በአዲስ አበባ የ51 ሺህ 229 የጋራ መኖሪያ ቤቶች (ኮንዶሚኒየም ቤቶች) የዕድለኞች ስም ዝርዝር

Home Forums Semonegna Stories በአዲስ አበባ የ51 ሺህ 229 የጋራ መኖሪያ ቤቶች (ኮንዶሚኒየም ቤቶች) የዕድለኞች ስም ዝርዝር

Viewing 4 posts - 1 through 4 (of 4 total)
  • Author
    Posts
  • #10078
    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – በዛሬው ዕለት (የካቲት 27 ቀን 2011 ዓ.ም.) በአዲስ አበባ 51 ሺህ 229 የጋራ መኖሪያ ቤቶች (ኮንዶሚኒየም ቤቶች) ዕጣ ማውጣት ሥነ ስርዓት ተካሄደ።

    ዕጣ ከወጣባቸው ቤቶች ውስጥም 32 ሺህ 653 ቤቶች የ20/80 ቤቶች ሲሆኑ፥ ቀሪዎቹ 18 ሺህ 576 ደግሞ የ40/60 ቤቶች ናቸው። በዚህም መሠረት የ20/80 ፕሮግራም ኮንዶሚኒየም ቤቶች ውስጥ 1 ሺህ 248 ስቲዲዮ፣ 18 ሺህ 823 ባለ አንድ መኝታ፣ 7 ሺህ 127 ባለ ሁለት መኝታ እና 5 ሺህ 455 ቤቶች ደግሞ ባለ ሦስት መኝታ ክፍሎች ናቸው። በእነዚህ የ20/80 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ ውስጥ የሚካተቱት በ1997 ዓ.ም ተመዝግበው በ2005 ዓ.ም በነባር መደብ የተመዘገቡና በ2005 ዓ.ም የአዲስ ባለ ሦስት መኝታ ክፍል ተመዝጋቢዎች ናቸው።

    በዕጣ አወጣጥ ሥነ ስርዓቱ ላይ የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ ኢንጂነር ታከለ ኡማ እንደተናገሩት፥ በግንባታ ሂደት ሁሉም ተጠቃሚ እንደሚሆን ቢታሰብም በጥንቃቄ ጉድለት ለጉዳትና ማኅበራዊ ቀውስ የተዳረጉ የህብረተሰብ ክፍሎች አሉ። ኢንጅነር ታከለ ልማት በጋራ ተጠቃሚነት ካልተመኅረተ ተጎጅና ተጠቃሚን የሚፈጥርም ነው ብለዋል። በተለይ ለቤቶች ግንባታ ሲባል ከእርሻ ቦታቸው የለቀቁ አርሶ አደሮችና የአርሶ አደር ልጆች የሁላችንም ህመም ነው ብለዋል። በዚህም የከተማ አስተዳደሩ ካቢኔና የቤቶች አሰተዳደር ቦርድ አርሶ አደሮችና የአርሶ አደር ልጆች ያለ ዕጣ እንዲሰጣቸው መወሰኑን ይፋ አድርገዋል።

    ተሰርዞ የነበረው የ20/80 እና 40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ ወጣ (የዕድለኞች ስም ዝርዝር) 

    ኢንጂነር ታከለ በቀጣይም የቤት ልማትን ከአርሶ አደሩ ተጠቃሚነት ጋር ለማስኬድ ትኩረት በማድረግ ይሠራል ነው ያሉት። በቤት ልማቱ የመንግስትን ተሳትፎ በመቀነስ የግሉንና የባለሀብቱን ተሳትፎ የማሳደግ ሥራ እንደሚከናወንም ጠቁመዋል። ከንቲባው በዘርፉ የመንግስትና የባላሀብቶችን ግንኙነትን ለማጠናከር በትኩረት ለመንቀሳቀስ ኮሚቴ መዋቀሩን ነው ያስታወቁት።

    የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስትር አቶ ዣንጥራር አባይ በበኩላቸው፥ መንግስት በቤት ልማት ዘርፍ የሚታየውን ችግር ለመቅረፍ በርካታ ሥራዎች ሲያከናውን መቆየቱን የተናገሩ ሲሆን፥ በዚህ ወጤቶች መመዝገባቸውን አንስተዋል። በቤት ልማት ዘርፉ የፍላጎቱን ያህል ባይሠራም የተሻለ ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

    አቶ ዣንጥራር በኢትዮጵያ ያለው የቤት ልማት ዘርፍ ህዝቡን የቤት ባለቤት ከማድረግ ባለፈ ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል የፈጠረ መሆኑን አስታውቀዋል። ባለፉት 13 ዓመታት በአዲስ አበበና በመላ ሀገሪቱ ከ385 ሺህ በላይ ቤቶች እንደተገነቡና በግንባታ ላይ እንደሚገኙ የገለፁ ሲሆን፥ በዚህም 1 ሚሊየን ለሚጠጉ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር እንደተቻለ ተናግረዋል።

    በተለያዩ ወገኖች በተደረገ ጥናት መሠረት ካለው የቤት ፍላጎት አንፃር ከ2007 እስከ 2017 ዓመተ ምኅረት ባለው ጊዜ ውስጥ 471 ሺህ ቤቶችን በየዓመቱ እየገነቡ ማቅረብ ይገባ ነበር። ሆኖም መንግስት በፋይናንስ እና በግንባታ ፕሮጀክት የማስፈፀም አቅም ባለበት ክፍተት ምክንያት ይህን ማድረግ እንዳልተቻለ በመጠቆም በቀጣይ የግሉን ዘርፍ በማሳተፍ ፍላጎቱን ለማሟላት እንደሚሠራ ነው አቶ ዣንጥራር በንግግራቸው ላይ ያነሱት።

    ኮንዶሚኒየም ቤቶች ዕጣ የወጣላቸው ዕድለኞች ስም ዝርዝር

    13ኛ ዙር የ20/80 ፕሮግራም ባለ ስቱዲዮ ቤት የዕድለኞች ስም ዝርዝር
    13ኛ ዙር የ20/80 ፕሮግራም ባለ አንድ መኝታ ክፍል የዕድለኞች ስም ዝርዝር
    13ኛ ዙር የ20/80 ፕሮግራም ባለ ሁለት መኝታ ክፍል የዕድለኞች ስም ዝርዝር
    13ኛ ዙር የ20/80 ፕሮግራም ባለ ሦስት መኝታ ቤት የዕድለኞች ስም ዝርዝር
    የ40/60 መርሃ ግብር ባለ አንድ መኝታ ቤት የዕድለኞች ስም ዝርዝር
    የ40/60 መርሃ ግብር ባለ ሁለት መኝታ የዕድለኞች ስም ዝርዝር
    የ40/60 መርሃ ግብር የባለ ሦስት መኝታ ቤት የዕድለኞች ስም ዝርዝር

    ምንጭ፦ ፋና ብሮድካስቲንግ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ኮንዶሚኒየም ቤቶች


    #48422
    Semonegna
    Keymaster

    በአዲስ አበባ 25 ሺህ 491 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ለነዋሪዎች በዕጣ ተላለፉ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የ14ኛ ዙር የ20/80 እና የ3ኛ ዙር የ40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች የዕጣ አወጣጥ ሥነ-ሥርዓት ሐምሌ 1 ቀን፣ 2014 ዓ.ም ተካሂዷል። በዚህም በድምሩ 25 ሺህ 491 የጋራ መኖሪያ ቤት ዕጣ ዕድለኞች ተለይተዋል።

    በዕለቱ የዕጣ አወጣጥ ሥነ-ሥርዓት ላይ አዲስ የመረጃ መያዣ እና ዕጣ ማውጫ የቴክኖሎጂ ሥርዓት በጥቅም ላይ መዋሉ ተገልጿል። ይህንን ተከትሎም የቤት ተጠቃሚዎች በአዲሱ ሲስተም በቀጥታ የወጣውን የአሸናፊዎችን ሙሉ መረጃ በ‘ኦንላይን’ ማረጋገጥ እንደሚችሉም ተገልጿል።

    በማዘጋጃ ቤት አዳራሽ በተካሄደው የዕጣ አወጣጥ ሥነ-ሥርዓት ላይ ከንቲባ አዳነች አቤቤን ጨምሮ የከተማዋ ከፍተኛ አመራሮች፣ ቤት ፈላጊዎች እና ሌሎች እንግዶች ተገኝተዋል።

    በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት ከንቲባ አዳነች አቤቤ ለቤት ፈላጊዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት የእንኳን ደስ አላችሁ መልእክት በማስተላለፍ የዕጣ አወጣጥ መርሐ ግብሩን አስጀምረዋል።

    በብዙ ፈተናዎች መካከል ውስጥ ሆነንም ቢሆን ግንባታቸው የተጓተቱ የጋራ መኖሪያ ቤቶችን በማጠናቀቅ ለተጠቃሚዎች ለማስተላለፍ በቅተናል ነው ያሉት ከንቲባዋ።

    ከንቲባ አዳነች አቤቤ፥ “የከተማ አስተዳደራችን የከተማዋን የቤት ችግር ለመፋታት የተለያዩ የቤት ልማት አዳዲስ አማራጮችን በመዘርጋት የጀመረውን ርብርብ አጠናክሮ ይቀጥላል።” በማለት መልዕክታቸውን አስተላልገዋል።

    በተጨማሪም ከንቲባዋ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው የሚከተለውን መልዕክት አስተላልፈዋል።

    ለረጅም ዓመታት በትዕግስት ገንዘባችሁን እየቆጠባችሁ የመኖሪያ ቤት ባለቤት ለመሆን በጉጉት የተጠባበቃችሁ የቤት ባለእድለኞች በሙሉ፤ እንኳን ደስ አላችሁ! የከተማ አስተዳደሩ የተረከበውን በርካታ ውስብስብ ችግሮች የነበሩባቸው ቤቶች እንዲሁም በተረከብነው ከ54 ቢሊዮን ብር በላይ የባንክ እዳ ተስፋ ባለመቁረጥ ይልቁንም በቁጭትና እልህ ሌት ተቀን በመረባረብ ከ21 ቢሊየን ብር በላይ በጀት በመጠቀም ለዛሬ ውጤት በመብቃታችን መላውን የከተማ በተለይም የቤቶች ልማትና የቤቶች ኮርፖሬሽን አመራሮችና ሰራተኞች፤ ኮንትራክተሮች፤የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፤ እና ሌሎች ለዚህ ስራ ስኬታማነት ሚናችሁን የተወጣችሁ በሙሉ ልባዊ ምስጋናዬን አቀርባለሁ! የከተማዋን የቤት ችግር ለመፍታት የተለያዩ የቤት ልማት አዳዲስ አማራጮችን በመዘርጋት የጀመረውን ስራ አጠናክረን የምንቀጥል ሲሆን የከተማችን ነዋሪዎች እንደ ሁልጊውም ከጎናችን በመሆን ጉዞ ከጫፍ እንድናደርስ ጥሪዬን ማስተላለፍ እወዳለሁ!

    የከተማ አስተዳደሩ ለቤቶቹ መሠረታዊ ግንባታ የሚሆን ወደ 21 ቢሊዮን ብር በማውጣት ሥራውን ሲያከናውን መቆየቱንና ለበርካቶችም የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን አክለዋል።

    በዕጣው የተካተቱት በ1997 እና በ2005 ዓ.ም ተመዝግበው እስከ የካቲት 21 ቀን 2014 ዓ.ም ድረስ በአማካይ ለ60 ወራት የቆጠቡ የ20/80 እና 40 በመቶ እና ከዚያ በላይ የቆጠቡ የ40/60 ቤት ፈላጊዎች ናቸው ተብሏል።

    በዚሁ መሠረት በ20/80 የቤት ልማት ፕሮግራም 27 ሺህ 195 እና በ40/60 የቤት ልማት ፕሮግራም 52 ሺህ 599 በአጠቃላይ 79 ሺህ 794 ተመዝጋቢዎች ለዕጣ ብቁ ሆነው በዕጣ እንዲካተቱ ተደርጓል ነው የተባለው።

    በዕለቱ ዕለት ዕጣ የወጣባቸው ቤቶች የሚገኙባቸው ሳይቶችም በ40/60 መርሃ ግብር የተገነቡ ቤቶች አያት 2፣ ቦሌ በሻሌ እና ቡልቡላ ሎት 2 እንዲሁም በ20/80 መርሃ ግብር የተገነቡ ቤቶች በረከት፣ ቦሌ አራብሳ (ሳይት 3፣5፣6)፣ ወታደር፣ የካ ጣፎ፣ ጀሞ ጋራ፣ ጎሮ ሥላሴ፣ ፉሪ ሃና እና ፋኑኤል መሆናቸው ተገልጿል።

    ሐምሌ 1 ቀን፣ 2014 ዓ.ም የተላለፉ የጋራ መኖርያ ቤቶችን የተመለከቱ መረጃዎች፡-

    • አሁናዊ የአንድ ካሬ የቤት ማስተላለፊያ ዋጋ፦ የሥራ አመራር ቦርዱ ታህሳስ 5 ቀን 2014 ዓ.ም በወሰነው መሠረት አሁን በሥራ ላይ ያለው አሁናዊ የአንድ ካሬ ማስተላለፊያ ዋጋ፡-
      • 20/80 ቤት ልማት ፕሮግራም 7,997.17 ብር
      • 40/60 ቤት ልማት ፕሮግራም 11,162.97 ብር ነው።
    • ለዕጣ የቀረቡ ቤቶች የሚገኙባቸው ሳይቶች፣ የቤት ዓይነትና ብዛት በተመለከተ
      • የ40/60 የቤት ልማት ፕሮግራም — አያት 2፤ ቦሌ በሻሌ፤ ቡልቡላ ሎት 2 ሲሆኑ
      • የ20/80 ቤት ልማት ፕሮግራም — በረከት፣ ቦሌ አራብሳ (ሳይት 3፣ 5፣ 6)፣ ወታደር፣ የካ ጣፎ፣ ጀሞ ጋራ፣ ጎሮ ስላሴ፣ ፉሪ ሃና እና ፋኑኤል
    • በቤት ዓይነትና ብዛት ሲታይ
      • በ20/80 የቤቱ ብዛት ስቱዲዮ ፡-3318 ባለአንድ መኝታ ፡- 7171 ባለሁለት መኝታ፤- 8159 በድምሩ 18648 ናቸው።
      • በ40/60 ባለአንድ መኝታ፤- 1870 ባለሁለት መኝታ 4220 እና ባለሶስት መኝታ 753  በአጠቃላይ በድምሩ 25491 ቤቶች ናቸው።
    • በዚህ ዙር ለዕጣ የቀረቡ ቤቶች የግንባታ አፈጻጸም ሁኔታ በጋራ መኖሪያና ንግድ ቤቶችን ለተጠቃሚዎች ለማስተላለፍ በወጣ መመሪያ ቁጥር 3/2011 በሥራ አመራር ቦርድ በማስወሰን
      • የ20/80 ከ96% በላይ፣ በ40/60 ከ87% በላይ የግንባታ አፈጻጸም ያላቸው ቤቶች ለዕጣ ቀርበዋል።
    • የዚህ ዙር የዕጣ ተሳታፊዎች ሁኔታ (የቤት ፈላጊ ተመዝጋቢ ሁኔታ) የ20/80 ነባር ተመዝጋቢዎች (1997) በመመሪያው መሠረት ዝቅተኛውን የ60 ወራት ቁጠባ መጠን ያሟሉ ለእጣ ውድድር ብቁ የሆኑ እስከ የካቲት 21 2014 ዓ.ም ድረስ እና የ40/60 40% እና ከዚያ በላይ ቁጠባ ያላቸው እስከ የካቲት 21 2014 ዓ.ም የቆጠቡ ናቸው።
    • በዕጣ ውስጥ የተካተቱት ተመዝጋቢዎችን በተመለከተ ከባንክ በተገኘው መረጃ መሠረት በ20/80 የቤት ልማት ፕሮግራም 27,195 እና 40/60 የቤት ልማት ፕሮግራም  52,599 በአጠቃላይ 79,794 ተመዝጋቢዎች ለዕጣ ብቁ ሆነው በዚህ ዙር ዕጣ እንዲካተቱ ተደርጓል። የዕጣ ተሳታፊዎች ሁኔታ ለዕጣ ከቀረቡ የቤት ዓይነቶች አኳያ በዝርዝር ሲታይ
    • በልዩ ሁኔታ ተጠቃሚ የሚደረጉ ማህበረሰብ ክፍሎችን በተመለከተ  በመመሪያ ቁጥር 3/2011 በተገለጸው መሠረት ከ20/80 ነባር ተመዝጋቢዎች (1997) እና 40/60 ተመዝጋቢዎች ውስጥ
      • መንግሥት ሠራተኞች 20 በመቶ፣
      • ሴቶች 30 በመቶ፣
      • አካል ጉዳተኞች 5 በመቶ እና አጠቃላይ ተመዝጋቢዎች 45 በመቶ በዕጣ የቤት ተጠቃሚዎች የሚለዩ ይሆናሉ።
    • በከተማ አስተዳደሩ ፕሮጀክቱን ለመኖር ብቁ ለማድረግ ና ቤቶቹን ለማጠናቀቅ ከባንክ ቦንድ ብድር ብር 18.7 ቢሊዮን እና ለመሠረተ ልማት ግንባታ ከመደበኛ በጀት ብር 2.871 ቢሊዮን  በድምሩ ብር 21.571 ቢሊዮን በሥራ ላይ ውሏል።
    • በ20/80 የቤት ልማት ፕሮግራም 27,195 እና 40/60 የቤት ልማት ፕሮግራም 52,599 በአጠቃላይ 79,794 ተመዝጋቢዎች ለዕጣ ብቁ ሆነው በዚህ ዙር ዕጣ እንዲካተቱ ተደርጓል።
    • በዚህ ዙር ከተላለፉ ቤቶች ውስጥ ከዚህ በፊት በማጣራት ሂደት የተገኙ ቤቶች ለልማት ተነሺ ሲስተናገዱበት ቆይተው የቀሩት ተካተዋል።
    • የቤት ልማት ፕሮግራም ከጀመረበት አንስቶ በ17 ዓመታት ውስጥ ለህብረተሰቡ ማቅረብ የተቻለው 300 ሺህ ያህል ቤቶችን ብቻ ነው።
    • የቤት ዕጣ አወጣጡ  እንደ ቅደም ተከተል ሲሆን በ20/80 ፕሮግራም  የ97 ተመዝጋቢዎች ቅድሚያ አግኝተዋል።
    • የባለ ሦስት መኝታ ቤት በተመለከተ ፕሮግራሙ ባለፈው ዙር  በቦርድ ውሳኔ በመዘጋቱ  በቀጣይ በልዩ ሁኔታ የሚስተናገዱ ይሆናል።

    የጋራ መኖሪያ ቤቶች

    #54149
    Semonegna
    Keymaster

    ተሰርዞ የነበረው የ20/80 እና 40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ ወጣ ((የዕድለኞች ስም ዝርዝር))

    አዲስ አበባ (ኢዜአ) – የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከዚህ ቀደም ተሰርዞ የነበረውን የ20/80 እና የ40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ዕጣ አወጣ። የ14ኛዉ ዙር የ20/80 እና 3ኛዉ ዙር የ40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች (condominium houses) ዕጣ የማውጣት ሥነ-ሥርዓት ህዳር 6 ቀን 2015 ዓ.ም ተካሂዷል።

    በዕጣ ማውጣት ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ አዳነች አቤቤን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የተለያዩ የማኅበረሰብ ክፍሎች ተወካዮች በታዛቢነት ተገኝተዋል።

    በዕጣው የ20/80 የቤት ልማት ፕሮግራም 18,930 ቤቶች፣ በ40/60 ደግሞ 6,843 ቤቶች እንዲሁም ተጨማሪ 18 ስቱዲዮ ቤቶች በድምሩ 25,791 ቤቶች በዕለቱ ዕጣ ወጥቶባቸዋል።

    የጋራ ቤቶች (condominium houses) ዕጣ ሐምሌ 01 ቀን 2014 ዓ.ም ወጥቶ የነበረ ቢሆንም በዕጣው ማውጣት ሂደት በገጠመ ችግር ምክንያት ዕጣው በመሰረዙ ነው አሁን በድጋሚ የዕጣ ማውጣት ሂደት የተከናወነው።

    የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዕጣ ማውጣት ሥነ-ሥርዓቱ ላይ እንዳሉት፥ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ከግንባታ እስከ ዕጣ ማውጣት ሂደት ባለፉት ጊዜያት ከውስጥም ሆነ ከውጭ በርካታ ችግሮች አስተናግዷል። ከዚህ አንፃር ዛሬ የወጣው የ20/80 እና 40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ በርካታ ችግሮችን በማለፍ በስኬት መከናወኑን አንስተዋል።

    በተለይ በለውጡ ዋዜማ የሥራ ተቋራጮች ሥራውን አቋርጠው የመጥፋት፣ የመሠረተ ልማት ዝርፊያ የግንባታ ጥራት ችግር፣ የፋይናንስ እጥረትን ጨምሮ ዘርፉ የተወሳሰበ ሂደት ውስጥ ለማለፍ ተገድዷል ነው ያሉት።

    የከተማ አስተዳደሩ እነዚህን ውስብስብ ችግሮች ለመፍታት ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከ21 ቢሊዮን ብር በላይ በመበደር ጥረት ሲያደርግ መቆየቱንም እንዲሁ አስታውቀዋል።

    ሆኖም ከዚህ በፊት ዕጣ የወጣባቸውን የጋራ ቤቶች ለተጠቃሚዎች ለማድረስ የተደረገው ሙከራ በተለያዩ የሌብነት ተግባራት ምክንያት ሳንካ ገጥሞት እንደነበርም ጠቅሰዋል። ይህ ደግሞ ለረጅም ዓመታት በትዕግስት ሲጠባበቅ ለነበረው ሕዝብ አሳዛኝ ዜና እንደነበር አውስተዋል።

    በዕጣ ማውጣት ሂደቱ ከተፈጠረው ችግር ጀርባ የቤት ልማት መርሃ-ግብርን ለግል ጥቅም ማካበቻ ከማድረግ ባለፈ በመንግሥትና በሕዝብ መካከል አለመተማመን ለመፍጠር ያለመ ሴራም እንደነበር ነው የተናገሩት። የከተማ አስተዳደሩ የገጠመውን ችግር ለሕዝብ በግልፅ ይፋ በማድረግ በአጥፊዎች ላይ ተጠያቂነትን ማስፈኑን ጠቅሰዋል።

    ተዓማኒነቱ የተረጋገጠ አዲስ የዕጣ ማውጫ ሥርዓት በማልማትም ከዚህ ቀደም ተሰርዞ የነበረው የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ አሁን (ህዳር 6 ቀን 2015 ዓ.ም) በድጋሚ እንዲወጣ መደረጉን ተናግረዋል። የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ በድጋሚ እንዲወጣ ያለመታከት ጥረት ያደረጉ ሰራተኞችና አመራሮችን አመስግነው ባለእድለኞችንም እንኳን ደስ ያላችሁ ብለዋል።

    ዛሬ የጋራ መኖርያ ቤት ዕጣ ለደረሳችሁ 25,791 ባለ እድለኞች እንኳን ደስ አላችሁ!!
    ለዘመናት በትዕግስት ስትቆጥቡና ስትጠባበቁ የነበራችሁ የ14ኛ ዙር የ20/80 እንዲሁም የ3ኛ ዙር የ40/60 የጋራ መኖርያ ቤት ባለ እድለኞች በሙሉ እንኳን ደስ አላችሁ ለማለት እወዳለሁ!!
    ከዚህ ቀደም በቤት የዕጣ አወጣጥ ሂደት በገጠመን የማጭበርበር ችግሮች ምክንያት የእጣ አወጣጥ ሂደቱ ቢዘገይና እክል ቢገጥመውም የህዝብን ሃብት ለማዳን ያደረግነውን ጥረት በመረዳት ከጎናችን ስለሆናችሁና በከፍተኛ የሃላፊነት ስሜት የህግ የበላይነት እንዲከበር በትዕግስትና በማስተዋል እገዛችሁ ላልተለየን የከተማችን ነዋሪዎች በሙሉ ምስጋናችን ላቅ ያለ ነው፡፡
    እንዲሁም ለዚህ ስራ ስኬት በትጋት የተሳተፋችሁ ፤በየደረጃው የምትገኙ የስራ ሃላፊዎች፣ አመራሮች ፣ሰራተኞች፣ ባለሙያዎችና የፌደራል ተቋማት ስላበረከታችሁት ታላቅ አስተዋፅኦ በከተማ አሳተዳደሩ ስም ልባዊ ምስጋናዬን ለማቅረብ እወዳለሁ!!
    አሁንም የጀመርነውን ከተማችንን እንደ ስሟ ውብና ደማቅ ለነዋሪዎቿ የምትስማማ የማድረግ ስራ ቃላችንን ጠብቀን በመቀጠል ከተማችንን ተወዳዳሪ ብቁና የቱሪስት መዳረሻ የማድረግ ስራ አጠናክረን የምንቀጥል ይሆናል፡፡
    ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ህዝቦቿን አብዝቶ ይባርክ!!
    ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ

    የ14ኛ ዙር የ20/80 የጋራ መኖርያ ቤት ባለ ዕድለኞችን ለማየት ተከታዩን የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን (ኢቢሲ) ቴሌግራም ማስፈንጠሪያ ይጫኑ – EBC Telegram Link

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት

    የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ ወጣ

    #55148
    Semonegna
    Keymaster

    የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና የአዲስ አበባ ከተማ ቤቶች ልማት እና አስተዳደር ቢሮ የ70/30 የማኅበር ቤት ግንባታ ፕሮግራም ይፋ አደረጉ

    • ፕሮግራሙን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈርሟል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና የአዲስ አበባ ከተማ ቤቶች ልማት እና አስተዳደር ቢሮ የ70/30 የማኅበር ቤት (ኮንዶሚኒየም ቤቶች) ግንባታ ፕሮግራም ይፋ አደረጉ። ታህሳስ 10 ቀን 2015 ዓ.ም የተደረገው ስምምነት የከተማ አስተዳደሩ የነዋሪዎችን የቤት ችግር ለመቅረፍ ካቀረባቸው አማራጮች አንዱ በሆነው የጋራ መኖሪያ (ኮንዶሚኒየም) ቤቶች ልማት ፕሮግራም ተጠቃሚ ለመሆን በ2005 ዓ.ም በ20/80 እና በ40/60 ኮንዶሚኒየም ቤቶች ፕሮግራሞች የተመዘገቡና በሕብረት ሥራ ማኅበራት በመደራጀት ቤት ለማልማት ፍላጎት ላላቸው ነዋሪዎች ብድር ለማመቻቸት ያለመ ነው።

    በስምምነቱ መሠረት በማኅበራት የተደራጁ ቤት ገንቢዎች የግንባታ ወጪውን 70 በመቶ ያህል ሲቆጥቡ 30 በመቶውን ደግሞ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በብድር እንዲያገኙ ይደረጋል።

    በስምምነቱ ወቅት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዝዳንት አቶ አቤ ሳኖ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመኖሪያ ቤት ችግርን ለመፍታት በሚያከናውናቸው ተግባራት ባንኩ ድርሻውን በከፍተኛ ደረጃ ሲወጣ መቆየቱን ገልፀዋል።

    አሁን ከተማ አስተዳደሩ ተግባራዊ ለማድረግ ያቀደው የ70/30 የማኅበር ቤት ((ኮንዶሚኒየም ቤቶች) ግንባታ ፕሮግራምም እንዲሳካ ባንኩ ልክ እንደ ከዚህ ቀደሙ በጋራ ይሠራል ብለዋል።

    በምክትል ከንቲባ ማዕረግ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቤቶች ልማት እና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ወ/ሮ ያስሚን ውሃብረቢ እንዳሉት፥ ቢሮው ባደረገው ጥሪ መሠረት ፍላጎት አሳይተው ከተመዘገቡት ከ12,000 በላይ ቆጣቢዎች ውስጥ 4,580 የሚሆኑት በዳግም ምዝገባው ተገቢውን መረጃ ይዘው የቀረቡ በመሆኑ በመጀመሪያው ምዕራፍ ወደ ትግበራ ይገባሉ።

    በአሁኑ ወቅት የተዘገቡት 4,580 በላይ ቆጣቢዎችን በ57 ሕብረት ሥራ ማኅበራት እንዲደራጁ የመደልደል ሥራ ተጠናቋል ያሉት ወ/ሮ ያስሚን ውሃብረቢ፥ ለአዲሱ ፕሮግራም 30,000 ሄክታር መሬት መዘጋጀቱንም ነው የገለፁት።

    በቤት ልማት ዘርፉ የኢትዮጰያ ንግድ ባንክ ለዓመታት የዘለቀ ድጋፍ ሲያደርግ መቆየቱን የገለፁት ወ/ሮ ያስሚን፥ ባንኩ ሃገራዊ ግዴታውን በመወጣቱ ሊመሰገን ይገባል ብለዋል።

    በቀጣይ ተገቢውን ቅድመ-ሁኔታ አሟልተው ህጋዊ ሰውነት አግኝተው በሕብረት ሥራ ማኅበር ሲደራጁ የፕሮጀክት ሳይት እና የብሎክ እጣ በማውጣት የመሬት ርክክብ ለማኅበራቱ በማድረግ ግንባታ እንደሚጀመር በስምምነቱ ወቅት ተገልጿል።

    ከዚሁ ፕሮግራም ጋር በተያያዘ በርካታ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች መከናወናቸውን፥ ከእነዚህም መካከል የአሠራር ሥርዓት መዘርጋት፣ በከተማ አስተዳደሩ አስፈላጊው የመሬት አቅርቦት ዝግጅት፣የህንፃ ዲዛይን ሥራ፤ ከአዲስ አበባ የሕብረት ሥራ ማኅበር ኤጀንሲ በቀጣይ ሥራ ስምምነት ማመቻቸትን እንደሚያካትት የአዲስ አበባ ከተማ ኮሙኒኬሽን ቢሮ አስታውቋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ

    የአዲስ አበባ ከተማ ቤቶች ልማት እና አስተዳደር

Viewing 4 posts - 1 through 4 (of 4 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.