Search Results for 'አዲስ አበባ'

Home Forums Search Search Results for 'አዲስ አበባ'

Viewing 15 results - 346 through 360 (of 495 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    በአደጋው የሁሉም ህይወት (157 ሰዎች) ያለፈ ሲሆን፥ ከተሳፋሪዎቹ መካከል 32ቱ ኬኒያዊያን ሲሆኑ፤ 17ቱ ኢትዮጵያዊያን ቀሪዎቹ ደግሞ የሌሎች አገራት ዜጎች መሆናቸውን የኢትዮጵያ አየር መንገድ አስታውቋል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– በዛሬው ዕለት የተከሰከሰው የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን ተሳፋሪዎች በሙሉ ህይወታቸው ማለፉ ተገለጸ።

    ከአዲስ አበባ ወደ ናይሮቢ (ኬንያ) ሲጓዝ በምሥራቅ ሸዋ ዞን ጊምቢቹ ወረዳ ላይ የተከሰከሰው የበረራ ቁጥር ET302 የሆነው ቦይንግ 737 የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን የ33 አገራት 149 መንገደኞችና ስምንት የበረራ አስተናጋጆችን ይዞ ነበር።

    ከተሳፋሪዎቹ መካከል 32ቱ ኬኒያዊያን ሲሆኑ፤ 17ቱ ኢትዮጵያዊያን ቀሪዎቹ ደግሞ የሌሎች አገራት ዜጎች መሆናቸውን አየር መንገዱ ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት አስታውቋል።

    አውሮፕላኑ አደጋው የደረሰበት ዛሬ ማለዳ ከቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት በተነሳ በስድስት ደቂቃ ልዩነት መሆኑ የተገለጸ ሲሆን የአደጋው መንስዔ እስካሁን አልታወቀም።

    በአደጋው የሁሉም ህይወት (157 ሰዎች) ያለፈ ሲሆን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት በአደጋው የተሰማውን ሀዘን በመግለጽ ለሟች ቤተሰቦችና ወዳጅ ዘመዶች መጽናናትን ተመኝቷል።

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቦይንግ 737 በረራ ዛሬ ጠዋት ከአዲስ አበባ ተነሥቶ ወደ ኬንያ ናይሮቢ ይበር በነበረው አውሮፕላን በደረሰው የመከስከስ አደጋ ወዳጅ ዘመዶቻቸውን ላጡ ሁሉ የጠ/ሚር ጽ/ቤት በኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት ስም ኀዘኑን ይገልጻል።የኢትዮጵያ ተቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ያሰፈረው።

    በተመሳሳይ የኬኒያው ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ በአደጋው የተሰማቸውን ሀዘን ገልጸው ለአደጋው ሰለባ ቤተሰቦች መፅናናትን ተመኝተዋል።

    የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ በአደጋው ህይወታቸውን ላጡ ሰዎች ቤተሰቦች የተሰማቸውን ሀዘን ገልጸዋል። ፕሬዝዳንቷ የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን ከአዲስ አበባ ወደ ናይሮቢ በመጓዝ ላይ እያለ አደጋ አጋጥሞት የመከስከሱን ዜና በከፍተኛ ድንጋጤና መሪር ሀዘን እንደሰሙ ገልጸዋል።

    ፈጣሪ አምላክ በቸርነቱ ለቤተሰቦቻቸው በሙሉ፣ ከብዙ በጥቂቱ ናይሮቢ ለማውቃቸው ለካፒቴን ያሬድ ወላጆች፣ ዶ/ር ጌታቸውና ዶ/ር ራያን፣ ለሆስተስ ሣራ ባለቤትና ሕጻን ልጆቿ፣ ከጥቂት ሳምንታት በፊት ላየኋት የጂቡቲዋ ራሻ ቤተስብ… መጽናናትን ይስጥልን። ዛሬ በ157 ሟች ቤተሰቦች ላይ የወደቀው መሪር ሐዘን እኔና ቤተሰቤ ኮሞሮስ በደረሰው አደጋ ያየነው በመሆኑ የሚያሳልፉትን ከባድ ፈተና ከማንም በላይ እረዳዋለሁ። 149 መንገደኞችና 8 የበረራ ሠራተኞችን ይዞ ከአዲስ አበባ ወደ ናይሮቢ ሲግዋዝ የነበረው [ET 302] በረራ ላይ በደረሰው የመከስከስ አደጋ በውስጡ የነበሩት ኢትዮጵያውያንና የ33 አገሮች ዜጎች ሕይወት ማለፍ ልቤን ሰንጥቆታል፤ እጅግ በጣም ነው ያዘንኩት።ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ በትዊተር ገጻቸው ላይ ያሰፈሩት።

    “ለኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊያን ትልቅ የሀዘን ቀን ነው” ያሉት ፕሬዝዳንቷ “በዜጎቻችንና ሌሎች የአየር መንገዱ ደንበኛ መንገደኞች ላይ በደረሰው አደጋ ልቤ ተሰብሯል” ብለዋል። በአደጋው ተጎጂ ለሆኑ ቤተሰቦች ፣ ወዳጅ ዘመዶችና ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብም መጽናናትን ተመኝተዋል።

    በተመሳሳይ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከአዲስ አበባ ወደ ናይሮቢ ሲበር በተከሰከሰው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቦይንግ 737 አውሮፕላን አደጋ ጥልቅ ሀዘን እንደተሰማው ገልጾ በአደጋው ቤተሰቦቻቸውን ላጡ መፅናናትን ተመኝቷል።

    የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባርም (ኢህአዴግ) እንዲሁ በአደጋው የተሰማውን ሀዘን በመግለጽ የሟች ወገኖች ነፍስ በአፀደ ገነት እንዲያርፍ ፣ ለወዳጅ ዘመድ ቤተሰቦቻቸውና ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብም መፅናናትን ተመኝቷል።

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ በበኩሉ በደረሰው አደጋ የሰው ሕይወት በመጥፋቱ የተሰማውን ጥልቅ ሃዘን ገልጿል። አውሮፕላኑ ምንም ዓይነት ቴክኒካዊ ችግር እንዳልነበረበትም አመልክቷል።

    የአየር መንገዱ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ተወልደ ገብረማርያም በሰጡት መግለጫ፤ በአውሮፕላኑ መከስከስ የመንገደኞችና የአውሮፕላኑ ሠራተኞች ሕይወት በማለፉ ከፍተኛ ሃዘን እንደተሰማቸው ገልጸዋል። ህይወታቸው ያለፉት ቤተሰቦችና ወገኖች ማስተናገጃ በአዲስ አበባ እና በናይሮቢ ቢሮ መከፈቱን ተናግረዋል።

    በአጠቃላይ 1ሺ 200 ሰዓታትን የበረራ ሰዓት ያስመዘገበው አውሮፕላን ከአዲስ አበባ ለበረራ የተነሳው 2 ሰዓት ከ38 ደቂቃ ሲሆን፤ 2 ሰዓት ከ40 ላይ ችግር እንዳጋጠመውና ከራዳር እይታ ውጪ እንደሆነም ገልጸዋል።

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከቦይንግ ኩባንያ ከተረከበው አራት ወር የሆነው ቦይንግ 737 ወደ ኬንያ የሚያደርገወን ጉዞ ከመጀመሩ በፊት ከጆሃንስበርግ ደቡብ አፍሪካ ተመልሶ ለሦስት ሰዓት ያህል አርፏል።

    ይሄው በዋና አብራሪ ካፒቴን ያሬድ ሙሉጌታ ወደ ኬንያ እየተጓዘ የነበረው አውሮፕላን፤ ቀደም ብሎ በተካሄደ የቴክኒክ ፍተሻ ምንም ዓይነት ችግር እንዳልነበረበት አመልክተዋል። ረዳት አብራሪው አህመድ ኑር መሃመድ ኑር የሚባል ሲሆን፤ ከ200 ሰዓታት በላይ መብረሩም ተገልጿል።

    የአደጋው መንሰኤ አለማቀፍ የአቬሽን ሕግን በተከተለ መልኩ ዓለምአቀፍ ምርመራ ተካሂዶ ዝርዝር መረጃው ወደፊት እንደሚገለጽ አመልክተዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ


     

    Semonegna
    Keymaster

    የአቶ ገዱ አንዳርጋቸውን የስልጣን መልቀቅ ጥያቄ ተከትሎ የአዴፓ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል እና የጠቅላይ ሚኒስትር የመሠረተ ልማት እና የከተማ ልማት አማካሪ ሚኒስትር የሆኑት ዶ/ር አምባቸው መኮንን ርዕስ መስተዳደር ሆነው ተሹመዋል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው መልቀቂያ ጥያቄ አቀረቡ። ርዕሰ መስተዳድሩ እየተካሄደ ባለው የክልሉ ምክር ቤት ስብሰባ ላይ ነው ጥያቄውን ያቀረቡ ሲሆን፥ ምክር ቤቱም ጥያቄያቸውን ተቀብሏል። የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (አዴፓ)በበኩሉም የርዕሰ መስተዳድሩን ጥያቄ መቀበሉን የ አማራ ብዙሃን መገናኛ ድርጅት እና ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ዘግበዋል።

    አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ባለፈው ዓመት የካቲት ወር ለሦስተኛ ዙር በርዕሰ መስተዳድርነት ተመርጠው ሲያገለግሉ እንደነበር ይታወሳል። በአጠቃላይም ከታህሳስ ወር 2006 ዓ.ም. ጀምሮ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር በመሆን አገልግለዋል።

    አቶ ገዱ አንዳርጋቸው “ታላቁን የአማራ ሕዝብ ለመምራት ዕድል የሰጠኝን ፓርቲዬን አመሠግናለሁ፤ በስልጣን ዘመኔ በሰጠኋቸው ውሳኔዎች ያስከፋኋችሁ ካላችሁ ከልብ ይቅርታ እጠይቃለሁ። ወኔና ጉልበት ሆኖኝ የኖረውን የአማራ ሕዝብ አመሠግናለሁ፤ ለአዲሱ ርዕሰ መስተዳድርም መልካም የሥራ ዘመን እመኛለሁ” ብለዋል በመሰናበቻ ንግግራቸው።

    የአቶ ገዱ አንዳርጋቸውን የስልጣን መልቀቅ ጥያቄ ተከትሎ ምክር ቤቱ የአዴፓ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል የሆኑትን ዶ/ር አምባቸው መኮንንን ርዕስ መስተዳደር አደርጎ ሾሟል። ዶ/ር አምባቸው ከአዴፓ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባልነታቸው በተጨማሪ የጠቅላይ ሚኒስትር ቢሮን የመሠረተ ልማት እና የከተማ ልማት አማካሪ ሚኒስትር በመሆን እያገለገሉ ነበር።

    እድገታቸው ጋይንት፣ ጎንደር ውስጥ የሆነው ዶ/ር አምባቸው መኮንን የጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ ሆነው ከመሾማቸው በፊት በተለያዩ የመንግስት ቦታዎች ለ28 ዓመታት ሠርተዋል።

    ዶ/ር አምባቸው ከኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ ዩንቨርሲቲ በኢኮኖሚክስ፣ ቀጥሎም ደቡብ ኮርያ ከሚገኘው ከኮርያ የልማት ኢንስቲትዩት (Korea Development Institute) በፐብሊክ ፖሊሲ የማስተርስ ዲግሪ፣ ከዚያም እንግሊዝ ሀገር ካንተርበሪ ከተማ ከሚገኘው ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ኬንት (University of Kent) ሌላ ማስተርስ ዲግሪ እና የዶክትሬት ዲግሪያቸውን አግኝተዋል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    ዶ/ር አምባቸው መኮንን


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – በዛሬው ዕለት (የካቲት 27 ቀን 2011 ዓ.ም.) በአዲስ አበባ 51 ሺህ 229 የጋራ መኖሪያ ቤቶች (ኮንዶሚኒየም ቤቶች) ዕጣ ማውጣት ሥነ ስርዓት ተካሄደ።

    ዕጣ ከወጣባቸው ቤቶች ውስጥም 32 ሺህ 653 ቤቶች የ20/80 ቤቶች ሲሆኑ፥ ቀሪዎቹ 18 ሺህ 576 ደግሞ የ40/60 ቤቶች ናቸው። በዚህም መሠረት የ20/80 ፕሮግራም ኮንዶሚኒየም ቤቶች ውስጥ 1 ሺህ 248 ስቲዲዮ፣ 18 ሺህ 823 ባለ አንድ መኝታ፣ 7 ሺህ 127 ባለ ሁለት መኝታ እና 5 ሺህ 455 ቤቶች ደግሞ ባለ ሦስት መኝታ ክፍሎች ናቸው። በእነዚህ የ20/80 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ ውስጥ የሚካተቱት በ1997 ዓ.ም ተመዝግበው በ2005 ዓ.ም በነባር መደብ የተመዘገቡና በ2005 ዓ.ም የአዲስ ባለ ሦስት መኝታ ክፍል ተመዝጋቢዎች ናቸው።

    በዕጣ አወጣጥ ሥነ ስርዓቱ ላይ የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ ኢንጂነር ታከለ ኡማ እንደተናገሩት፥ በግንባታ ሂደት ሁሉም ተጠቃሚ እንደሚሆን ቢታሰብም በጥንቃቄ ጉድለት ለጉዳትና ማኅበራዊ ቀውስ የተዳረጉ የህብረተሰብ ክፍሎች አሉ። ኢንጅነር ታከለ ልማት በጋራ ተጠቃሚነት ካልተመኅረተ ተጎጅና ተጠቃሚን የሚፈጥርም ነው ብለዋል። በተለይ ለቤቶች ግንባታ ሲባል ከእርሻ ቦታቸው የለቀቁ አርሶ አደሮችና የአርሶ አደር ልጆች የሁላችንም ህመም ነው ብለዋል። በዚህም የከተማ አስተዳደሩ ካቢኔና የቤቶች አሰተዳደር ቦርድ አርሶ አደሮችና የአርሶ አደር ልጆች ያለ ዕጣ እንዲሰጣቸው መወሰኑን ይፋ አድርገዋል።

    ተሰርዞ የነበረው የ20/80 እና 40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ ወጣ (የዕድለኞች ስም ዝርዝር) 

    ኢንጂነር ታከለ በቀጣይም የቤት ልማትን ከአርሶ አደሩ ተጠቃሚነት ጋር ለማስኬድ ትኩረት በማድረግ ይሠራል ነው ያሉት። በቤት ልማቱ የመንግስትን ተሳትፎ በመቀነስ የግሉንና የባለሀብቱን ተሳትፎ የማሳደግ ሥራ እንደሚከናወንም ጠቁመዋል። ከንቲባው በዘርፉ የመንግስትና የባላሀብቶችን ግንኙነትን ለማጠናከር በትኩረት ለመንቀሳቀስ ኮሚቴ መዋቀሩን ነው ያስታወቁት።

    የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስትር አቶ ዣንጥራር አባይ በበኩላቸው፥ መንግስት በቤት ልማት ዘርፍ የሚታየውን ችግር ለመቅረፍ በርካታ ሥራዎች ሲያከናውን መቆየቱን የተናገሩ ሲሆን፥ በዚህ ወጤቶች መመዝገባቸውን አንስተዋል። በቤት ልማት ዘርፉ የፍላጎቱን ያህል ባይሠራም የተሻለ ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

    አቶ ዣንጥራር በኢትዮጵያ ያለው የቤት ልማት ዘርፍ ህዝቡን የቤት ባለቤት ከማድረግ ባለፈ ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል የፈጠረ መሆኑን አስታውቀዋል። ባለፉት 13 ዓመታት በአዲስ አበበና በመላ ሀገሪቱ ከ385 ሺህ በላይ ቤቶች እንደተገነቡና በግንባታ ላይ እንደሚገኙ የገለፁ ሲሆን፥ በዚህም 1 ሚሊየን ለሚጠጉ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር እንደተቻለ ተናግረዋል።

    በተለያዩ ወገኖች በተደረገ ጥናት መሠረት ካለው የቤት ፍላጎት አንፃር ከ2007 እስከ 2017 ዓመተ ምኅረት ባለው ጊዜ ውስጥ 471 ሺህ ቤቶችን በየዓመቱ እየገነቡ ማቅረብ ይገባ ነበር። ሆኖም መንግስት በፋይናንስ እና በግንባታ ፕሮጀክት የማስፈፀም አቅም ባለበት ክፍተት ምክንያት ይህን ማድረግ እንዳልተቻለ በመጠቆም በቀጣይ የግሉን ዘርፍ በማሳተፍ ፍላጎቱን ለማሟላት እንደሚሠራ ነው አቶ ዣንጥራር በንግግራቸው ላይ ያነሱት።

    ኮንዶሚኒየም ቤቶች ዕጣ የወጣላቸው ዕድለኞች ስም ዝርዝር

    13ኛ ዙር የ20/80 ፕሮግራም ባለ ስቱዲዮ ቤት የዕድለኞች ስም ዝርዝር
    13ኛ ዙር የ20/80 ፕሮግራም ባለ አንድ መኝታ ክፍል የዕድለኞች ስም ዝርዝር
    13ኛ ዙር የ20/80 ፕሮግራም ባለ ሁለት መኝታ ክፍል የዕድለኞች ስም ዝርዝር
    13ኛ ዙር የ20/80 ፕሮግራም ባለ ሦስት መኝታ ቤት የዕድለኞች ስም ዝርዝር
    የ40/60 መርሃ ግብር ባለ አንድ መኝታ ቤት የዕድለኞች ስም ዝርዝር
    የ40/60 መርሃ ግብር ባለ ሁለት መኝታ የዕድለኞች ስም ዝርዝር
    የ40/60 መርሃ ግብር የባለ ሦስት መኝታ ቤት የዕድለኞች ስም ዝርዝር

    ምንጭ፦ ፋና ብሮድካስቲንግ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ኮንዶሚኒየም ቤቶች


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ የተከፈተው ቆንስላ ጽ/ቤት ቆንሱል ጄኔራል አምባሳደር እውነቱ ብላታ ቆንስላ የጽ/ቤቱ መከፈት በሚኒሶታ ግዛት ለሚኖሩ በሺዎች ለሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን ዳያስፖራ አባላት ምቹ ሁኔታና መነቃቃትን እንደሚፈጥር ገልጸዋል።

    ዋሽንግተን፥ ዲሲ (ሰሞነኛ) – የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢፌዴሪ) መንግስት በሀገረ አሜሪካ በሎስ አንጀለስ ከተማ (ካሊፎርንያ ግዛት) ከሚገኘው ቆንጽላ ጽ/ቤት ቀጥሎ ሁለተኛውን ቆንጽላ ጽ/ቤት በሴይንት ፓል ከተማ (ሚኖሶታ ግዛት) ከፍቷል።

    ቆንስላ ጄኔራል ጽ/ቤቱ የተከፈተው የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ክቡር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ባሳለፍነው ዓመት ነሃሴ ወር ላይ በአሜሪካ ባደረጉት ጉብኝት በገቡት ቃል መሠረት ነው።

    በመክፈቻ ሥነ-ስርዓቱ ላይ የኦሮሚያ ክልል መንግስት ፕሬዝዳንት አቶ ለማ መገርሳ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ክብርት ብርቱካን አያኖ፣ የሴይንት ፓል ከተማ ከንቲባ ሚስተር ሜልቪን ካርተር፣ ከአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እንዲሁም በርካታ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን የዳያስፖራ አባላት ተገኝተዋል።

    ክቡር አቶ ለማ መገርሳ እንደገለጹት የቆንስላ ጽ/ቤቱ መከፈት ለአካባቢው ብሎም በመላው አሜሪካ የሚኖረውን ዳያስፖራ ለማገልግል የጎላ ፋይዳ ይኖረዋል። ዳያስፖራው በኢትዮጵያ እየተካሄደ ባለው የኢኮኖሚና ፖለቲካ ለውጥ የበኩሉን ሚና እንዲወጣ፣ ለዚህም የኢትዮጵያ መንግስት ከምንጊዜውንም በላይ ቁርጠኛ መሆኑን ገልጸዋል።

    አዲስ የተከፈተው ቆንስላ ጽ/ቤት ቆንሱል ጄኔራል አምባሳደር እውነቱ ብላታ በበኩላቸው የጽ/ቤቱ መከፈት በሚኒሶታ ግዛት ለሚኖሩ በሺዎች ለሚቆጠሩ የዳያስፖራ አባላት ምቹ ሁኔታና መነቃቃትን እንደሚፈጥር ገልጸዋል።

    የሴይንት ፖል ከተማ ከንቲባ ሚስተር ማልቪን ካርተር በዚሁ ወቅት ባደረጉት ንግግር ከቆንስላ ጄኔራል ጽ/ቤቱ ጋር ተቀራርቦ ለመሥራትና አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርጉ ገልጸዋል። የካቲት 23 ቀን 2011 ዓ.ም. (ማርች 2 ቀን 2019) በከተማ ደረጃ “የኢትዮጵያ ቀን” ተብሎ እንዲከበር መወሰኑንም ጠቁመዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ኤምባሲ፤ ዋሽንግተን፥ ዲሲ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    ቆንስላ ጽ/ቤት


    Semonegna
    Keymaster

    በተሽከርካሪ ላይ የሚገጠመው የተቀናጀ የተሸከርካሪ ፍጥነት መቆጣጠሪያ መሣሪያ ከዓለም አቀፍ ስርዓት አቅጣጫ (GPS) ጋር የተጣመረ ሆኖ ወደ ተሸከርካሪው ሞተሩ የሚገባውን ነዳጅ አሊያም አየር በመቀነስ የተሸከርካሪውን ፍጥነት የሚቆጣጠር መሣሪያ ነው።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– የመንገድ ትራፊክ አደጋ እያደረሰ ያለውን የሰው ልጅ ሞት፣ የአካል ጉዳትና የንብረት ውድመት ለመቀነስ እየተሠራ ቢሆንም አደጋው ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ ይገኛል። ለመንገድ ትራፊክ አደጋ መከሰት በርካታ ምክንያቶች የሚጠቀሱ ሲሆን ከተወሰነው የፍጥነት ገደብ በላይ ማሽከርከር በቀዳሚነት ከሚጠቀሱ ምክንያቶች ውስጥ በቀዳሚነት ይገኛል።

    የፌደራል ትራንስፖርት ባለስልጣን አሽከርካሪዎች ፍጥነታቸውን ቀንሰው በጥንቃቄ በማሽከርከር አደጋውን መቀነስ እንዲችሉ የግንዛቤ ሥራዎችን ከመሥራት ጎን ለጎን የተሸከርካሪዎችን ፍጥነት መገደብ እንደሚገባ በማመን በተሸከርካሪዎች ላይ የፍጥነት መገደቢያ መሣሪያ ስለመግጠም እና ስለማስተዳደር የሚገልጽ መመርያ አዉጥቷል።

    በተሽከርካሪ ላይ የሚገጠመው የተቀናጀ የተሸከርካሪ ፍጥነት መቆጣጠሪያ መሣሪያ ከዓለም አቀፍ ስርዓት አቅጣጫ (GPS) ጋር የተጣመረ ሆኖ እንደተሸከርካሪው ሁኔታ ወደ ሞተሩ የሚገባውን ነዳጅ ወይም አየር በመቀነስ የተሸከርካሪ ፍጥነት በህግ ከተደነገገ በላይ እንዳይፈጥን የሚቆጣጠር መሣሪያ ነው።

    የሚገጠመው የፍጥነት መቆጣጠሪያ ጣሪያም የፍጥነት ወሰን ህጉ በሚደነግገው ከፍተኛ የፍጥነት ወሰን ጣሪያ መሠረት ይሆናል። አሽከርካሪው በትራፊክ መቆጣጣሪያ ደንብ መሠረት ፍጥነቱን ከተፈቀደለት የፍጥነት ወሰን በታች ማሽከርከር የሚገባው ሁኔታ ሲኖር ፍጥነቱን ቀንሶ ማሽከርከር እንደሚገባ ይገልፃል።

    የፍጥነት መገደቢያው የሚገጠምላቸው ተሸከርካሪዎች የምርት ዘመናቸው እንደ አውሮፓውያን ዘመን አቆጣጠር ከ2000 እና በኋላ ያሉ ተሽከርካሪዎች ናቸው። ከተካተቱት ውጪ ያሉ ተሽከርካሪዎች ላይ የፍጥነት መገደቢያ መሣሪያው ስለሚገጠምበት ሁኔታ ባለስልጣኑ ወደፊት የሚወስን ሲሆን ይህ መመሪያ ከጸደቀበት ቀን ጀምሮ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገቡና በሀገር ውስጥ የሚመረቱ ተሸከርካሪዎች ባለስልጣኑ ፍቃድ ከሰጠው አካል የፍጥነት መገደቢያ መሣሪያ የተገጠመላቸዉ ብቻ ይሆናሉ።

    ምንጭ፦ የፌደራል ትራንስፖርት ባለስልጣን / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    የተሸከርካሪ ፍጥነት


    Semonegna
    Keymaster

    የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የሴቶችን ጫና በሚያቀልሉ ቴክኖሎጂዎች ዙሪያ ከባለድርሻ አካላት ጋር እየመከረ መሆኑን የሚኒስቴሩ የሴቶች፤ ህፃናትና ወጣቶች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ወ/ሮ ኤልሳቤጥ ገብረሥላሴ አስታውቀዋል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር በ7 ክልሎች ውስጥ በቴክኖሎጂ ውጤቶች ሊደገፉ የሚችሉ ሴቶች ላይ ከፍተኛ ጫና እያሳደሩ ያሉ ሥራዎችን በጥናት ለይቷል።

    ችግሮቹ የተለዩት በአፋር፤ በቤኒሻንጉል፤ በጋምቤላ፤ በደቡብ፤ በአማራ፤ በትግራይና በሶማሌ ክልል በተጠናው ጥናት መሠረት መሆኑን ሚኒስቴሩ አስታውቋል።

    በፀሐይ ኃይል የሚሠራ የምግብ ማብሰያ፤ በሬ ለምኔ ዘመናዊ ማረሻ እና የቆጮ መፋቂያ ማሽን በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ ሥራ እንደሚገቡ ተገልጿል። ዘመናዊ የበቆሎ መፈልፈያና የአፋ አሊ (የአፋር ቤት) መሥሪያ በመካከለኛ ጊዜ ወደ ሥራ ለማስገባት የታቀደ ሲሆን በመስመር መዝሪያ እና ከጉድጓድ ውሃ ማውጫ መሣሪያ ደግሞ በረጅም ጊዜ ወደ ሥራ ለማስገባት በዕቅድ ተይዟል።

    የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የሴቶችን ጫና በሚያቀልሉ ቴክኖሎጂዎች ዙሪያ ከባለድርሻ አካላት ጋር እየመከረ ነው። የሚኒሰቴሩ የሴቶች፤ ህፃናትና ወጣቶች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ወ/ሮ ኤልሳቤጥ ገብረሥላሴ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የሴቶችን የሥራ ጫና የሚያቃልሉና ምርታማ የሚያደርጉ ቴክኖሎጂዎች ላይ በትኩረት እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል። ለስኬታማነቱ የሚመለከታቸው ሁሉ ድጋፋቸውን እንዲያደርጉም ዳይሬክተሯ ጥሪ አቅርበዋል።

    ምንጭ፦ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ 
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    የሴቶችን ጫና የሚያቃልሉ የቴክኖሎጂ ውጤቶች


    Semonegna
    Keymaster

    በቤተ ጉራጌ ዘንድ በወጌሻ ሕክምና ሙያቸው ስማቸው እጅግ ከፍ ብሎ የሚጠራው አቶ ፈንቅር ሳረነ ሲሆኑ፥ ይህም ሙያ ከእርሳቸው አልፎና ከልጅ ልጆቻቸው ተዋርሶ፣ አሁን የልጅ ልጆቻቸው በቤተ ጉራጌ ብቻ ሳይሆን በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች እያገለገሉ ይገኛሉ። አቶ መኮንን አመርጋ ደግሞ የአቶ ፈንቅር ሳረነ አራተኛ የልጅ ልጅ ናቸው።

    ኑሬ ረጋሳ (የጉራጌ ዞን ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ)

    ወልቂጤ (ሰሞነኛ) – ከባህላዊ የሕክምና ዘዴዎች ውስጥ የወጌሻ ሕክምና አንዱ ነው። የሰዉ ልጆች በተለያዩ ምክንያቶች በአካላቸዉ ላይ የተለያዩ አደጋዎች ይገጥማቸዋል። በአንድ ወቅት በወጌሻ ፈንቅር ሳረነ በሰውነታቸው ላይ እባጭ ወጥቶባቸው ሁለተኛ ወገን ባለማግኘታቸው በቻሉት አቅም ራሳቸውን አክመው እባጩን በማዳናቸው ምክንያት አድርገው የጀመሩት የባህላዊ ወጌሻ ሙያ ከልጅ ልጅ እየተላለፈ አሁንም ድረስ የፈንቅር ሳረነ የልጅ ልጆቻቸው ከቤተ ጉራጌ ክልል አልፈው በሌሎችም ቦታዎች ህብረተሰቡን እያገለገሉ ይገኛሉ።

    አቶ ፈንቅር ሳረነ የተወለዱት በ1814 ዓ.ም. በጉራጌ ዞን ኧዣ ወረዳ የወግወረ በቢባል አካባቢ ነበር። የአካባቢው ማህበረሰብ አንደግባ የሚል የክብር ስም ሰጥቷቸዋል። በባህላዊ ሕክምና ህዝቡን የማገልገል እሳቤ ይዘው ወደ ወጌሻነት ሙያ የገቡት ፈንቅር ሳረነ ለዘመናት ህዝቡን አገልግለዋል። የወጌሻነ ሕክምና አገልግሎታቸው እና ከተለያዩ እፅዋት በባህላዊ መንገድ በመቀመም የሚያዘጋጇቸው መድኃኒቶች እስከ በጊዜው እስከ ቤተ መንግስት ድረስ አድርሷቸዋል። ፈንቅር ሳረነ የ8 ወንድ ልጆችና የአንድ ሴት ልጅ ወላጅ አባት ሲሆኑ ለአብነት ያህል ካቤ ፈንቅር ሳረነ፣ ጫሚሳ ፈንቅር፣ ድድራ ፈንቅር፣ ገብረማሪያም ፈንቅር፣ እንዱሁም ሌሎችም ይጠቀሳሉ። ወጌሻ መኮንን አመርጋ የአራተኛ የልጅ ልጅ (ማለትም ፈንቅር፣ መኮንን አመርጋ ጫሚሳ ፈንቅር) ሲሆኑ፥ እሳቸውም በሚሰጡት የወጌሻነት ሕክምና አገልግሎት አንቱታን አትርፈዋል።

    ወጌሻ መኮንን አመርጋ እንደሚሉት በባህላዊ ሕክምና ሙያ፣ ልምድና ዕውቀት የቀሰሙት የልጅ ልጅ በሆኑት በወጌሻ ወልዴ ጫሚሳ እንደሆነና ወጌሻ ወልዴ ጫሚሳ ከቤተ ጉራጌ ክልል አልፈው እስከ ስልጢ ድረስ እየዞሩ ያገለግሉ እንደነበረም ተናግረዋል። ድርድራ ፈንቅር ከጅማ እስከ ከፋ ድረስ የባህላዊ ሕክምና ሲሰጥ እንደነበረ እንዲሁም የካቤ ፈንቅር ልጆች (ለምሳሌ ዜናዬ ካቤ፣ መዝገበ ካቤ) አዲስ አበባ ላይ አገልግሎት እንደሰጡ፤ በወሊሶና አካባቢው ደግሞ ተክሌ ሙራረ በአግባቡ የወጌሻነት አገልግሎት ለህብረተሰቡ ይሰጡ እንደነበረም አስረድተዋል። የልጅ ልጅ የሆኑትን ወይዘሮ ዙሪያሽ ደግሞ አጠቃላይ ቤተ ጉራጌ በአካለለ መልኩ ቸሃ ላይ መቀመጫ አድርገው ይሠሩ እንደነበረም ጠቅሰዋል።

    የEBS ቴለቭዥን አርአያ ሰብ መርሀግብር በፈንቅር ሳረነ የሕይወት ታሪክ ላይ የሠራውን ጥንቅር እዚህ ጋር ይመልከቱ

    የወጌሻነት ሙያ ከአጎታቸው የተማሩት መኮንን አመርጋ ወልቂጤ ከተማ ላይ በመምጣት ለህብረተሰቡ አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ። ወልቂጤና አካባቢዋ የሚኖሩ የህብረተሰብ ክፍሎችን በማገልገል ተጠቃሽ የሆነው ወጌሻ መኮንን አመርጋ ለበርካታ ዓመታት ቤታቸው ውስጥ በተለያዩ ምክንያቶች የተጎዱ የህብረተሰብ ማለትም በስፖርታዊ ውድድሮች ተሰብሮና እግሩ ወልቆ ለሚመጣ፣ የተሸከርካሪ አደጋ ለደረሰበት፣ ውልቃትና መሰል አደጋ ለደረሰበት ሰው አገልግሎት በመስጠት ይታወቃሉ።

    ወጌሻ መኮንን አመርጋ የወልቂጤ ከነማ እግር ኳስ ክለብ ብሔራዊ ሊግ እያለ ለሁለት ዓመት ከመንፈቅ ያህል በወጌሻነት በማገልገል ለስፖርተኞች ጥሩ ወንድማዊ ፍቅርን በመለገስ በጫወታ ወቅት የሚደርስባቸው ጉዳት በማከም ስፖርተኞች ውጤታማ እንዲሆኑና አሁን ለደረሱበት ከፍተኛ ሊግ በሙያቸው የበኩላቸውን ሚና ተወጥተዋል። ከዚህም በተጨማሪ ለበርካታ ዓመታት የወረዳውና የዞን ውድድሮችን እንዲሁም በየዓመቱ በሚደረጉ የትምህርት ቤቶች ውድድሮች ላይ ሳይሰለቹ በቅንነት በማገልገል ስማቸው ከምስጋና ጋር ይነሳል።

    ለሙያው እና ለተገልጋዩ ህብረተሰብ ባላቸው ክብር የተነሳ በጣም ጉዳት ደርሶበት ውይም ደርሶባት መኖሪያ ቤቱ መምጣት የማይችሉት ጉዳተኞች እስከ መኖሪያ ቤታቸው ድረስ በመሄድ ሙያዊ እገዛ በማድረግ ይታወቃሉ – ወጌሻ መኮንን። አንድ ባለ ጉዳይ አገልግሎቱን ለማግኘት ከመጣ ገንዘብ እንኳን ባይኖረውም መጎዳትና አካለ ስንኩል መሆን የለበትም በማለት አገልግሎቱን በነጻ በመስጠት በጎነታቸው የሚታወቁት መኮንን ዓመርጋ፥ የወጌሻነት ሙያ ወደ ልጆቻቸው ለማስረጽ ሙያውን ሙሉ ለሙሉ እንዲያውቁት ለማድረግ የዕውቀትና የሙያ ሽግግር የማድረግ ዓላማ ይዘውም ይሠራሉ።

    በዚህም የበኩር ልጃቸው የአባቱን የወጌሻነት የጥበብ ትምህርት የእረፍት ጊዜውን በመጠቀም አባቱን በማገዝና ለህብረተሰቡ የሚሰጡትን አገልግሎት በመቅሰም ወይም ትምህርት በመውሰድ፣ ወጌሻ መኮንን ራቅ ወዳለ ቦታ ከሄዱ አገልግሎት ፈልገው ለሚመጡ ደንበኞች አገልግሎት እየሰጠ እንደሆነና ሙያውን ሙሉ ለሙሉ አውቆ በእረፍት ጊዜው እየሠራበት እንደሆነም ወጌሻ መኮንን ገልጸዋል።

    መንግስት የባህላዊ ሕክምናው ዘርፍ ለማዘመን ነጻ የትምህርትና ስልጠና እድል በማመቻቸት የሕክምናውን ሳይንስ እንዲያውቁት በማድረግ ረገድ ውስንነት መኖሩን አስታውቀው፥ የጤናውን ትምህርት ባይወስዱም ህብረተሰቡን እያገለገሉበት ያለውን የወጌሻ ሙያ ዕውቀታቸውን የበለጠ ለማዳበር ቴክኖሎጂ በመጠቀም እና ሀኪም ጓደኞቻቸውን በማማከር ትምህርት እየተማሩ እንደሆነና በሥራ ላይ የሚገጥማቸውን ውስንነት እየቀረፉ እንደሆነም አስረድተዋል። በሳምንት በርካታ ሕመምተኞች በቀላልና ከባድ አደጋ ቤት ድረስ መጥተው አገልግሎት እንደሚያገኙ የተናገሩት መኮንን ዓመርጋ በከተማው ለበርካታ ዓመታት አገልግሎት የሚሰጡት በመኖሪያ ቤታቸው ሲሆን መንግስት በከተማው ሴንተር ቦታዎች ላይ ቋሚ መሥሪያ ቦታ ቢያመቻችላቸው የበለጠ ለህብረተሰቡ ቀልጣፋና ውጤታማ አገልግሎት መስጠት ያስችላቸዋል።

    የወጌሻ ሙያ ከጀመሩ ብዙ ዓመታትን ያስቆጠሩት መኮንን በሥራ ላይ ብዙ ገጠመኞች እንደገጠማችው አስታውሰው ለአብነት ያህል በአንድ ወቅት በእግር ኳስ ሜዳ ላይ አንድ አጥቂ ጎል ለማግባት ሲል እርስ በእርስ ተጋጭተዉ ላንቃው ሙሉ ለሙሉ ተዘግቶ ምላሱን ማንቀሳቀስ አቅቶት ሊሞት ሲል አንደምንም ርብርብ አድርገን አፉን በመክፈት በባንድራ እንጨት አፉን በመክፈት ወደ ሕክምና ማእከል በመውሰድ እንዳዳኑትም ተናግረዋል።

    አቶ ኢሳያስ ናስር ቀደም ሲል የወልቂጤ ከነማ ሥራ አስኪያጅ የነበሩ ሲሆ ወጌሻ መኮንን ዓመርጋ ከሕክምናው ሙያው በተጨማሪ ክለቡን ውጤታማ እንዲሆን ከፍተኛ መስዋትነት የከፈሉ ምርጥ ባለሙያ ናቸው ብለው ይመስክሩላቸዋል። አክለውም፥ ስፖርተኞች የከፋ አደጋ እንኳን ቢደርስባቸው ጊዜያቸውንና ዕውቀታቸውን በመጠቀም የተቻላቸውን ጥረት በማድረግ ጉዳት የደረሰባቸው ሲታደጉ ነው የሚታዩት። ከስፖርተኞች ጋር ጥሩ ፍቅር በማሳየት ከብሔራዊ ሊግ ጀምሮ ክለቡ አሁን ለደረሰበት ሁኔታ የአንበሳውን ሥራ ሰርተዋል፤ አሁንም ድረስ በበጎ ፍቃደኝነት በሙያው አገልግሎት በመስጠት ናቸው በማለት የወጌሻ መኮንን አመርጋ ታታሪነት ይመሰክራሉ። አቶ ኢሳያስ በመቀጠልም የሙያና የዕውቀት ሽግግር እንዲኖር ለማድረግ መንግስት እነዚህ የወጌሻ ባለሙያተኞች በተገቢው ምቹ የሥራ ቦታ ቢያመቻችላቸው የተሻለ ሥራ እንዲሠሩ ያስችላቸዋል ብለዋል።

    አንዳንድ የአገልግሎቱ ተጠቃሚ የህብረተሰብ ክፍሎች በሰጡት አስተያየት ወጌሻ መኮንን ዓመርጋ ቅንና ለሙያው ክብር ሰጥተው የሚሠሩ ባለሙያ እንደሆኑ፣ ሰውን ለማዳን እንጂ ገንዘብ ማትረፍን ዓላማ አድርገው የማይሠሩና አቅም ለሌላቸው በነጻ ሕክምና እንዲያገኙ በማድረግ ከህመማቸው እንዲድኑ ለማድረግ ከፍተኛ ጥረት የሚያደርጉ ባለሙያ መሆናቸውን ይመሰክሩላቸዋል። የዚህ ጹሁፍ አዘጋጅም ወጌሻ መኮንን ዓመርጋ በሙያው ያላቸውን የካበት ልምድ እና ህብተረሰቡን ለማገልገል ያላቸውን ከፍተኛ ፈላጎት ከግምት ውስጥ በማስገባት ለሙያው ያላቸውን መልካም ፍቃድ የበለጠ አጠናክሮ እንዲሰራበትና በተለያዩ ምክንያቶች የአካል ጉዳት የሚደርስባቸው የህብረተሰብ ክፍሎችን እንዲታደግ እያልኩኝ ወጌሻ መኮንን ዓመርጋ መንግስት በዘርፉ ውጤታማ ሥራ እንዲሰራ የመስሪያ ቦታ እንዲያመቻችለት እና ተተኪ ባለሙያተኞች መፍጠር ይኖርበታል።

    ምንጭ፦ የጉራጌ ዞን ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    መኮንን ዓመርጋ


    Semonegna
    Keymaster

    ለገጣፎ ለገዳዲ ከተማ መኖሪያ ቤታቸው ለፈረሱባቸው ዜጐች ተገቢዉን ድጋፍ እና ተመጣጣኝ ካሳ በአስቸኳይ እንዲያደርጉና በሠላም የመኖር መብታቸውን እንዲያስጠብቁላቸው የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ጉባኤ (ሰመጉ) ጠይቋል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – በአዲስ አበባ ዙሪያ ኦሮሚያ ልዩ ዞን፣ ለገጣፎ ከተማ፣ የዜጐች መኖሪያ ቤት መፍረሱ በእጅጉ እንዳሳሰበው የገለፀው የተባበሩት መንግስታት (ተመድ)፥ ጉዳዩን በትኩረት እንደሚመረምር አስታውቋል። በተባበሩት መንግስታት የመኖሪያ ቤት ምጣኔ ኃላፊዋ ለይላኒ ፋራህ (Ms. Leilani Farha) እንደገለፁት፥ በለገጣፎ 12ሺህ ቤቶች እንዲፈርሱ መወሰኑ በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎችን ቤት አልባ አድርጐ፣ ለእንግልት ይዳርጋል፤ ይህም ግልጽ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ነው ብለዋል።

    ስለ ቤቶቹ መፍረስ መረጃው ለተቋማቸው መድረሱን ያረጋገጡት ለይላኒ ፈራህ፥ በቀጣይ ጉዳዩ በልዩ መርማሪዎች ተመርምሮ፣ በዚህ ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት ላይ የተሳተፉ ወገኖች እንዲጋለጡ ይደረጋል ብለዋል። የዜጐችን መኖሪያ ቤት በዚህ መልኩ ማፍረስ በተባበሩት መንግስታት፣ ሀገራት ቃል ኪዳን የገቡለትን የማንኛውም ዜጋ፣ መጠለያ መኖሪያ ቤት የማግኘት መብት በእጅጉ የሚፃረር ነው ብለዋል – ኃላፊዋ።

    በሌላ በኩል የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ጉባኤ (ሰመጉ) በለገጣፎ ዜጐች መጠለያ አልባ መደረጋቸውን በጽኑ አውግዞ፥ ቤት ለፈረሰባቸው ወገኖች፣ የፌደራል መንግስትና የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ተገቢውን ድጋፍና ተመጣጣኝ ካሣ በአስቸኳይ እንዲያቀርብ እንዲሁም እየተካሄደ ያለው የመኖሪያ ቤቶችን የማፍረስና ዜጐችን የማፈናቀል ተግባር በአስቸኳይ እንዲቆም ጠይቋል።

    የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ጉባኤ በጉዳዩ ላይ ያወጣው መግለጫ የሚከተለው ነው።

    ዜጐችን ማፈናቀል በአስቸኳይ ይቁም!!

    በኦሮሚያ ክልል አዲስ አበባ ዙሪያ ልዩ ዞን የለገጣፎ ለገዳዲ ከተማ አስተዳደር በ01 እና 02 ቀበሌዎች፣ ጭላሎ፣ ወበሪ፣ ለገዳዲ ቄራ፣ ገዋሳ፣ እና በከተማዋ ውስጥ በሚገኙ የተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ መኖሪያ ቤቶችን “ህገወጥ ግንባታዎች ናቸው፤ ለአረንጓዴ ልማት ይፈለጋሉ” በማለት ከየካቲት 12 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ በኃይል በማፍረስ ላይ ይገኛል። የከተማዋ ከንቲባ ለመገናኛ ብዙሃን እንደገለፁትም በቀጣይም ከ12 ሺህ በላይ ቤቶችን እንደሚያፈርሱም አረጋግጠዋል። ሰመጉ ስለጉዳዩ የከተማዋን ከንቲባ ለማነጋገር ያደረገው ጥረት አልተሳካም።

    ሰመጉ ያነጋገራቸው ቤቶቻቸው የፈረሱባቸው በርካታ ዜጐች እንዳስረዱት ከ1997 ዓ.ም. ጀምሮ በመንግስት ላይ እምነታቸውን ጥለው በተለያየ ወቅት በገዙት ቦታ ላይ የገነቡትን መኖሪያ ቤቶች በመገንባት እና አካባቢ በማልማት ከተማዋን ለእድገት አብቅተዋታል። በእነዚሁ ዓመታት ውስጥም የአካባቢው የመንግስት ኃላፊዎች እያወቁት የመብራት እና ውሃ አገልግሎት ተጠቃሚዎች መሆናቸውን፣ ግብር ሲከፍሉ መቆየታቸውን፤ በተለያዩ አስተዳደራዊና የልማት እንቅስቃሴ ላይ የነቃ ተሳትፎ ሲያደርጉ መቆየታቸውንም አስረድተዋል። ይሁን እንጂ የከተማዋ አስተዳደር ከክልሉ ፖሊስ ጋር በመተባበር ከነዋሪዎች ጋር በቂ ምክክር ሳያደርግ እና ሊመጣ የሚችለውን ሰብዓዊ ቀውስ ላይ ምንም ዓይነት ቅድመ ዝግጅት ሳይኖረው ቤቶችን በማፍረስ ህፃናት፣ ሴቶችና አቅመ ደካሞችን ጨምሮ በሺዎች የሚቆጠሩ ዜጐች ሜዳ ላይ እንዲወድቁ አድርጓል። በዚህም የዜጐችን ለኑሮ አመቺ በሆነ አካባቢ የመኖርን መብት፣ ንፁህ የመጠጥ ውሃና ምግብ የማግኘት መብት፣ የአካል ደህንነት መብት እንዲሁም ሌሎች ተያያዥ መብቶች ተጥሰዋል።

    የከተማው አስተዳደር የወሰደውን የኃይል እርምጃ ይበልጥ አስከፊ እና አጠያያቂ የሚያደርገው ከመኖሪያቸው በ7 ቀናት የማስጠንቀቂያ ጊዜ በኃይል እንዲፈናቀሉ ለተደረጉ ዜጐች ምንም ዓይነት አማራጭ የመኖሪያ ስፍራም ሆነ ጊዜያዊ የመጠለያ ስፍራ ያልተዘጋጀላቸውና ሰብዓዊ እርዳታም ያልተደረገላቸው መሆኑ ነው።

    የፌዴራል መንግስትም ሆነ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት በዜጐች ላይ እየተፈፀመ ያለውን መጠነ ሰፊ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ተገቢውን ትኩረት በመስጠት፤ እየተካሄደ ያለውን የመኖሪያ ቤቶች ማፍረስና ዜጐችን ማፈናቀል በአስቸኳይ እንዲያስቆሙ፣ መኖሪያቸው ለፈረሱባቸው ዜጐች ተገቢዉን ድጋፍ እና ተመጣጣኝ ካሳ በአስቸኳይ እንዲያደርጉና በሠላም የመኖር መብታቸውን እንዲያስጠብቁላቸው ሰመጉ ይጠይቃል።

    ምንጮች፦ አዲስ አድማ ጋዜጣሰመጉሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ጉባኤ


    Anonymous
    Inactive

    ለ123ኛው የአድዋ ድል መታሰቢያ በዓል የሚደረገው ዝግጅት መጠናቀቁን የአዲስ አበባ አስተዳደር አስታወቀ
    —–

    123ኛው የአድዋ ድል መታሰቢያ በዓል ምክንያት በማድረግ ለበዓሉ አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት መጠናቀቁን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አስታወቀ።

    የከተማ አስተዳደሩ የኪነ ጥበብ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ዛሬ በሰጠው መግለጫ በዓሉ የአድዋ ድልን ለቀጣዩ ትውልድ ለማስተላለፍ በሚያስችሉ የተለያዩ መርሃ ግብሮች ታስቦ ይውላል ብለዋል።

    የቢሮው ኃላፊ ረዳት ፕሮፌሰር ነብዩ ባዬ በሰጡት መግለጫ የአድዋ ድል የአባቶች ተጋድሎ መስዋዕትነት የሚዘከርበት በዓል ነው ብለዋል።

    በዋዜማው በጣይቱ ሆቴል የኪነጥበብ ድግስ መዘጋጀቱም በመግለጫው ተገልጿል።

    በተመሳሳይ በዋዜማው በሚኒሊክ አደባባይ የተለያዩ ትያትር ቤቶች የባህል ትሪዒቶችን ጨምሮ የተለያዩ ዝግጅቶችን ያቀርባሉ።

    በዕለቱም በሚኒሊክ አደባባይ ድሉን በማስመልከት የተለያዩ መርሃግብሮች ይከናወናሉ።

    በምኒሊክ አደባባይ የሚኖረው መርሃግብር ከተጠናቀቀ በኋላም ከሚኒሊክ አደባባይ እስከአድዋ ድልድይድረስ የእግር ጉዞ ይካሄዳል።

    ድሉን ከትውልድ ወደ ትውልድ ለማስተላለፍ በማሰብ በተጨማሪም በዕለቱ በእንጦጦ ቤተመንግስት ግብር የማብላት ስነስርዓት ይከናወናል።

    ከ8 ሰዓት ጀምሮ ደግሞ በመስቀል አደባባይ አንጋፋና ወጣት አርቲስቶች የተለያዩ ዝግጅቶችን እንደሚያቀርቡም ይጠበቃል።

    በተያያዘም 123 የአድዋ ድል ለማሰብ የደራሼ ባህል ቡድን አባላት አዲስ አበባ ገብተዋል።

    የአድዋ ድል ከ123 ዓመታት በፊት በአድዋ ተራሮች ላይ የተደረገ ኢትዮጵያውን አባቶች አውሮፓዊውን ቅኝ ገዢ ጣሊያንን መክተው የመለሱበት መሆኑ ይታወሳል።

    ምንጭ፦ ፋና ብሮድካስቲንግ

    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት የሕብረተሰቡን ዘርፈ ብዙ የጤና ችግሮች ለመፍታት በሚደረገው ጥረት ባለድርሻ አካላት በመናበብ እና አቅማቸውን ይበልጥ አጠናክረው መሥራት እንዳለባቸው ተገለጸ።

    የኢንስቲትዩቱ የሕብረተሰብ ጤና አደጋዎች ቁጥጥር ማዕከል የስድስት ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ ከየካቲት 18 እስከ 21 ቀን 2011 ዓ.ም. በኢንስቲትዩቱ አዳራሽ ተካሂዷል።

    የዕቅድ አፈጻጸም ግምገማው ዋና ዓላማ በሃገር አቀፍ ደረጃ የሕብረተሰብ ጤናን ከማስጠበቅ አንጻር የተሠሩትን በርካታ የሕብረተሰብ ጤና አደጋዎች ቁጥጥር ከዕቅድ አኳያ ምን ያክሉን ማሳካት እንደተቻለ፥ በመቀጠልም የታዩ ክፍተቶችን በመለየት በቀጣይ የተሻሉ ዘዴዎችን በመቀየስ ችግሮቹን ለማስወገድ ታስቦ የተዘጋጀ የውይይት መድረክ ነበር።

    የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ኤባ አባተ በመክፈቻ ሥነ-ስርዓቱ ወቅት እንደገለጹት አጠቃላይ የሕብረተሰቡን ጤና አደጋዎች ለመከላከልና ለመቆጣጠር ይቻል ዘንድ ከፌዴራል ጀምሮ እስከ ታችኛው የሕብረተሰብ ክፍል ያለው አስተዳደራዊ መዋቅር ሰንሰለቱን ጠብቆ ጠንካራ የሆነ መስተጋብር ሊፈጥር ይገባል፤ በመሆኑም የክልል ጤና ቢሮዎች እና የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት በጤናው ዘርፍ በቅንጅት እየሠሩ የሚገኙ ሲሆን፥ ይህ መድረክ በዚህ የግማሽ ዓመት የሕብረተሰቡን ጤና ችግሮች ከመፍታት አንጻር የታዩ ጠንካራ ሥራዎች እና ድክመቶችን በመለየት በቀጣይ ለሚሠሩ ተግባራት ላይ የጋራ መግባባት የሚደረስበት በመድረክ ነው ብለዋል።

    ዶ/ር በየነ ሞገስ የኢንስቲትዩቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር በበኩላቸው እንደሀገር ከሕብረተሰብ ጤና አደጋዎች ቁጥጥር አንጻር እየሠራን ነው፣ ምን ላይስ እንገኛለን፣ በዚህ ግማሽ ዓመት ምን ዋና ዋና ውጤቶች ተመዝግበዋል የሚሉትን በመፈተሽ በቀጣይ ችግር ፈቺ የሆኑ አቅጣጫዎችን በማስቀመጥ የጋራ መግባባት የሚደረስበት መድረክ ነው የተዘጋጀው ሲሉ ተናግረዋል።

    የሕብረተሰብ ጤና አደጋዎች ቁጥጥር ማዕከል ከዕቅድ አንጻር በግማሽ ዓመቱ ያከናወናቸውን ተግባራት፣ በመቶ ቀናት ውስጥ የታቀዱ ተግባራት፣ የነበሩ ጠንካራና አፈፃፀሞችና የነበሩ ክፍተቶች እንዲሁም የነበሩ ስጋቶች፣ ተይዞ የነበረው የበጀት አፈጻጸም፣ ዓለም አቀፍና አገር አቀፍ በሽታዎች ከዕቅድ አንጻር ምን ደረጃ ላይ እንደሚገኙ፣ ሀገራዊ የጤና ደህንነት እቅድ፣ የሕብረተሰብ ጤና አደጋዎች ቁጥጥር ስጋቶች፣ ተጋላጭነትና ምላሽ ዳሰሳ ጥናት በግምገማ መድረኩ ላይ በዝርዝርና በስፋት ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል።

    የጤና ሚኒስቴር እና በስሩ የሚገኙ መሥሪያ ቤቶች፣ የኢንስቲትዩቱ የበላይ ኃላፊዎች እና ባለሙያዎች፣ የክልል ጤና ቢሮዎች፣ የሕብረተሰብ ጤና አደጋዎች ቁጥጥር የሥራ ሂደት ኃላፊዎች፣ የዕቅድ ክትትል እና ምዘና ኃላፊዎች እንዲሁም የእናቶችና ህፃናት ቡድን መሪዎች በውይይትና ግምገማ መድረኩ ላይ ተሳታፊ ሆነዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት / ሰሞነኛ ኢትዮጵ

    የኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት


    Semonegna
    Keymaster

    የአድዋ ድል ለኢትዮጵያ ነጻነትና ኩራትን፣ በዓለም ዙሪያ በተለይ በአሜሪካዎቹ ሰፋፊ እርሻዎች ለ500 አመታት በባርነት ለተጋዙ ጥቁር ሕዝቦች ደግሞ፥ የማንነት ማረጋገጫ፣ የዘመናት ጭቆናና የስነ-ልቦና ቁስልን አውልቆ የመጣያ የተስፋ ትንሳኤ ሆኖ ነበር።

    ሰለሞን ተሰራ (ኢዜአ)

    በርሊን ከተማ ውስጥ የጀርመን ግዛት አስተዳዳሪ (ቻንስለር)በነበረው ኦቶ ቫን ቢስማርክ (Otto von Bismarck) መኖርያ ሳሎን ፌሽታ በፌሽታ ሆኗል። እለቱ እንደ አውሮጳውያን አቆጣጠር (እ.አ.አ) የካቲት 16 ቀን 1885 ሶስት ወር ሙሉ አሰልቺ ውይይት የተደረገበትና ዋና ዋናዎቹ የአውሮፓ ቅኝ ገዢዎች ተሰብስበው ”አንተ ይሄን ያዝ አንተ ያንን ያዝ” ተባብለው ከወታደራዊ ዘመቻ በፊት አፍሪካን የተቃረጡት።

    በስብሰባው ከ80 በመቶ በላይ የሚሆነውን የአፍሪካ መሬት የሃሳብ መስመር እያሰመሩ ያለከልካይ ተከፋፈሉት። ከሦስት ወራት በላይ (እ.አ.አ ከኅዳር 15 ቀን 1884 እስከ የካቲት 26 ቀን 1885) ሲካሄድ የነበረው የበርሊን ጉባዔ (Berlin Conference) መደምደሚያ የነበረው ‘የበርሊን ጉባዔ ጠቅላላ ግብአተ ሰንድ’ (በእንግሊዝኛው፥ General Act of Berlin conference) በታሪክ አጥኚዎችና ፖለቲካ ተመራማሪዎች ዘንድ በ አብዛኛው “አፍሪካን የመቀራመት ጉባዔ” (“The Division of Africa” ወይም “Scramble of Africa”) ተብሎ ይታወቃል። በጉባዔው ላይ የጀርመን፣ ኦስትሮ-ሀንጋሪ፣ ቤልጅየም፣ ዴንማርክ፣ ፈረንሳይ፣ ብሪታንያ፣ ጣልያን፣ ኔዘርላንድስና ፖርቱጋል ተወካዮች ተገኝተዋል።

    አውሮፓውያን አፍሪካን ለመቀራመት በበርሊን ስምምነት ሲያደርጉ፤ አፍሪካዊያን ደግሞ የውጭ ወራሪዎችን ለመከላከል ከዚህ አለፍ ሲልም እርስ-በርሳቸው መተነኳኮስ የጀመሩበት ጊዜ እንደነበር ታሪክ ያስረዳል። ወቅቱ በአራቱም የአህጉሪቷ አቅጣጫዎች የሚገኙ ነገስታት እና የጭፍራ አለቆች በተናጠል ከአውሮፓውያኑ ጋር በገጠሟቸው ውጊያዎች ትርጉም ያለው ስኬት ሳያገኙ፤ አፍሪካውያን በቅኝ ግዛት መውደቅ የጀመሩበት ነው።

    ይህን ተከትሎ ጣልያንም ኢትዮጵያን በቁጥጥሯ ስር ለማድረግ ብትነሳም እምቢተኛው ጥቁር ሕዝብ ማንነቱንና ክብሩን አሳልፎ ላለመስጠት በመወሰኑ ያልተመጣጠነ ውጊያ ቢገጥሙም አሳፍሮ መልሷታል። ዘመናዊ የጦር መሣሪያ የታጠቀው የጣልያን ጦር የቅኝ ግዛት ተልእኮውን እውን ለማድረግ የተመመው በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ በአግባቡ የሰለጠኑ ወታደሮችን ይዞ ነው። ነገሩ እንደታቀደው ሳይሆን ቀርቶ የጣልያን ጦር በአድዋ ድል ተነሳ። ታሪክም ይህን ጦርነት <የአድዋ ጦርነት> (The Battle of Adwa) በማለት፣ ለጥቁር ሕዝቦች ታላቅ መነቃቃትና ተስፋ የሰጠውን የጦርነቱን ድል ደግሞ <የአድዋ ድል> (The Victory of Adwa) ብሎ ሲገዝበው ይኖራል።

    የታሪክ ሊቃውንት እንደሚያስቀምጡት የአድዋ ጦርነት በአፍሪካ ምድርና ታሪክ ከተከናወኑት ጦርነቶች ከፍተኛውን የዋጋና የክብር ስፍራ ይዟል። የሰሜን አፍሪካን በስፋት ይገዛ የነበረው አኒባል የአልፕን ተራሮች ዞሮ የአውሮፓን ኃያል መንግሥት ካሸነፈ ወዲህ (Hannibal’s crossing of the Alps)፣ አንድ አውሮፓዊ ጦር በአፍሪካውያን ጦር ሲሸነፍ ለመጀመሪያ ጊዜ ነበር። ስለሆነም፣ ጦርነቱ ብዙ መልክና ብዙ ቅጽል ተሰጥቶታል።

    የአድዋ ድል ለኢትዮጵያ ነጻነትና ኩራትን፣ በዓለም ዙሪያ በተለይ በአሜሪካዎቹ ሰፋፊ እርሻዎች ለ500 አመታት በባርነት ለተጋዙ ጥቁር ሕዝቦች ደግሞ፥ የማንነት ማረጋገጫ፣ የዘመናት ጭቆናና የስነ-ልቦና ቁስልን አውልቆ የመጣያ የተስፋ ትንሳኤ ሆኖም ነበር።

    የታሪክ ተመራማሪና ደራሲውፖል ሄንዝ በጻፉት ንብረ ጊዜ፥ የኢትዮጵያ ታሪክ (Layers of Time: A History of Ethiopia, by Paul B. Henze) በተሰኘው የታሪክ ድርሳናቸው “አውሮፓውያን የፈለጉትን ገድለዋል፣ ባሪያ ፈንግለዋል፣ አካባቢን፣ ሀብትን፣ ጉልበትን መዝብረዋል፤ ምክንያቱ በግልጽ ባይታወቅም ‘ኢትዮጵያን በጦር ከማስገበር ይልቅ እንቃረጣት ብለው’ ብሪታኒያ፣ ፈረንሳይና ጣልያን የሦስትዮሽ ስምምነት (Tripartite Agreement) ተፈራርመው አጼ ምኒልክን ‘እወቁልን’ ብለው ጦማር ሰደዋል። አጼ ምኒልክም ‘ስለነገራችሁኝ አመሰግናለሁ፣ ነገር ግን እኔ በሌለሁበት የተወሰነውን አላውቅም’ በማለታቸው ጣልያን ኢትዮጵያን በወረራ ያዘች።

    ወረራውን ለመቀልበስ በአጼ ምኒልክ የሚመራው የኢትዮጵያ መንግስት ሰላማዊ ትግል ቢያደርግም የወራሪዎቹ ብልጣብልጥነት ጦርነቱን አይቀሬ አደረገው። ወደ ጦርነት ተገዶ የገባው የኢትዮጵያ የጦር ኃይል በአምባላጌ፣ በመቀሌና በአድዋ በተከታታይ ባደረገው ጦርነት የበላይነት ወስዶ የካቲት 23 ቀን 1988 ዓ.ም. ላይ በአድዋ የድል ባለቤት መሆኑ ተበሰረ። የድሉ ዜና እንደናኘ በአፍሪካ ተስፋ፣ በአውሮፓ ድንጋጤ ፈጠረ። የኢትዮጵያ ድል አውሮፓውያን በዓለም የነበራቸውን ልዕለ ኃያልነት ለመጀመሪያው ጊዜ ጥያቄ ውስጥ ከቷል። ፖል ሄንዝ ”ዛሬ ላይ ሆነን ስናየው” የኢትዮጵያ ድል የአውሮፓ ተሰሚነት የቁልቁለት ጉዞ መነሻ ነበር” ሲሉ በጽሁፍ አስፍረዋል።

    ድሉ ታላቋ ብሪታንያን ኢትዮጵያን በእኩል ዓይን ዓይታ ”የምስራቁን የደቡቡን የምእራቡን ድንበራችንን እንካለል” ብላ በፊርማ እንድታጸድቅ አስገድዷታል። ከዚህ በተጨማሪ በአውሮፓ ቅኝ ግዛት መዳፍ ስር ሲማቅቁ የነበሩትን አፍሪካውያን እና ካሪቢያን ጥቁሮች ለነፃነታቸው እንዲታገሉ ብርታት እና ምሳሌ ሆኗቸዋል። ለጥቁር አሜሪካውያን ምሁራን ከፍተኛ የመንፈስ መነቃቃት እንዲያገኙ አድርጓል።

    የአድዋ ድል (ማለትም፥ በአውሮፓውያን ዘንድ የአድዋ ጦርነት ሽንፈት) በተሸናፊ የአውሮፓ ገዢዎች ዘንድ ቁጭት ፈጥሮ ከ30 ዓመት በኋላ ፋሺዝም በጣልያን ውስጥ ስር እንዲሰድ እና መሪ የፖለቲካ ርዕዮተ ዓለም (አይዲዮሎጂ) እንዲሆን ምክንያት ሆኗል። ለኢትዮጵያ ደግሞ የተረጋጋ መንግስታዊ አስተዳደር አስገኝቷል። በዚህ የከሸፈ የቅኝ-ግዛት ዕቅድና የአውሮፓውያን ተስፋፊነት የተደሰቱ ሶሻሊስት አመለካከት ያላቸው ወገኖች በጣልያን፣ በብሪታንያና በፈረንሣይም ነበሩ።

    ዕውቁ የታሪክ ተመራማሪና የአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ ፕሮፌሰር የነበሩት ሪቻርድ ፓንክረስት እና ሌላው ኢትዮጵያዊ የታሪክ ተማራማሪ ዶ/ር አብዱልሳማድ አህመድ በጋራ በጻፉት ስለ አድዋ ድል በጻፉት መጽሐፍ (Adwa Victory Centenary Conference, 26 February – 2 March 1996) ውስጥ እንዳሰፈሩት የኢጣሊያኑ ክሪቲካ ሶሻሌ (Critica Sociale) ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ ፊሊፖ ቱራቲ (Filippo Turati) በወኔና በምልዓት ለእውነት ስለእውነት ጻፈ። “ጣልያን ወደ አድዋና ወደ ሌሎችም ከኢትዮጵያ ጋር ወደ ተደረጉት ጦርነቶች የገባችው፣ ለእንግሊዛውያን አገልጋይና አሽከር ሆና ነው። በዚህም የተነሳ የጣሊያናውያን ሀብትና ደም ያላግባብ ፈሰሰ” ሲል ወረራውን በማውገዝ ድፍረት የተሞላበት ጽሁፉን ማስነበቡን ይገልጻሉ።

    ጋዜጠኛው በጽሁፉ “የጣልያንና የእንግሊዝ መንግሥታት በአፍሪካ ስለተቀዳጁት የቅኝ-ግዛትና የተስፋፊነት ድል እንደጽጌረዳ የፈካ ውሸት እየፈበረኩ ይመጻደቁ እንጂ፣ በእርግጥ ኢትዮጵያ ድል አድርጋለች… ቪቫ ምኒልክ! ቪቫ ኢትዮጵያ!” ሲል አወድሷል።

    በአጼ ምኒልክ መሪነት የኢትዮጵያ ኃይል በጣልያን ወራሪ ኃይል ላይ በአድዋ የተቀዳጀው ድል ድልድይ ሆኖ የጥንታዊቷን ኢትዮጵያ የታላቅነት ክብር ከዘመናዊ ዓለም ጋር ያገናኘ ድልድይ ሆኗል። ታዲያ ይህ ድልድይ በ1890ዎቹ ግንባታው የተጀመረው የተቀረው የአፍሪካ ክፍል በውጭ ኃይሎች አገዛዝ ቀንበር ስር ሲወድቅ ኢትዮጵያውያን ብቻ በተከታታይ የተሰነዘረባቸውን ወረራ በድል ሲመልሱ ነበር።

    በዚያው ክፍለ ዘመን ኢትዮጵያውያን ለውጭ ወራሪዎች የማይንበረከኩ መሆናቸውን ማሳየታቸውን ማስታወስ ይቻላል። በ1870ዎቹ የግብፃውያንን፣ በ1880ዎቹ የመሃዲስቶችን ተደጋጋሚ ጥቃቶች መክተው መልሰዋል። የአድዋ ድል ደግሞ ይህን የነፃነት ቀናዒነት ይበልጥ ከማድመቅ አልፎ የዓለምን ትኩረት ስቧል።

    የአውሮፓ መንግሥታት ዲፕሎማቶቻቸውን ወደአዲስ አበባ እንዲልኩ፣ ከኢትዮጵያ ጋር 19 ድንበርን የሚመለከቱ ስምምነቶችን እንዲፈራረሙ አደረጋቸው ። በአርነት ትግሉ መስክ በቅኝ ግዛት ሥር ለነበሩት እህት የአፍሪካ አገሮች ታጋዮችም ኢትዮጵያ ፋና ወጊ መብራታቸውና የራዕይ ምንጫቸው ነበረች።

    የአድዋ ድል የፓን አፍሪካን ንቅናቄ መሠረት መሆኑን የኢትዮጵያውያንን የአድዋ ውሎ ከዘከሩ የታሪክ ጠበብት መካከል የዋሽንግተኑ የታሪክ ሊቅ ፕሮፌሰር ራየሞንድ ጆናስ፥ “የአድዋ ጦርነት – የአፍሪካውያን ድል በዘመነ ግዛት” (The Battle of Adwa: African Victory in the Age of Empire, by Raymond Jonas” በሚለው መጽሐፋቸው አስፍረዋል፡፡ በዚህ ጽሁፋቸው “የአድዋ ድል ለአፍሪካውያን ቅኝ አገዛዝን ታግሎ መጣል እንደሚቻል ያሳየ፣ የኢትዮጵያንም ታላቅነት ያስመሰከረ” ስለመሆኑ ደጋግመው አውስተዋል።

    ለዚህም ነው የናይጄሪያ ድኀረ ነፃነት የመጀመሪያ ፕሬዚዳንት የነበሩት ዶ/ር ናምዲ አዚኪዊ (Nnamdi Azikiwe) “ኢትዮጵያ ጥቁር ራሱን በራሱ የሚያስተዳድርባት አገር ነች። በዚህ ክፍለ አህጉር ላይ የአፍሪካ ቀደምት አባቶች የመሠረቱት መንግሥት የታሪክ ዋቢ ነች። ኢትዮጵያ ከዘመን ወደ ዘመን እየተሸጋገረች ህልውናዋን ጠብቃ መኖሯ የሚደነቅና መደነቅም ያለበት ነው” በማለት የተናገሩት።

    ከአድዋው ድል አርባ ዓመት በኋላ ጣልያን ቂሟን ልትወጣ ወረራ ስታካሂድ በግልጽም ይሁን በተዘዋዋሪ የአውሮፓና የአሜሪካ መንግሥታት ከእሷ ጎን ቆመዋል። በተቃራኒው ድሉ በአፍሪካም ይሁን በተቀረው ዓለም የተቀጣጠለውን የአፍሪካዊነት የትግል ስሜት አነሳስቷል፤ እልህ አጭሯል። በአጠቃላይ መላው ጥቁር ሕዝብ፣ በቁጥር አነስተኛ ቢሆኑም ለፍትህ የታመኑ አውሮፓዊያን ነጮችም ለኢትዮጵያ ያላቸውን ወገናዊነት እንዲያጠናክሩ ጥርጊያውን አመቻችቷል። የነኝህም ጥረት በውጭ የነበረውን ሕዝባዊ ድጋፍ ወደ ኢትዮጵያ ያደላ እንዲሆን አድርጎታል። ባህላዊ እሴቶቻቸውን ያልጣሉ የአፍሪካ ምሁራን ከነበሩባቸው የአህጉሩ ከተሞች፣ ከካርቢያን ደሴቶች፣ ከጥቁር አሜሪካዊያን በኩል ተሰባስበው ወረራው ያጫረባቸውን የመጠቃት ስሜት በይፋ አንጸባርቀዋል።

    ደቡብ አፍሪካ ውስጥ ለነበሩት የአፍቃሪ ኢትዮጵያዊነት እንቅስቃሴ መሪዎችም የአድዋው ድል የሞራል እርሾ ሆኗቸዋል። ከእንቅስቃሴው ግንባር ቀደም መሪዎች አንዱ ጀምስ ድዋኔ (James Mata Dwane) ግብጽና ሱዳን ውስጥ ያሉትን ክርስቲያን አፍሪካዊያን ሁኔታ ትኩረት ሰጥተው መፍትሄ ይፈልጉለት ዘንድ ለአጼ ምኒልክ ደብዳቤ የፃፉት የአድዋውን ድል ተከትሎ ነበር።

    ስለአድዋ ድል የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩት ዊንስተን ቸርችል “የካቲት 23 ቀን 1888 የአድዋ ጦርነት ተካሂዶ፥ ጣልያን በኢትዮጵያውያን የደረሰባት ሽንፈት ደረሰባት። (ይህም) ሌሎች ሕዝቦችን የሚነካ ሁለት ውጤቶች አስከተለ፤ አንደኛ፥ ሰሜን አፍሪካ ላይ አውሮፓዊ ክብርን ትልቅ ምች መታው። ሁለተኛ፥ በአውሮፓ ፖለቲካ ማንነት ረገድ የኢጣልያ ዋጋ ወደታች ወረደ” ብለው ጽፈዋል።

    ዊንስተን ቸርችል ስለ ኢጣልያ ሽንፈትና ውጤቱ ከመጻፍ ይልቅ ስለ ኢትዮጵያ ድልና በአፍሪካና በሌሎቹ ጭቁን አገሮች ዘንድ የኢትዮጵያን ማንነት ሽቅብ መናሩን መግለጽ አልፈለጉም። ይህ ሊሆን የቻለው ምናልባትም አድዋ ላይ የተገኘው ድል ለጥቁር ሕዝቦች ከነጻነት ለመውጣት የተስፋ እርሹ በመሆኑ፣ ለአውሮፓውያኑ የቅኝ ግዛቶቻቸውን ሊያጡ የሚችሉበት ጅምር በመሆኑ ሊሆን ይችላል።

    የሆነ ሆኖ አድዋ ላይ የተለኮሰው የድል ችቦ በቅኝ ግዛት ስር ለነበሩት የአፍሪካ አገሮች ቀንዲል ሆኗል። ለዚህም ክብር ለመስጠት 17 የአፍሪካ አገሮች የሰንደቅ ዓላማ ቀለማቸውን ከኢትዮጵያ ወስደዋል። አረንጓዴ፣ ቢጫና ቀይ የሆነው የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ ቀለም ማሊ፣ ጋና፣ ካሜሩን … አገሮች በተለያየ ቅርጽ የአገራቸው መለያ ሰንደቅ አላማ እንዲሆን አድርገዋል።

    Pankhurst, Richard. “”Viva Menelik!”: The Reactions of Critica Sociale to the Battle and to Italian Colonialism” In Adwa Victory Centenary Conference, 26 February – 2 March 1996, edited by Abdussamad Ahmad and Richard Pankhurst, 517-548. Addis Ababa: Institute of Ethiopian Studies, Addis Ababa University, 1998.

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የአድዋ ድል


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – አዲስ አበባን እንደስሟ ውብ አድርጎ ለትውልድ ለማሸጋገር የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የከተማዋ ምክትል ከንቲባ ኢንጂነር ታከለ ኡማ ተናገሩ።

    የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) እንደዘገብው፥ ምክትል ከንቲባ ኢንጂነር ታከለ ኡማ የአዲስ አበባን የወንዞችና ወንዝ ዳርቻዎች ማልማት አዲስ ፕሮጀክትን በይፋ ባስጀመሩበት ወቅት “በተራሮች ከፍታ ላይ የምትገኘው አዲስ አበባ እንደ ስሟ አዲስ ሆና ለትውልድ የምትሸጋገር ውብ ከተማ ማድረግ ይገባል” ብለዋል።

    በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) መሪነት በከተማ አስተዳደሩ አስተባባሪነትና በከተማዋ ነዋሪዎችና በወጣቶች ትብብር ለትውልድ የሚሸጋገር ድንቅ ከተማ መገንባታችንን እንቀጥላለንም ነው ያሉት ኢንጂነር ታከለ። ፕሮጀክቱ ለትውልድ የሚተላለፍ የትውልድ አሻራ ያለበትና ሁላችንም የጋራ እሴቶቻችንን የምናስተላልፍበት በመሆኑ ልንደሰት ይገባል በማለት አጽንዖት ሰጥተዋል።

    ፕሮጀክቱ ከተማዋ እንደስሟ እንድትኖር ወንዞችና የወንዞች ዳርቻዎች ሁሉ የቆሻሻ መናኸሪያ ሳይሆኑ የሰው ልጅ በተለይም ደግሞ ወጣቶች ቁጭ ብለው በመነጋገር ሀሳብ የሚቀያየሩበትና ለቀጣይ ትውልድ የተሻለች የጋራ ሀገር ለመገንባት የሚያስችል መሆኑንም አብራርተዋል።

    ፕሮጀክቱ ከእንጦጦ ተራራ ተነስቶ ፒያሳን አካሎ እስከ ብሔራዊ ቤተመንግስት የሚዘልቅ እንዲሁም በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በኩል እስከ ብሔራዊ ቤተመንግስት ገራዥ የሚያልፍ ሆኖ እንደማሳያ የሚጀመር ነው ብለዋል።

    በከተማዋ የተያዘው የልማት የወደፊት ስሌት (strategy) ሕዝቦቿ ከልማቱ ጋር የሚያድጉና የሚበለፅጉ እንዲሆኑ የሚያስችል እንጂ አንዱን የህንፃ ባለቤት በማድረግ ሌላውን ለማፈናቀል የሚሠራ አለመሆኑንም ተናግርዋል ኢንጂነር ታከለ ኡማ።

    የአዲስ አበባ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ ረዳት ፕሮፌሰር ነብዩ ባዬ በበኩላቸው ከተማዋ ብዙ ታላላቅ ቅርሶች ያሏት፣ አብያተ መንግስት፣ ቤተ እምነቶችና እንደመርካቶ ያሉ የታላላቅ ገበያዎች መገኛ ናት ብለዋል። ከዚህም ባሻገር የኢትዮጵያ ምርጥ ሕዝቦች በፍቅር በአንድነት በደም ተሳስረው የሚኖሩባት ከተማ መሆኗንም አስረድተዋል ኃላፊው።

    ራሳችን ተንፍሰንና ተዝናንተን ቁጭ ብለን የምንወያይበት እነጂ የተጣበበ የአስተሳሰብ መንገድ እንዳይኖረን ሰፋ ያለ የስፍራ አጠቃቀምን የሚያሳዩ የቱሪስት መዳረሻዎች የሉንም ያሉት ኃላፊው፤ ፕሮጀክቱ ለልጆቻችን ልናተርፍላቸው የሚገባ የመዝናኛ፣ የመነጋገሪያና የመናፈሻ ቦታ እንዳለውም ተናግረዋል። ከዚህም ባሻገር ልጆቻችን ሌሎች ሰዎችን ጋብዘው የሚጠቀሙበት የቱሪስት መዳረሻ እንደሚሆንም ተናግረዋል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ምክትል ከንቲባ ኢንጂነር ታከለ ኡማ


    Anonymous
    Inactive

    የመርካቶ አውቶቡስ ተርሚናል ግንባታ 46 በመቶ ደርሷል
    —–

    የመርካቶ አውቶቡስ ተርሚናል ግንባታ 46 በመቶ መድረሱን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የትራንስፖርት ፕሮግራሞች ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ገለጸ።

    የጽህፈት ቤቱ የእግረኛና ብዙሃን ትራንስፖርት አስተዳደር ኃላፊ አቶ ናትናኤል ጫላ እንዳሉት በመርካቶ የተሳፋሪዎችን ምቾት ጠብቆ በርካታ አገልግሎቶችን በአንዴ መስጠት የሚያስችል ዘመናዊ ተርሚናል በ200 ሚሊዮን ብር እየተገነባ ነው።

    ግንባታውን በ2011 በጀት ዓመት ለማጠናቀቅ ታቅዶ በፍጥነት እየተከናወነ መሆኑንና አፈጻጸሙ 46 በመቶ መድረሱን ተናግረዋል።

    20 አውቶቡሶችን በአንድ ጊዜ የሚያስተናግደው ተርሚናሉ የራሳቸው መግቢያና መውጫ ያላቸው ሁለት ወለሎች፣ የአስተዳደር ቢሮዎች፣ የአውቶቡስ መጠበቂያ ቦታ፣ የትኬት መሸጫ፣ የተሳፋሪ መጫኛና ማራገፊያ ስፍራዎችን ያካተተ ነው።

    ከ50-80 ሺህ የመርካቶ ገበያተኛችን የትራንስፖርት እጥረት ለማቃለል ታስቦ የሚገነባው ተርሚናሉ በ4 ሺህ 125 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ያረፈ ሲሆን በሠዓት ለ6 ሺህ የብዙሃን ትራንስፖርት ተጠቃሚዎች አገልግሎት ይሰጣል።

    ከተማ አስተዳደሩ አሮጌ ተርሚናሎችን ዓለም በደረሰበት ደረጃ ማሻሻል፣ የማስተናገድ አቅማቸውን ማሳደግና ማልማት ስራ በመከወን ላይ መሆኑን የገለጹት ኃላፊው፤ የመርካቶ ተርሚናል ግንባታ የመሰረት ድንጋይ የተቀመጠው ነሐሴ 1 ቀን 2010 ዓ.ም እንደነበረ አውስተዋል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ

    Anonymous
    Inactive

    በመዲናዋ በሞተር ብስክሌት በመታገዝ የቅሚያ ወንጀል ከፈፀሙ ግለሰቦች መካከል ግማሽ ያህሉ ተይዘዋል – አዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን
    —–

    በአዲስ አበባ በሞተር ብስክሌት በመታገዝ የቅሚያ ወንጀል ከፈፀሙ ግለሰቦች መካከል ግማሽ ያህሉ መያዛቸውን የመዲናዋ ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ።

    የኮሚሽኑ የኢንዶክትሬሽንና ህዝብ ግንኙነት ምክትል ዳይሬክተር ኮማንደር ፋሲካ ፈንታ በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ አጋማሽ 61 በሞተር ሳይክል የተደገፈ ቅሚያ በከተማዋ መፈጸሙን ገልጸዋል።

    ኮማንደሩ ወንጀሉ የተፈፀመው በከተማዋ በሚገኙ 8 ክፍለ ከተሞች መሆኑንም ተናግረዋል።

    ከፍተኛ የቅሚያ ወንጀል የተፈፀመበት የቦሌ ክፍለ ከተማ 21 በሞተር ሳይክል የተደገፉ ወንጀሎች የተፈፀመበት ሲሆን፥ ዝቅተኛ የቅሚያ ወንጀል የተፈፀመው በልደታ ክፍለ ከተማ መሆኑን ገልጸዋል።

    በአቃቂ ቃሊቲና ቂርቆስ ክፍለ ከተሞች ምንም አይነት በሞተር ብስክሌት የተደገፈ ቅሚያ አለመፈጸሙን ገልጸዋል።

    ኮማንደሩ ወንጀል ፈፃሚዎቹ በራሳቸውና በተከራዩት የሞተር ብስክሌት የቅሚያ ወንጀሉን እየፈፀሙ መሆኑን ገልጸዋል።

    ወንጀሉን ፈጽመው በቁጥጥር ስር የዋሉ ግለሰቦች በፍርድ ቤት ጉዳያቸው እንደተያዘና ቀሪ የወንጀል ፈጻሚዎች ለመያዝ ጥረት እየተደረገ መሆኑን አብራርተዋል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ

    Semonegna
    Keymaster

    ኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባል ለመሆን ከየካቲት 10 ቀን 2003 (እ.ኤ.አ.) ጀምሮ የተለያዩ ቅድመ ዝግጅቶችንና አባል ለመሆን ብቁ የሚያድርጓትን የማሻሻያ እርምጃዎችን ስትወስድ ቆይታለች።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባል ለመሆን የሚያስችላትን የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እየሠራች መሆኑን ንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር አስታወቀ።

    በንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የባለ ብዙ ዘርፍ የንግድ ግንኙነትና ድርድር ዳይሬክተር አቶ ሙሴ ምንዳዬ የዓለም ባንክ የንግድና ክልላዊ ትብብር ዳይሬክተር ጋር ኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባልነት ሂደትን እና የአፍሪካ ነፃ ንግድ ቀጠና ስምምነትን ለማጽደቅ እያደረገች ባለው እንቅስቃሴ ዙሪያ በንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር በተወያዩበት ወቅት ኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባል ለመሆን እና በድርድሩ ሂደት የሚገጥሟትን ችግሮች ተቋቁማ ወደ ድርጅቱ እንድትቀላቀል ለማድረግ በርካታ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ ገልጸዋል።

    ምንም እንኳን ኢትዮጵያ በተከታታይ የኢኮኖሚ እድገት ብታስመዘግብም የግል ዘርፉ በኢኮኖሚው ውስት ያለው ተሳትፎ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየቀነሰ ነው

    አቶ ሙሴ አያይዘው በአሁኑ ወቅት መንግስት በተለይም በአገልግሎት ንግድ ሰጭ ተቋማት ላይ እየሠራቸው ያሉት የማሻሻል (ሪፎርም) ሥራዎች እና የቴሌኮም ድርጅትን የቁጥጥር/ርጉላቶሬ/ መስሪያ ቤት የተለያዩ ዘርፎች ለግሉ ሴክተር ለማስተላለፍ በሚኒስትሮች ምክር ቤት መጽደቁ ሀገሪቷ የዓለም ንግድ ድርጅት አባል ለመሆን የምታደርገውን ድርድር ሊያግዝ የሚችል መልካም አጋጣሚ ነው ያሉ ሲሆን፤ ኢትዮጵያ በ2011 ዓ.ም. 4ኛውን የሥራ ቡድን ስብሰባ ለማካሄድ የተለያዩ ዶክመንቶችን የማዘጋጀት ሥራዎች እየተሰሩ መሆኑንም ተናግረዋል።

    በዓለም ባንክ የማክሮ፣ ንግድና ኢንቨስትመንት ዳይሬክተር ወ/ሮ ካሮሊን ፍረንድ (Caroline Freund) በበኩላቸው ንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር በዓለም የንግድ ድርጅት ድርድር እና በአፍሪካ ነፃ ንግድ ቀጣና ዙሪያ የሚሠራቸው ሥራዎች መልካም መሆናቸውን ገልጸው ወደፊት ለሚደረጉ የግንዛቤ ማስጨበጫ መድርኮች እንዲሁም ዘመናዊና ደረጃውን የጠበቀ ቢሮና መሠረተ- ልማት እንዲኖር ድጋፍ እንደሚያደርጉ ቃል ገብተዋል።

    እ.ኤ.አ. ጥር 1 ቀን 1995 በ124 አገራት የአባልነት ፊርማ የተመሠረተውን የዓለም ንግድ ድርጅት (World Trade Organization)፣ በአሁኑ ሰዓት ዋና መቀመጫውን ጄኔቭ ከተማ፣ ስዊዘርላን አድርጎ 164 አገራትንም በአባልነት አቅፏል።ኢትዮጵያም የዚህ ድርጅት አባል ለመሆን ከየካቲት 10 ቀን 2003 (እ.ኤ.አ.) ጀምሮ የተለያዩ ቅድመ ዝግጅቶችንና አባል ለመሆን ብቁ የሚያድርጓትን የማሻሻያ እርምጃዎችን ስትወስድ ቆይታለች።

    ምንጭ፦ በንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነትና ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    የዓለም ንግድ ድርጅት


Viewing 15 results - 346 through 360 (of 495 total)