓይነት አይን ያወጣ ማን አለብኝነት ከአሁን በኋላ እንዲታቀብ እናሳስባለን።

    በዚህ አጋጣሚ የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ እና ከፍተኛ ፍርድ ቤቶች ፖሊስ ለዜጎች መብት ግድ ሳይሰጥ በእስር ላይ ለማቆየት ያቀረበውን ጥያቄ ውድቅ በማድረግ የሕግ የበላይነትን ለማስከበር እና የዜጎችን መብት ለመጠበቅ ለሰጡት ውሳኔ ያለንን አክብሮት እና ምስጋና እንገልጻለን።

    በመጨረሻም ከፍትሃዊ እና ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ውጪ አሰተማማኝ ሰላም፣ ዕድገት እና አንድነት የተጎናፀፈች ኢትዮጵያን መገንባት የማይታሰብ መሆኑን ሁላችንም ተረድተን ለፍትሃዊ እና ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መገንባት ሁላችንም ባለድርሻ አካላት የበኩላችንን አውንታዊ አስተዋፅዖ እንድናደርግ አጥብቀን እንጠይቃለን።

    ነሐሴ 1 ቀን 2012 ዓ.ም
    የኢዜማ ሕዝብ ግንኙነት

    #15413
    Anonymous
    Inactive

    የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ መግለጫ
    ሀገራችን ካጋጠማት ፈተና እንድትወጣ በሰላማዊ ትግላችን እንድንቀጥል የቀረበ ጥሪ

    ያለፈው የሰኔ 22 ቀን 2012 ዓ.ምን ክስተት ተከትሎ በሀገራችን በተቀሰቀሰው የዘር ማጥፋት ወንጀል የንብረት ጉዳት ደርሷል፤ ዜጎች በሃይማኖታቸው እና በብሔራቸው ምክንያት ለህልፈተ ሕይወት ተዳርገዋል፤ ሃብት ንብረታቸውም ወድሟል። ለዚህ የዘር ማጥፋት ወንጀል ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ) ዋነኛ ተጠያቂው የሥርዓቱ አውራዎች በተለይም የኦህዴድ/ብልጽግና፤ ብሔረሰብን በብሔረሰብ ላይ የሚያነሳሳ እኩይ ተግባር መሆኑን በወሰድነው የአቋም መግለጫ በተደጋጋሚ መግለፃችን ይታወሳል። ከሰሞኑም በድብቅ ወጥቶ የተደመጠው የአቶ ሽመልስ አብዲሳ ምስጢራዊ ንግግር የአቋማችንን ትክክለኛነት አረጋግጦልናል።

    ሆኖም የሥርዓቱ ዓይን ያወጣ ክህደት ከዚህ እኩይ ክስተት ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት የሌላቸውን የፓርቲያችን ከፍተኛ አመራር አባላት አቶ እስክንድር ነጋ፣ አቶ ስንታየሁ ቸኮል፣ ወ/ሮ ቀለብ ስዩም እና ሌሎች አባላትና ደጋፊዎቻችን ለሰው ሕይወትና ንብረት ውድመት ተጠያቂ ናችሁ በሚል አስረው እጅግ የሚያሳዝን ተግባር በመፈፀም ላይ ይገኛል። ከአንድ ወር በላይ በቆየው የፍርድ ቤት ሂደት የታየው እጅግ አሳፋሪ ትዕይንት በኢትዮጵያ አሁንም ፍትህ ቀን እንዳልወጣላት በገሃድ ያሳየ ነው። የሥርዓቱ ቁንጮ ነኝ የሚለው ኦህዴድ/ብልጽግና በገሃድ በሚታይ መልኩ የፍትህ ሥርዓቱን መቀለጃ እና የፖለቲካ ፍላጎቱን ማስፈፀሚያ መሣሪያ አድርጎታል። የፍትህ ሥርዓቱ እንኳን ሊሻሻል በህወሓት/ኢህአዴግ ዘመን ከነበረው ሁኔታ በብዙ መልኩ የባሰ ሁኖ ይገኛል። በተለይ ሰሞኑን በድምጽ የተለቀቀው የኦህዴድ/ብልጽግና ከፍተኛ አመራር ሕገ-ወጥ እና ለሀገር ህልውና አደገኛ የሆነ ንግግር /በከፊልም ወደ መሬት የወረደ መሆኑን ልብ ይሏል/ እንደሚያስረዳው፥ በተደጋጋሚ ስንወተውት የነበረውን በአዲስ አበባም ሆነ በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተዘረጋ ያለውን በተረኝነት ፖለቲካ የተቃኘ፣ አምባገነናዊ አገዛዝን ለማዳበር ተግቶ የሚሠራ አመራር መሆኑን ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ ማስረጃ ሁኖ ቀርቧል። ከመጋረጃ በስተጀርባ ተደብቀው በዘር ማጥፋት ሂደት ውስጥ በዋነኛነት ሲመሩ የነበሩት የሥርዓቱ ዋነኛ ባለስልጣናት ሳይጠየቁ በሰብዓዊ መብት ተሟጋችነታቸው የሚታወቁት የፓርቲያችን ከፍተኛ አመራሮች መጠየቃቸው ሳያንስ፥ የፍርድ ሂደቱ በድብቅና በዝግ ችሎት እንዲከናወን የተፈለገበት መንገድ በእጅጉ አሳፋሪ፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት ካገኘው በግልጽ ችሎት የመዳኘት ሕገ መንግሥታዊ መብት ያፈነገጠ፣ ሥርዓት አልበኝነትና ምን ታመጣላችሁ የሚል መልዕክት ያለው ሆኖ አግኝተነዋል።

    የባልደራስ ከፍተኛ አመራሮች የችሎት ውሎ አሳፋሪነቱ ምንም እንኳን ከአቃቤ ሕጉ ቅድመ ምርመራ መዝገብ የጀመረ ቢሆንም፥ የተቋሙን ገለልተኛነትና የፍትህ ሂደቱን የኢትዮጵያ ሕዝብ እንዲታዘብ በማሰብ መታገሳችን ይታወሳል። ሆኖም ረቡዕ ዕለት /ነሐሴ 06 ቀን 2012 ዓ.ም./ በዋለው ችሎት አቃቤ ሕግ ሦስት ምስክሮች ከመጋረጃ በስተጀርባ እና ማንነታቸው ሳይገለጽ፥ እንዲሁም አራት ምስክሮች ደግሞ በዝግ ችሎች እንዲደመጡ የሚል ጥያቄ ለፍርድ ቤቱ ሲያቀርብ የአመራሮቻችን ጠበቆች ለመመካከር እንዲሁም ውሳኔያችንን በጽሁፍ እንድናቀርብ ባሉት መሠረት የተከሰሱበት ወንጀል ዓለም አቀፍ ይዘት ያለውና ወደ ዘር ማጥፋት የሚወስድ በመሆኑ ይህንን የሚመሰክሩ ምስክሮች በግልጽ ችሎት ፊት ለፊት ቀርበው እንዲያስረዱ፥ ክርክሩ አስተማሪና ሂደቱ ለሕዝብ ግልጽ እንዲሆን ቢጠይቁም በአንፃሩ የፍርድ ቤቱ ዳኛ በአቃቤ ሕግ ብቻ የተጠየቀውን ተቀብሎ ሂደቱ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ዝግ ሆኖ እንዲቀጥል ወስኗል።

    አቶ እስክንድር ነጋ ፈጽማችኋል የተባልነው ጉዳይ የዘር ማጥፋት ወንጀል ይዘት ስላለው በአደባባይ እንጠየቅ፤ ክሱም ዓለም አቀፍ ይዘት ያለው በመሆኑ ችሎቱ በድብቅ ምስክርነት እንዲሰማ ከወሰነ እራሳችንን ከፍርድ ሂደቱ አግልለናል፤ ጠበቆቻችንንም አሰናብተናል፤ ፍርድ ቤትም አንገኝም፤ ፍርድ ቤቱ የሚሰጠውን ብይን ራሱ ተከታትሎ ይስጥ የሚል አቋም ወስዷል። ይሁንና አቃቤ ሕግ እነ አቶ እስክንድር በፖሊስ ተገደው እንዲቀርቡ ትዕዛዝ ይሰጥልኝ ማለቱን ተከትሎ ፍርድ ቤቱ ይህንኑ የአቃቤ ሕግ ጥያቄ ተቀብሎ ትዕዛዝ ማሳለፉ የዳኝነት ሂደቱ በሕገ መንግሥቱና በወንጀለኛ መቅጫ ሕግ ድንጋጌዎች ሳይሆን በፖለቲካ አመራር እየታዘዘ የሚሠራ መሆኑን በገሃድ ለመገንዘብ ተችሏል። በኦህዴድ/ብልጽግና “የለውጥ ዘመን” የፍርድ ሂደቱ አያያዝ ከህወሓት/ኢህአዴግ ዘመን በከፋ ደረጃ ኢ-ፍትሃዊነትን እየተላበሰ ስለመሆኑ አስረጂ ሆኗል። አቶ እስክንድር ነጋ መንግሥት የሚያቀርብለትን ጠበቃም ሆነ በፖሊስ ተገዶ መቅረብ እንደማይቀበል “ለፍርድ ቤቱ” አበክሮና አስረግጦ አስረድቷል።

    በከፍተኛ አመራሮቻችን የክስ ሂደት ፖሊስ በተደጋጋሚ ማስረጃ አቅርብ በሚባልበት ወቅት ከተከሰሱበት ጉዳይ ጋር የተያያዘ አንዳችም ማስረጃ ለማቅረብ መቸገሩን በተደጋጋሚ በፍርድ ቤቱ ሂደት ሲታይ እንደነበር ይታወሳል። ፖሊስ ለመክሰስ የሚያስችለው ምንም ማስረጃ ማቅረብ ሲያቅተው በድብቅ ምስክሮችን ለማቅረብ በማሰብ ተለዋጭ ቀጠሮ ይሰጠን እያለ የፍርድ አሰጣጡን ሂደት ያለበቂ ምክንያት ሲያራዝመው መታየቱ፥ ከጅምሩም ክሱ የሃሰት እንደሆነ ለከፍተኛ አመራሮቻችን፣ ለጠበቆቻቸው እንዲሁም የችሎቱን ሂደት በአንክሮ ይከታተል ለነበረው ፓርቲያችን ግልጽ ነበር። እስከዛሬ ለማሳየት የደከምንበት ሃቅ ይህንኑ የሚያስረዳ ነው። መሪያችን ከዚህ ትክክለኛ ካልሆነ ከሕገ መንግሥቱና ከወንጀለኛ መቅጫ ሕጉ ድንጋጌዎች ካፈነገጠና በተግባር ካልተሻረው የፀረ-ሽብር ሕግ በተወሰነ አንቀጽ ከሚመራ የፍርድ ቤት ሂደት ራሱን ማግለሉ በእጅጉ ትክክለኛ እና የምንደግፈውነው። በዚህ ዓይነት ቅጥ አንባሩ ከጠፋው የአምባገነኖች “ካንጋሮ ፍርድ ቤት” ፍትህ ማግኘት ስለማይቻል የአመራሮቻችን ውሳኔ ትክክል መሆኑን ድርጅታችን ያምንበታል። በመሆኑም ድርጅታችን ከአመራሮቻችን ጎን ዛሬም እንደትላንቱ ከጎናቸው በጽናት እንደሚቆም ማረጋገጥ ይወዳል።

    ኦህዴድ/ብልጽግና በኦሮሚያ ክልል በተደጋገሚ የዜጎችን ዘር እና ሃይማኖት ተገን ተደርጎ ለተፈጠረው የዘር ማጥፋት /genocide/ እና የሥርዓቱ ጋሻጃግሬዎች ላደረሱት ወንጀል ሽፋን በመስጠት በሌሎች ንፁሃን ላይ በማላከክ ሕግ እንዳይከበር እና አለመረጋጋቱ ተባብሶ እንዲቀጥል እንየተደረገ እንደሆነ ባለፉት ሁለት ዓመታት ጉዟችን በአግባቡ ተገንዝበናል። በመሆኑም ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ በሀገራችን በተደጋጋሚ የደረሱት የዘር ማጥፋት ወንጀሎች ሆን ተብለው በሥርዓቱ አመራሮች ድጋፍና ተሳትፎ ጭምር የተካሄዱ እንደሆነ በተደጋጋሚ የሚቀርቡት እውነታዎች በገሃድ የሚያሳዩ መሆናቸውን ተመልክተናል። እንደማሳያነትም በቅርቡ በኦህዴድ/ብልጽግና ከፍተኛ አመራር በድብቅ ወጥቶ በተደመጠ ንግግር “ቄሮን የምናዘው፣ የምናወጣውም እንዲሁም የምንበትነው እኛ ነን” ማለታቸውን ልብ ይሏል። እውነተኛ ፍትህ ቢኖር በዚህ አቶ ሽመልስ አብዲሳ አባባል መሠረት ቄሮ በተሰኘው ኢ-መደበኛ አደረጃጀት እስካሁን ለተፈፀመው ወንጀል ተጠያቂ መሆን የሚገባው ማን እንደሆነ በግልጽ መገንዘብ ይቻላል።

    ስለዚህ የዓለም አቀፍ ሕብረተሰብ በጉዳዩ ጣልቃ በመግባት የዘር ማጥፋት ወንጀል የፈፀሙት ብቻ ሳይሆን፥ ከመጋረጃው ጀርባ ሆነው ያስፈጸሙትን ጭምር ለሕግ እንዲቀርቡ እንዲደረግ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ያሉ ዜጎች የፓርቲያችንን ጥረት እንዲያግዙ በድጋሚ እንጠይቃለን። በተጨማሪም በሀገራችን የሕግ የበላይነት እንዲሰፍን አስቀድመን ስንጮህ ከጎናችን የነበራችሁ በሀገር ውስጥና በውጭ ያላችሁ ኢትዮጵያውያን፣ የፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች፣ የዓለም አቀፍ ማኅብረሰብ፣ ለፓርቲያችን ቀጣይና ቁርጠኛ ለሆነው ሰላማዊ እና ሕጋዊ ለሆነው የትግል እንቅስቃሴያችን ከጎናችን በመቆም ድጋፍና እገዛ እንድታደርጉልን በአክብሮት እንጠይቃለን።

    ድል ለዲሞክራሲ!

    ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ
    አዲስ አበባ
    ነሐሴ 8 ቀን 2012 ዓ.ም.

    ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ

    #15423
    Semonegna
    Keymaster

    በደቡብ ክልል ወላይታ ዞን የክልልነት ጥያቄ በማንሳት የሚንቀሳቀሰው የዞኑ አመራርና ሕዝብ
    በሕገ-መንግሥቱ ድንጋጌ መሠረት ተገቢ መልስ በሰላማዊ አግባብ ሊሰጠው ይገባል!
    የኢትዮጵያ ሶሻል ዴሞክራቲክ ፓርቲ (ኢሶዴፓ)

    ከኢትዮጵያ ሶሻል ዴሞክራቲክ ፓርቲ (ኢሶዴፓ) የተሰጠ መግለጫ

    የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ራስን በራስ የማስተዳደርና ክልላዊ መንግሥት የማቋቋም መብት እንዳላቸው በሕገ-መንግሥቱ አንቀፅ 47(2) ላይ ተደንግጓል። ይህን ሕገ-መንግሥታዊ መብት ለማስከበር ከአስር በላይ የሆኑ የደቡብ ብሔራዊ ክልል ዞኖች፣ በየዞናቸው ምክር ቤት በማስወሰን ለክልሉ ምክር ቤት ጥያቄዎቻቸውን ማቅረባቸውንና ውሳኔ እንዲሰጣቸው በመጠየቅ ላይ መሆናቸውን ከተለያዩ ምንጮች ስንሰማ ቆይተናል።

    እስከ አሁን ጥያቄያቸውን ካቀረቡት ዞኖች መካካል በሕገ-መንግሥቱ መሠረት ሕዝበ-ውሳኔ ተካሂዶ በክልልነት የመደራጀት መብት የተከበረለት የሲዳማ ዞን ብቻ ሲሆን፥ የሌሎች ዞኖችን በተመለከተ በአሁኑ ወቅት የተለያዩ የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦችን በቡድን /በክላስተር/cluster/ በማሰባሰብ ከአንድ በላይ በሚሆኑ ክልሎች ለማደራጀት በመንግሥት እንቅስቃሴ እየተደረገ መሆኑ ይታወቃል። ይህ እየሆነ ባለበት ሁኔታ በመንግሥት እየተደረገ ያለውን በክላስተር የማደራጀትን አማራጭ የሚቃወሙ እንቅስቃሴዎች በአንዳንድ ዞኖች እየታዩ ናቸው። በመሆኑም ከሚመለከተው አካል ፈጣን ምላሽ አልተሰጠንም ከሚል ተስፋ መቁረጥ ተነስቶ፥ ሕዝቡ ወደ ግጭት እንዳይገባ የኢትዮጵያ ሶሻል ዴሞክራቲክ ፓርቲ (ኢሶዴፓ) ከዚህ ቀደም ባወጣው መግለጫ ሥጋቱን ገልጿል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ፥ የተፈራው ስጋት እውን ሁኖ የወላይታ ዞን አመራር የመንግሥትን የመፍትሄ አቅጣጫ በመቃወም የምክክር ስብሰባ እያደረገ ባለበት ወቅት መንግሥት በወሰደው እርምጃ በቁጥጥር ስር እንዳዋላቸው ተሰምቷል። በዚህ መነሻነትም ሕዝቡ ተቃውሞ እያሰማ እንደሆነና ከፀጥታ አስከባሪ ኃይሎች ጋር በሚፈጠሩ ግጭቾች የሰው ሕይወት እስከ መጥፋት እየደረሰ መሆኑም በእጅጉ አሳስቦናል።

    ስለሆነም፥ መንግሥት የጉዳዩን ሰፊ እንደምታ በጥልቀት በመመልከት፣ በዞኑ ለተነሳው ሕገ-መንግሥታዊ ጥያቄ ተገቢ ምላሽ በመስጠት፣ ጥያቄውን በማንገብ ምላሽ ለመሻት የተንቀሳቀሱትን የወላይታ ዞን አመራር አካላትን እና በጉዳዩ ሳቢያ የታሰሩትን ሁሉ በመፍታት፣ ለተከሰተው ችግር ሰላማዊ መፍትሄ በአስቸኳይ እንዲፈልግ ኢሶዴፓ ያሳስባል። አስተዋዩ ሰፊ የወላይታ ሕዝባችንም ጉዳዩን በወትሮ ጥበቡ በትዕግስት በመያዝ፣ የሰላማዊ መፍትሄ አካል እንዲሆን ኢሶዴፓ በአክብሮት ጥሪ ያደርጋል!!

    የኢትዮጵያ ሶሻል ዴሞክራቲክ ፓርቲ (ኢሶዴፓ)
    ነሐሴ 6 ቀን 2012 ዓ.ም.
    አዲስ አበባ

    *የኢትዮጵያ ሶሻል ዴሞክራቲክ ፓርቲ (ኢሶዴፓ) በሀገራችን ኢትዮጵያ ሕዝባዊ፣ ዴሞክራሲያዊ መንግሥት በመመሥረት ለመሠረታዊ ችግሮች መፍትሔ ለመስጠት ርዕዮተ-ዓለሙ ማኅበረ-ዴሞክራሲ (social democracy) ሆኖ ኢኮኖሚያዊና ማኅብራዊ ፍትህን በሀገሪቱ እውን ለማረግ የሚንቅሳቅስ ሀገር አቀፍ የፖለቲካ ፓርቲ ነው።

    የፖለቲካ ፓርቲዎች ድምጽ (ኢትዮጵያ ውስጥ የሚነቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች)

    የኢትዮጵያ ሶሻል ዴሞክራቲክ ፓርቲ

    #15441
    Semonegna
    Keymaster

    “የወላይታ ዞን ነዋሪዎች ራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄ ሕጋዊ ነው።”
    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) በወላይታ ዞን የተቀሰቀሰውን ሕዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ ሕይወታቸውን ያጡና ጉዳት የደረሰባቸው ዜጎች ጉዳይ በአስቸኳይ እንዲጣራና ለሕዝብ ይፋ እንዲሆን ጠየቀ።

    ፓርቲው በሕዝብ ግንኙነት ክፍሉ በኩል ነሐሴ 05 ቀን 2012 ዓ.ም «በወላይታ ዞን የተፈጠረው አለመረጋጋት በሰላማዊ መንገድ ይፈታ» በሚል ርዕስ ባወጣው መግለጫ በዞኑ በተፈጠረው አለመረጋጋት ሕይወታቸውን ባጡ ዜጎች ምክንያት የተሰማውን ሐዘን ገልፆ፥ መንግሥት በአስቸኳይ ጉዳዩን አጣርቶ ይፋ ያድርግ ሲል ጠይቋል። «የመንግሥት የፀጥታ ኃይል ተገቢ ያልሆነ ኃይል በፍጹም እንዳይጠቀም እና የዜጎችን ሕይወት ለአደጋ ሳይዳርግ ሕግን በማስከበር ዞኑን ለማረጋጋት ከማኅበረሰቡ ጋር በቅርበት እንዲሠራ» በማለት ኢዜማ ማሳሰቢያውን ሰጥቷል።

    በክልሉ የሚገኙ ማኅበረሰቦች የሚያነሷቸውን የራስን በራስ የማስተዳደር ተገቢ ጥያቄዎች ቀጥተኛ እና ዘላቂ በሆነ መልኩ መመለስ ይገባል ማለቱን ያስታወሰው ኢዜማ፥ ይህን ለማድረግ ግን ማኅበረሰቡ በነፃ እና ገለልተኛ በሆነ መንገድ የመረጣቸው፣ የሚፈልገውን የሚፈጽሙለት ተወካዮች መኖራቸው እና በጉዳዩ ላይ ሰፊ ሕዝባዊ ውይይቶች መደረጋቸው አስፈላጊ ስለሆነ ሕዝቡ ተወካዮቹን መርጦ ሰፊ ሕዝባዊ ውይይቶች ተደርገው ሕዝበ ውሳኔ እስኪሰጥ ድረስ በትዕግስት እንዲጠብቅም ጠይቆ እንደነበር አስታውሷል። ፓርቲው ይህንን ጥያቄውን አቅርቦ የነበረውም ሰኔ 9 ቀን 2012 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ እንደነበር ጠቁሟል።

    የዞኑ ነዋሪዎች ራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄ ሕጋዊ መሆኑን እንደሚያምን በመግለጫው ላይ የጠቆመው ኢዜማ፥ ሀገሪቷ እና ዓለም ያለበት ሁኔታ ግን ሕገ መንግሥቱ የሚፈቅደውን የክልልነት ሒደት ለማሟላት የሚያስችል እንዳልሆነ መገንዘብ ያስፈልጋል ብሏል። ለዚህም በምክንያትነት ኮቪድ-19 ወረርሽኝ መከሰትን አንስቷል። ኮቪድ ወረርሽኝ ተከትሎ በታወጀው አስቸኳይ ግዜ አዋጅ የተነሳ ውይይት ማድረግም ሆነ ሕዝበ ውሳኔ ማድረግ የሚቻልበት ሁኔታ እንደሌለ ያስታወሰው ኢዜማ፥ በክልሉ በአጠቃላይ ራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄን ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ በሕጋዊ መንገድ ለመፍታት የሕዝብ ውክልና ያላቸው ተወካዮች መኖራቸው እንዲሁም በቂ ውይይት እና መግባባት ስለሚያስፈልግ በትዕግስት መጠበቁ የተሻለ አማራጭ መሆኑን ለማስታወስ እወዳለሁ ብሏል።

    ጥያቄውን የሚያነሱት ወገኖችም ሰላማዊ ከሆነ መንገድ ውጪ ዘላቂ መፍትሄ እንደማይገኝ መረዳት እንዳለባቸው እና እንቅስቃሴያቸውን ሁሉ በሰላማዊ መንገድ ማድረግ እንደሚገባቸው ፓርቲው አሳስቧል።

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ገዢው ፓርቲ የደቡብ ብሔር፣ ብሔረሰብ እና ሕዝቦች ክልልን መልሶ ለማዋቀር ለፌደሬሽን ምክር ቤት ያቀረበው ምክረ ሀሳብ ክልል ለመሆን ጥያቄ ያቀረቡትን የዞን አስተዳደሮች ጥያቄን የማይመልስ፣ ክልሉ መጀመሪያ ሲዋቀር የተሠራውን ስህተት መልሶ የሚደግም፣ ሕገ ወጥ እና ግጭት የሚጋብዝ እንዲሁም እንደሀገር ካሉ ውስብስብ ችግሮች ላይ ሌላ ችግር የሚጨምር መሆኑን በማስረዳት ወደትግበራ እንዳይገባ በማለት ሰኔ 9 ቀን 2012 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ ማሳሰቡ የሚታወስ ነው።

    ምንጭ፦ ኢዜማ

    ራስን በራስ የማስተዳደር ጥያቄ

    #15528
    Anonymous
    Inactive

    በወቅታዊ ሀገራዊ ሁኔታዎች ላይ የተሰጠ የአቋም መግለጫ ― ኢሕአፓ

    በጀግኖች ሰማዕታት ብርቱ ተጋድሎና ክቡር መስዋዕትነት የተገነባዉ የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢ.ሕ.አ.ፓ)፥ በታሕሳስ 4 እና 5 ቀን 2012 ዓ.ም. 9ኛ ጉባኤውን በተሳካ ሁኔታ አድርጎ አመራሮቹን መምረጡ ይታወቃል። የኢሕአፓ ቋሚ ኮሚቴ በሀገራዊና ድርጅታዊ አጅንዳዎቸ ላይ ከነሐሴ 2 እስከ ነሐሴ 8 ቀን 2012 ዓ.ም. ድረስ በወቅታዊ የኢትዮጵያ የፖለቲካ-ኢኮኖሚ ሁኔታዎች ላይ፣ በኢትዮጵያ ስላለው የሰላም፣ የዲሞክራሲና የልማት ክንዉን ሂደቶች በስፋት መክሯል። ፓርቲው የ2012 ዓ.ም. የ6 ወራት የዕቅድ አፈጻጸሙን ግምግሞ የ2013 ዓ.ም. የበጀት ዓመት የፓርቲዉ ዕቅድ ላይ ከፍተኛ ዉይይት አድርጓል። በተጨማሪም፥ የፓርቲው አባላትና ደጋፊዎች የሰላማዊ ትግል መርሆዎችና ስልቶችን ተግባራዊ በሚያደርግ፣ የትግል ቁርጠኝነታቸውን ጠብቀው ለማይቀረው ድል እንዲሰለፉና ሀገራቸውንና ሕዝባቸውን ካንዣበበባቸው አደጋ እንዲከላከሉ ጥሪውን አቅርቧል።

    የኢሕአፓ ቋሚ ኮሚቴም የሚከተሉትን ዉሳኔዎችና የአቋም መግለጫዎችን በሰፊው ከተወያየ በኋላ አዉጥቷል።

    1ኛ. መንግሥት የሕግ የበላይነትን ለማስከበርና በቅርቡ የጀመረውን ለሰላም፣ ለልማትና ለዲሞክራሲ እውን መሆን የሚያደርገዉን ጥረት እያደነቅን፥ ይህን መሰሉ ሕግን የማስከበር ጉዳይ አስቀድሞ ተከናውኖ ቢሆን ኖሮ ዜጎች በጠራራ ጸሐይ ከመገደልና ሃብት ንብረታቸውም ከመውደም መታደግ ይቻል እንደነበር ኢሕአፓ እምነቱን እየገለጸ፥ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ግጭት፣ ሁከትና ብጥብጥ በመፍጠር ለንጹሀን ዜጎች ሞት፣ ስደት፣ እንግልትና መፈናቀል ምክንያት የሆኑ፣ ንብረት ያወደሙና የዘረፉ ወንጀለኞችን ለሕግ በማቅረብ ተጠያቂ የማድረገረ ሂደቱን አጠናክሮ እንዲቀጥል፤ እና ተጠርጣሪዎችና ከሁከቶች ጋር ግንኙነት ያላቸው ሁሉ አፋጣኝ የፍርድ ሂደት እንዲያገኙ ኢሕአፓ መንግሥትን ይጠይቃል።

    2ኛ. የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የመጀመሪያ ዙር የውሃ ሙሌት በታቀደለት ጊዜ በመጠናቀቁ ኢሕአፓ የተሰማውን ልባዊ ደስታ እየገለጸ፥ መንግሥት በጣና ሐይቅ ዙሪያ የተከሰተውን የእንቦጭ አረም ችግርና በወንዞቻችን፣ ሐይቆቻችንና በተፈጥሮ ሀብቶቻችን ላይ እየደረሰ ያለውን ብሔራዊ አደጋ ለማስቀረት ሕዝባዊ ንቅናቄ አስፈላጊ በመሆኑ፥ የኢሕአፓ አባላትና ደጋፊዎች የተፈጥሮ ሃብት እንክብካቤንና ጥበቃን ለማጎልበት በንቃት እንዲሳትፉ ጥሪውን ያስተላልፋል።

    3ኛ. በደቡብ ክልል እየተከሰቱ ያሉት ግጭቶችና ሰሞኑን በወላይታ ዞን የተፈጸመው ሁከትና ብጥብጥ ወደከፋ ሁኔታ ከመቀየሩ በፊት መንግሥት የ’ክልል እንሁን’ ጥያቄዎችና የአከላልለ ጉዳይን በተመለከተም በተጠናና በማያዳግም ሁኔታ እንዲፈታው እየጠየቅን፥ ችግሮችን በክልሉ በሚኖሩት ሕዝቦች ፍላጎትና ውይይት መሠረት አድርጎ መፍታት አለበት። የአስተዳደር በደል ጥያቄዎቹንና አለመረጋጋቱን ተገን አድርገዉ በሚቀሰቀሱ ግጭቶች ተከትሎ የሚጠፋዉ የሰዉ ሕይወትና የሀገር ሀብት ውድመት በአስቸኳይ እንዲያቆምና ችግሮችም በሰላማዊና ሕጋዊ መንገድ እንዲፈቱ ኢሕአፓ በአንክሮ ይጠይቃል። በግጭቱ ሰበብ ለሞቱት ወገኖች የተሰማንን ጥልቅ ሃዘን እየገለጽን፥ በየትኛውም የፌዴራሉ ክልሎች ውስጥ ለዘመናት ተዋዶና ተከባብሮ የሚኖረውን ሕዝብ እርስ በርስ ለማጋጨትና ሀገራችንን ወደ አልተፈለገ የእርስ በርስ ግጭት ለመክተት የሚሯሯጡ ቡድኖችና ኃይሎችን ለፍርድ ለማቅረብ መንግሥት እየወሰደ ያለውን ርምጃ ኢሕአፓ ይደግፋል።

    4ኛ. የኮቪድ-19 ወረርሽኝኝ በሀገራችን ከተከሰተ ጊዜ ጀምሮ፣ በመላው ኢትዮጵያ ከፍተኛ የሆነ የኑሮ ውድነትና ሥራ አጥነት፣ የኢኮኖሚ ጫና በመላው ሕዝባችን ላይ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ በመሆኑና የዕለት-ተዕለት የምግብና ሸቀጣ ሸቀጦችም ላይ ከፍተኛ የሆነ የዋጋ ንረት እየተከሰተ ስለሆነ፥ የዋጋ ንረቱም የሀገራዊ ምርት እጥረት ሳይሆን የአቅርቦት ውሱንነት ያስከተለው በመሆኑ፣ መንግሥት በአፋጣኝ ገበያውን በመቆጣጠርና ሕዝቡን ካልተገባ የኢኮኖሚ ምዝበራ እንዲታደገው እንጠይቃለን። ከዚህ በተጨማሪ በአዲስ አበባ ከተማ ያለዉ ከፍተኛ የሕዝብ ትራንስፖርት እጥረት ረጃጅም ሰልፎችን እየፈጠረ ሕብረተሰቡን ለቫይረሱ ተጋላጭ እንዲሆን እያደረገዉ ስለሆነ አፋጣኝ መፍትሄ እንዲፈለግለት አሕአፓ በአጽንኦት ያሳስባል።

    5ኛ. በተለያዩ የሀገራችን ክልሎች በሰላምና መረጋጋት እጦት ምክንያት አካላቸው ለጎደለባቸው፣ ንብረታቸው ለወደመባቸው፣ ከመኖሪያ ቀያቸው ለተፈናቀሉና ለችግር ተጋላጭ ለሆኑ ዜጎች መንግሥት ወደ ሰላማዊ ኑሮአቸው መመለስ የሚችሉበትን ካሳ እንዲከፍልና ዜጎች በብሔራቸዉና በማንነታቸዉ እየተለዩ የሚደርስባቸዉን ጥቃት እንዲከላከል ኢሕአፓ ጥሪዉን ያቀርባል።

    6ኛ. የተለያዩ ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣናትና የብልጽግና ከፍተኛ አመራሮች በተለያዩ ሕዝባዊ መድረኮች ስብሰባዎችና ብዙሃን መገናኛ ድርጅቶች ላይ የሚያደርጉት ከፋፋይና በተወሰኑ ብሄሮች ላይ የሚያነጣጥር ንግግር በኢትዮጵያዉያን ዜጎች መካከል ለብዙ ዘመናት አብሮ የኖረዉን የመቻቻልና የመከባበር እሴት የሚሸረሽርና ለጥላቻ፣ ለግጭትና እርስ በርስ በጥርጣሬ ዓይን ለመተያየት በር የሚከፍት አደገኛ ተግባር ስለሆነ፥ ኢሕአፓ እንደዚህ ዓይነት ንግግሮች እንዲታረሙ በጥብቅ ያሳስባል፤ ለአብነትም፥ ሰሞኑን የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝደንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ ብልጽግናን በተመለከተ ያደረጉት ንግግር በኢትዮጵያዉያን መካከል የነበረዉን የእርስ በርስ ግንኙነትና ዉሁድ ኢትዮጵያዊነትን የሚሸረሽር፣ አደገኛና ዘረኛ ሀሳብ መሆኑ ግልጽ ነዉ፤ ይህ ሀሳብ እዉን የብልጽግና ፓርቲ ሀሳብ ከሆነ የተረኝነት ጉዳይ እንጂ የለዉጥ ጉዳይ ሊሆን ስለማይችል ሀሳቡ የግለሰብ ወይም የፓርቲዉ ሀሳብ መሆን አለመሆኑን መንግሥት ግልጽ እንዲያደረግ እንጠይቃለን።

    7ኛ. በፌደራል መንግሥትና አምባገነኑ ህወሓት በሚመራዉ በትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት መካካል ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተካረረ የመጣዉ ዉዝግብና አለመግባባት በንጹሃን የአማርኛና የትግርኛ ቋንቋ ተናጋሪ ማኅበረሰቦች የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴና ኑባሬ ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ እየፈጠረ መሆኑ እሙን ነዉ። ስለዚህ መንግሥት ለንጹሃን ዜጎች ሲል የሕግ የበላይነትን በማስከበር በኩል ጥብቅ እርምጃ በመዉሰድ ስርዓት አልበኞችንና አምባገነኖችን ለሕግ እንዲያቀርብ እየጠየቅን፥ ያለምርጫ ቦርድ ፈቃድና ዕዉቅና ሁሉም ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ሳያካትት ህወሓቶች በተናጠል የፊታችን ጳጉሜ 4 ቀን 2012 ዓ.ም. ሊያደርጉት ያቀዱትን ምርጫም ጣልቃ ገብቶ እንዲያስቆም ኢሕአፓ በአጽንኦት ይጠይቀል።

    8ኛ. ፓርቲያችን ኢሕአፓ ባለፉት 6 (ስድስት) ወራት ውስጥ ያከናወናቸዉን ዋና ዋና ተግባራት በጥልቀት የገመገመ ሲሆን፥ በኢትዮጵያ የዘመናዊ የፖለቲካ ታሪክ ውስጥ ደማቅና ጉልህ ስፍራ ያለውና ዘመን ተሻጋሪ የሆነዉ የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) የኢትዮጵያን ሕዝብ ታግሎ-በማታገል መርሆውና አይበገሬነቱ ጸንቶ የሚገኝ ድርጅት መሆኑን ለመላው አባላቱና ደጋፊዎቹ እየገለጸ፥ ከርዕዮት-ዓለማችን ከማኅበራዊ ዲሞክራሲ (social democracy) ጋር ተመሳሳይነትና ተቀራራቢነት ያላቸውንና በኢትዮጵያ ሕዝብ አንድነትና እኩልነት ላይ ጽኑ እምነት ያላቸውን ፓርቲዎችና የፖለቲካ ኃይሎች ሁሉ የትብብርና የአጋርነት ጥሪ ያቀርብላችኋል።

    ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!!

    ኢ.ሕ.አ.ፓ ለተሻለ ነገ!!

    የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ)

    #15610
    Anonymous
    Inactive

    እውነታውን በማድበስበስ ከተጠያቂነት ማምለጥ አይቻልም! ― የኢዜማ ሕዝብ ግንኙነት

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) በአዲስ አበባ ከተማ መሬት ወረራን እና የጋራ መኖሪያ ቤቶች ኢ-ፍትሃዊ ዕደላን በተመለከተ የሚደርሱትን ጥቆማዎች በመቀበል ጉዳዩን የሚመረምር ከብሔራዊ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት የተወጣጣ ኮሚቴ አቋቁሞ ጥናት ሲያደርግ ቆይቷል። የጥናቱን ውጤት ለሕዝብ እና ለመገናኛ ብዙኃን ይፋ ለማድረግ ዛሬ አርብ ነሐሴ 22 ቀን 2012 ዓ.ም ጋዜጣዊ መግለጫ ተዘጋጅቶ ነበር።

    ይህ ጋዜጣዊ መግለጫ ሲዘጋጅ ከዚህ ቀደም ጋዜጣዊ መግለጫ ስንሰጥ እንደምናደርገው ሁሉ ጋዜጣዊ መግለጫው ለሚደረግበት ራስ ሆቴል እንዲሁም በደብዳቤ ቁጥር ኢዜማ/695/12 ለኢፌዴሪ ሰላም ሚኒስቴር አስቀድመን አሳውቀናል።

    ፓርቲያችን ሊሰጥ የነበረውን መግለጫ ለመከታተል እና ለሕዝብ ለማድረስ የተጠሩ ጋዜጠኞች ከተባሉት ሰዓት ቀድመው በአዳራሹ ውስጥ የተገኙ ሲሆን፥ ብዙዎቹም የቀረጻ መሣሪዎቻቸውን አሰናድተው  የመግለጫውን መሰጠት በመጠባበቅ ላይ እያሉ የቂርቆስ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ አባል መሆናቸውን የገለፁ የፖሊስ አባላት መግለጫው መሰጠት እንደማይቻል በማሳወቅ፥ ጋዜጠኞቹ አዳራሹን ለቀው እንዲወጡ አድርገዋል። ፖሊሶቹ ጋዜጣዊ መግለጫውን ለማስቆም የሰጡት ምክንያት ጋዜጣዊ መግለጫው እንዲካሄድ ትዕዛዝ አልተሰጠንም የሚል ነበር።

    በስፍራው የተገኙት የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) አመራሮች ሙሉ ትብብር ያደረጉ ሲሆን፥ ስለመግለጫው ለሰላም ሚኒስቴር በደብዳቤ ማሳወቃቸውን ለፖሊስ አባላቱ አስረድተዋል። ወደ ሰላም ሚኒስቴር በመደውልም የተፈጠረውን ለሚንስትር መሥሪያ ቤቱ ያሳወቁ ሲሆን፥ የፖሊስ አባላቱን ከሰላም ሚኒስቴር ጋርም በስልክ የማገናኘት ሥራ ተሠርቷል። ነገር ግን የፖሊስ አባላቱ መልሰው “የሰላም ሚኒስቴር ሊፈቅድ የሚችለው ስብሰባዎችን እንጂ ጋዜጣዊ መግለጫዎችን አይደለም። የመግለጫ ጉዳይ የሚመለከተው ፖሊስን ነው።” በሚል መግለጫውን በመከልከል ጸንተዋል። ይህንንም ተከትሎ የኢዜማ በአዲስ አበባ ከተማ እየተፈፀመ ያለውን የመሬት ወረራ እና የጋራ መኖሪያ ቤቶች ኢ-ፍትሃዊ ዕደላን አስመልክቶ የሠራውን ጥናት ውጤት ለሕዝብ ለማሳወቅ ያዘጋጀው ጋዜጣዊ መግለጫ ተስተጓጉሏል።

    ትላንት የአዲስ አበባ መሬት በሕገ-ወጥ መንገድ እየታጠረ ሲወረር እና ሲዘረፍ ማቆም ያልቻሉ የሕግ አስከባሪዎች፥ በሕጋዊ መንገድ የተጠራ ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳይሰጥ አጥር ሆነዋል። የሕዝብ የሥልጣን ባለቤትነትን እና የሕግ የበላይነትን የሚያረጋግጥ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ውስጥ እንደዛሬው ዓይነት እክል ትላንትናም አላስቆመንም፤ ዛሬም አያስቆመንም! የተፈጸመ ስህተት ካለ አዳምጦ ለማረም ከመዘጋጀት ይልቅ የዜጎችን እና የፖለቲካ ፓርቲዎችን ሀሳብን የመግለጽ ነፃነት በማፈን እና እውነቱን በማድበስበስ ከተጠያቂነት ለመራቅ መሞከር ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እንቅፋት እንደሆነ ግልጽ ሊሆን ይገባል። ዛሬ በተከሰተው መግለጫውን የማስተጓጎል ተግባር እውነታውን ማድበስበስ እና ከተጠያቂነት ማምለጥ አይቻልም።

    ከዚህ ቀደም የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ ጽሕፈት ቤት፣ የመሬት ልማት ቢሮ እና የቤቶች ልማት ኤጀንሲ በጥናታችን የደረስንበትን ውጤት አያይዘን የእነሱን ምልከታ በጥናት ውጤታችን ውስጥ ለማካተት ምላሽ እንዲሰጡን ጠይቀን የነበረ ቢሆንም፥ ሁሉም ምላሽ ለመስጠት ፈቃደኛ ካለመሆናቸው በተጨማሪ የመሬት ልማት ቢሮ እና የቤቶች ልማት ኤጀንሲ የላክንላቸውን ደብዳቤም ለመቀበል ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል።

    ኢዜማ በጥናቱ የደረሰበትን ሕገ-ወጥነት እና ኢፍትሃዊነት ሰኞ ነሐሴ 25 ቀን 2012 ዓ.ም ከሰዓት 8 ሰዓት ለሕዝብ ይፋ ያደርጋል። ሀሳባችንን የመግለጽ ሕገ-መንግሥታዊ መብታችንን ለማስከበር ወደኋላ እንደማንል እና ያገኘነውን ውጤት ሕዝብ ጋር እንደምናደርስ እንዲያውቁት በድጋሚ ለኢፌዴሪ ሰላም ሚኒስትር እና ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ደብዳቤ ልከናል።

    የኢዜማ ሕዝብ ግንኙነት

    የኢዜማ ሕዝብ ግንኙነት

    #15655
    Anonymous
    Inactive

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)
    በአዲስ አበባ ከተማ መሬት ወረራ እና የጋራ መኖሪያ ቤቶች ኢፍትሃዊ ዕደላ ጥናት አንኳር

    • የከተማው አስተዳደር እያየ እና እየሰማ፥ በሕገ ወጥ እና በተደራጀ መልኩ በወረራ የተያዙ ቦታዎች በፍጥነት ካርታና ፕላን ተሠርቶላቸው ለሦስተኛ ወገን በሽያጭ ተላልፈዋል። በማኅበር እና በግል ለማምረቻና ለንግድ አገልግሎት እንዲውሉ ተደርገዋል፤ በምንም መስፈርት የቤት ተጠቃሚ ሊሆኑ የማይገባቸው ግለሰቦችና ቡድኖች ቤት እና የነዋሪነት መታወቂያ ተሰጥቷቸዋል።
    • በዋናነት በመሬት ወረራው ላይ ግንባር ቀደም ተሳታፊ የነበሩት ሰዎች የአርሶ አደር ልጆች ነን የሚሉ፤ ቦታዎቹ ከዚህ ቀደም የቤተሰቦቻችን መሬቶች ናቸው፤ በቂ ካሳ ሳይከፈለን ከቦታችን ተነስተናል የሚሉ ግለሰቦች እና ወረራ የተፈፀመባቸው ቦታዎች አካባቢ ላይ የሚገኙ የክፍለ ከተማ እና የወረዳ ኃላፊዎች ናቸው።
    • ይህ በጠራራ ፀሐይ በተደራጀ መልኩ የተፈፀመው የመሬት ወረራ በመንግሥት ሥልጣን ላይ ያሉ አመራሮች፤ የፍትህና ፀጥታ አካላት ተጠሪዎች ከፍተኛ እገዛ የተደረገበት ብቻ ሳይሆን እነዚህ አካላት የጉዳዩ ዋና ተዋንያን ነበሩ። በተለያየ መልኩ ሊጠቅሟቸው ለሚፈልጉ ግለሰቦች፣ ቡድኖች እና አደረጃጀቶች መሬቱን ወረው እንዲይዙ አመቻችተዋል፤ የመንግሥትን ሥልጣን ለሕገ ወጥ ተግባር ከለላ እና ሽፋን እንዲሆን አድርገዋል፤ ከዚህም ባስ ሲል ከግለሰቦች ጋር በመመሳጠር እራሳቸው ወረራ ፈፅመዋል።
    • በጠቅላላው 213,900 ካ.ሜ ያህል ስፋት ያለው ቦታ ጥናቱ ባያቸው ጥቂት ቦታዎች ላይ ብቻ መወረራቸውን ለማረጋገጥ ችለናል።
    • ከጋራ መኖሪያ ቤት ጋር በተገናኘም በግልፅ የታየው የመንግሥት አካላት ሕገ ወጥ ተግባር ነው። ኢፍትሐዊ ሕጎችን እና መመሪያዎችን በማውጣት እና ሕጋዊ ባልሆነ መንገድ ሕጎችን እና ደንቦችን በማሻሻል ለካቢኔው እና ለከንቲባው በተሰጠ ልዩ ሥልጣን ከንቲባውም ሆነ ካቢኔያቸው ቤቶችን እንደፈለጉ እንዲያድሉ ምክንያት ሆኗል።
    • በዚህ መሠረት ከኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ቢሮዎች ሳር ቤት አካባቢ ከሚገኘው ጽሕፈት ቤት ሁሉም የተመዘገቡ ሠራተኞች በሰኔ 12 ቀን 2012 ዓ.ም ብዙ ሺህ ቤቶች የድልደላ እጣ የወጣላቸው ሲሆን፣ የድልድል እጣ ለደረሳቸው ሰዎች ሰኔ 16 ቀን 2012 ዓ.ም ድልድል ተደርጎላቸዋል። በዚህ ቀን ሁሉም ሠራተኞች የኮንዶሚኒየም ብሎክ ቁጥር እና የቤቱን ቁጥር በስማቸው ተረጋግጦ የተሰጣቸው ሲሆን፤ በተሰጣቸው የቤት ቁጥር የነዋሪነት መታወቂያ የተዘጋጀላቸው መሆኑን ለማወቅ ችለናል።
    • የጋራ መኖሪያ ቤቶች ሕንጻዎች ውስጥ የተሠሩ የንግድ ቤቶች በተመለከተ የልማት ተነሺ አርሶ አደሮች፣ ልጅ እና የልጅ ልጅ ተብለው በገፍ ስለመታደላቸው፤ በእግር ኳስ ደጋፊነት ስም ለተሰባሰቡ ማኅበራት መከፋፈላቸው ተጨባጭ ማስረጃዎች ተገኝተዋል።

    ሙሉውን ሪፖርት ያንብቡ፦ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) በአዲስ አበባ መሬት ወረራ እና የጋራ መኖሪያ ቤቶች ኢፍትሃዊ ዕደላ ላይ ያደረገው ጥናት ውጤት።

    ተመሳሳይ ዜናዎች፦

    1. እውነታውን በማድበስበስ ከተጠያቂነት ማምለጥ አይቻልም! ― የኢዜማ ሕዝብ ግንኙነት
    2. አዲስ አበባ ― ዳቦ፣ የመኖሪያ ቤት፣ መብራት እና ውሃ፣ የመሬት ቅርምት፣ ተረኝነተ፣ ሙስና፣ ግፍ፣ ወዘተ…

    ምንጭ፦ ኢዜማ

    የጋራ መኖሪያ ቤቶች

    #15779
    Anonymous
    Inactive

    ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ድርጅታዊ ህልውና ባገኘባቸው ባለፉት ሁለት ዓመታት ውስጥ የአማራ ሕዝብ እውነተኛ ድምፅ በመሆን ሕዝባችንን ከህልውና ስጋት ለመታደግ፣ አንድነቱን ለማረጋገጥና ጥቅሞቹን ለማስጠበቅ የተቀጣጠለውን ንቅናቄ ጠንካራና የማይቀለበስ መሠረት በማስያዝ ረገድ የበኩሉን አስተዋጽዖ አድርጓል። የአማራውን ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊና ምጣኔ ሀብታዊ ጥያቄዎች ከፍ አድርጎ በመያዝና ለነፃነት፣ ለፍትህና ለእኩልነት የሚደረገውን ትግል በመምራት ሕዝባዊ አመኔታን ለማትረፍ ችሏል።

    አብን ጠንካራ ኢትዮጵያዊ ርእይ የሰነቀ ንቅናቄ በመሆኑ በሀገራዊ የሽግግር ሂደት ውስጥ አዎንታዊ ሚና ለመጫወት ከፍተኛ ጥረት አድርጓል። አማራው በታላቅ መስዕዋትነት ያስገኘው ለውጥ መስመሩን እንዳይስት፣ በትግላችን የተንበረከኩ ጠላቶች መልሰው እንዳያንሰራሩ፣ የፈነጠቀው የለውጥ ተስፋ እንዳይጨነግፍና ዳግም የሀገራችንና የሕዝባችን ህልውና አደጋ ላይ እንዳይወድቅ ያላሰለሰ ትግል ሲያደርግ ቆይቷል።

    ይሁን እንጂ ጥረቶቻችን እንደሚጠበቀው ያህል ፍሬ ከማፍራት ይልቅ እየመከኑና የሀገራዊው የፖለቲካ አውድ ከጊዜ ጊዜ ተስፋ አስቆራጭ እየሆነ መምጣቱን የሚጠቁሙ በርካታ ምልክቶችን አስተውለናል። ንቅናቄያችን በዚህ ረገድ በአማራ ሕዝብና በኢትዮጵያ ላይ ያንዣበበውን ጽኑ አደጋ በሚያሳዩ ሦስት አበይት ጉዳዮች ላይ ያለውን አቋም በግልፅ ለማሳወቅ ይሻል።

    1. በአማራ ሕዝብ ላይ የሚፈፀሙ በደሎችና የዘር ጥቃቶችን በተመለከተ፦

    አብን በሀገራችን በየትኛውም ክፍል፣ በማናቸውም ኃይልና በየትኛውም ሕዝብ ላይ የሚፈፀሙ የሽብርና የዘር ጥቃቶችን ያለማመንታት አውግዟል። የጋሞ ተወላጆች በቡራዩ በግፍ ሲጨፈጨፉ፣ የአዲስ አበባ ወጣቶች ታፍሰው ወደ ጦር ካምፕ ሲጋዙ፣ የጌዴዖ ወገኖቻችን ሰብዓዊ እርዳታ ተነፍገው በርሀብ ሲረግፉ፣ ቤተ እምነቶች በእሳት ሲጋዩና አማኞች በጭካኔ ሲታረዱ ድምፃችንን ከፍ አድርገን ለኢትዮጵያ መንግሥትና ሕዝብ እንዲሁም ለዓለም ማኅበረሰብ በማሰማት ዜጎች ከጥቃት እንዲጠበቁና ሰብዓዊ መብቶቻቸው ተከብረው እንዲኖሩ ጥረት አድርገናል።

    በተለይ በኦሮሚያ ክልል በተደጋጋሚ የተከሰቱትን ማንነትና እምነት ተኮር የዘር ማፅዳት፣ የዘር ፍጅትና ሰብዓዊ ወንጀሎችን ለመከላከልና ለማስቆም ሰፊና ያላሰለሰ ትግል አድርገናል። ዜጎች በአማራነታቸው ተመርጠው ቤታቸው ሲፈርስና ሲፈናቀሉ፣ አማራ ተማሪዎች ከኦሮሚያ ክልል ዩኒቨርሲቲዎች በዘር ጥቃት ተገደው ሲለቁና እገታ ሲፈፀምባቸው፣ በኦሮሚያና በሌሎች ክልሎች በሚኖረው ሕዝባችን ላይ የዘር ማጽዳትና ሰብዓዊ ወንጀሎች ሲፈጸሙ ከማውገዝና ማዕከላዊና ክልላዊ መንግሥታት ጥቃቶቹን በአስቸኳይ እንዲያስቆሙ ግፊት ከማድረግ ባለፈ አደጋውን አስቀድሞ መከላከልና ማስቀረት በሚቻልበት መንገድ ላይ ሰፊና የተቀናጁ ጥረቶችን ስናደርግ ቆይተናል።

    በዚህ ረገድ ንቅናቄያችን ካደረጋቸው በርካታ ጥረቶች መካከል ለአብነት ሚያዚያ 29 ቀን 2012 ዓ.ም በኦሮሚያ ክልል የሽብር ኃይሎች ማንነት ተኮርና በተለይም አማራውን ዒላማ ያደረጉ የዘር ጥቃቶች ሊፈፅሙ እንደሚችሉ ከሁኔታዎች ጥናት በመተንበይ ለዚህ ማዕከላዊ መንግሥቱ ልዩ ቅድመ ዝግጅት እንዲያደርግ በአካል ለሀገሪቱ ከፍተኛ መሪዎች ከማስረዳት ባለፈ በመግለጫ ጭምር በአንክሮ ማሳሰቡ ይታወሳል።

    1.1. ከሰኔ 22 ለሊት እስከ ሰኔ 25 ቀን 2012 ዓ.ም በኦሮሚያ ክልል የተደረገው የዘር ማጥፋት፦

    መንግሥት ተቀዳሚ የሆነውን ሰላምና ደኅንነት የማሰከበር ኃላፊነቱን በአግባቡ ሊወጣ ባለመቻሉ የአርቲስት ሀጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ሽፋን በማድረግ ጽንፈኛ ኃይሎች ጥምረት ፈጥረውና ተዘጋጅተው በኦሮሚያ ክልል በሚኖሩ በዋነኝነት በአማሮች ላይ፣ በተጓዳኝም በኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ላይ ከሰኔ 22 ሌሊት እስከ ሰኔ 25 ቀን 2012 ዓ.ም ድረስ በሽፋኑም ባስከተለው ሰብዓዊና ቁሳዊ ውድመትም እስከዛሬ ከታየው እጅግ ሰፊና አሰቃቂ የዘር ጥቃት ፈፅመዋል።

    አብን ይህን መረን የለቀቀ የዘር ማጥፋት ድርጊት በወቅቱ ከማውገዝ ባሻገር ጭፍጨፋው በተፈፀመባቸው አካባቢዎች የጥናት ቡድን ልኮ በደረሰው ሰብዓዊና ቁሳዊ ጉዳት ላይ ዝርዝር መረጃዎችን በማሰባሰብና በማጠናቀር ሰነድ አዘጋጅቷል። ሰነዱ በአማርኛና በእንግሊዝኛ ቋንቋዎች ተዘጋጅቶ ለሚመለከታቸው የሀገር ውስጥና ዓለማቀፍ አካላት በተለይም ለዲፕሎማቲክ ማህበረሰቡ ፣ ለሰብአዊ መብት ተቋማትና ለአማራ አደረጃጀቶች እየተሰራጨ ሲሆን ፣ ንቅናቄያችን የዘር ፍጅቱ እውቅናና ትኩረት እንዲያገኝና ፍትህ እንዲረጋገጥ ቀጣይ እርምጃዎችን የሚወስድ ይሆናል።

    ሀ. የጥፋቱ አድማስ፦

    ንቅናቄያችን ያደረገው ጥናት በወቅቱ በኦሮሚያ ክልል ከተፈፀመው ሰፊ የዘር ጥቃት ውስጥ በስድስት ዞኖች በሚገኙ በ26 ከተሞችና አካባቢዎች የደረሰውን ያካትታል። በምሥራቅ ሸዋ ዞን ደብረዘይት፣ ናዝሬት፣ መተሐራ፣ ዝዋይ፣ አዳሚ ቱሉ፣ ቡልቡላ፣ መቂ ከተሞችን፤ በምዕራብ አርሲ ዞን ሻሸመኔ፣ አርሲ ነገሌ፣ አሳሳ፣ ዶዶላ ከተሞችን፤ በምሥራቅ ሃረርጌ ዞን ሃረማያ፣ ባቴ፣ ከምቦልቻ፣ ጉርሱም ከተሞችን፤ በሃረማያ ወረዳ ኦዳ በሊናና መልካ ገመቹ አካባቢዎችን፤ በጃርሶ ወረዳ አሌ ከተማን፣ ሚደጋ ቶላ ወረዳን፤ በባቢሌ ወረዳ የተለያዩ ስፍራዎችን፤ እንዲሁም በሃረሪ ክልል ሃረር ከተማን፤ በምዕራብ ሃረርጌ ዞን ጭሮ ወይም አሰበ ተፈሪ፣ ሚኤሶ፣ አሰቦት ከተሞችና አካባቢዎችን፤ በምዕራብ ሸዋ ዞን በተለይም ወሊሶ፤ በጅማ ዞን በጅማ ከተማ የደረሱትን የዘር ጥቃቶች ያካትታል።

    በጥቃቱ ከወደመው ሀብትና ንብረት መካከል 378 መኖሪያ ቤቶች፣ 111 ከብቶችና በርካታ የእርሻ ማሳዎች፣ የእህልና የሸቀጣሸቀጥ ክምችቶች፤ ከ300 በላይ ከአነስተኛ እስከ ከፍተኛ የንግድ ድርጅቶችና ህንፃዎች፣ 189 ሆቴሎችና ፔንሲዮኖች፣ 5 ትምህርት ቤቶች፣ 15 መድሃኒት ቤቶችና የህክምና ተቋማት፣ 8 ባንኮችና የኢንሹራንስ ተቋማት፣ 117 የተለያዩ ተሸከርካሪዎች ተዘርፈዋል፤ ተሰባብረዋል፤ በእሳት ተቃጥለዋል። አብያተ ክርስቲያናት፣ የእምነት መገልገያዎችና ታሪካዊ ቅርሶች ሳይቀር የጥቃቱ ሰለባ ሆነዋል። በተፈፀመው እጅግ ከፍተኛ ጥቃት በብዙ ቢሊዮን ብር የሚገመት ሀብትና ንብረት ወድሟል።

    አብን በተጨባጭ መረጃና ማስረጃ ባጠናቀረው ዘገባ ግኝት መሠረት ከሰኔ 22 ለሊት እስከ ሰኔ 25 ቀን 2012 ዓ.ም በኦሮሚያ ክልል የተፈፀመው ጥቃት ዓለምአቀፍ የዘር ማጥፋት መስፈርቶችን የሚያሟላና የማያሻማ የዘር ማጥፋት ድርጊት መሆኑን ያምናል።

    ጥቃቱ በዘርና በእምነት ላይ የተመሠረተ በመሆኑ ‹‹ነፍጠኛ›› እና ‹‹የነፍጠኛ ኃይማኖት›› በሚል የዘር ፍጅት መለያ በዋነኝነት በተጠቀሱት ዞኖች የሚኖሩትን በሚሊዮን የሚቆጠሩ አማሮችን ዒላማ ያደረገ ነው። ሙስሊም አማሮችም የጥቃቱ ሰለባ ሆነዋል። የኦርቶዶክስ ኃይማኖት ተከታይ ኦሮሞዎችና ሌሎችም ኢትዮጵያውያን ለጥቃት ተዳርገዋል።

    በዚህ የዘር ማጥፋት ጥቃት ከ200 በላይ አማሮች በአሰቃቂ ሁኔታ በሜንጫ፣ በዱላና በድንጋይ እየተጨፈጨፉ ሕይወታቸው አልፏል።

    በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ የጥቃቱ ሰለባዎች ከቀላል እስከ ፅኑ አካላዊ ጉዳት ደርሶባቸዋል። በጥቂቱ ከ20 ሺህ የሚበልጡ ወገኖችም አስቸኳይ የእለት እርዳታ ፈላጊ ሆነው ሜዳ ላይ ተጥለዋል።

    የአማሮች ሀብትና ንብረቶች እየተመረጡ በመውደማቸው ጥቃቱ በተፈፀመባቸው አካባቢዎች የሚኖሩ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎች ሆን ተብሎ የህይወት ዋስትና እንዲያጡ ተደርገዋል። ችግሩ በነዚህ አካባቢዎች ብቻ የሚወሰን ሳይሆን በመላው ኦሮሚያ የሚኖሩ ወደ 15 ሚሊዮን የሚጠጉ አማሮችና ኦርቶዶክስ አማኞችን ለከፍተኛ የህልውና ስጋትና ሥነ-ልቡናዊ ጉዳት ዳርጓቸዋል።

    ለ. የጥፋቱ ተዋንያን፦

    በሁሉም አካባቢዎች ጥቃቱን በተቀናጀ ሁኔታ በመምራት፣ በማስተባበርና በመፈፀም በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል። በተለይ በኦሮሞ ፅንፈኛ የፖለቲካ ቡድኖች፣ ድርጅቶችና ታዋቂ ግለሰቦች ሳይቀር ‹‹ቄሮ›› በሚል ስም የተደራጁ ወጣቶች ዋነኛ የጥቃት ኃይሎች ነበሩ።

    እነዚህ ቡድኖች ከአንዱ ከተማ ወደ ሌላው አቅራቢያ ከተማ ወይም ከገጠር ቀበሌዎች ወደ ከተማ እየተሰማሩ የሚያጠቁ ፣ በከተማው የሚገኙ ዒላማ የተደረጉ ሰዎችን ቤቶችና ንብረቶችን ዝርዝር የያዙ ጠቋሚዎች በቅንጅት የሚሰሩበት ነው። ለንብረቶች ማቃጠያ ቤንዚንና መሰል ግብአቶችንም የሚያቀርቡ ነበሩበት።

    በተለያዩ ደረጃ ያሉ የመንግሥት ኃላፊዎች፣ የክልሉ የፀጥታ መዋቅር አመራሮችና አባላት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ በጥቃቱ ከመሳተፋቸውም በላይ ጭፍጨፋውን ለማስቆም ፍላጎት አጥተው ቆመው መመልከታቸውንም ከፍጅቱ የተረፉ እማኞች አስረድተዋል። የፌዴራል መከላከያ ሰራዊት አመራሮችም እንደ ሻሸመኔና አርሲ ነገሌ ባሉ አካባቢዎች ለቀረበላቸው የድረሱልን ጥያቄ ‹‹ከበላይ ትዕዛዝ አልተሰጠንም›› በሚል ለእርዳታ አልተገኙም።

    የዘር ፍጅቱን ተከትሎ የኦሮሚያ ክልልም ሆነ የፌዴራሉ መንግሥት ወንጀሉን በስሙ በመጥራት ወንጀለኞችን ለሕግ ከማቅረብ ይልቅ ድርጊቱን ተራ ግጭት በማስመል ወደ ማስተባበል ገብተዋል። ከዘር ፍጅቱ የተረፉ ተጠቂ ወገኖችንም በተገቢው ሁኔታ በማቋቋም ረገድ ዳተኝነት ይስተዋላል።

    1.2. የአብን አቋም፦

    በአጠቃላይ አብን በጥናቱ ባረጋገጠው መሠረት በኦሮሚያ ክልል የተደረገው የዘር ማጥፋት ተገቢውን ትኩረት ያለማግኘቱና ችግሩን በአጭር ጊዜም ይሁን በዘለቄታ ለመፍታት የሚታየው ዳተኝነት ፓርቲያችንን ክፉኛ ያሳስበዋል። ስለሆነም፦

    ሀ) የተፈፀመው ወንጀል የዘር ማጥፋት መሆኑ ታምኖበት በስሙ እንዲጠራና ለተፈፀመው ወንጀልም ይፋዊ ይቅርታ እንዲጠየቅ፤

    ለ) መንግሥት የተፈፀመውን የዘር ፍጅት የሚያጣራና የሚመረምር ልዩ የምርመራ ኮሚሽንና አቃቤ ሕግ ጽ/ቤት እንዲያቋቁምና ወንጀለኞች የሚዳኙበት ልዩ ችሎት እንዲሰይም፤

    ሐ) መንግሥት በንፁሃን ዜጎች ላይ የተፈፀመውን አሰቃቂ ወንጀል የሚዘክር ቋሚ መታሰቢያ እንዲያቆም፤

    መ) ችግሩን በዘለቄታ ለመፍታት በክልሉ በሚኖሩ የተለያዩ ማህበረሰቦችና ሕዝቦች መካከል የእርቅና የመግባባት ስራዎች እንዲጀመሩ ፤

    ሠ) የኦሮሚያ ክልልም በክልሉ ለሚኖሩ ኦሮሞ ያልሆኑ ማህበረሰቦችና ሕዝቦች ሰብአዊና ህገ መንግሥታዊ መብቶቻቸው የሚከበሩበት ዋስትና እንዲሰጥ ፤

    ረ) መንግሥት የዘር ፍጅቱን በመዘገባቸው ምክንያት ያሰራቸውን የአስራት ሚዲያ ጋዜጠኞች ያለምንም ቅድመሁኔታ በአስቸኳይ እንዲለቅ አብን ይጠይቃል።

    2. በአዲስ አበባ የሚፈፀሙ ወንጀሎችና ብክነቶችን በተመለከተ፦

    ፓርቲያችን አብን በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርና በፌዴራል መንግሥቱ በከተማዋ ውስጥ የሚፈፅሙትን ወንጀሎች ፣ ሙስናና ብክነቶች የሚመረምር ቡድን በማቋቋም ሰፊ ጥናት እያካሄደ ይገኛል። ከዚህ ጥናት የተገኘ መረጃን መሠረት በማድረግ በከተማዋ ከፍተኛ ሕገ-ወጥ የመሬት ወረራ፣ ተቋማትን በአንድ ብሔር ተወላጆች የመሙላት፣ ሕገ-ወጥ የመታወቂያ እደላና በርካታ ተያያዥ ወንጀሎች እንደተፈፀሙ አረጋግጧል። ይህም በተለይ ከሰኔ 2011 ወዲህ እጅግ የተባባሰ እንደነበር ተገንዝቧል።

    2.1. ሕገ-ወጥ ወረራ፣ ሰፈራና ማፈናቀል

    የአዲስ አበባ ነዋሪዎች በአንጡራ ሃብታቸው ያቆሙት ጎጇቸውና ድርጅቶቻቸው ያለርህራሄና ያለሕግ አግባብ የሚፈርሱባትና ዜጎች ሜዳ ላይ የሚወረወሩበት፤ ከፊሎች ደግሞ በዘር፣ በፖለቲካ ወገንተኝነትና በጥቅም ትስስር በገፍ መሬት የሚቸራቸው፤ የከተማዋ ነዋሪ ከእለት ጉርሱ ቀንሶ የገነባው የጋራ መኖሪያ ቤት በልዩ መብት የሚታደላቸው ከተማ ሆናለች።

    አብን በከተማዋ የሚፈፅሙትን ሕገወጥነቶች ከማውገዝና በተለያዩ መድረኮችና መገናኛ ብዙሃን አማካኝነት ከማጋለጥ ባሻገር አቅም በፈቀደ መጠን የሰብአዊ ርዳታዎችን በማቅረብ ኢትዮጵያውያን ወገኖችን ለመታደግ ጥረት አድርጓል። መላው ሕዝባችን በተለይም ለሕዝብና ለሀገር ጥቅሞች ፣ መብቶችና ፍላጎቶች ቆመናል የሚሉ የፖለቲካ ኃይሎች ከንቅናቄያችን ሀገርን የማዳን ታሪካዊ ጥሪ ጎን እንዲቆሙ ወትውተናል።

    ከዚህም ባለፈ ንቅናቄያችን ጉዳዩን ትኩረት ሰጥቶ በማጥናት ለሀገሪቱ ከፍተኛ የመንግሥት አካላት በተደጋጋሚ አቤት ብሏል። ታህሳስ 2 ቀን 2011 ዓ.ም በብሔራዊ ቤተመንግሥት በመገኘት ጉዳዩ በቀጥታ ከሚመለከታቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አሕመድ ጋር እስከመወያየት ደርሷል። በወቅቱም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ችግሮች መኖራቸውን በማመን አስቸኳይ መፍትሔ እንደሚበጅላቸው ቃል ቢገቡም አንዳችም ሳይደረግ አሁን ካለንበት ሁኔታ ላይ ተደርሷል።

    ሰለዚህም የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ ይህ እጅግ አሳሳቢ ጉዳይ በአስቸኳይ መፍትሄ ካላገኘ ፅኑ ብሔራዊ ቀውስ የሚፈጥር በመሆኑ፦

    ሀ) አዲስ አበባ ላይ የተፈፀመውን ሁሉንአቀፍ ወረራ በተመለከተ የተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ጨምሮ ሌሎች የሚመለከታቸውን ባለድርሻ አካላት ያካተተ አንድ አጣሪ ኮሚቴ እንዲቋቋም፤

    ለ) ባለፉት ሁለት ዓመታት የነበረውን የመሬት አስተዳደርና ማስተላለፍ፣ የመታወቂያ አወጣጥ፣ የቅጥርና ዝውውር እንዲሁም ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮችን እንዲያጣራ/ኦዲት እንዲደረግ፤

    ሐ) በኦዲት ግኝቱ በሚመጣው መሠረት ጥፋተኛ ሆነው የሚገኙ ሁሉም አካላት ለፍትህ እንዲቀርቡ፤

    መ) በኦዲት ግኝቱ ለተለዩ ጉድለቶች አጣሪ ኮሚቴው በሚያቀርበው ምክረ ሐሳብ መሠረት የማስተካከያ የእርምት እርምጃ እንዲወሰድ፤ እንዲሁም

    ሠ) ምርጫ ተካሂዶ ቅቡልነት ያለው ሕጋዊ የከተማ አስተዳደር ምክርቤትና ካቢኔ እስኪዋቀር ድረስ አሁን ያለው የሽግግር አስተዳደር ዘላቂ ውጤት ሊኖራቸው ከሚችሉ ውሳኔዎች እንዲታቀብ፤ አብን ጥሪውን ያቀርባል።

    2.2. ሜጋ ፕሮጀክቶችን በተመለከተ፦

    ፓርቲያችን የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ በጠቅላይ ሚኒስቴር ፅ/ቤትና በከተማ አስተዳደሩም በኩል የሚሰሩ ዋና ዋና 15 ሜጋ ፕሮጀክቶችን ሁኔታ በንቃት በመከታተል ስለፕሮጀክቶቹ ዝርዝር መረጃዎችን ሲያሰባስብ ቆይቷል።

    በዚህም መሠረት በጀታቸው/ወጪያቸው የታወቁ ፕሮጀክቶች የገንዘብ መጠን በአጠቃላይ 5.737 ቢሊዮን ዶላር (ወቅታዊ ምንዛሪው ከ212 ቢሊዮን ብር በላይ) እና ተጨማሪ 59.2 ቢሊዮን ብር በአንድ ላይ ወደ 271 ቢሊዮን ብር የሚጠጋ እንደሆነ ተረድቷል። በጀታቸው ካልታወቁ ጋር ሲደመር ከዚህ ከፍተኛ መሆኑ አያጠራጥርም።

    አዲስ አበባ ተመራጭ የቱሪዝም መዳረሻ ከተማ እንድትሆን የሚደረገውን መንግሥታዊ እንቅስቃሴ በመርኅ ደረጃ አብን ይደግፋል።

    ይሁንና የሜጋ ፕሮጀክቶቹ እጅግ የተጋነነ ወጭ የሚወጡባቸው በመሆናቸው (White Elephant Projects)፤ ይኸው ከፍተኛ በጀት ሀገራችን በብድርና እርዳታ የምታገኘው በመሆኑ፤ አንዳንዶቹ ፕሮጀክቶች ሀገራችን አሁን ካለችበት ሁኔታ አንፃር የቅደም ተከተል ችግር ያለባቸው መሆናቸው ፤ ከአዋጭነት፣ ባለድርሻዎችን ከማሳተፍ፣ ከዲዛይንና ግንባታ አካሄድ፣ ከብክነትና ሙስናን ከማስቀረት፣ በግልጽ ጨረታ የግንባታ ኮንትራክተሮችን ከመለየት እንዲሁም በየጊዜው ስለፕሮጀክቶቹ ለሕዝብ ግልጽ መረጃ ከመስጠት አንፃር ክፍተቶች ያሉባቸው መሆናቸውን አብን ያምናል።

    መንግሥት ይህን ያህል ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብ ግልጽነት ባልተሞላበትና የቅድሚያ ቅድሚያ የሚሰጣቸውን አንገብጋቢ ጉዳዮች ባላስቀመጠ መልኩ ማዋሉ ፓርቲያችንን ክፉኛ ያሳስበዋል። ስለሆነም፦

    ሀ) መንግሥት ስለፕሮጀክቶቹ ለሕዝብ ግልፅ ማብራሪያ እንዲሰጥ፤

    ለ) በኮሮና ወረርሽኝ ምክንያት የሀገራችን ኢኮኖሚ ክፉኛ እየተደቆሰ በመሆኑ ቀውሱ ሀገርን ለከፋ አደጋ የሚዳርግ ማኅበራዊ ቀውስ ከማደጉ በፊት አስፈላጊ የኢኮኖሚ ድጋፍ ማእቀፎችን ቀርፆ ወደ ሥራ እንዲገባ፤

    ሐ) የተጋነኑና አንገብጋቢ ያልሆኑ ሜጋ ፕሮጀክቶችን በማጠፍ በጀቱን የነፍስ አድን ርዳታ ለሚፈልጉ ወደ 18 ሚሊዮን ዜጎች ድጋፍ እንዲያውለው፤

    መ) በሀገራችን ያለው የሥራ አጥነት በአስከፊ ሁኔታ ላይ መገኘቱን በማጤን መንግሥት ጊዜውንና አቅሙን ለወጣቶች ሥራ እድል ፈጠራና ለኢኮኖሚ ሽግግር እንዲያውል አብን ጥሪውን ያቀርባል።

    3. ብሔራዊ ውይይትና መግባባትን በተመለከተ፦

    አብን የሀገራችን የፖለቲካ ቀውስ በምርጫ ብቻ እልባት ያገኛል የሚል አቋም የለውም። ስለዚህም ከምርጫ በፊት እንደ ሀገር መደማመጥ፣ መከባበርና መተማመን እንዲቻልና አሁን የተፈጠረው የሽግግር ጊዜም እንዳለፉት ዘመናት እድሎች እንዳይከሽፍ ሁሉን አቀፍ ሀገራዊ የሰለጠነ ውይይት፣ ምክክርና ድርድር እንዲዘጋጅ፤ ለዚህም ግልጽ ማእቀፍ እንዲኖርና ሁሉንም ባለድርሻ አካላት ያሳተፈ የብሔራዊ ውይይት መድረክ እንዲከፈት ወትውቷል።

    መንግሥት ለእውነተኛ የፖለቲካ ድርድርና ብሄራዊ መግባባት ዳተኝነት በማሳየቱ ምክንያት ፅንፈኛ ኃይሎች ሀገር አፍራሽ ድርጊታቸውን በማናለብኝነት እንዲቀጥሉ እድል ሰጥቷቸዋል። በዚህ ረገድ ትሕነግ የሚዘጋጅበት ሕገ-ወጥ ምርጫ በወረራ በተያዙ የአማራ መሬቶች በወልቃይት፣ ጠገዴ፣ ጠለምትና ራያ የሚኖረው ሕዝባችን ላይ የሚያደርሰውን ፅኑ አፈናና ግፍ መንግሥት እንዲያስቆም በተደጋጋሚ ጥሪ አቅርበናል።

    የፌዴሬሽን ም/ቤት ዘግይቶም ቢሆን የወሰነውን ውሳኔ የፌዴራል መንግሥቱ በአስቸኳይ ተግባራዊ እንዲያደርግና ትህነግ በህገወጥ ምርጫ በወልቃይትና ራያ ሕዝባችን ላይ የሚያደርሰውን ሰብአዊ ቀውስ እንዲያስቆም የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ ጥሪ ያቀርባል።

    በተጨማሪም ፡-

    ሀ) ሀገርን ወደ ዴሞክራሲ ለማሻገር ሁሉም ባለድርሻ አካላት የማይተካ ሚና እንዳላቸው በማመን መላው የፖለቲካ ኃይሎች የሀገራችን አደገኛ ወቅታዊ ሁኔታ ባጤነ መልኩ በኃላፊነት እንዲንቀሳቀሱ፤

    ለ) መንግሥት በውል የታወቀና የታቀደ ሁሉንአቀፍ ብሔራዊ ውይይት፣ ምክክርና ድርድር የማስተባበርና የማመቻቸት ኃላፊነቱን እንዲወጣ፤

    ሐ) ሁሉም ዜጎች በተለይም ሲቪክ አደረጃጀቶች፣ የሚዲያ ተቋማት፣ ምኁራን፣ የኃይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ ታዋቂ ግለሰቦች፣ ወጣቶችና ሴቶች እንዲሁም ባለሀብቶች ለሚደረገው ብሔራዊ ውይይት፣ ምክክርና ድርድር ውጤታማነት የየድርሻቸውን አስተዋፅኦ እንዲኖራቸው፤

    መ) የዓለምአቀፍ ማኅበረሰቡ የሁሉንአቀፍ ብሔራዊ ውይይት፣ ምክክርና ድርድር ሂደት እንዲደግፍና መንግሥት የሚጠበቅበትን ኃላፊነት እንዲወጣም ጫና እንዲፈጥር የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ታሪካዊ ጥሪውን ያስተላልፋል።

    “አንድ አማራ ለሁሉም አማራ ፤ ሁሉም አማራ ለአንድ አማራ!›”
    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን)
    አዲስ አበባ፣ ሸዋ፤ ኢትዮጵያ!
    ጳጉሜ 2 ቀን 2012 ዓ.ም

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን)

    #15784
    Anonymous
    Inactive

    አዲስ አበባ በራሷ ግዛተ-መሬት ላይ የፌዴራል አድያምነት /ክልልነት/ መብት ሊረጋገጥላት ይገባል!
    ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ

    የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ አወቃቀር በመመዘኛዎቹ ላይ በኢትዮጵያ ተፃራሪ አቋም ባላቸው ልሂቃን ዘንድ ስምምነት ላይ ሊደርስ ቢችል፣ ፌዴራላዊ የመንግሥት አደረጃጀት የፖለቲካ አለመግባባት መንስ ዔ ሊሆን የሚችል አልነበረም። ይህ ጥያቄ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ችግር ዋነኛ መገለጫ ሊሆን የበቃው የኢትዮጵያ የፖለቲካ ልሂቃን በዚህ ጥያቄ ዙሪያ ላለፉት ሃምሳ ዓመታት ሊግባቡ ባለመቻላቸው ነው። ሊግባቡ ያልቻሉበትም ምክንያት በኢትዮጵያ ሀገረ-መንግሥት የግንባታ ታሪክ ላይ ልዩነታቸውን ማጥበብ ባለመቻላቸው ነው። ይህ ትውልድ ደግሞ በአጼ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግሥት በ1940ዎቹ ዓመታት ተወልዶ በ1950ዎቹ መጨረሻና በ1960ዎቹ መጀመሪያ ላይ ለዩኒቨርሲቲ ደረጃ የደረሰው ትውልድ ነበር። እንደ አጋጣሚ ሆኖ በ1960ዎቹ ሁኔታ ደግሞ ዓለም በሁለት ተፃራሪ የካፒታሊዝምና የሶሻሊዝም ጎራዎች ፉክክር ተቀስፋ ተይዛ የነበረችበት ወቅት ነበር። በ1960ዎቹ ለጉልምስና ከደረሰው ትውልድ ውስጥ አብዛኛው ነው ባይባልም ተራማጅ የሆነ አስተሳሰብ አለኝ ብሎ ያቀነቅን የነበረው የትውልዱን የአመራር ሚና የተጫወተው የማርክሲዝም ሌኒኒዝም (Marxism–Leninism) አስተምህሮ የተቀበለው ነበር።

    ይሁንና የዚህ የ1960ዎቹ የተማሪ አብዮተኞች እና የ እ ነሱ ከፊል ውጤት ሆነው ያቆጠቆጡት የነገድ ድርጅት መሪዎች የኢትዮጵያን ታሪክ በተፃረረና ባልተገናዘበ ሁኔታ የሶቭየት ሕብረትን የኮሚኒስት ፓርቲ መሪ የስታሊንን “የብሔርና የቅኝ ግዛት ጥያቄ” መጽሐፍ ቃል በቃል በመገልበጥ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ዋነኛ ችግር “የጨቋኝና የተጨቋኝ ብሔረሰቦች መስተጋብር ነው” የሚል የሀሰት የታሪክ ትርክት ይዘው ተነሱ። እነዚህ ከተማሪ አብዮተኝነት ወደ ነገድ ድርጅትነት የተሸጋገሩት ከደርግ መንግሥት ጋር ለ17 ዓመታት ጦርነት አድርገው በታሪካዊ የኢትዮጵያ ጠላቶች ያላሰለሰ ድጋፍ በ1983 ዓ.ም በኢትዮጵያ ጦር ላይ ድል ሊቀዳጁ በቁ። አነዚህ ኃይሎች በተጠናወታቸው “የጨቋኝና የተጨቋኝ ብሔረሰቦች” የሀሰት ትርክት ውጤት የሆነውን የመገንጠል መብት ሕገ-መንግሥታዊ መብት ያደረገ፣ ይህንንም ተግባራዊ ለማድረግ ያለመ ቋንቋን መሠረት ያደረገ መንግሥታዊ የፌዴራል አወቃቀር በኢትዮጵያ ላይ አነበሩ።

    በሀገራችን ታሪክ ታይቶ በማይታወቅ ደረጃ የጐሳና የዘረኝነት ፖለቲካዊ አደረጃጀት የመንግሥት የፖለቲካ እና የኢኮኖሚ አደረጃጀት ዓይነተኛ መገለጫ ከመሆን አልፎ ይኸው ዓይነት አደረጃጀት  ወደ እምነት ተቋማት ሳይቀር ዘልቆ እንዲገባ ተደረገ። በሀገሪቱ ታሪክ በማይታወቅ ሁኔታ በተረኝነት መንፈስ የተቃኘ ተቋማዊ/መንግሥታዊ ሙስና እና የፍትህ መዛባት የሥርዓት መገለጫ ሊሆን በቃ። ከሕዝቡ ታሪካዊ አሠራር ጋር ባልተገናዘቡ የክልል አደረጃጀቶች ምክንያት በሀገራችን እንግዳ በሆነ መልኩ ማንነትን እና እምነትን መሠረት ያደረጉ ግጭቶች እንዲበራከቱ፣ ሕዝብ የተረጋጋ ሕይወት እንዳይኖረው በፌዴራል መንግሥቱና በክልል መንግሥታት መካከል የኃላፊነትና የተጠያቂነት ጉዳይ አሻሚ በማድረግ፣ የሀገሪቱ ብሔራዊ ስሜት እንዲላሽቅ በምትኩ ጠባብና ክልላዊ አስተሳሰብ እንዲሰፍን ተደረገ። በኢትዮጵያ የዘውግ ፌዴራሊዝም ሥርዓት ችግር ብሔረሰብን ዋነኛው የፌዴራል ሥርዓቱና የሀገር መንግሥት ግንባታ መሠረት ማድረጉ ነው።

    እዚያው ተወልዶ ያደገውና ከአራቱም የኢትዮጵያ ማዕዘናት የመጣውን የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ አንድ ብሔረሰብን እና አንድ ቋንቋ ተናጋሪነትን መሠረት አድርጎ በተዋቀረ ክልል ውስጥ አስገብቶ እንዲተዳደር ማድረግ  ፍትሃዊነት የለውም። የአዲስ አበባ ሕዝብ ጥያቄ ከራሴ ውጭ በእኔ ዕጣ ሌላ ሊወስንብኝ አይገባም የሚል ነው። አዲስ አባባ በኦሮሚያ ምድረ ፅፋዊ (geographic) ክልል ውስጥ በመገኘቷ ብቻ ለአዲስ አበባ ባለቤትነት የመብት መብለጫ፣ ለተፈጠረ ውጥንቅጥ ደግሞ የአዲስ አበባ ሕዝብን መብት ማሳነሻ ማድረግ በምንም መመዘኛ ተገቢነትም ሆነ ተቀባይነት የለውም።

    የኢፌዲሪ ሕገ-መንግሥት በአንቀጽ 69 “የፌዴራሉ መንግሥት ርዕሰ ከተማ አዲስ አበባ ነው። የከተማው አስተዳደር ራሱን በራሱ የማስተዳደር ሙሉ ሥልጣን ይኖረዋል። ዝርዝሩ በሕግ ይወሰናል” ይላል። የአዲስ አበባ ከተማ ራሱን በራሱ የማስተዳደር ሙሉ ሥልጣን እንዳለው ቢታወቅም የህወሓት እና የኦነግ በሆነው ሕገ-መንግሥት ውስጥ “በአዲስ አበባ ከተማ የኦሮሚያ ክልል ልዩ ጥቅም ይኖረዋል” በሚል መካተቱ ችግሩን ሆን ተብሎ እንዲወሳሰብ አድርጎታል።

    በ1989 ዓ.ም የወጣው የአዲስ አበባ ከተማ አስተደደር ማቋቋሚያ ቻርተር መሠረት አዲስ አበባ ራሷን በራሷ እንድታስተዳድር ሲደነገግ፣ በሕገ-መንግሥቱም ሆነ በአዲስ አበባ ከተማ ቻርተር መሠረት የከተማዋ ስምና ስያሜ አዲስ አበባ እንደሆነ ተደንግጓል። ይሁንና ቻርተሩን መሠረት በማድረግ ተዘጋጅቶ የቀረበው ረቂቂ አዋጅ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ የመጽደቅ ሂደቱ በደባ እንዲቀር ተደርጓል። አዲስ አበባ እንደ ዋሽንግተን ዲሲ እና እንደ ካንቤራ (Washington, DC and Canberra) የፌዴራል መንግሥት ግዛት ናት የሚል የሕግ አንቀጽ የለም። ይህ አይደለም እንዳይባል በወንጀልም ሆነ በፍትሀ-ብሔር ጉዳይ በአዲስ አበባ የግዛት ክልል ውስጥ የተፈፀመ ወይም የተከናወነ የሕግ ጥሰት ግን ልክ የፌዴራል መንግሥት ይዞታ አንደሆነችው ዋሽንግተን የመዳኘት ሥልጣንን ለፌዴራል መንግሥቱ ይሆን ዘንድ በሕግ ተለይቶ ተሰጥቷል። ማለትም በተግባር የፌዴራል መንግሥቱ አዲስ አበባን እና ድሬደዋን የራሱ ግዛት አድርጓቸዋል።

    ሕገ-መንግሥቱ አዲስ አበባ እራሱን የማስተዳደር ሙሉ ሥልጣን የሰጠው መሆኑ ከላይ የተጠቀሰው የወንጀልና የፍትሀ-ብሔር ጉዳዮችን ለመዳኘት ከተሰጠው ሥልጣን ጋር ሲዳመር አዲስ አበባ ልክ እንደ ዋሽንግተን የፌዴራል ግዛት እንደሆነች ለመረዳት ይቻላል። በተጨባጭ ግን አዲስ አበባ ከተማ የተተወላት የከተማ-ነክ አስተደደርና ከማዘጋጃ ቤት አገልግሎት ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን የመዳኘት ሥልጣን ነው። ማለትም ስለ ዳኘነት ሲሆን መሬቱ የፌዴራል መንግሥት፣ ስለ ሌሎች አስተዳደራዊ ጉዳዮች ሲሆን የከተማ መስተዳድሩ ሆኗል።

    አዲስ አበባ ራሷን የማስተዳደር መብት በሕገ-መንግሥቱ የታወቀ ቢሆንም፤ በፌዴሬሽን ምክር ቤት ጭምር ኢ-ፍትሀዊ በሆነ መንገድ ውክልና የላትም። ሕገ-መንግሥቱ ከሚደነገገው ውጭ ስትደዳደር የቆየችው በህወሓት/ኢህአዴግ፣ አሁን ደግሞ በኦህዴድ/ብልጽግና ነው። በሌሎች ክልሎች ክልሎችን የሚያስተዳድሩ የክልል ፓርቲዎች አሉ /ትግራይ፣ ኦሮሚያ፣ አማራ፣ ደቡብ ወዘተ…/ አዲስ አበባ ላይ ግን የሚወክላት የፖለቲካ ፓርቲ የለም። ገዥ ፓርቲዎች ፍላጎታቸውን የሚጭኑባት ከተማ ናት። ቀደም ሲል ህወሓት/ኢህአዴግ አሁን ደግሞ ኦህዴድ/ብልጽግና ፓርቲ አዲስ አበባን ማስተዳደሩን ቀጥሎበታል። ይህ ሁኔታ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች በሕገ-መንግሥቱ የተሰጣቸውን ራሳቸውን የማስተዳደር መብት ፍፁም የሚጥስ ነው።

    አዲስ አበባን እንዲመራ የሚመደበው በገዢው ፓርቲ ውስጥ ከነበሩ ወይም ካሉ የክልል ገዢ ፓርቲዎች እንጂ በከተማው ሕዝብ ነፃ ምርጫ አልነበረም፤ አሁንም አይደለም። አዲስ አበባ ቀደም ሲል ከሁለቱ ክልሎች /ትግራይኦሮሚያ/ አሁን ከ “ለውጡ” ወዲህ ደግሞ ከኦሮሚያ ክልል በሚመጡ ተሹዋሚዎች እንድትደዳደር መደረጉ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ጥቅምና ፍላጎት እንዳይከበር ያደረገ የፖለቲካ ደባ ነው። ከዚህም ባሻገር ከ7 ሚሊዮን የሚልቀውን የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ በኢኮኖሚ እንቅስቃሴው በግብር መልክ በቢሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ ለመንግሥት ካዝና የሚያስገባውን ነዋሪ የፖለቲካ ባይተዋር ያደረገ እና በዕጣ ፈንታው ላይ  እንዳይወስን ያደረገ ኢ-ፍትሀዊ የሆነ የፖለቲካ አካሄድ ነው። የአሜሪካን አብዮት እንደቀሰቀሰው /Taxation without Political Representation/ እንደሚለው መፈክር ሠርቶ ግብሩን እየገበረ የፖለቲካ ባይተዋር በማድረግ በዕጣ ፈንታው ላይ እንዳይወስን አድርጎታል። ይህ ፍትሀዊ ያልሆነ የፖለቲካ አካሄድ ከመሆኑም በተጨማሪ በግልጽ የሕገ-መንግሥቱን አንቀጽ 49 እና አንቀጽ 89 ይጥሳል።

    የኢትዮጵያ ሕገ-መንግሥት ትልቁ ወለፈንዲ የአዲስ አበባ ጉዳይ ነው። በአንቀጽ 69 መሠረት የአዲስ አበባ ከተማ የፌዴራሉ ርዕሰ ከተማ እና የከተማው ነዋሪ ሕዝብ እራሱን በራሱ የማስተዳደር መብት ይኖረዋል ሲል ደንግጓል። ማለትም፥ አዲስ አበባ የተወላጆቿና እና የሁሉም ከ80 በላይ የሆኑት የኢትዮጵያ ብሔረሰቦች በባለቤትነት የሚኖሩባት ከተማ ናት። የአዲስ አበባን አስተዳደር ስንት አማራ፣ ስንት ኦሮሞ፣ ስንት ትግሬ፣ ስንት ጉራጌ፣ ስንት ወላይታ፣ ስንት ሱማሌ፣ ስንት አደሬ፣ ስንት ጋምቤላ፣ ስንት ቤንሻንጉል፣ ስንት ማኦ ወዘተ… እንደሚኖሩባት በተጨባጭ የተረጋገጠ አሃዛዊ መረጃ (statistics) ስለሌለ የአዲስ አበባ ባለቤትነት ሊሰጥ የሚችለው ከሕገ-መንግሥቱ መንፈስ ውጭ ለመላ ቋሚ ነዋሪዎቿ ነው ሊሆን የሚችለው። ይሁንና የአዲስ አበባን ከተማ ባለቤትነት በተመለከተ እንደ ሌሎች የፌዴራል መንግሥት ዋና ከተማዎች እንደሆኑት እንደ ሞስኮ፣ በርሊን፣ ቪየና እና ብራስልስ ለፌዴራል መንግሥት ተጠሪ ያልሆኑ፣ በኢትዮጵያም ከ1983 ዓ.ም ሰኔ ወር ጀምሮ ሕገ-መንግሥቱ ተግባራዊ እስከ ተደረገበት 1987 ዓ.ም ነሐሴ ወር ድረስ ክልል 14 ተብላ የክልልነት ደረጃ የተሰጠበትን ሁኔታ መልሶ ተግባራዊ ማድረግ  ፍትሃዊ እና የነዋሪዎቿን ሕጋዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ነው።

    አዲስ አበባ እንደ ፌዴራል መንግሥት ርዕሰ ከተማነቷ የግዛተ-መሬቷ ባለቤትነትን ለፌዴራል መንግሥቱ ሳይሆን በሽግግር ወቅት እንደነበረው በፌዴራል አድያምነት /በክልልነት/ ደረጃ እንደገና እንድትዋቀር ባልደራስ እውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ) ለከተማዋ ሕዝብ ጥሪውን ያቀርባል።

    ከሀገራችን ዘመናዊ የታሪክ ጅማሮ ጋር የተሰናሰለ እድሜ ያላት አዲስ አበባ ከተማ፥ በመልክ-ዕምድር አቀማመጧ የሀገሪቱ እምብርት ላይ መገኘቷ ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታዋን የጎላ አድርጓታል። ይህ ሁኔታዋ ለሀገራችን ዜጎች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ለመስጥ የሚያስችል አቅም ያላት ከተማ እንድትሆን ሰፊ ዕድል ሰጥቷታል። ነገር ግን ከተማዋ ያላትን ሰብዓዊና ቁሳዊ አቅም አሟጣ በመጠቀም ለነዋሪዎቿ ተስፋ መሆን እንዳትችል በሀገራቸን የነበሩ እና ያሉት ገዢዎች አተያይ እና የአመራር ፈሊጥ ትልቅ ተግዳሮት ሆኗል። “በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ” እንዲሉ ጎሳን መሠረት ያደረገው የባለፉት 30 ዓመታት የሀገራችን ፖለቲካን ያነበረው ሥርዓት የአዲስ አበባ ከተማን ህልውና የበለጠ ተፈታትኖታል፤ ከባድ አደጋንም የፈጠረ ሆኗል።

    አዲስ አበባ የሀገራችን ርዕሰ መዲና ከመሆኗ ባሻገር፣ የአፍሪካ ሕብረት እና የጥቁር ሕዝቦች የነጻነት ተምሳሌትና መናኸሪያ፣ የትላልቅ ዓለም አቀፍ ተቋማት መታደሚያ ናት። የሀገራችን 65% ምጣኔ-ሀብት በአንበሳ ድርሻነት ይዛለች፤ በሀገሪቱ ውስጥ የሚገኙ የተለያዩ ቤተ-እምነቶች እና የእምነቱ ተከታዮች ተቻችለው የሚኖሩባት የአብሮነት መገለጫ ከተማ ስትሆን፥ የታሪካችን መገለጫ የሆኑ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ ቅርስ እና ትውፊት የተመዘገበባት፣ እንዲሁም የተለያዩ ቋንቋዎችና ባህሎች ሕብር ፈጥረው በነፃነት የሚንጸባረቁባት የኢትዮጵያ ብዝሃነት ማሳያ ፈርጥ ናት።

    ከተማችን አዲስ አበባ ባለፉት 3 አስርት ዓመታት ሲመሯት የነበሩት ሁሉ ምን ልጠቀምባት እንጂ ምን ላድርግላት የሚል ኃላፊነት የሚሰማቸው ባለመሆኑ ችግሮቿን የተወሳሰቡ አደርጎታል። እንደ ፓርቲያችን እምነት፥ ለዚህ ችግር በዋነኝነት ያጋለጣት በዲሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጠ አስተዳድር ተሰይሞ ሊያስተዳድራት አለመቻሉ ጉልህ ስፍራ ይይዛል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርን በከንቲባነት ሲመሩ የቆዩት ግለሰቦች በአብዛኛው የከተማውን ነዋሪ ሥነ-ልቦና በቅጡ ያልተረዱ፣ ራዕይ-አልባ የሆኑ እና ከፍተኛ የብቃት ጉድለት የሚስተዋልባቸው ናቸው።

    አዲስ አበባ ከተማ ራስ ገዝ (በአሁኑ አጠራር ክልል) እንድትሆን መሆኑ እውነተኛ ፌዴራላዊ አስተዳደር በኢትዮጵያ ውስጥ ለማንበር በሚደረገው ጥረት ወሳኝ ሚና እንደሚኖረው ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ ያምናል፤ በመሆኑም አዲስ አበባ ራስ ገዝ አስተዳደር እንዲኖረው በላቀ መንገድ መታገል አስፈላጊ ሆኗል።

    የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ ላለፉት ዘመናት በተለይም የህወሓት/ኢህአዴግ ሥልጣን ዘመን ጀምሮ በመረጠው የመተዳደር መብቱን ተነፍጎ፣ ከኢህአዴግ አባል ድርጅቶች ኦህዴድ በውክልና ተቀብሎ አስተዳድራለሁ በሚል የተረኝነት፣ የሙስና፣ የባህል በአጠቃላይ የዘረኝነት ሰለባ ሆኗል። የተረኛነት ስሜት ነቀርሳ የሆነበት ኦህዴድ/ብልጽግና የአዲስ አበባን ሕዝባዊ አውቃቀር (demography) ከመቀየር ጀምሮ ተጠንቶ የከተማው ሕዝብ ባልመከረበት የትምህርት ሥርዓት ውስጥ ረጅም እጁን ሕገ-ወጥ በሆነ መንገድ በመስደድ፣ የከተማውን መሬት በማስወረር እና ነዋሪው ጥሮ ግሮ ቆጥቦ የሠራውን ቤት አንዴ ለኦሮሚያ የመንግሥት ሠራተኞች በሚል ሌላ ጊዜ ደግሞ የተለየ ምክንያት በመስጠት እየዘረፈ  መሆኑ የከተማዋን ነዋሪ በደል ጫፍ አድርሶታል።

    ዛሬ ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞካራሲ ፓርቲ ይህንን የዘመናት የአዲስ አበባ ሕዝብ ጥያቄ ምላሽ እንዲያገኝ መብቱን የሚጠይቅበት ጊዜ ላይ መድረሱን ተገንዝቧል። በኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊ እና ፖለቲካዊ ፍትህ ማግኘት የሚቻለው የከተማው ነዋሪ ራሱ የመረጠው ሥርዓት ሲዘረጋ መሆኑን በቅርቡ ተረድቷል። አሁን እየደረሰበት ያለው ግፍ መነሻው ለሕዝብ ተጠያቂነት ያለው ትክክለኛ አስተዳደር አለመኖሩና ይህንን ተገን በማድረግ ወደ ዝርፊያ የገቡና ለዚሁ ሁኔታ እንዲያመቻቸው ብቻ የሚሠሩ የውክልና መሪዎች በመሆናቸው ከእነዚህ አስተዳደር ውጭ እንዲሆን ለማስቻል ዴሞክራሲን ለማስፈን እንዲረዳ ነው።

    ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ አዲስ አበባ ከተማ ራስ ገዝ እንድትሆን ብዙ ዜጎች ጥያቄ ሲያነሱ እንደነበረ ያምናል። ይህ የከተማው ነዋሪ ጥያቄም፣ ፓርቲው እንዲመሠረት ገፊ ምክንያት እንደሆነ በመገንዘብ፣ ትላንት ዜጎች ሲያነሱት የነበረው ጥያቄ ወደላቀ ምዕራፍ መሸጋገሩን በማብሰር፤ የአዲስ አበባ ሁለንተናዊ ችግር አስጨንቋቸው እና እንቅልፍ ነስቷቸው ለነበሩ ዜጎች ሁላ ይህ የእናንተ የትላንትና የትግል ጥያቄ በመሆኑ ከፍ ያለ ምስጋና ይገባችኋል። የዜጎች በደልና ጭቆና እንዳንገበገባችህ እናምናለን፤ ይህንንም ለመቅረፍ በጋራ እንድንቀሳቀስ እንጠይቃለን።

    ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ የከተማችንን ነዋሪ የሚመጥን አስተዳደር እንዲዘረጋ የሚያደርገው ጥረት፣ ከአንድ የፖለቲካ ድርጅት ጥያቄ በላይ እንደሆነ ያምናል። በመሆኑም በሀገራችን የምትገኙ የፖለቲካ ኃይሎች፣ ለከተማው ነዋሪ የራሱን ራስ ገዝ አስተዳደር እንዲመሠረት አስፈላጊውን ሁሉ ድጋፍና ትብብር እንድታደርጉለት፤ ምሁራን እና ታዋቂ ግለሰቦችም የሚመሠረተው አስተዳደር የሚያስፈልገውን ድጋፍና አወቃቀር በአግባቡ እንዲይዝ መልክ ለማስያዝ የሚረዳ ልምዳችሁን፣ እውቀታችሁን እንዲሁም ተፅዕኖ የመፍጠር አቅማችሁን እንድታበረክቱ ጭምር አደራ ይላል።

    በዋነኝነት የአዲስ አበባ ራስ ገዝ አስተዳደር ባለቤት ሁሉም የከተማው ነዋሪ እንደሆነ ባልደራስ በጽኑ ያምናል። ይህንንም ለማድረግ የሚያስችል ሕጋዊና ሰላማዊ ትግል በማድረግ የፌዴራል መንግሥት ጥያቄውን እንዲቀበልና በሀገሪቱ አሁን ባለው ሥርዓት መሠረት ሕዝበ-ውሳኔ ተካሂዶ የራስ ገዝ አስተዳደር (ክልል) እንዲሆን እንጠይቃለን። ይህንንም ጥያቄ እውን ለማድረግ እና በሕጉ አግባብ እንዲስተናገድ ለማድረግ የተከማው ነዋሪ የስምምነት ፊርማ የማሰባሰብ ሂደት ውስጥ ተሳታፊ እንዲሆን ጥሪ እናቀርባለን። ጥሪውም በነዋሪ ሕዝቧ ፍላጎት ላይ የተመሠረተ መሆኑን ለማስረገጥ ድጋፉን በፊርማ የሚያቀርብበት የአሠራር ዘዴ ይቀይሳል።

    በመጨረሻም ይህንን የጳጉሜን ሣምንት በግፍ ለታሰሩ የፓርቲያችን መሪ አቶ እስክንድር ነጋ፣ አቶ ስንታየሁ ቸኮል፣ ወ/ሮ ቀለብ ስዩም እና ሌሎች የፓርቲው አባላትና አመራሮች በግፍ ከታሰሩበት እንዲፈቱ በተለያዩ መንገድ ግፊት ለምታደርጉ ወገኖች ምስጋናችንን እያቀረብን፥ መንግሥት በማን አለብኝነት ያለኃጢያታቸው አስሯቸው የሚገኙ ንፁሃን መሪዎቻችንን እና አባላቶቻችንን በአስቸኳይ እንዲፈቱ በድጋሚ ጥሪያችንን እናቀርባለን።

    መጪው የኢትዮጵያ አዲስ ዓመት፣ ከኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ስጋት ተላቀን በሰላም ወጥተን የምንገባበት፣ ለሀገራችን ዜጎች ሰብዓዊ መብት የሚከበርባት፣ ለተበደሉ ፍትህ የሚሰፍንበት፣ ዴሞክራሲ የሚያብብበት እንዲሆን እንመኛለን፤ ለብሔራዊ መግባባት ሁሉም የፖለቲካ ወገኖች አንድ ላይ ተቀምጠው ስምምነት ላይ የሚያደርስ ተጨባጭ ሥራዎች የምናከናውንበት ዘመን እንዲሆን መልካም ምኞቱን ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ ይገልጻል።

    ድል ለእውነተኛ ዲሞክራሲ!
    ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ)
    ጳጉሜ 3 ቀን 2012 ዓ.ም

    ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ

    #15825
    Anonymous
    Inactive

    የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) መግለጫ
    መስከረም 13፥ 2020

    የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) ለኢትዮጵያ ውስብስብ የፖለቲካ ችግሮች አስተማማኝና ዘላቂ መፍትሄ ሊገኝ የሚችለው ሁሉን በሚያካትት ዴሞክራሲና በሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች ተሳትፎ ብቻ ነው የሚል ቅን እምነት አለው። ይህንንም ለማድረግ ኦነግ ሀገሪቱን የማስተዳደር ስልጣን ያላቸውን እና የተቃዋሚ ቡድኖችን ጨምሮ ከተለያዩ የፖለቲካ ኃይሎች ጋር በመሆን በኢትዮጵያ የፖለቲካ ቀውሶችን ለመፍታት የጋር ብሔራዊ መግባባት ለመፍጠር ሲሠራ ቆይቷል። ኦነግ ከፍተኛ አመራሩን ወደ ሀገር ካዛወረ እ.ኤ.አ. ከመስከረም 15 ቀን 2018 ወዲህ ወደ ሁሉን አቀፍ እውነተኛ ዴሞክራሲ የሚያመራውን የሰላም ሂደት ስኬታማ ለማድረግ በሐቀኝነትና በታማኝነት ለመሥራት ወሰነ።

    ምንም እንኳን ከመጀመሪያው ጀምሮ በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ሽግግር አያያዝ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ መንግሥት እንዴት እንደተከናወነ አስመልክቶ ኦነግ ደስተኛ ባይሆንም፣ ይሻሻላል ብለን ተስፋ በማድረግ ሁኔታዎችን በትዕግስት ተቋቁመናል፤ ያለ ዋጋ ግን አይደለም።

    ሆኖም እ.ኤ.አ. በ2018 የተጀመረው የፖለቲካ ለውጥ ከውስጥ ከገዢው ፓርቲ እንዲሁም ከውጭ ከተቃዋሚ ቡድኖች ግዙፍ ተግዳሮቶች አጋጠመው። ሁኔታዎቹ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሱ በመሄድ በአሁኑ ወቅት ሁሉም ነገር ከቁጥጥር ውጭ ወደሆነበት ደረጃ በመድረስ መንግሥትን ወደ ውድቀት እያመራው ይገኛል። አሁን በሀገሪቱ ውስጥ በጣም እጅግ አሳሳቢ አለመረጋጋትና የተሰበረ ፖለቲካ ተስፋ ይስተዋላል፤ ሕዝቡ ከገዢው ፓርቲ ተስፋና እምነት አጥቷል። በሀገሪቱ ውስጥ ግልጽ “የሕገ-መንግሥታዊ ቀውስ” የተመለከትን ሲሆን፥ በስልጣን ላይ ያለው ፓርቲ መጀመሪያ ከገባቸው ቃላት ማሽቆለቆሉና ሕገ-መንግሥቱን የማስጠበቅ ኃላፊነት ያለባቸውን የመንግሥት አካላት ለራሱ የፖለቲካ ጥቅም ሲገለገልባቸው ቆይቷል።

    የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎች አመራሮችንና አባላትን ማሰርና ከፍተኛ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የዕለት ተዕለት ሥራ ናቸው። ምንም እንኳን የጭካኔ ድርጊቶች ቢኖሩም፤ ኦነግ እና ሌሎች ተቃዋሚ ፓርቲዎች ለውጡን በተናጥል እንዲሁም በጋራ ለመደገፍ ያላቸውን ፍላጎት መግለፃቸውን ቀጥለዋል።

    በተናጠል ካለው የመፍትሄ ሀሳብ በተጨማሪ የኦሮሞ ነፃነት ግንባር ዴሞክራሲያዊ ሽግግሩን ለመደገፍ በተለያዩ የተቃዋሚ ፓርቲዎች መድረክ ላይ ተሳትፏል። ከመድረኮቹ መካከል ለሽግግሩ እና ለዴሞክራሲያዊ ሂደቱ የጋራ ድጋፍ ለመስጠት ያለመው ትብብር ለሕብረ-ብሔር ዴሞክራሲያዊ ፌዴራሊዝም (ትብብር) አንዱ ነበር። እ.ኤ.አ. በሚያዝያ 2020 ይህ ትብብር በሽግግር ሂደት ላይ ለመንግሥት ሁሉን አቀፍ የመፍትሔ ምክረ-ሀሳቦችን አቅርቧል። የመፍትሄ ምክረ-ሀሳቦቹ በመግባባት ላይ ለተመርኮዘ የፖለቲካ እልባት በለውጡ እንዴት መቀጠል እንደሚቻልና የተረጋጋ ዴሞክራሲያዊ አስተዳደር እንዴት በደረጃ-በደረጃ ሂደት ሊመሠረት እንደሚችል በግልጽ አስቀምጧል።

    የመፍትሄ ሀሳቦቹ በኢትዮጵያ ሕገ-መንግሥት ማዕቀፍ ውስጥ የተቀረፁ ሲሆን የለውጡ ሂደት ስህተቶችና የገዢው ፓርቲ ባህሪይ፣ አሁን ያሉ የአለመረጋጋትና የፀጥታ ጉዳዮች፣ እና የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን ግምት ውስጥ ያስገባ ነው። በአጠቃላይ የለውጥ ሥርዓቱን ተግዳሮቶች በሁለቱም አቅጣጫዎች (ገዢው ፓርቲ እና ተቃዋሚዎች) በመተንተን በገዢው ፓርቲና በተቃዋሚ ቡድኖች በጋራ የሚተገበር ተግባራዊ የመፍትሔ ምክረ-ሀሳብ አቅርበናል።

    የቀረቡት ሀሳቦች ሌሎች የፖለቲካ ፓርቲዎች እንዲሳተፉ የሚያስችላቸው አስገዳጅ የፖለቲካ ኮንቬንሽን እንዲኖርና እውነተኛ ዴሞክራሲን ለመገንባትና በሀገሪቱ ውስጥ ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን ለማድረግ የለውጡ ሂደት ትክክለኛ ቁጥጥርን ለማረጋገጥና ትብብሩና አባል ድርጅቶች እንዲሁም ሌሎች ኃይሎች ሁሉ የበኩላቸውን ሚና የሚጫወቱበትን የዜጎች ኑሮ መሻሻልን ያረጋግጣል።

    የታሰበው አስገዳጅ የፖለቲካ ኮንቬንሽን የሚከተሉትን ያካትታል፦

    1. የውጭ ግንኙነት ምክር ቤት፦ የሀገር ውስጥ አመኔታን ለማነሳሳት እና ዓለምአቀፍ ተቀባይነት እንዲያገኝ ለማድረግ
    2. የተቀናጀ ብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤት፦ በክልሎች ውስጥ የፀጥታ አደረጃጀቶችን ትግበራ ለመከታተል
    3. የዴሞክራሲ ግንባታ ተቋም፦ አስፈፃሚዎችን ተጠያቂ ሊያደርጉ የሚችሉ ገለልተኛ የፍትህ አካላት፣ የምርጫ ቦርድና ነጻ ሚዲያ ራስን ማስተዳደርና ስልጣንን ለመጠበቅ
    4. ከፍተኛ የፖለቲካ ችግሮችን ለመፍታት ብሔራዊ የጋራ መግባባት እንዲፈጠር መንግሥት ግንባታና በሀገር ግንባታ መካከል ያሉ አለመግባባቶችንና ልዩነቶችን የሚፈታ አካል
    5. ማንኛውንም ለምርጫው የሚደረግ ሌላ የጊዜ ማራዘሚያ ጥያቄን ለመገደብና አመቺውን የምርጫ ቀን ለማስቀመጥ የኮንቬንሽኑን አፈፃፀም የሚከታተል አካል

    በተጨማሪም እነዚህ አካላት የሚሠሩበትን የኃላፊነት፣ የሥርዓትና የአሠራር ዘዴ ዝርዝርን ጨምሮ የመፍትሔ ምክረ-ሀሳቦቹን ተግባራዊነት አመልክተናል። እነዚህን የመፍትሔ ሀሳቦች ተግባራዊ ማድረጉ ዴሞክራሲን ለመገንባትና በሀገሪቱ ውስጥ ዘላቂ ሰላም ለመፍጠር ይረዳል ብለን እናምናለን። ከዚህም ሌላ በክልላዊ መንግሥታት መካከል ያለውን የፀጥታ ጉዳዮች እንዲሁም በመንግሥትና በተቃዋሚ ፓርቲዎች መካከል እና በተቃዋሚዎች እርስ በርሳቸው መካከል ያሉ ልዩነቶችን እንዲሁም “በመንግሥት ግንባታ” እና “በሀገር ግንባታ” ላይ ተቃራኒ አቋም ላላቸው ጉዳዮችም መፍትሄ ያቀርባል።

    ስለሆነም በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ የተስፋፉ ቀውሶችን ይፈታል ብለን ስለምናምን የኢትዮጵያ መንግሥት እነዚህን የመፍትሄ ምክረ-ሀሳቦች እንደገና እንዲያጤን በጥብቅ እናሳስባለን። እንዲሁም ባለድርሻ አካላት ኃላፊነታቸውን የሚወጡ ከሆነ በእውነተኛ ዴሞክራሲያዊ ሂደት ውስጥ የበኩላችንን ለመወጣት ፈቃደኛ መሆናችንን በድጋሚ ለመግለጽ እንወዳለን።

    በዚህ አጋጣሚ ዓለምአቀፍ ማኅበረሰብ ኢትዮጵያን ከሕገ-መንግሥታዊ ቀውሶች እና ከጠቅላላው ትርምስ ለመታደግ ጠንካራ እርምጃ እንዲወስድ ጥሪ እናቀርባለን።

    በተለይም የአፍሪካ ሕብረትየተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አካላት፣ የአውሮፓ ሕብረት እና ሌሎችም ዓለምአቀፍ ማኅበረሰብ የኢትዮጵያ መንግሥት ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር ድርድር እንዲያደርግ እና ነፃና ፍትሃዊ ምርጫን የሚያዘጋጅና ተግባራዊ የሚያደርግ በሥልጣን መጋሪያ የሽግግር መንግሥት አማካይነት ሁሉን አካታች የዴሞክራሲ ፍኖተ-ካርታ በጋራ እንዲያስቀምጥ እንዲያሳስቡ አጥብቀን እንጠይቃለን።

    የአፍሪካን ሰላምና ፀጥታ ለማስጠበቅ በብዙ የአፍሪካ አገራት ግጭትን ለመከላከል እና መፍትሄ ለማምጣት ውይይትን ማዕከል ያደረገ አቀራረብን በመምራት እና በማስተዋወቅ የአፍሪካ ሕብረት እየተጫወተ ያለውን ሚና እናደንቃለን። አሁን በኢትዮጵያ ውስጥ ያለው ቀውስ ከማንኛውም አካል የበለጠ የአፍሪካ ሕብረትን የላቀ ትኩረት ይጠይቃል ብለን እናምናለን። በአፍሪካ ሕብረት አዋጅ አንቀጽ 4 (ሸ) መሠረት ህብረቱ ከባድ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን ለመከላከል በአባል ሀገር ውስጥ ጣልቃ የመግባት መብት አለው።

    ብሔራዊ እና ዓለምአቀፉ ማስረጃዎች የኢትዮጵያ ሥርዓት ቀጣይነት ያለው የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን ላለፉት 27 ዓመታት በሀገሪቱ ዜጎች ላይ መፈጸሙንና ባለፉት ሁለት ዓመታትም ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ እንደተፈፀመ በግልጽ ያሳያሉ። በተጨማሪም በአብዛኛዎቹ የክልል መንግሥታት አጠቃላይ አስተዳደርን አደጋ ላይ የሚጥሉና በመላ ሀገሪቱ የፀጥታ ቀውስ የሚያመጡ የተደራጁ እና ጠንካራ የታጠቁ ኃይሎች አሉ። አሁን ካሉት ቀውሶች እና በፍጥነት ከሚጓዙ እምቅ ግጭቶች እና ስጋቶች አንጻር የአፍሪካ ሕብረት በአፋጣኝ ጣልቃ ገብቶ ኃላፊነቱን መወጣት አለበት።

    አሁን በኢትዮጵያ ያለው ሁኔታ በአፍሪካ ሁለተኛዋን ትልቅ ሀገር መበታተን ብቻ ሳይሆን “ሰላማዊና የተረጋጋች አፍሪካን” የሚመኝ አጀንዳ 2063 የተባለውን የአፍሪካ ሕብረት ምኞት 4 (Aspiration 4) ለማሳካት ካሉ ዋና እንቅፋቶች መካከል አንዱ መሆኑን ማሳሰብ እንወዳለን። በተጨማሪም ፊንፊኔ (አዲስ አበባ) የኢ.ፌ.ዲ.ሪ መቀመጫ፣ የኦሮሚያ ዋና ከተማና የአፍሪካ ሕብረት ዋና መሥሪያ ቤት በመሆኗ የአፍሪካ ሕብረት ጽሕፈት ቤትና እዚያ የሚሠሩ ከ2000 በላይ ሠራተኞች ደህንነት አሁን በኢትዮጵያ በተለይም በኦሮሚያ ካለው የሰላም የአለመረጋጋት ጉዳዮች ጋር ከግምት ውስጥ መግባት አለበት።

    የተባበሩት መንግሥታት በዓለም ላይ የሚከሰቱ ቀውሶችን በማስወገድ ረገድ የተጫወተውን ሚና የምንገነዘብ ሲሆን፥ የተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት (UNSC)፣ የተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (UNHRC) እና ሌሎችም በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ የሚከሰቱ ቀውሶችን ለማስወገድ የድርሻቸውን እንዲወጡ እንጠይቃለን። በተለይም በዓለምአቀፍ ደረጃ ሰላምንና ፀጥታን ለማስጠበቅ በተባበሩት መንግሥታት ቻርተር መሠረት ቀዳሚ ኃላፊነት ያለው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት በአፍሪካ ካሉ ትልልቅ ሀገሮች ሁለተኛ የሆነችዋ ኢትዮጵያ የፖለቲካ፣ ማኅበራዊ፣ ሰብዓዊ መብቶች እና ኢኮኖሚያዊ ቀውሶች ሲያጋጥሟትና ወደ ውድቀት ስታመራ ጆሮ ዳባ ብሎ ማለፍ የለበትም።

    የአውሮፓ ሕብረት ብሔራዊ የለውጥ አጀንዳውን ለመደገፍና ከኢትዮጵያ ጋር ልዩ ልዩ የልማት ትብብሮችን በመፍጠር በኢትዮጵያ ኢኮኖሚያዊ ውህደት፣ ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን እየተጫወተ ያለውን የመሪነት ሚና እናደንቃለን። ሆኖም እ.ኤ.አ. በ2018 የተጀመረው የፖለቲካ ለውጥ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በአግባቡ ባለመመራቱ ግዙፍ ፈተናዎች ገጥሞት ወድቋል። ይህም የአውሮፓ ሕብረት ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን አጋርነትና ሕብረት ለኢትዮጵያ ያለውን ሁሉንም ምኞት ይገታል። ስለዚህ የአውሮፓ ሕብረት በቀጠናው ያሉ ቁልፍ አጋሮቹ ያጋጠማቸውን የፖለቲካ ቀውሶችን ለማስቀረት ባለው አቅም ጣልቃ እንደሚገባ እናምናለን።

    ስለሆነም፦

    1. በአፍሪካ ሕብረት በአንቀጽ 4 (ሸ) /Article 4(h)/ እና በሌሎች የሕብረቱ ደጋፊ አንቀጾች ላይ በተቀመጠው መብቱ ላይ በመመሥረት በኢትዮጵያ ቀውሶች ውስጥ ጣልቃ እንዲገባ ጥሪ እናቀርባለን።
    2. በኢትዮጵያ የሰላምና ደህንነት አደጋዎች በግልጽ የሚታዩ በመሆናቸው የጸጥታው ምክር ቤት በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አንቀፅ 39 እና 41 ላይ በተመለከቱት ግዴታዎች መሠረት ተገቢ እርምጃዎችን እንዲወስድ ጥሪ እናስተላልፋለን። የመንግሥታቱ ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ጉባዔም (UNHRC) በኢትዮጵያ የተፈጸሙ ከባድ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን ለመቅረፍ በዚሁ መሠረት እርምጃ እንዲወስድ እንጠይቃለን።
    3. ይህ የመቶ ዓ መት ግዙፍ ግጭትና በአፍሪካ ቀንድ ሰላምና መረጋጋት ላይ የጎላ ጉዳት ስለሚያስከትልና የአውሮፓ ሀገራትና የኢትዮጵያን ዲፕሎማሲያዊ እና የልማት አጋርነት የሚነካ በመሆኑ የአውሮፓ ሕብረት በኢትዮጵያ በተለይም በኦሮሚያ ለተፈጠረው አለመረጋጋት ከፍተኛ ትኩረት እንዲሰጥ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን።
    4. በኢትዮጵያ ያሉ ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች ያቀረብነውን የመፍትሄ ሀሳብ በቁም ነገር በመመልከት እየተቃረበ ያለውን አስከፊ ቀውስ ለማስቀረት ከእኛ ጋር እንዲሠሩ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን።

    ገለልተኛ የኦሮሞ የፖለቲካ ኃይሎችና መላው ኦሮሞ ሕዝብ ማንኛውንም ዓይነት የፖለቲካና የፀጥታ ችግር ለማስወገድ ለኦሮሚያ የሽግግር መንግሥት እንዲዘጋጁ ጥሪ እያቀረበ፥ የኦሮሞ ነፃነት ግንባር በዚህ አቋም ላይ ባለድርሻ አካላትን በሁለቱም የመንግሥት ደረጃዎች ማማከሩ እንደሚቀጥል ያሳውቃል።

    ድል ለሰፊው ሕዝብ!
    የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)
    ፊንፊኔ
    መስከረም 13፥ 2020

    የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ)

    #15839
    Anonymous
    Inactive

    በብሔራዊ መግባባት ዙሪያ ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ (ነእፓ) ጥናታዊ ጽሁፍ አቀረበ

    አዲስ አበባ (ነእፓ) – በኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት አስተባባሪነት በሀገራችን ብሔራዊ መግባባት በመፍጠር ሰላምና መረጋጋት እንዲሁም ዴሞክራሲያዊ ሽግግር እውን ለማድረግ በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል የመጀመሪያ ዙር ውይይት ነሐሴ 16 ቀን 2012 ዓ.ም መካሄዱ ይታወሳል። የዚሁ መድረክ ሁለተኛ ዙር ውይይት ነሐሴ 30 2012 ዓ.ም በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (ECA) ተካሂዷል።

    በውይይቱ ላይ በከፍተኛ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች አራት የተለያዩ ጽሁፎች የቀረቡ ሲሆን፥ የነጻነትና እኩልነት ፓርቲ (ነእፓ) ሊቀመንበር ዶ/ር አብዱልቃድ አደም “ብሔራዊ መግባባት በኢትዮጵያ፡ ዘላቂ ሰላም፣ ሀገራዊ አንድነት እና ዴሞክራሲያዊ ሽግግር” በሚል ርዕስ ጥናታዊ ጽሁፍ አቅርበዋል።

    ዶ/ር አብዱልቃድር የብሔራዊ መግባባት ምንነት፣ አጠቃላይ ማዕቀፍ፣ አደረጃጀት፣ ዓለም አቀፍ ተሞክሮ እና ሌሎች ከብሔራዊ መግባባት ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን በዝርዝር ያቀረቡ ሲሆን ብሔራዊ መግባባትን አስመልክቶ የፖለቲካ ፓርቲዎች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ግልጽ እና ተቀራራቢ አቋም እንዲኖራቸው ለማድረግ እንዲሁም ብሔራዊ መግባባትን አስመልክቱ የተሳሳቱ ግንዛቤዎችን ለማስተካካል ጥናታዊ ጽሁፉ ከፍተኛ ፋይዳ እንደነበረው በውይይቱ የተሳተፉ የፖለተካ ፓርቲዎች ገልጸዋል።

    የቀረበው ወረቀት (ጥናታዊ ጽሑፍ) በሀገራችን በቅርቡ ይጀመራል ተብሎ በሚጠበቀው ሁሉን አቀፍ የብሔራዊ መግባባት ሂደት ላይ ከፍተኛ አስተዋጽዖ እንደሚኖረው ይታመናል።

    ነእፓ ቀደም ሲል በሀገራችን በብሔራዊ መግባባት ዙሪያ የመነሻ ጽሁፍ  በማዘጋጀት ሀሳቡን ለመንግስት፣ ለፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ለሲቪክ ማኅበራትና በኢትዮጵያ ለሚገኙ የውጪ ሀገር የዲፕሎማቲክ ማኅበረሰብ ማሰራጨቱ ይታወሳል።

    ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ በሀገራችን ሰላም፣ መረጋጋትና አንድነት እንዲሰፍን፣ ቀጣዩ ምርጫ ነጻ ፍትሀዊ እና ቅቡል እንዲሆን ሁሉን አቀፍ የብሔራዊ መግባባት ሂደት በአፋጣኝ መካሄድ እንዳለበት በጽኑ ያምናል። ይህንኑ እውን ለማድረግ ፓርቲው የጀመረውን ጥረት ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን አጠናክሮ ይቀጥላል።

    በመድረኩ የቀረበውን ጽሁፍ እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን ማግኘት ይቻላል።

    ምንጭ፦ ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ (ነእፓ)

    ተመሳሳይ ዜናዎች

    ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ

    #15904
    Anonymous
    Inactive

    የሀገር ሰላምና መረጋጋት፣ የዜጎች ሰብዓዊ-መብትና ክብር ከሁሉም ይቀድማል፤ ብሔራዊ መግባባት እና ውይይት በአስቸኳይ!
    ከአብሮነት ለኢትዮጵያ ፌዴራላዊ አንድነት (አብሮነት) የተሰጠ መግለጫ

    በቅድሚያ ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ እንኳን ለ2013 ዓ.ም አዲስ ዓመት በሰላም አደረሳችሁ በማለት መልካም ምኞቱን ይገልፃል። አዲሱ ዓመት የሰላም፣ የጤና፣ የፍቅር፣ የመተሳሰብ፣ የመከባበር፣ የመግባባት፣ የሀገራችንን ዘርፈ ብዙ ችግሮች በመወያየት፣ በመነጋገርና በእርቅ የምንፈታበት ዘመን እንዲሆንልን ይመኛል።

    አብሮነት ላለፉት 27 ዓመታት በሀገራችን ተንሰራፍቶ የነበረው የህወሓት/ኢህአዴግ አፋኝ አገዛዝ ሥርዓት “የለውጥ ኃይል” በሚባለው የብልጽግና የሪፎርም አካሄድ ከተተካ ባለፍነው ሁለት ዓመት ከግማሽ ያህል ጊዜ የሀገራችንን አጠቃላይ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ሁኔታዎች፥ በአጠቃላይ ወቅታዊ ጉዳዮችን በተለይ በአዲሱ ዓመት መባቻ ገምግሟል።

    በአጠቃላይ የሀገራችን ተጨባጭ ሁኔታ ግምገማው አብሮነት የሀገራችን ሕዝብ በሪፎርሙ ጅማሬ የተገባውን ቃል እና የፈነጠቀውን የፖለቲካ ምህዳር መሻሻል ተከትሎ የቋጠረው ተስፋ፣ ያሳደረው እምነት በጊዜ ውስጥ እየሟሸሸ፣ በሀገሪቱ የሚታየው ሁኔታ ከቁጥጥር ውጪ እየሆነ “የሽግግሩ መንግሥት” የሀገሪቱ ፍኖተ-ካርታ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ በበዓለ ሲመታቸው ያደረጉት ንግግር ነው ከተባለው ጋር በከፋ ተቃርኖ ውስጥ ገብቷል። የሕግ የበላይነትን አክብሮ ስለማስከበር፣ የዜጎች ሀሳብን በነፃ መግለጽና መቀበል መብት፣ “አሸባሪዎች እኛ ነን” በማለት ይቅርታ ጠይቀው የሽብር ሕጉን ያወገዙበትና በዚህ ሕግ የታሰሩ ፍርደኞች የተፈቱበት፣ የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋት የፖለቲካ ፓርቲዎችን ተሳትፎ ያበረታቱበት፣ የሰብዓዊ መብት መከበር ለጥያቄ የሚቀርብ አይሆንም የተባለበት… ሌሎች አዎንታዊ ቃል-ኪዳኖች በፈጣን ሁኔታ ተቀልብሰው [ቀድሞ] ወደ ነበርንበት፣ ሲያልፍም ከድጡ ወደ ማጡ ሊያስብል በሚችል ወደ ከፋ ደረጃ መድረሳችንን ተረድቷል።

    በሀገሪቱ ወቅታዊ ሁኔታ የሚታየው ሁለንተናዊ ምስቅልቅል፣ ያጋጠሙን ፈተናዎች ከውስጥም ከውጪም እየገዘፉ፣ እየሰፉና እየተወሳሰቡ መጥተው ከመንግሥት የቁጥጥር አቅም በላይ በመሆናቸው ችግሮቹን የብልጽግና መንግሥት በተናጠል ሊሸከማቸውም ሆነ ሊያስተካክላቸው ከሚቻለው በላይ ሆነዋል፤ መፍትሄውም አብሮነት ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ ሲያቀነቅነው የነበረው “በሁሉን-አቀፍ የብሔራዊ መግባባት ውይይት ሕገ-መንግሥታዊና መዋቅራዊ ለውጥ የሚመጣበትን ሥርዓት የመዘርጋት ፖለቲካ መፍትሄ እንጂ በምርጫም ሆነ ሌላ ከብልጽግና ብቻ በሚቀርብ መፍትሄ አያገኝም። ከአማራጭ መፍትሄዎች አንዱ የሽግግርና እርቅ መንግሥት ነው” የሚለው አቋሙ ትክክልና ዛሬ የበለጠ ግልጽ መሆኑን አረጋግጧል።

    በመሆኑም አብሮነት ሰላማዊ ትግሉን አጠናክሮ የመቀጠል ዓላማና ተልዕኮውን አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትና ለዚህም ግንኙነቱን በማጽናት፣ ማጠናከርና በማስፋት ለመሥራት ቃልኪዳኑን አድሷል። ወደ ወቅታዊ ሁኔታዎች ስንገባ አብሮነት የፖለቲካ ፓርቲዎችን እንቅስቃሴና የፖለቲካ እስረኞችን፣ የሀገራችን ቀጣይ ምርጫና የትግራይ ምርጫ፣ በአዲስ አበባ የሚፈጸመውን ዘርፈ ብዙ ሕገ-ወጥ ተግባራት፣ የኮቪድ-19 ወረርሽኝ እና በሀገራችን በጎርፍና በዜጎች ላይ በሚፈጸም ጥቃት እየደረሰ ያለውን አደጋ፣ የሚመለከቱ ጉዳዮችን ገምግመናል።

    የፖለቲካ ፓርቲዎችን እንቅስቃሴ በሚመለከት፥ ከጅምሩ ታይቶ የነበረው የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች በሕጋዊና ሰላማዊ መንገድ ተደራጅተው እንዲንቀሳቀሱ የማበረታታት አካሄድ ተቀልብሶ ፓርቲዎች በሕጋዊ መንገድ በነፃነት ተንቀሳቅሰው ብቃት ያላቸው ተፎካካሪ ሆነው ለዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ የሚያደርጉት አስተዋጽኦ በሕግ ማስከበር ስም በገዢው ፓርቲ እንዲገደብ ተደርጓል።

    ለዚህም እንደቅድመ 2010 ከገዢው ፓርቲ በሀሳብ የሚለዩትን፣ የሚተቹና የሚቃወሙትን፣ በገዢ ፓርቲውና መንግሥት ባለሥልጣናት በተጨባጭ የሚፈጸሙ ሕገ-ወጥ ተግባራት እንዲቆሙ፣ እንዲስተካከሉና አጥፊዎች በሕግ እንዲጠየቁ የሚጠይቁትን፣ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችንና አባላት በፈጠራ ውንጀላ ማሰርና ማሰቃየት፣ ትናንት ከተወገዘው ባልተናነሰ፥ እንዲያውም በከፋ ሁኔታ እየተፈጸሙ ነው። በዚህም ከሰላማዊ ታጋይነታቸው ውጪ የማይታሙት የአብሮነት ከፍተኛ አመራሮች በፈጠራ ውንጀላ ለእሥራትና ሥቃይ ተዳርገዋል።

    በፖለቲካ ሀሳብ ጥራታቸውና ነገሮችን አስቀድመው አርቀው በማስተዋላቸው የሚታወቁት ኢ/ር ይልቃል ጌትነት ያለምንም ማስረጃ ተሰቃይተው በነፃ ተለቀዋል፤ ትናንት የብልጽግና ፓርቲ አባል እንዲሆኑ ተጠይቀው ያልተቀበሉት የሰላማዊ አማራጭ መፍትሄ ሀሳብ አፍላቂ እውቁ ፖለቲከኛ አቶ ልደቱ አያሌው በተጠረጠሩበት ወንጀል ፖሊስ ማስረጃ ሊያቀርብ ባለመቻሉ ነፃ መሆናቸው በፍርድ ቤት ቢረጋገጥም ለህይወታቸው አስጊ የልብ ህመምተኛ በመሆናቸው የቅርብ የሐኪም ክትትል እንደሚያስፈልጋቸው ማስረጃ አቅርበውም የፍትህ ሥርዓቱን ግምት ላይ በጣለ፣ ሰብዓዊነትን በረገጠ አሳፋሪ ሁኔታ ዛሬም በከፍተኛ ስቃይ ውስጥ ይገኛሉ። አዲስ አበባ ውስጥ በማስረጃ አስደግፎ እንዲያቆም ችግሩን አደባባይ ያወጣው፣ በቀዳሚነት የታገለው የባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ሊቀ-መንበሩን ጨምሮ ከፍተኛ አመራሮችም የዚሁ ፈጠራ ወንጀል ሰለባ ከመሆን አልፈው በተወገዘው “የፀረ-ሽብር ሕግ” እንዲከሰሱ ተበይኖባቸዋል። በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ከፖለቲካ አመለካከታቸውና አቋማቸው ጋር በተያያዘ ጉዳይ ክስ ሳይመሠረትባቸው፣ በትምህርት ቤቶች ጭምር ታስረው ይገኛሉ የሚሉ መረጃዎች በስፋት ይቀርባሉ።

    አብሮነት ኮሮና ቫይረስ /ኮቪድ-19 ወረርሽኝ ከመከሰቱ አስቀድሞም “የሀገራችን ነባራዊና ወቅታዊ ሁኔታ በሀገራችን ነፃ፣ ዲሞክራሲያዊና ፍትሃዊ ምርጫ ማካሄድ አያስችልም፤ ምርጫ ቢደረግ የሀገሪቱን ችግሮች ከሚያባብስ በቀር መፍትሄ አይሆንም፤ ያሳለፍናቸው ተደጋጋሚ ምርጫዎች ለውስብስብ ችግራችን መፍትሄ አላመጡም፤ በቀጣይም ምርጫ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ቢደረግ ለውጥ አያመጣም፤ ለሀገራችን ዘላቂና አስተማማኝ መፍትሄው ሕገ-መንግሥታዊና መዋቅራዊ ለውጥ ነው፤ ይህ ፖለቲካዊ መፍትሄ ማለት ሁሉን አቀፍ የብሔራዊ መግባባት ውይይት ነው” የሚል ግልጽ አቋም መውሰዱ ይታወቃል። ይህንን አቋም የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ መከሰት አግዞት ሀገራዊ ምርጫው እንዲራዘም ተደርጓል። ይሁን እንጂ ብዙ ፓርቲዎች የእኛን የብሔራዊ መግባባት ውይይት መፍትሄ ሀሳብ ቢቀበሉትም ገዢው የብልጽግና ፓርቲ/መንግሥት ባለመቀበላቸው መንግሥት ዕድሜውን በሕገ- መንግሥት ትርጉም ስም ላልተወሰነ ጊዜ ሲያራዝም፣ ህወሓት ደግሞ ሕገ-መንግሥትን ማክበር በሚል የብሔራዊ ምርጫ ቦርድየፌደሬሽን ምክር ቤትም ሆነ አስፈጻሚው እንዳይደረግ ቢወስኑም፣ ቢያሳስቡም፤ እምቢኝ በማለት ምርጫ በክልሉ አካሂዷል። ለዚህ ችግር ምላሽ ይሆናል፣ የውጥረቱን ጊዜ ያሳጥራል በሚል ይመስላል መንግሥት ከሰሞኑ ምርጫው በዚህ ዓመት ይደረጋል ሲል እየሰማን ነው፤ አንዳንድ እንቅስቃሴዎችም እየታዘብን ነው።

    አብሮነት መንግሥት በሕገ- መንግሥት ሥም ዕድሜውን ያለገደብ ማራዘሙም ሆነ ህወሓት /የትግራይ ክልል መንግሥት ያቀረብነውን የብሔራዊ መግባባት ውይይት ቢቀበልም፥ ተግባራዊ ለማድረግ ከመታገል ይልቅ የተናጠል ምርጫ ማድረጉ ትክክል አይደለም፤ የሁለቱም – ብልጽግና እና ህወሓት – የእልህ አካሄድ የሀገሪቱን ፖለቲካ ወደ ከፋ ውጥረት ከማሸጋገር ያለፈ ሰላማዊና ዘላቂ አስተማማኝ መፍትሄ ሊያመጡ አይችሉም ብሎ ያምናል።

    የሀገራችንና የአፍሪካ ዋና ከተማ በሆነችው አዲስ አበባ የሚፈጸሙት ዘርፈ-ብዙ ሕገ-ወጥ ተግባራት ካለፈው ጥፋት በቀጠለ ስህተት እና በዕውቀትና የፖለቲካ ዓላማ መሠረት አድርጎ በተነደፈ ስልት በስፋት እየተካሄደ ነው። በተለይ የመሬት ወረራና የኮንድሚኒየም ቤቶች ዝርፊያ ጎልተው ከወጡና አደባባይ ከዋሉ በርካታ ወራት ተቆጥረዋል። ዛሬ አቤቱታ አቅራቢዎች ቢበራከቱም የመጀመሪያው በማስረጃ የተደገፈ አቤቱታ አቅራቢዎች – የባልደራስ አመራሮች – ዛሬ ወህኒ ተጥለዋል። ችግሩ መፍትሄ አላገኘም፤ ጥያቄዎች አልተመለሱም፤ በቀረቡት ማስረጃዎች መሠረት የከንቲባ ሹም ሽር ከመደረግ ያለፈ አጥፊዎች ለሕግ አልቀረቡም፤ በቀጣይም ይህን ለማስተካከል ቁርጠኝነት ስለመኖሩ አመላካች እርምጃዎች አልታዩም፤ ይልቁንም በነበረው መሠረት ለማስቀጠልና “‹በከተማዋ የባለቤትነት ጥያቄ” ላይ የሚደረገው ሽኩቻ ሲባባስ እንጂ ለማስቆም የሚደረግ ጥረት አልተስተዋለም። በመሆኑም ችግሩ ወደ ከፋ ደረጃ እንዳያድግና በፍጥነት እንዳይስፋፋ፥ ብሎም ጥፋትና ስርቆቱን እንዳያባብስ አብሮነት ሥጋት ገብቶታል። አፋጣኝ ሕጋዊ የእርምት እርምጃ በመውሰድ የሕግ የበላይነት ማስከበር፣ ከተማይቱንም በግልጽ የአስተዳደራዊ ባለቤት ለሆኑት ነዋሪዎቿ ማስረከብ እንደሚያስፈልግ በጽናት ያምናል።

    የኮቪድ-19/ኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በሚመለከት በተለይ ከወረርሽኙ መከሰትጋርተያይዞ ተጥሎ የነበረው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መነሳትን ተከትሎ በሕብረተሰቡ ላይ እየታየ ያለው መዘናጋት አብሮነትን አሳስቦታል። መንግሥት በአዋጁ መነሳት ሕብረተሰቡ እንዳይዘናጋ በቂ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎችን መሥራት ባለመቻሉ ሕብረተሰቡ ወረርሽኙ የለም የተባለ ይመስል ከፍተኛ መዘናጋት ውስጥ ገብቷል። ሕብረተሰቡ የበሽታው መከላከያ የሆኑትን እርምጃዎች ሁሉ በመተው እራሱን ለበሽታው በሚያጋልጡ እንቅስቃሴዎች ውስጥ በማስገባቱ በሽታው የበለጠ እንዳይስፋፋ አብሮነትን አስግቶታል። በመሆኑም መንግሥትም ሆነ ሕብረተሰቡ የወረርሽኙን አደገኛነት በመገንዘብ ለበሽታው የሚመጥን ጥንቃቄ እንዲያደርጉ በአንክሮ ያሳስባል።

    በሀገራችን በጎርፍ እየደረሰ ያለውን አደጋ፣ በተለያዩ የሀገራችን ክልሎች/አካባቢዎች ከመጠን በላይ በጣለው ዝናብ የአዋሽ ወንዝ፣ የኦሞ ወንዝ፣ የባሮ ወንዝ፣ የአባይ ገባር ወንዞች ከመሙላታቸው በተጨማሪ ከግድቦች በተለቀቀ ውሃ ከ580,000 በላይ ዜጎች ለጉዳት ተዳርገዋል፤ ከዚህ ውስጥ ግማሽ ያህሉ ተፈናቅለዋል። በሌላ በኩል በተለያዩ አካባቢዎች (ኦሮሚያ ክልል፣ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል፣ ደቡብ ክልል/ኮንሶ…) በዜጎች ላይ ጥቃት እየተፈጸመ ነው፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በአሰቃቂ መንገድ እየተገደሉና በሺዎች ህይወታቸውን ለማትረፍ ከቀዬአቸው እየተፈናቀሉ ነው። በመንግሥት በኩል ለመከላከል በቂ ዝግጅት፣ አደጋው ከደረሰም በኋላ በቂ ክትትልና ድጋፍ ያለመደረጉን፣ እንዲሁም በቀጣይ ሊደርሱ ለሚችሉ አደጋዎች በቂ የመከላከል ዝግጅት እየተደረገ ያለመሆኑን፣ ከአካባቢው የሚደርሱን መረጃዎች ያመለክታሉ። በሌላ በኩል የሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር በዚህ ልክ በሀገራችን በደረሰው አደጋና ጉዳት ምንም ሳይሉ በጎረቤት ሀገር ሱዳን በደረሰው ሀዘናቸውን ገልጸዋል፣ እንዳይቀጥልም ከጎናቸው እንደሚቆሙ ቃል ገብተዋል። ዜጎች በማያውቁት በተፈጸመባቸው ጥቃት ለሞት ተዳርገዋል፤ እየተዳረጉም ነው። በተረፉት ዜጎቻችን የደረሰው አደጋን ተከትሎ የሚመጣው የጤናና ምግብ ችግር፣ እንዲሁም ሊደርስ የሚችለው አደጋ በአንድ በኩል፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ዝምታና “የራሷ እያረረባት፣ የሰው ታማስላለች” አካሄድ በሌላው፣ በእጅጉ ያሳስበናል። ስለዚህ መንግሥት በራሱ እና ሕዝቡንና ዓለምአቀፍ ማኅበረሰቡን በማስተባበር በአፋጣኝ እንዲደርስላቸው ያስፈልጋል።

    በመጨረሻ ገዢው ፓርቲ /መንግሥት በአፈናና የሸፍጥ ፖለቲካ በተመሳሳይ መንገድ እየተጓዘ በፕሮፖጋንዳና ባዶ የተስፋ ቃላት ጋጋታ ፣ የተለየ ውጤትም ሆነ ችግሮቻችን መፍታት እንደማይችል በተደጋጋሚ ተመልክተናል። ስለዚህ አብሮነት ችግሮቻችንን በአስተማማኝና ዘላቂ መንገድ ለመፍታት፣ ሃቀኛ የብሔራዊ መግባባት ውይይት ለነገ የማይባል ተግባር እንደሆነ ያምናል፤ ገዢው ፓርቲ ለዚህ ያለውን ከፍተኛ ኃላፊነት እንዲወጣ በአጽንኦት ጥሪ ያደርጋል።

    ለዚህ እንዲረዳም፡-

    1ኛ/ በፖለቲካ አመለካከታቸው ከገዢው ፓርቲ በመለየታቸውና በሀገሪቱ ለሚታዩት ችግሮችና በሕዝብና ሀገር ሀብት ላይ እየደረሰ ያለውን በደል በማስረጃ አስደግፈው ተቃውሞ በማሰማታቸውና ጥያቄ በማቅረባቸው ብቻ የታሰሩ የፖለቲካና የኅሊና እስረኞች በአስቸኳይ እንዲፈቱ፤

    2ኛ/ ለ27 ዓመታት አንድ ሆነው ሕዝባችን ሲያሰቃዩ የነበሩትና ዛሬ በሥልጣን ጥያቄና ያለፈውን በማስቀጠል ስልት ላይ ባለመስማማታቸው በተለያዩት በህወሓት እና በብልጽግና ፓርቲዎች መካካል ትናንትም ሆነ ዛሬ በሚደፈጥጡት ሕገ-መንግሥትና አምስት ጊዜ ባጭበረበሩት ምርጫ ሥም የሚታየው መካረርና ፍጥጫ በአስቸኳይ ተገትቶ፥ ለብሔራዊ መግባባት ውይይት ችግሮቻቸው እንዲፈታ የፖለቲካ ቁርጠኝነታቸውን እንዲያረጋግጡ፤

    3ኛ/ የሀገራችን ችግሮች ምንጭ ምርጫ ባለመሆኑ፥ በምርጫም የሚፈቱ ያለመሆናቸው ባለፉት አምስት ምርጫዎች በመረጋገጡ፥ ለሕገ-መንግሥታዊና መዋቅራዊ የፖለቲካ መፍትሄ ምርጫ ለማድረግ የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችም ሆነ እንዲደረግ የሚደረጉ ግፊቶች በአስቸኳይ ቆመው ሁሉንም ወገኖች የሚያሳትፍ የውይይት መድረክ እንዲመቻች ለዚህም ሁሉም ዜጋ አስፈላጊውን ተፅዕኖ በመንግሥት ላይ እንዲያሳርፍ፤

    4ኛ/ መንግሥትም ሆነ ሕብረተሰቡ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን በመከላከል ረገድ እያሳዩ ያሉትን ቸልተኝነት በማቆም አስፈላጊውን የመከላከል ጥንቃቄና የመለየት ምርመራ እንዲያደርጉ፣ ለተጠቂዎች አገልግሎት ማቅረቡንና የግንዛቤ ማሳደግ ተግባራት በስፋት እንዲያከናውኑ፤

    5ኛ/ በሀገራችን በተፈጥሮና ሰው-ሠራሽ ምክንያት ጎርፍ እያደረሰ ላለው ከፍተኛ አደጋ መንግሥት “የራሷ እያረረባት የሰው ታማስላለች” ከሚያስብል አካሄድ ወጥቶ በዜጎች ህይወት፣ ሥቃይ፣ የንብረት ውድመትና ቀጣይ ህይወት ላይ ትኩረት እንዲያደርግ፤

    6ኛ/ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች እንደየቱም ክልል ነዋሪ የከተማቸው አስተዳዳራዊ ባለቤት መሆናቸው እንዲረጋገጥ፣ በከተማዋ የባለቤትነት መብት የሚደረገው በብልጽግና ውስጥ ጭምር የሚደረገው ሽኩቻ እንዲቆም፣ የተበዘበዘውና የተዘረፈው የከተማዋ ሀብት በሕግ ተመልሶ ለከተማዋ ልማት እንዲውል፣ አጥፊዎች ለሕግ እንዲቀርቡ፣ እንዲደረግ፤

    7ኛ/ በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች በዜጎች ላይ የደረሰው ጥቃት በገለልተኛ ወገን በአስቸኳይ እንዲጣራና ተገቢው ካሳ እንዲደረግላቸው፥ እንዲሁም አጥቂዎችና ተባባሪዎቻቸው በሕግ እንዲጠየቁ እንዲደረግ፣ ለጥቃቱ ሰለባዎች አስፈላጊው የዕለት ደራሽ ዕርዳታና የማቋቋሚያ ድጋፍ በአስቸኳይ እንዲደርሳቸው፤ ለዚህ ተፈጻሚነትም የፖለቲካ ፓርቲዎች ጅምሩ የብሔራዊ መግባባት ውይይት እንዳይነጠቅና በገዢው ፓርቲ እጅ እንዳይወድቅ፣ ከላይ ያቀረብናቸው እንዲፈጸሙ በልዩነታችን ውስጥ በሀገራዊ ጉዳዮች በቅድሚያ በሕግ የበላይነትን በማክበርና ማስከበር ለሰላምና መረጋጋት፣ ለሰብዓዊ መብት መከበር ተባብረን እንድንቆም ጥሪያችንን እናቀርባለን፤ ለተግባራዊነቱ ያለንን ቁርጠኝነት እናረጋግጣለን።

    ከአሳታፊ ሁሉን አቀፍ ሃቀኛ የብሔራዊ መግባባት ውይይት ውጪ የቱም አንድ ፓርቲና ከብሔራዊ መግባባት ውይይት በፊት የሚደረግ የይስሙላ ምርጫ ለሀገራችን ችግሮች ዘላቂና አስተማማኝ መፍትሄ አያመጣም።

    ከሁሉም በፊት መንግሥት የሕግ የበላይነት በማክበርና በማስከበር በሃቀኛ ሕዝባዊ ተሳትፎ የሀገራችን ሰላምና መረጋጋት፣ የዜጎችን የመኖር ሰብዓዊ መብት የማረጋገጥ ኃላፊነቱን ይወጣ፤ ከሥልጣኑ ይልቅ ለሀገርና ሕዝብ ጉዳይ ቅድሚያ ይስጥ።

    አብሮነት ለኢትዮጵያ ፌደራላዊ አንድነት (አብሮነት)
    መስከረም 07 ቀን 2013 ዓ.ም
    አዲስ አበባ

    ብሔራዊ መግባባት እና ውይይት

    #15946
    Anonymous
    Inactive

    በወቅታዊ ጉዳዮች ከአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) የተሰጠ መግለጫ

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ መስከረም 9 እና 10 ቀን 2013 ዓ.ም ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ ሕዝባችንን ባጋጠሙት ወቅታዊ ሰው ሠራሽና ተፈጥሯዊ አደጋዎች ላይ ተወያይቶ የሚከተሉትን ውሳኔዎች አሳልፏል።

    1] በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል በሕዝባችን ላይ የተፈፀመውን የዘር ጥቃት በተመለከተ፦

    አብን በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል በመተከል ዞን ቡለን ወረዳ ከጳጉሜን 1 ቀን 2012 ዓ.ም ጀምሮ ለተከታታይ ቀናት ማንነትን መሠረት አድርገው የተፈፀሙ ጥቃቶችን በተመለከተ ተጨባጭ መረጃዎችን ሲያሰባስብ ቆይቷል። በዚህም ከ160 በላይ ወገኖቻችን በአሰቃቂ ሁኔታ እንደተጨፈጨፉ ተገንዝቧል።

    የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል የአማራው ሕዝብ ጥንተ ርስቱን ተነጥቆ፣ ሰብዓዊና ዜግነታዊ መብቱ ተገፎ ለሦስት አስርት ዓመታት ለዝርፊያ፣ ለመፈናቀል እና ለተደጋጋሚ የዘር ፍጅት የተጋለጠበት ነው። በተለይም “ለውጥ” እየተባለ በሚጠራው ባለፉት ሁለት ዓመታት ጊዜ ውስጥ በክልሉ ውስጥ ባለው የአማራ ሕዝብ ላይ የሚደረገው የዘር ማጽዳትና ሰብዓዊ ጥቃት ከመቼውም ጊዜ በላይ ተባብሶ ቀጥሏል።

    ንቅናቄያችን ልክ ከሰኔ 22 እስከ 24 ቀን  2012 ዓ.ም በኦሮሚያ ክልል ውስጥ በአማራው ሕዝብ ላይ  የደረሰውን ጥቃት አስመልክቶ እንደገለገፀው ሁሉ በቤንሻንጉል ክልል የተፈፀመው ጥቃት ተራ የማኅበረሰቦች ግጭት ወይም የሽፍቶች ድርጊት ውጤት ሳይሆን በአማራ-ጠል ትርክት ላይ የተመሠረተ፣ ስልታዊ የሆነ እና በመንግሥታዊ መዋቅር ጭምር የተደገፈ የሽብርና የዘር ማጥፋት ድርጊት መሆኑን ያምናል።

    በዚህ አሰቃቂ ጥቃት የትህነግ ተቀጥላ የሆኑ በተለያዩ ደረጃዎች የሚገኙ የቤንሻንጉል ክልል መንግሥት ኃላፊዎችን ጨምሮ የአማራ ሕዝብንና የሀገሪቱን ሰላም ለማሳጣት የሚታትሩ ባዕዳንና ውስጣዊ ኃይሎች ያሰማሯቸው የሽብር ቡድኖች እጃቸው እንዳለበት አብን ያምናል።

    የጥቃቱ ፈፃሚዎች ለተከታታይ ቀናት ሕዝባችንን (አማራ/አገው) በማንነታቸው እየመረጡ በአካባቢው ባሉ ትምህርት ቤቶች ውስጥ በኃይል አሰባስበው ለጅምላ ጭፍጨፋ ሲያዘጋጁ የክልሉ መንግሥት መረጃ እና ጥሪ እየቀረበለት ባለመድረሱ፤ የፌዴራል መንግሥቱም ባለው የደኅንነት መረጃ ተመርኩዞ ጥቃቱን ለመከላከል ፈጥኖ እርምጃ ባለመውሰዱ ተጠያቂ መሆን እንዳለባቸው አብን በጥብቅ ያምናል።

    አብን በሕዝባችን ላይ ከእንግዲህ ማናቸውንም ዓይነት ማንነቱን መሠረት አድርገው የሚፈፀሙ ጥቃቶች ሊታገስ የማይችልበት ደረጃ መድረሱን እየገለፀ፤ ለችግሩ አስቸኳይ መፍትሄ ካልተበጀለት ጉዳዩ  ከአማራው አልፎ ታላቅ ብሔራዊ ቀውስ ሊያስከትል እንደሚችል በመገንዘብ፦

    (ሀ) መሣሪያ የታጠቁ ገዳዮችን በመደገፍና እንዳላዩ በማለፍ ለጥቃቱ መዋቅራዊ ከለላ የሰጡና በቀጥታም ሆነ በእጅ አዙር የዘር ማጥፋቱ ተባባሪ የሆኑ የክልሉ ባለሥልጣናት በአስቸኳይ በሕግ ተጠያቂ እንዲሆኑ፤

    (ለ) በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ለሚኖረው ሕዝባችን አስተማማኝ የደህንነት ዋስትና እንዲሰጥ፣ በየአካባቢያቸው የፖሊስና የደኅንነት መዋቅሮች ውስጥ የመሳተፍ መብታቸው እንዲከበር፣ በማኅበረሰብም ደረጃ ደህንነታቸውን የሚያስጠብቁበት አስቸኳይ መፍትኄ እንዲፈለግ፤

    (ሐ) የፌደራል መንግሥቱና ገዥው ብልፅግና ፓርቲ በአማራው ሕዝብ ላይ በሚፈፀሙ የዘር ጥቃቶች ላይ የያዘውን ዳተኝነት እንዲያቆምና ችግሩን ለመከላከልና ከመሠረቱ ለመቅረፍ ተጨባጭ እርምጃ እንዲወስድ፤

    (መ) የአማራ ብልጽግና ፓርቲና የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት በአማራ ሕዝብ ላይ በሦስት ወራት ውስጥ ብቻ ሁለት እጅግ አሰቃቂ የዘር ማጥፋት ድርጊቶች ሲፈፀሙ ወንጀሉን በስሙ ከመጥራት ጀምሮ ለችግሩ ዘላቂ መፍትኄ በመፈለግ ረገድ ያሳየው አቅም እና ፍላጎት ከደረጃ በታች መሆኑና ከእንግዲህም ለችግሩ ዘላቂ መፍትሄ ከዚህ አካል ሊመጣ እንደማይችል ሕዝባችን በግልፅ እንዲገነዘበው፤

    (ሠ) ሕዝባችን በተከታታይ ለዘር ማጥፋት እና ዘር ማጽዳት ጥቃቶች የተጋለጠበት የቤንሻንጉል ክልል አማራው ፍጹም ሥነ-ሕዝባዊ አብላጫ እያለው ፖለቲካዊ ውክልና በማጣቱ የተነሳ በመሆኑ ችግሩን በዘላቂነት ለማስወገድ የክልሉ መዋቅር የነዋሪዎቹን መብቶች በሚያረጋግጥ ሁኔታ እንዲከለስ ድርጅታችን አብን ያሳስባል።

    2] በአማራ ክልል የደረሰውን በጎርፍ የመጥለቅለቅ አደጋ በተመለከተ፦

    በአማራ ክልል በዘንድሮ ክረምት ዝናብ ምክንያት በተፈጠሩ የመሬት መንሸራተትና የጎርፍ አደጋዎች በአጠቃላይ በ6 ዞኖች በሚገኙ 36 ወረዳዎች ውስጥ ባሉ 164 ቀበሌዎች በተለያዩ ደረጃዎች የሚገለፁ ጉዳቶች እንዳደረሱ ይታወቃል።

    በተለይ ደግሞ በማዕከላዊ ጎንደር በምሥራቅ ደምቢያ ወረዳ፣ እንዲሁም በደቡብ ጎንደር በሊቦከምከም፣ ደራና ፎገራ ወረዳዎች በከፍተኛ የጎርፍ መጥለቅለቅ በመጠቃታቸው በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ወገኖች ከመኖሪያ ቤታቸው ተፈናቅለው በጊዜያዊ መጠለያዎች ይገኛሉ።

    አብን እነዚህ በጎርፍና በመጥለቅለቅ የተፈናቀሉ ወገኖች በአስቸኳይ የእለት እርዳታ እንዲያገኙ የበኩሉን አስተዋፅኦ እንደሚያደርግ እየገለፀ፤ በመላው ዓለም የሚገኙ የድርጅታችን አባላትና ደጋፊዎች፣ መላው የአማራ ሕዝብና ኢትዮጵያውያን ወገኖች ለድጋፍ እጃቸውን እንዲዘረጉ ይጠይቃል።

    በጎርፉ ጉዳት በደረሰባቸው አካባቢዎች ሊነሱ በሚችሉ የወባ እና ሌሎች ውሃ-ወለድ በሽታዎች ሕዝቡ እንዳይጋለጥ ጥንቃቄ እንዲደረግ ይጠይቃል።

    ተጎጂዎች ሰብሎቻቸው እና ንብረቶቻቸው የወደሙባቸው በመሆኑ አፋጣኝ ድጋፍ እና የመልሶ ማቋቋም ተግባራት እንዲከናወኑ፣ ለመጪው ዘመንም የሚያስፈልጋቸውን ሁለገብ እርዳታ የማዘጋጀት ሥራ እንዲሁም ለዘለቄታው በየዓመቱ የክረምት ወቅት ሊከሰቱ ከሚችሉ ተመሳሳይ አደጋዎች ለመጠበቅ ዘላቂ መፍትኄ እንዲፈለግ ይጠይቃል።

    በመጨረሻም በአማራ ሕዝብ ታላቅ መስዋዕትነት የተገኘው ለውጥ አቅጣጫውን በመሳቱ በሕዝባችን ላይ ሥርዓት እና መዋቅር ሠራሽ ጥቃቶቹ ስጋት ደቅነውበት እንደቀጠሉ አብን ይገነዘባል።

    እጅግ ራስ-ወዳድ በሆነው ሰፊ የፖለቲካ ውቅር ውስጥ ጨካኞች እና ያልተገሩ ስብስቦች በአማራው ላይ ጥቃታቸውን ባስቀጠሉበት አግባብ፣ ለኩርፊያቸው እና ለደም ጥማታቸው አማራ ቋሚ ግብር ወይም ማስያዥያ የሚሆንበት የፖለቲካ ድባብ በትግላችን መገፈፍ ይኖርበታል።

    በተፈፀመው የዘር ማጥፋት ወንጀል ውስጥ ያሉ ተዋንያንንና በቸልተኝነትና በሴራ ተባባሪ የሆኑ አካላትን ጭምር ለማጋለጥ እና በኃላፊነት እንዲጠየቁ ለማድረግ አብን እንደሚሠራ በአፅንዖት ለማስገንዘብ ይወዳል።

    በመጨረሻም አብን በቤንሻንጉል ጉሙዝና በኦሮሚያ ክልሎች በአሰቃቂ ሁኔታ የዘር ጭፍጨፋ ወንጀል ሰለባ ለሆኑ ወገኖቻችን የተሰማንን ጥልቅ ሐዘን ለመግለፅ ለመላው የአማራ ሕዝብና ለሕዝባችን ወዳጆች ከነገ ሰኞ መስከረም 11 ቀን 2013 ዓ.ም  ጀምሮ እስከ ማክሰኞ መስከረም 12 ቀን 2013 ዓ.ም ድረስ ለሁለት ቀናት በምናደርገው ጥቁር የመልበስ እና ተያያዥ የሐዘን መግለጫ ሥርዓቶች እንዲካፈሉ አብን የአክብሮት ጥሪውን ያቀርባል።

    አንድ አማራ ለሁሉም አማራ ፥ ሁሉም አማራ ለአንድ አማራ!
    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) /NaMA/
    መስከረም 9 ቀን 2013 ዓ.ም
    አዲስ አበባ ፣ ሸዋ ፣ ኢትዮጵያ

    የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን)

Viewing 15 posts - 1 through 15 (of 54 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.