ሀገራችን ካጋጠማት ፈተና እንድትወጣ በሰላማዊ ትግላችን እንድንቀጥል የቀረበ ጥሪ

Home Forums Semonegna Stories የፖለቲካ ፓርቲዎች ድምጽ (ኢትዮጵያ ውስጥ የሚነቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች) ሀገራችን ካጋጠማት ፈተና እንድትወጣ በሰላማዊ ትግላችን እንድንቀጥል የቀረበ ጥሪ

#15413
Anonymous
Inactive

የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ መግለጫ
ሀገራችን ካጋጠማት ፈተና እንድትወጣ በሰላማዊ ትግላችን እንድንቀጥል የቀረበ ጥሪ

ያለፈው የሰኔ 22 ቀን 2012 ዓ.ምን ክስተት ተከትሎ በሀገራችን በተቀሰቀሰው የዘር ማጥፋት ወንጀል የንብረት ጉዳት ደርሷል፤ ዜጎች በሃይማኖታቸው እና በብሔራቸው ምክንያት ለህልፈተ ሕይወት ተዳርገዋል፤ ሃብት ንብረታቸውም ወድሟል። ለዚህ የዘር ማጥፋት ወንጀል ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ (ባልደራስ) ዋነኛ ተጠያቂው የሥርዓቱ አውራዎች በተለይም የኦህዴድ/ብልጽግና፤ ብሔረሰብን በብሔረሰብ ላይ የሚያነሳሳ እኩይ ተግባር መሆኑን በወሰድነው የአቋም መግለጫ በተደጋጋሚ መግለፃችን ይታወሳል። ከሰሞኑም በድብቅ ወጥቶ የተደመጠው የአቶ ሽመልስ አብዲሳ ምስጢራዊ ንግግር የአቋማችንን ትክክለኛነት አረጋግጦልናል።

ሆኖም የሥርዓቱ ዓይን ያወጣ ክህደት ከዚህ እኩይ ክስተት ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት የሌላቸውን የፓርቲያችን ከፍተኛ አመራር አባላት አቶ እስክንድር ነጋ፣ አቶ ስንታየሁ ቸኮል፣ ወ/ሮ ቀለብ ስዩም እና ሌሎች አባላትና ደጋፊዎቻችን ለሰው ሕይወትና ንብረት ውድመት ተጠያቂ ናችሁ በሚል አስረው እጅግ የሚያሳዝን ተግባር በመፈፀም ላይ ይገኛል። ከአንድ ወር በላይ በቆየው የፍርድ ቤት ሂደት የታየው እጅግ አሳፋሪ ትዕይንት በኢትዮጵያ አሁንም ፍትህ ቀን እንዳልወጣላት በገሃድ ያሳየ ነው። የሥርዓቱ ቁንጮ ነኝ የሚለው ኦህዴድ/ብልጽግና በገሃድ በሚታይ መልኩ የፍትህ ሥርዓቱን መቀለጃ እና የፖለቲካ ፍላጎቱን ማስፈፀሚያ መሣሪያ አድርጎታል። የፍትህ ሥርዓቱ እንኳን ሊሻሻል በህወሓት/ኢህአዴግ ዘመን ከነበረው ሁኔታ በብዙ መልኩ የባሰ ሁኖ ይገኛል። በተለይ ሰሞኑን በድምጽ የተለቀቀው የኦህዴድ/ብልጽግና ከፍተኛ አመራር ሕገ-ወጥ እና ለሀገር ህልውና አደገኛ የሆነ ንግግር /በከፊልም ወደ መሬት የወረደ መሆኑን ልብ ይሏል/ እንደሚያስረዳው፥ በተደጋጋሚ ስንወተውት የነበረውን በአዲስ አበባም ሆነ በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተዘረጋ ያለውን በተረኝነት ፖለቲካ የተቃኘ፣ አምባገነናዊ አገዛዝን ለማዳበር ተግቶ የሚሠራ አመራር መሆኑን ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ ማስረጃ ሁኖ ቀርቧል። ከመጋረጃ በስተጀርባ ተደብቀው በዘር ማጥፋት ሂደት ውስጥ በዋነኛነት ሲመሩ የነበሩት የሥርዓቱ ዋነኛ ባለስልጣናት ሳይጠየቁ በሰብዓዊ መብት ተሟጋችነታቸው የሚታወቁት የፓርቲያችን ከፍተኛ አመራሮች መጠየቃቸው ሳያንስ፥ የፍርድ ሂደቱ በድብቅና በዝግ ችሎት እንዲከናወን የተፈለገበት መንገድ በእጅጉ አሳፋሪ፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት ካገኘው በግልጽ ችሎት የመዳኘት ሕገ መንግሥታዊ መብት ያፈነገጠ፣ ሥርዓት አልበኝነትና ምን ታመጣላችሁ የሚል መልዕክት ያለው ሆኖ አግኝተነዋል።

የባልደራስ ከፍተኛ አመራሮች የችሎት ውሎ አሳፋሪነቱ ምንም እንኳን ከአቃቤ ሕጉ ቅድመ ምርመራ መዝገብ የጀመረ ቢሆንም፥ የተቋሙን ገለልተኛነትና የፍትህ ሂደቱን የኢትዮጵያ ሕዝብ እንዲታዘብ በማሰብ መታገሳችን ይታወሳል። ሆኖም ረቡዕ ዕለት /ነሐሴ 06 ቀን 2012 ዓ.ም./ በዋለው ችሎት አቃቤ ሕግ ሦስት ምስክሮች ከመጋረጃ በስተጀርባ እና ማንነታቸው ሳይገለጽ፥ እንዲሁም አራት ምስክሮች ደግሞ በዝግ ችሎች እንዲደመጡ የሚል ጥያቄ ለፍርድ ቤቱ ሲያቀርብ የአመራሮቻችን ጠበቆች ለመመካከር እንዲሁም ውሳኔያችንን በጽሁፍ እንድናቀርብ ባሉት መሠረት የተከሰሱበት ወንጀል ዓለም አቀፍ ይዘት ያለውና ወደ ዘር ማጥፋት የሚወስድ በመሆኑ ይህንን የሚመሰክሩ ምስክሮች በግልጽ ችሎት ፊት ለፊት ቀርበው እንዲያስረዱ፥ ክርክሩ አስተማሪና ሂደቱ ለሕዝብ ግልጽ እንዲሆን ቢጠይቁም በአንፃሩ የፍርድ ቤቱ ዳኛ በአቃቤ ሕግ ብቻ የተጠየቀውን ተቀብሎ ሂደቱ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ዝግ ሆኖ እንዲቀጥል ወስኗል።

አቶ እስክንድር ነጋ ፈጽማችኋል የተባልነው ጉዳይ የዘር ማጥፋት ወንጀል ይዘት ስላለው በአደባባይ እንጠየቅ፤ ክሱም ዓለም አቀፍ ይዘት ያለው በመሆኑ ችሎቱ በድብቅ ምስክርነት እንዲሰማ ከወሰነ እራሳችንን ከፍርድ ሂደቱ አግልለናል፤ ጠበቆቻችንንም አሰናብተናል፤ ፍርድ ቤትም አንገኝም፤ ፍርድ ቤቱ የሚሰጠውን ብይን ራሱ ተከታትሎ ይስጥ የሚል አቋም ወስዷል። ይሁንና አቃቤ ሕግ እነ አቶ እስክንድር በፖሊስ ተገደው እንዲቀርቡ ትዕዛዝ ይሰጥልኝ ማለቱን ተከትሎ ፍርድ ቤቱ ይህንኑ የአቃቤ ሕግ ጥያቄ ተቀብሎ ትዕዛዝ ማሳለፉ የዳኝነት ሂደቱ በሕገ መንግሥቱና በወንጀለኛ መቅጫ ሕግ ድንጋጌዎች ሳይሆን በፖለቲካ አመራር እየታዘዘ የሚሠራ መሆኑን በገሃድ ለመገንዘብ ተችሏል። በኦህዴድ/ብልጽግና “የለውጥ ዘመን” የፍርድ ሂደቱ አያያዝ ከህወሓት/ኢህአዴግ ዘመን በከፋ ደረጃ ኢ-ፍትሃዊነትን እየተላበሰ ስለመሆኑ አስረጂ ሆኗል። አቶ እስክንድር ነጋ መንግሥት የሚያቀርብለትን ጠበቃም ሆነ በፖሊስ ተገዶ መቅረብ እንደማይቀበል “ለፍርድ ቤቱ” አበክሮና አስረግጦ አስረድቷል።

በከፍተኛ አመራሮቻችን የክስ ሂደት ፖሊስ በተደጋጋሚ ማስረጃ አቅርብ በሚባልበት ወቅት ከተከሰሱበት ጉዳይ ጋር የተያያዘ አንዳችም ማስረጃ ለማቅረብ መቸገሩን በተደጋጋሚ በፍርድ ቤቱ ሂደት ሲታይ እንደነበር ይታወሳል። ፖሊስ ለመክሰስ የሚያስችለው ምንም ማስረጃ ማቅረብ ሲያቅተው በድብቅ ምስክሮችን ለማቅረብ በማሰብ ተለዋጭ ቀጠሮ ይሰጠን እያለ የፍርድ አሰጣጡን ሂደት ያለበቂ ምክንያት ሲያራዝመው መታየቱ፥ ከጅምሩም ክሱ የሃሰት እንደሆነ ለከፍተኛ አመራሮቻችን፣ ለጠበቆቻቸው እንዲሁም የችሎቱን ሂደት በአንክሮ ይከታተል ለነበረው ፓርቲያችን ግልጽ ነበር። እስከዛሬ ለማሳየት የደከምንበት ሃቅ ይህንኑ የሚያስረዳ ነው። መሪያችን ከዚህ ትክክለኛ ካልሆነ ከሕገ መንግሥቱና ከወንጀለኛ መቅጫ ሕጉ ድንጋጌዎች ካፈነገጠና በተግባር ካልተሻረው የፀረ-ሽብር ሕግ በተወሰነ አንቀጽ ከሚመራ የፍርድ ቤት ሂደት ራሱን ማግለሉ በእጅጉ ትክክለኛ እና የምንደግፈውነው። በዚህ ዓይነት ቅጥ አንባሩ ከጠፋው የአምባገነኖች “ካንጋሮ ፍርድ ቤት” ፍትህ ማግኘት ስለማይቻል የአመራሮቻችን ውሳኔ ትክክል መሆኑን ድርጅታችን ያምንበታል። በመሆኑም ድርጅታችን ከአመራሮቻችን ጎን ዛሬም እንደትላንቱ ከጎናቸው በጽናት እንደሚቆም ማረጋገጥ ይወዳል።

ኦህዴድ/ብልጽግና በኦሮሚያ ክልል በተደጋገሚ የዜጎችን ዘር እና ሃይማኖት ተገን ተደርጎ ለተፈጠረው የዘር ማጥፋት /genocide/ እና የሥርዓቱ ጋሻጃግሬዎች ላደረሱት ወንጀል ሽፋን በመስጠት በሌሎች ንፁሃን ላይ በማላከክ ሕግ እንዳይከበር እና አለመረጋጋቱ ተባብሶ እንዲቀጥል እንየተደረገ እንደሆነ ባለፉት ሁለት ዓመታት ጉዟችን በአግባቡ ተገንዝበናል። በመሆኑም ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ በሀገራችን በተደጋጋሚ የደረሱት የዘር ማጥፋት ወንጀሎች ሆን ተብለው በሥርዓቱ አመራሮች ድጋፍና ተሳትፎ ጭምር የተካሄዱ እንደሆነ በተደጋጋሚ የሚቀርቡት እውነታዎች በገሃድ የሚያሳዩ መሆናቸውን ተመልክተናል። እንደማሳያነትም በቅርቡ በኦህዴድ/ብልጽግና ከፍተኛ አመራር በድብቅ ወጥቶ በተደመጠ ንግግር “ቄሮን የምናዘው፣ የምናወጣውም እንዲሁም የምንበትነው እኛ ነን” ማለታቸውን ልብ ይሏል። እውነተኛ ፍትህ ቢኖር በዚህ አቶ ሽመልስ አብዲሳ አባባል መሠረት ቄሮ በተሰኘው ኢ-መደበኛ አደረጃጀት እስካሁን ለተፈፀመው ወንጀል ተጠያቂ መሆን የሚገባው ማን እንደሆነ በግልጽ መገንዘብ ይቻላል።

ስለዚህ የዓለም አቀፍ ሕብረተሰብ በጉዳዩ ጣልቃ በመግባት የዘር ማጥፋት ወንጀል የፈፀሙት ብቻ ሳይሆን፥ ከመጋረጃው ጀርባ ሆነው ያስፈጸሙትን ጭምር ለሕግ እንዲቀርቡ እንዲደረግ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ያሉ ዜጎች የፓርቲያችንን ጥረት እንዲያግዙ በድጋሚ እንጠይቃለን። በተጨማሪም በሀገራችን የሕግ የበላይነት እንዲሰፍን አስቀድመን ስንጮህ ከጎናችን የነበራችሁ በሀገር ውስጥና በውጭ ያላችሁ ኢትዮጵያውያን፣ የፓርቲ አባላትና ደጋፊዎች፣ የዓለም አቀፍ ማኅብረሰብ፣ ለፓርቲያችን ቀጣይና ቁርጠኛ ለሆነው ሰላማዊ እና ሕጋዊ ለሆነው የትግል እንቅስቃሴያችን ከጎናችን በመቆም ድጋፍና እገዛ እንድታደርጉልን በአክብሮት እንጠይቃለን።

ድል ለዲሞክራሲ!

ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ
አዲስ አበባ
ነሐሴ 8 ቀን 2012 ዓ.ም.

ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ