Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Home Forums Search Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Viewing 15 results - 436 through 450 (of 730 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    ሰሞነኛ የተማሪዎች ምርቃት — በተለያዩ የኢትዮጵያ ዩኒቨርሲቲዎችና ኮሌጆች (የግል/ የመንግስት) የተማሪዎች ምርቃት።

    የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በመጀመሪያና ሁለተኛ ዲግሪ ፕሮግራም ያስተማራቸውን ተማሪዎችን አስመረቀ። በተመሳሳይ የጎንደር መምህራን ትምህርት ማሰልጠኛ ኮሌጅ በተለያዩ የትምህርት መስኮች ለሦስት ዓመታት ያስተማራቸውን ተማሪዎችን አስመረቀ።

    አዲስ አበባ (ኢዜአ) – የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በመጀመሪያና ሁለተኛ ዲግሪ ፕሮግራም ያስተማራቸውን 1 ሺህ 313 ተማሪዎችን አስመረቀ።

    ዩኒቨርሲቲው በአምስት ኮሌጆች ውስጥ ያስተማራቸውን ተማሪዎች 1 ሺህ 112 በመጀመሪያ ዲግሪ እና 201 በሁለተኛ ዲግሪ ሰኔ 22 ቀን 2011 ዓ.ም. አስመርቋል።

    የዩኒቨርሲቲው ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ታረቀኝ ብርሃኑ የተማሪዎች ምርቃት ሥነ ስርዓቱ ላይ እንደተናገሩት፥ ተማሪዎች ከዩኒቨርሲቲው ባገኙት ዕውቀትና ክህሎት አገራቸውንና ህዝባቸውን በታማኝነት ማገልገል አለባቸው።

    ዩኒቨርሲቲው በሳይንስ፣ በኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ (ICT) እና በኢንጅነሪንግ ትምህርት ላይ ትኩረት አድርጎ የሚያስተምር በመሆኑ ተማሪዎችም በዚሁ መስክ የአገሪቱን ዕድገት ለማፋጠን መሥራት ይኖርባቸዋል” ብለዋል።

    የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ከኢንዱስትሪዎች ጋር ትስስር በመፍጠር ችግር ፈቺ የሆኑ ምርምሮችን እንደሚያካሂድና አጫጭር ስልጠናዎችን በመስጠት ለአገሪቱ ዕድገት የበኩሉን እየተወጣ እንደሆነም ጠቁመዋል።

    ተመራቂዎች በበኩላቸው ባገኙት ዕውቀት አገራቸውንና ህዝባቸውን ለማገልገል ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል።

    በኮንስትራክሽን ቴክኖሎጂ ማኔጅመንት ተመራቂ የሆኑ ተማሪዎች ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) ሪፖርተር እንደተናገሩት፥ ከዩኒቨርሲቲው ባገኙት ዕውቀትና ክህሎት አገራቸውንና ቤተሰቦቻቸውን ለመጥቀም ይሠራሉ። ወደ መንግስትም ሆነ ግል ተቋማት በመሄድ በንድፈ-ሐሳብ ደረጃ ያገኙትን ትምህርት በተግባር ማስደገፋቸውን ገልጸው በኮንስትራክሽ ዘርፍ የበኩላቸውን ለመወጣት ዝግጁነታቸውን አረጋግጠዋል።

    በተመሳሳይ በኢንዱስትሪያል ኬሚስትሪ የተመረቁ ተማሪዎች ያገኙትን ዕውቀት ለማህበረሰቡ ለማበርከት መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።

    በተያያዘ ዜና የጎንደር መምህራን ትምህርት ማሰልጠኛ ኮሌጅ በተለያዩ የትምህርት መስኮች ለሦስት ዓመታት ያሰለጠናቸውን 1ሺህ 578 ዕጩ መምህራንን በተመሳሳይ ዕለት በዲፕሎማ አስመርቋል።

    ከዕውቀት ባለፈ በሥነ-ምግባር የታነፀ ትውልድ ለመፍጠር ጠንክረው እንደሚሠሩ የኮሌጅ ተመራቂ እጩ መምህራን ተናግረዋል።

    ከተመራቂ መምህራን መካከል በሒሳብ ትምህርት ክፍል የተመረቀችው መምህርት ስንቂት ማሙየ እንዳለችው፥ በቀጣይ ዕውቀቷን ለተማሪዎች ከማካፈል በተጨማሪ ሀገራቸውን የሚወዱና በሥነ-ምግባራቸው የተመሰገኑ ተማሪዎችን ለማፍራት በኃላፊነት እንደምተሠራ ተናግራለች።

    “ሀገራችን ከመምህራን ብዙ ትጠብቃለች፤ እኛ መምህራንም ትውልድን በዕውቀት አንፀን በመቅረፅ ለሀገራቸው እድገት ከፍተኛ ሚና እንዲጫወቱ ማድረግ አለብን” ብላለች።

    በማኅበራዊ ሳይንስ ዕጩ መምህርና በኮሌጁ 3 ነጥብ 8 በማምጣት የዋንጫ ተሸላሚ የሆነው መንግስቱ ማሬ በበኩሉ ቀጣዩ ትውልድ በዕውቀት የዳበረና ማኅበረሰቡን አገልጋይ እንዲሆን በተመደበበት የሥራ ቦታ ተማሪዎቹን እንደሚያበቃ ተናግሯል።

    “መመረቅ የመጨረሻ ሳይሆን ለአስተማረችኝ ሀገሬና ወገኔ አገልግሎት መስጠት የምጀመርበት ነው” ያለው ተመራቂው ሲሆን፥ በቀጣይም ዕውቀቱን በማዳበር የነገ ሀገር ተረካቢ ትውልድ የመቅረፅ ኃላፊነቱን በብቃት ለመወጣት መዘጋጀቱን አስረድቷል።

    “የአንደኛ ደረጃ ተማሪዎች ዕውቀትንና ማኅበራዊ ግብረ-ገብነትን ይዘው እንዲያድጉ ማድረግ በቀጣይ የሥራ ዘመኔ የምከተለው መርህ ነው” ያለችው ደግሞ በሥነ-ዜጋና ሥነ-ምግባር ትምህርት ዘርፍ የተመረቀችው መምህርት መሰረት የኔሁን ናት።

    የኮሌጁ ዲን አቶ ስንታየሁ ነጋሽ በበኩላቸው ኮሌጁ ከተቋቋመ 38 ዓመታትን ያስቆጠረ መሆኑን ጠቅሰው በእነዚህ ዓመታት ከ44 ሺህ በላይ መምህራንን ማስመረቁን ተናግረዋል። በዕለቱ ከተመረቁ 1ሺህ 578 እጩ መምህራን መካከልም 798ቹ ሴቶች መሆናቸውን አስረድተዋል።

    እንደ ዲኑ ገለጻ፥ ተመራቂዎቹ በትምህርት ቆይታቸው በቂ ዕውቀት ይዘው መውጣት የሚያስችላቸውን የተግባርና የንድፈ ሀሳብ ትምህርት አግኝተዋል። ምሩቃን በቀጣይ ሙያውን አክብረው በመሥራትና ራሳቸውን ወቅቱ በሚፈልገው ልክ አቅማቸውን በማሳደግ ለትምህርት ጥራት መሻሻል ሀላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡም አሳስበዋል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የተማሪዎች ምርቃት


    Semonegna
    Keymaster

    ማለቂያ የሌላቸው ብዙ ብዙ የውሽት ትርክቶች ሰፊውን የአማራ ሕዝብ ጥቅምም ሆነ ኢትዮጵያን እንደ ሀገር ለማስቀጠል ፈጽሞ የማይበጅ፣ እንዲያውም በአማራው ክልልም ሆነ በበርካታ አካባቢዎች በጎጥና በአካባቢም ጭምር ወርዶ የእርስ በእርስ ግጭቶች ሊወልድ የሚችል አደጋ ያዘለ ሁኔታ እያደገ መሆኑን የሰሞኑ ክስተት ያመላክታል።

    ኢትዮጵያ ሀገራችንን ከጥፋትና ከእልቂት ለማዳን ቆም ብለን በሰከነ ሁኔታ ማሰብና መራመድ እጅግ አስፈላጊና ወሳኝ ጊዜ ላይ እንገኛለን።
    (ነአምን ዘለቀ)

    የአማራ መሰረት ያላችሁ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ፣ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ ሁሉ፥

    ዛሬ ከፊታችን ያፈጠጠው መሰረታዊ ጥያቄ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድን እንደግፍ ወይንም አንደግፍ የሚለው አይደለም። የዛሬው ማዕከላዊ ጥያቄ፣ የዛሬው ዋና ጥያቄ ‘ኢትዮጵያ እንደ ሀገር ትቀጥል ወይንስ አትቀጥል’ የሚለው ነው። አብይ መጣ፣ ከበደ፣ ዋቅጅራ፣ ወይንም ግደይ፣ እቺ ታሪካዊት ሀገር፣ እቺ መከረኛ ሀገር፣ እትብታችን የተቀበረባት፣ የምንወዳት፣ ሌት ተቀን የምንጨነቅላት ኢትዮጵያ ሀገራችን፣ በተማሩ ልጆቹ በተደጋጋሚ የተከዳና የተበደለ፣ በድህነትና በችጋር የሚማቅቀው፣ ነገር ግን ጨዋና ኩሩ የሆነው እብዛኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ አብሮነት እንዴት ይቀጥል ነው ዋናው፣ መሰረታዊው፣ ማዕከላዊው ጥያቄ፣ የዛሬው ጥያቄ፣ የአሁን ሰዓት ዋነኛ ጥያቄ ይሄው ነው።

    ሰሞኑን “ኣማራው ተጠቃ፣ ተበደለ፣ ተገፋ” በሚል ሽፋን፣ በአብይ አህመድ “የኦሮሞ/ የኦዴፓን የበላይነት” ለመጫን እየሠራ የሚገኝ የትሮጃን ፈረስ ተደርጎ በሰፊው የሚነዛው ጥላቻ፣ የሚረጨው ሰፊ መርዝና ቅስቀሳ ሰፊው የአማራ ሕዝብን ጥቅም (በአማራው ክልል ብቻ ሳይሆን በኦጋዴን፣ በሀረር፣ በባሌ፣ በአርሲ፣ በኢሉባቡር፣ በወለጋ፣ ወዘተ… በሌሎች አካባቢዎች የሚገኘውን ከ10 ሚሊዮን በላይ አማራኛ ተናጋሪ ማኅበረሰብ) የአማራውን ሕዝብ ደህንነትና ዋስትና ለማረጋገጥ ምን ያህል እንደሚጠቅም፡ ህልውናውንም እንደምን አርጎ ለማረጋገጥ እንደሚያገለግል ቆም ብሎ የታሰበበት አለመሆኑ ግልጽ ነው።

    በትናንሽና ፍጹም የማይናበቡ፣ የጋራ ራእይ፣ የጋራ ስልት (strategy) በሌላቸው በየጎጡ የተደራጁና አማራን እንወክላለን በሚሉ እንደ አሸን የፈሉ ቡድኖች የሚደረገው ይሄው በጣም የከረረ ጥላቻ፣ ማለቂያ የሌላቸው ብዙ ብዙ የውሽት ትርክቶች ሰፊውን የአማራ ሕዝብ ጥቅምም ሆነ ኢትዮጵያን እንደ ሀገር ለማስቀጠል ፈጽሞ የማይበጅ፣ እንዲያውም በአማራው ክልልም ሆነ በበርካታ አካባቢዎች በጎጥና በአካባቢም ጭምር ወርዶ የእርስ በእርስ ግጭቶች ሊወልድ የሚችል አደጋ ያዘለ ሁኔታ እያደገ መሆኑን የሰሞኑ ክስተት ያመላክታል። ይህ ደግሞ የሶማሊያ፣ የሊቢያ፣ የሶሪያን እልቂትና መበታተን የሚደግም፣ የሚያስከነዳም የምድር ሲኦል እንደሚፈጥር በተረጋጋ አዕምሮ ልብ ያለው ሁሉ ልብ ሊል ይገባል።

    ይልቅዬ በዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ የአማራው ዘላቂ ጥቅም የሚጠበቅበት፣ የሁሉም ሕዝቦች አብሮነት የሚረጋገጥበት፣ የኢትዮጵያ እንድነት የምናስቀጥልበት ሁኔታዎችና መንገዶችን፣ ሰከን ብሎ ማሰብ፣ በስሜት ሳይሆን በስትሪቴጂያዊ አስተሳሰብ፣ በጥበብና በስልት፣ በጋራ፣ ሰጥቶ በመቀበል እንጂ፣ ሰሞኑን በሶሻል ሚዲያ እንደሚራገበው አማራውን እንወክላለን የሚሉ በልዩ ልዩ ቡድኖች የተደራጁም ያልተደራጁም አክራሪ ብሄርተኞች እጅግ በሚያጦዙት መንገድ ፈጽሞ ሊሆን እንደማይችል የሮኬት ሳይንስ አውቀት የማያስፈልገው ሃቅ ይመስለኛል።

    ሰደድ እሳቱ ሲጀመር እያንዳንዱ ቤት አንደሚያንኳኳ ቆም ብሎ ማሰብ፣ ከሌሎች ሀገሮች ውድመት፣ ውድቀትና፣ ምስቅልቅል መማር ሰዓቱ ከመድረሱ በፊት ቆም በሎ ማሰብ ብልህነት፣ አስተውሎትም ነው። ስለዚህ ሰላም፣ መረጋጋት፣ ማዕከላዊ መንግስት የተከፈተውን ምህዳር ተጠቅሞ በሰላማዊ፣ ሕጋዊ፣ ስልታዊና ስትራቴጅካዊ አካሄድ በሰላማዊና በተደራጀ መልክ የአማራውን ሕዝብ ጥቅም፣ ደኅንነት ለማሰጠበቅ መንቀሳቀስ እንጂ፥ የሰፈር የጦር አበጋዞች (በሶማሊያና በሊቢያ እንዳየነው “warlords”)፣ ከሕግና ከስርዓት ውጭ የራሳቸውን ፍላጎት በጉልበት ለመጫን የሚፈልጉ አፈንጋጮችን (በሶሪያ እንደተከሰተው “rogue military commanders”) በማጀገን የአማራውን ሕዝብ ተገፍቻለሁ፣ ተጠቅቻለሁ ብሎ እንዲነሳሳ ሰፊ ቅስቀሳ ማድረግ ታሪክ ይቅር የማይለው፣ የአማራውን ሕዝብንም ሆነ፣ የአማራው ማኅበረሰብ በደም፣ በሕይወቱ፣ በላቡ ገብሮ፣ ለግንባታዋ ብዙ የተዋደቀላት ትላቋና ታሪካዊቷ ኢትዮጵያን የማይበጅ፣ ወደ ጥፋት፣ ወደ እርስ በእርስ ጦርነት፣ አልፎም ወደ ውድመትና ወደ መበታተን ሊያደርሰን የሚችል ሂደት እየተመለከትን ነው።

    በዚህ ሁሉ ትርምስ ደግሞ ዛሬ የሚፈነጥዘው፣ ይህን ሰፊ ትርምስ (turmoil) ለራሱ በሚገባ እየተጠቀመ የሚገኘው፥ እንደ አንድ ሰው የቆመው፣ እስከ አፍንጫው የታጠቀውም ሕዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ (ሕወሃት) ብቻ ነው። ሌላው ተከፋፍሏል፣ በአብይ አህመድ ላይ በሚወርደው የጥላቻ ውርጅብኝም ሀገሪቷን እንደ ሙጫ አጣብቆ ደካማ ቢሆንም የያዘውን ስርዓተ መንግስት (state)፣ ማዕከላዊ መንግስቱንም ለማዳከም ብዙ የድንጋይ ናዳ አየወረደ ነው። በየዕለቱ በተደራጀም በአልተደራጀም መልኩ እየተደረገ የሚገኘው ይሄው ነው።

    ሕዝብን እርስ በእርስ ሊያባላ፣ ሊያጫርስ የሚችል፣ ምንም አማራጭ ሃሳብ፣ ራእይና፣ ድርጅትም ሆነ ስትራቴጂ ለማቅረብ የማይችሉ፣ ነገር ግን አማራውን እንወክላለን የሚሉ፣ እንዲሁም በአብይ አህመድ ላይ የግል ጥላቻና ጥርጣሬ ያላቸው በርካታ ግለሰቦችና ቡድኖች ጭምር ተሳታፊ የሆኑበት ይሄው በከፍተኛ ስሜት በማጦዝ፣ የተገፊነትን ስሜት በመቀስቀስ ላይ የተመሰረተ ሰፊ ዘመቻ ያነጣጠረውና እየሄደ ያለው በዚሁ ግብ ላይ ነው። የእነዚህ ቡድኖች ምንም መናበብም ሆነ፣ የጋራ አማራጭ፣ እንዲሁም ለሀገራችንና ለሕዝባችን አሻግሮ የሚያይ ራእይ ማቅረብ ያማይችሉ፣ እርስ በእርሳቸው እንኳን ተቀምጠው በአግባቡ በምክኒያታዊነት መነጋገርና መደማመጥ የማይችሉ፣ ግለሰቦች፣ ቡድኖችና ኃይሎች የሚገፋውና የሚረጨው መርዝ ሁሉንም (እነሱንም ጨምሮ) ወደ ፍጹማዊ ኪሳራ፣ የዜሮ ድምር ፓለቲካ (zero-sum game) የሚወስድ፣ ማንም ምንም ወደማያተርፍበት የሲኦል መንገድ አገራችንንና ሕዝባችንን እየገፋ መሆኑን ሁሉም ኢትዮጵያዊ ዛሬ ላይ በሚገባ መገንዘብ አስፈላጊ የሆነበት ወቅት ላይ የደረሰን ይመስለኛል። ነገ በጣም ይዘገያል የዘገየ (too little too late) ይሆናል።

    ከዚህ አሳፋሪና ለሀገራችን ህልውና ብሎም ለኢትዮጵያ 105 ሚሊዮን ሕዝብ አብሮነት፣ ለኢትዮጵያ አንድነት ቀጣይነት እጅግ አስጊ ሁኔታ በተፈጠረበት በአሁኑ ወቅት አሸናፊ የሚሆነው ማነው? ሁሉንስ ድልና ወርቅ አፋሽ የሚሆነው ማነው? ብቸኛ ተጠቃሚስ ይኖራል ወይ? በሰላም ደሴት በደስታና በፍሰሃ ሊኖር የሚችለውስ ማነው? ስለእውነት፡ ስለሀቅ ለመናገር ማንም እንደማይሆን፣ ማንም እንደማይተርፍ በእርግጠኝነት መተንበይ ይቻላል። ሁላችንም ተያይዘን ወደ እልቂት፣ ወደ ሁለንተናዊ ውድቀት፣ ወደ ሲኦል እያዘገምን ይመስለኛል።

    ስለዚህ ወግኖቼ፥ ቆም ብለን ማሰብ ብልህነት ነው። ነገን ማሰብ፣ በተረጋጋና በምክንያታዊነት ዛሬን በትዕግስትና በስልት መራመድ አሰፈላጊና ወሳኝም ናቸው። የአማራውንም ጥቅምና ደኅንነት፣ የሌላውን ኢትዮጵያዊ ማኅበረሰቦች/ብሄሮች፣ አብሮነት፣ የአማራውንም ሆነ የሌላውን እኩልነት፣ መብት፣ ደህንነት፣ ለማምጣት በጥንቃቄ፣ በሕግ አግባብ፣ በሰላማዊ መንገድ፣ አስቦ፣ በአስተውሎ መራመድ የነገን ውድመት፣ የሀገር መበታተን፣ የሕዝብንም እልቂት የሚከላከል ሁሉም ሕዝቦች በጋራ በሰላም፡ በዴሞክራሲ፣ በሕግ የበላይነት፡ በእኩልነት የሚኖሩባት ኢትዮጵያን የሚያረጋግጥልን ብቸኛ መንገድ መሆኑን ሁሉም ኢትዮጵያዊ ዜጋ፣ ሁሉም የአማራ መሰረት ያለው ኢትዮጵያዊ ሁሉ በውጭም በሀገር ውስጥም ሊያጤነው የሚገባ ይመስለኛል። የመጨረሻው ደወል እያቃጨለ መሆኑ እየተሰማኝ ነው። ኢትዮጵያ እንደ ሀገር፣ ሁሉም ሕዝቦች፣ ማኅበረስቦች፣ በእኩልነት፣ በፍትህ፣ በሕግ የበላይነት የሚኖርባት ኢትዮጵያን ሁሉም ኢትዮጵያዊ፣ የአማራ መሰረት ያለው ኢትዮጵያውያን ሁሉ በጥሞና አስበን፣ አስተውለን፣ አቅደን መንቀሳቀስና ሀገራችንን ከጥፋት የማዳኛው ወቅት አሁን ነው፣ ዛሬ ነው።

    እግዚአብሔር ሀገራችንና ሕዝባችንን ይጠብቅልን፤ ስላሙን ያውርድልን።
    ነአምን ዘለቀ

    የአማራ ሕዝብ


    Anonymous
    Inactive

    አብረው ማልቀስ እንጅ አብረው መቆም የማይችሉ ማሽንኮች ተፈልፍለው ሀገሬን ዕረፍት ነሷት። ለቅሶ ቤት ለመድረስ አዛኝ ቅቤ አንጓች ሁላ ከአለባበሱ እስከ አነጋገሩ አሳምሮ ይግተለተል እንደሆነ እንጅ፣ መቃብር ላይ ለመላቀስ ቀብር ለማስፈጸም ይደምቃል እንጅ ቁም ነገር ላይ ነጥፎ በጠመንጃ መፈላለጉን ትውልዱ ጀብድ አድርጎታል። እየሳቁ መግደል ሕገ-መንግሥቱ ሆኗል። የመግለጫ ቃል በማዥጎድጎድ የሸፍጥ ኑሮውን ተክኖታል።

    ሀገሬን ምን ነካት?
    አባይነህ ካሴ (ዲ/ን)

    ከሰቀቀናሟ ዕለተ ቀዳሚት ሰኔ 15 እስከ ዛሬዋ ዕለተ ሰኑይ ሰኔ 17 ቀን 2011 ዓ.ም. ሕይወታቸውን በጥይት ላጡት ሁሉ እግዚአብሔር ነፍሳቸውን በቅዱሳን እቅፍ በገነት ያኑርልን፤ ለሐዘንተኞች በሙሉ ሁሉም ሟቾች የኢትዮጵያ ቤተሰቦች ናቸውና ለኢትዮጵያውያን ሁሉ አረጋጊው መንፈስ ቅዱስ አጽናኝ መልአክን ይዘዝላችሁ። ሞት ማንም ይሞታል፤ ብርቆች ሲሞቱ ግን ራሱ ሞት ያነጋግራል።

    ከሩቅ ከአድማሱ ሥር የብርሃን ብልጭታ ሲታየን ‘ሊነጋ ነው’ ስንል፣ የሳቀልንን ወገግታ ተከትለን በተስፋ ዓለም ስንፏልል፣ ደረስንብህ ስንለው ብርሃናችን ወዴት ሔደብን? በጥሩር ፀሐይ ሰማይ ሥር የውኃ ሽታ ያዘለ ነጭ ባዘቶ ደመና ሊያዘንብልን ነው ስንለው እንዳንጋጠጥን መና ቀረ። በርኅቀት ሳይሆን በርቀት ተሰወረ። እኛን ቀርቶ ሊቃውንቱን አደናገረ። መጣ ያልነው እጃችን ገባ ያልነው ሁላ እየጣለን በረረ። ማር ያልነው ከምን ጊዜው መረረ፣ ወተት ስንለው የነበረው ከመቼው ጠቆረ፣ ሰላም ምነው ኢትዮጵያችንን አፈረ?

    ‘እኔ፣ እኔ፣ እኔ’ ከሚለው ባሕር ‘እኛ፣ እኛ፣ እኛ’ የሚል የቡድን ውሽንፍር ውስጥ ገባንና ኢትዮጵያን፣ ሀገሬን ረሳናት። እርሷም እነዚህ ከንቱዎች እንኳን ለእኔ ለራሳቸው የማይሆኑ ገልቱዎች ብላ መታዘቡን ቀጥላለች። የደሟን እንባ ወደ ውስጧ ሕቅ ብላ ታነባለች። ከላይ ከላይ ደማቅ ፈገግታ እያሳየች። የጣቷ አንጓዎች እኔ እበልጥ እኔ እበልጥ ሲሉ ሲገዳደሉ ዝም ብላ ታለቅሳለች። የጠጒሮቿ ዘለላዎች በራሷ ላይ ሲሻኮቱ በሐዘኗ በግናለች፤ በክፉ ጦር ልቧን ተወግታለች። ሀገሬን ምን ነካት? ምንስ ነው የሚበጃት?

    አብረው ማልቀስ እንጅ አብረው መቆም የማይችሉ ማሽንኮች ተፈልፍለው ሀገሬን ዕረፍት ነሷት። ለቅሶ ቤት ለመድረስ አዛኝ ቅቤ አንጓች ሁላ ከአለባበሱ እስከ አነጋገሩ አሳምሮ ይግተለተል እንደሆነ እንጅ፣ መቃብር ላይ ለመላቀስ ቀብር ለማስፈጸም ይደምቃል እንጅ ቁም ነገር ላይ ነጥፎ በጠመንጃ መፈላለጉን ትውልዱ ጀብድ አድርጎታል። እየሳቁ መግደል ሕገ-መንግሥቱ ሆኗል። የመግለጫ ቃል በማዥጎድጎድ የሸፍጥ ኑሮውን ተክኖታል።

    በተመቸ ግርድፍ ቃል ወንድምን በመዝለፍ ድንበር በመዝለል ከልክ በላይ በማለፍ አጥንት የሚወጋ የቃል ጦር በማላጋት እና በመወራወር ሀገር መቁሰሏን ማን የወደዳት ተረዳላት? ንክንኩ ድንጋይ ይፈልጣል፤ የመከራ መዓት በአፍላጋቱ ይጓፍጣል፤ አላውቅም የሚል ጠፍቶ ሁሉም ሁሉን ያውቃል። አዎ ሁሉ ዐዋቂ ሲሆን ሁሉም ይታመማል ያን ዕለት ያን ሠዓት መድኃኒት ይጠፋል።

    ለሞቱት አሟሟት የሰማነው ትርክት ልብ አያሳርፍም፤ ገና አበቅ አለበት። እርሱ ሲጠራ የሚታይ ለጊዜው ግን የተሸፈነ እውነት እንዳይኖር ያሰጋል። ከአንድ ወገን ብቻ የሚሰማ በጥፍር የሚያቆም ንግግርም ቢሆን ታማኝነቱ ምን ጊዜም ከአጠራጣሪነት አይዘልልም። ጊዜ እያወጣ የሚያሰጣው እውነት ይኖራል።

    ወታደር ዘር የለውም፤ ‘እኔ የኢትዮጵያ ወታደር ነኝ’ ሲል የነበረውን መልካም ወላዲቷ አምጣ የወለደችውን ጀግና እንደዋዛ ማጣት አለው ብዙ ንዴት፣ አለው ብዙ ቁጭት። ገዳይ የተባሉት ወይ በተኩስ ልውውጥ፣ ወይ ራስን በመግደል እየተባለ ሞታቸው ይነገራል። አይታመንም ባይባልም ተጠግቶ ላየው ምኑም አያሳምንም።

    አንደኛ፡- ብርጋዴር ጄኔራል አሳምነው ጽጌ ባሕር ዳር አጠገብ ዘንዘልማ በሚባለው አካባቢ መገደላቸው መነገሩ ጥርጣሬውን ከፍ ያደርገዋል። እኒህ ሰው ተሳዳጅ (fugitive) ሆነው ባለበት ጊዜ አብሯቸው ከነበሩም እንኳ ከጥቂት ተከታዮች በስተቀር ብዙ አጃቢዎች እንደማይኖሯቸው ይታወቃል። ዘንዘልማ ከባሕር ዳር ከተማ ዓባይን ተሻግሮ ያለ አካባቢ እንደመሆኑ በርከት ያለ አጃቢ ይዘው ሊሻገሩ ይችላሉ ብሎ መገመት አይቻልም። በሦስት ምክንያት፥ አንደኛ በከፍተኛ ጥበቃ ሥር ባለችው ከተማ ውስጥ ተሰውረው ቆይተው ነበርና። ሁለተኛ በድልድይ የሚሻገሩ ከሆነ ከፍተኛ ጥበቃ እንደሚደረግበት በመገመት በርከት ብሎ ለማለፍ ቀርቶ ራሳቸው ላለፉበት መንገድ እንኳ ያነጋግራል። ሦስተኛ በድልድይ ካልተሻገሩ ወይ በዋና ወይ በታንኳ ምናልባትም በጨለማ ዓባይን አቋርጠው ሊሆን ይችላል። ይህም በርከት ለማለት የሚመች አይደለም።

    እኒህ ሰው የነገሩ ሁሉ መነሻ እና አቀነባባሪ ተደርገው ስማቸው እየተነሳ ይገኛል። እንደዚህ ያለውን ቀንደኛ በከበባ መያዝ ሲገባ ወደ መግደል የተሔደበት መንገድ ሌላ ጥያቄ ከማስነሳት አያድንም። በዚህ ላይ ሰውዬው ሲታኮሱ ጥይት አልቆባቸው እንደነበር መረጃ ተሰጥቷል። ይህ ከሆነ ደግሞ አስጊነታቸውን በብዙ ደረጃ ቀንሶት ነበርና ለመያዝ የበለጠ ምቹ እንደነበር ያመላክታል። የተባሉት ሁሉ ትክክል ከሆኑ መረጃ ማጥፋት ዓይነተኛ ተልዕኮ ለነበረው ዘመቻ (operation) ብቻ የተፈጸመው ድርጊት ትክክል ይሆናል። ሰውዬው በአካል ቢያዙ የሚያወጡት መረጃ እንደሚኖር በመስጋት በሕይወት ከሚቆዩ ሞታቸውን ማቅረቡ ተመርጦ ሊሆን ይችላል። ራሳቸውን ገደሉ ሳይሆን የተባለው በተኩስ ልውውጥ ተገደሉ ነው። ቀባብቶ ማምጣት ሊኖር ይችላል። እውነትን መልሶ በማቋቋም ‘አይ ሰውየው ራሳቸውን ነው የገደሉት’ የሚል ዜና ከመጣ ደግሞ ነገሩ ዘወርዋራ የሆነበትን ምክንያት ማወቁ ይሻላል።

    ሁለተኛ፡- የአቶ ምግባሩ ከበደ ሞት። ሌላው ተስፋ ሊሰጥ ወደ እውነተኛው መረጃ ሊያደርስ ይችል የነበረው የምግባሩ ከበደ ሞት መረጃ የማጥፋቱን ሥራ አቀላጥፎታል ብሎ ላለማሰብ የሚከለክል ነገር የለበትም። ይህ ሰው በሠዓታት ውስጥ ቅርብ ሀገር እስራኤል ደርሶ ሊታከም ይችል እንደነበር መገመት የማንችልበት ዘመን ላይ አይደለንም። መሞኛኘት እንዳይሆን እንጅ ወዲያው የጸጥታ ቁጥጥር እንደተደረገ ሲነገረን አምሽቷል። በሄሊኮፕተር በታገዘ መንገድ ለተሻለ ሕክምና መወሰድ ነበረባቸው። ይህ ለምን አልሆነም?

    ሦስተኛ፡- የጀኔራል ሰዓረ መኮንን ጠባቂ ሞት*። ‘ተይዘዋል’ እየተባለ በየዜና ማሠራጫው ሲነገር የነበረው ሰው ‘ራሱን ገድሏል’ ወደሚል ዜና የተቀየረበት መንገድ እንድንጠረጥር እንጅ እንድንተማመን የሚያደርገን አይደለም። ራሱን የገደለን ሰው ተይዟል ብሎ ዜና የሚሠራባት ምክንያት ሴራን (conspiracy) ያሻትታል እንጅ ቅቡልነት አያስገኝም። [* የአገሪቱ ጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ጄነራል ሰዓረ መኮንንና ከፍተኛ ወታደራዊ መኮንን ጄነራል ገዛኢ አበራን ተኩሶ ገደለ የተባለው የጄነራል ሰዓረ ጠባቂ ራሱን ያጠፋው ወዲያው መሆኑን የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር እንደሻው ጣሰው ዛሬ በሰጡት መግለጫ መናገራቸው ይታወሳል። ማምሻውን ደግሞ ፌደራል ፖሊስ በብሄራዊው ቴሌቪዥን ኢቢሲ ራሱ የሰጠውን መግለጫ አስተባብሎ ጠባቂው በሕይወት እንደሚገኝ አስታውቋል። – ቢቢሲ ዜና አማርኛ]

    አራተኛ፡- በዚያ ጭንቅ ሰዓት ጀኔራል ሰዓረ ቤት መሆናቸውም ሌላው ያልተፈታ እንቆቅልሽ ነው። ከቤቱ ሆኖ “የመንግሥት ግልበጣ” የተባለን ነገር የሚከታታል ጀኔራል አለ ብሎ ለመናገር አያስደፍርም። ሰውዬውም እንደዚህ ዓይነት ጠባይ የለባቸውም፤ ሀገር ሳታርፍ የሚያርፉ ሰው አልነበሩምና። በቢሯቸው ሆነው ከፍተኛ የአመራር ሥራ ሊሠሩ በሚገባበት ሠዓት ቤታቸው የተኙበት ምክንያት ምንድን ነው? እውን ነገሩን አውቀውት ነበርን?

    አምስተኛ፡- ጉምቱዎቹ ባለሥልጣናት ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር ደመቀ መኮንን በግል ጉዳይ፣ የውጭ ጉዳይ ሚንስትር ገዱ አንዳርጋቸው ለሥራ ብለው አንዱ አሜሪካ ሌላው ጀርመን እግራቸው በረገጠበት ቀን የመሆኑ ግጥምጥሞሽስ እንዴት በዋዛ ይታለፍ ዘንድ ይችላል?

    እነዚህ ሁሉ ሲጠቀለሉ አቅጣጫቸው ሌላ ያሳያል። ከተነገረን ምህዋር በዘለለ ሁኔታ አንዳች የተቀነባበረ ሴራ ካልነበረ በቀር ወንድም በወንድሙ ላይ እንደዚህ ዓይነት ጭካኔ ያሳያል ብሎ መገመት ይከብዳል። ገና ደብዛዛ መረጃ ላይ ተቀምጠን ጣት ወደ መጠቋቆሙ መሔዱ አያዋጣም። ይሄኛው መንገድ ሌላ ጥፋት ያመጣልና።

    በዶ/ር አምባቸው መኮንን፣ በምግባሩ ከበደ፣ በእዘዝ ዋሴ፣ በጀኔራል ሰዓረ መኮንን፣ በብርጋዴር ጀኔራል ገዛኢ አበራ፣ በብርጋዴር ጀኔራል አሳምነው ጽጌ ሞት በእጅጉ አዝነናል። ስማቸው ባልተነገረን በሌሎችም ሰዎች ሞት በእጅጉ አዝነናል። በዚህ ሁሉ ውስጥ ግን የምትታየን ኢትዮጵያ ናት። ቁስል የሆንባት እስኪ እንራገፍላት።

    ምንጯ ደፈረሰ እንጅ አልነጠፈም። እስኪጠራ መታገስ ዋጋ ቢያስከፍልም ድፍርሱን ጠጥቶ ከመታመም ታግሶ ጥሩውን መጠጣት ጥምን ይቆርጣል፣ ጤናም ይጠብቃል። በደፈረሰ ውኃ ውስጥ ምን እንዳለ ማወቅ አይቻልም። ሲጠራ ግን ይለያል። የሦስቱን ቀን ሁናቴ በጥሞና እንየው፣ ድፍርሱን ለማጥራት ጊዜ እንስጠው። ለመኮነኑ አንቸኩል። ለመቧደንም አንጣደፍ። እነዚህ ከላይ የተነሡት እና ሌሎችም ጥያቄዎች ሲመለሱ የሚወገዘው ይወገዛል።

    ይህ ጥቁር ደመና መግፈፉ አይቀርም። እስከዚያው ግን ጨለማ መንገሡን ተቀብሎ ለብርሃኑ መትጋት መውጣት እና መውረድ ብቻ ነው አማራጩ። የዘሩን ዘጋተሎ አምዘግዝጎ ወዲያ ጥሎ፣ የሀገርን ሕመም ለመታመም አብሮ ቆስሎ የእናት ልጅ የእናቱን ልጅ ሲደክመው አዝሎ፣ ወድቆ እንዳይቀር ውኃ በልቶት ጉልበቱ ዝሎ፣ እየቆረሰ አጉርሶ እየቀደደ አልብሶ፣ ወደ ብርሃን መውጫው ሥር ካልተጓዘ በማለዳ፣ ተከፍሎ አያልቅም የእናት ሀገር የአደራ ዕዳ።

    አባይነህ ካሴ (ዲ/ን)

    ሀገሬን ምን ነካት?


    Anonymous
    Inactive

    የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ዶ/ር አምባቸው መኮንን መገደላቸው ተረጋገጠ
    —–

    የአማራ ክልል ፕሬዝደንት ዶ/ር አምባቸው መኮንን ትላንት (ሐምሌ 15 ቀን 2011 ዓ.ም.) በነበረው የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ተከትሎ መገደላቸውን የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን አስታውቋል።

    አቶ አምባቸውን ጨምሮ የርዕሰ መስተዳድሩ አደረጃጀት ዘርፍ አማካሪ የሆኑት አቶ እዘዝ ዋሴም በደረሰው ጥቃት ሕይወታቸውን ማጣታቸው ታውቋል። ጥቃቱ የተፈፀመው ግለሰቦቹ ስብሰባ ላይ ባሉበት ወቅት እንደሆነ ኢቲቪ አስታውቋል።

    አቶ አምባቸው መኮንን የቀድሞውን የክልሉን ፕሬዝደንት አቶ ገዱ አንዳርጋቸውን በመተካት የተሾሙት የካቲት 29 ቀን 2011 ዓ.ም. ነበር።

    የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (አዴፓ) ሐምሌ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ተፈፀመ በተባለው የመንፈቅለ መንግሥት ሙከራ እጃቸው አለበት የተባሉ ሰዎችን በቁጥጥር ሥር ማዋሉም ተሰምቷል።

    የክልሉ ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ ብርጋዴር ጀኔራል አሳምነው ፅጌ መንፈቅለ መንግሥቱን አቀነባብረዋል ተብለው በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ፓርቲው አስታውቋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ትላንት ከእኩለ ለሊት በኋላ በብሔራዊው ቴሌቪዥን ቀርበው በሰጡት መግለጫ የአማራ ክልል ባለስልጣናት የተገደሉት እና የቆሰሉት በስብሰባ ላይ እያሉ እንደነበር መናገራቸው አይዘነጋም።

    Anonymous
    Inactive

    በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ላይ የተደረገውን የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ የፌደራል መንግሥት አወገዘ
    —–

    በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ላይ የተደረገው የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ የሀገሪቱን ሕገ መንግሥት የሚፃረር፣ የክልሉ ሕዝብና መንግሥት ለረጅም ጊዜ የታገሉለትን ሰላምና መረጋጋት ለመንጠቅ የተደራጀ በመሆኑ የፌደራል መንግሥት ሙሉ በሙሉ እንደሚያወግዘው የጠቅላይ ሚንስትር ፅህፈት ቤት አስታወቀ።

    የፌደራል መንግሥት የጸጥታ መዋቅር የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራውን ሙሉ በሙሉ በቁጥጥር ሥር አውሎ በፈጸሙት አካላት ላይ ተገቢውን ርምጃ እንዲወስድ ትእዛዝ ተቀብሎ ተፈጻሚ በማድረግ ላይ ይገኛል። ይህ ጥቃት በመንግሥት መዋቅር ላይ ብቻ ሳይሆን በአማራ ሕዝብ ላይ የተቃጣ መሆኑን በመገንዘብ የክልሉ ሕዝብ አካባቢውን በንቃት እንዲጠብቅና ተረጋግቶ ሁኔታዎችን እንዲመለከት ጥሪ ቀርቧል።

    ይህን ሕገ ወጥ ሙከራ ክልሉ ብቻ ሳይሆን ማንኛውም ክልልና መላው ኢትዮጵያዊ ሊያወግዘው የሚገባ ሲሆን የፌደራል መንግሥት የታጠቁ ቡድኖችን ሕገ ወጥ እንቅስቃሴ የመቀልበስ፣ የመግታትና በቁጥጥር ሥር የማዋል ሙሉ ዐቅም ያለው መሆኑን ያረጋግጣል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን

    Semonegna
    Keymaster

    የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ዓላማው ክልሉን ለማተራመስና የህዝቡን ህልውና አደጋላይ ለመጣል ያለመ መሆኑን ገልጸው፥ በአሁኑ ወቅት የፌዴራል መንግስት ሁኔታውን የማስተካከልና ክልሉን የማረጋጋት ትዕዛዝ እንደተሰጠው አቶ ንጉሱ ጥላሁን ገልጸዋል።

    አዲስ አበባ (ኢዜአ) – በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ መደረጉን በኢፌዴሪ ጠቅላይ የሚኒስቴር ፅህፈት ቤት የፕሬስ ሴክሬታሪያት ኃላፊ አቶ ንጉሱ ጥላሁን ገለጹ። አቶ ንጉሱ ሐምሌ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ምሽት ላይ ለኢትዮጵያ ቴሌቪዥን (ኢቲቪ) በሰጡት መግለጫ በክልሉ መንግስት ላይ የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ተደርጓል።

    በተደራጀ ሁኔታ በመንግስት መዋቅር ላይ ጥቃት ለመሰንዘር የተሞከረው የተደራጀ እንቅስቃሴ ከሽፏል ነው ያሉት አቶ ንጉሱ ጥላሁን ።

    የአማራ ክልል ወደ መረጋጋት እየመጣ ባለበትና እና ሕዝቡ ቀደም ሲል ያነሳ የነበረውን የህግ የበላይነት ጥያቄ ለመመለስ እየተሠራ ባለበት ወቅት የተሰነዘረው ጥቃት የክልሉ መንግስት ብቻ ሳይሆን የአማራ ሕዝብ ላይ የተሞከረ ነው ብለዋል።

    ሙከራው ክልሉን ለማተራመስና የህዝቡን ህልውና አደጋላይ ለመጣል ያለመ መሆኑን ገልጸው፥ በአሁኑ ወቅት የፌዴራል መንግስት ሁኔታውን የማስተካከልና ክልሉን የማረጋጋት ትዕዛዝ እንደተሰጠው ገልጸዋል።

    የፌዴራል መንግስቱ ጣልቃ በመግባት ይህን መሰሉን ተግባር የመግታት ሥራ እንደሚሠራና ህብረተሰቡም አካባቢውን በንቃት እንዲጠብቅ መልዕክት አስተላልፈዋል።

    ጸረ-ህገ መንግስትና መፈንቅለ መንግስቶች እንዲሁም በታጠቁ ኃይሎች የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ተቀባይነት እንደሌላቸው ገልጸው፥ ክልሉን ወደነበረበት ሰላማዊ ሁኔታ ለመመለስ ህብረተሰቡ ከመንግስት ጋር በትብብር እንዲሠራ ጥሪ አቅርበዋል።

    አቶ ንጉሱ ጥላሁን በዚህ ጉዳይ ላይ ከኢትዮጵያ ቴለቭዥን ጋዜጠኛ ጋር ያደረጉትን አጭር ቃል ምልልስ እዚህ ጋር በመጫን ያዳምጡ።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦

    የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ


    Anonymous
    Inactive

    ቄሮ ነጻ ያወጣው እስክንድር ነጋን ሳይሆን እድሜያቸውን ሙሉ የህወሃት ተላላኪና ማላገጫ ሆነው የኖሩትን አቶ አዲሱ አረጋን እና ሌሎች የኢህአዴግ (የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ግንባር) ካድሬዎችን ነው።

    አቶ አዲሱ አረጋን ነጻ ያወጣችው የእስክንድር ፌስታል
    ያሬድ ኃይለማርያም

    ከወያኔ ጋር የተደረገው የነጻነት ትግል የዛሬ ሦስት ዓመት የተጀመረ የመሰላቸው አንዳንድ የኦዴፖ (የኦሮሞ ዴሞክራቲክ ፓርቲ) አመራሮች አልፎ አልፎ የሚሰጡት መግለጫ እጅግ አስተዛዛቢ እና አስነዋሪም ነው። ባላፊት ሃያ ሰባት ዓመታት ብዙዎች የህወሃት (ሕዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ) የማፈኛ መሣሪያ እና አሽከር ካድሬ ሆነው የገዛ ሕዝባቸውን ሲያሰቃዩ፣ ሲገድሉ፣ ሲገርፉ እና ሲያሰድዱ እንዳልኖሩ፤ በብዙ ሚሊዮኖች ‘ጎመን በጤና’ ብለው የአፈና እንቆቋቸውን እየተጋቱ ሁሉንም ነገር እንዳላየ እና እንዳልሰማ መስለው ለሥርዓቱ ጉልበት እንዳልሆኑ፤ ዛሬ በለውጥ ማግስት ያንን የአፈና ሥርዓት ያለፍርሃት ሲታገሉ፣ ሲታሰሩ እና ሲገረፉ የቆዩ የእስክንድር ነጋ አይነት የነጻነት ታጋዮችን ሲያጣጥሉ፣ ሲያንኳስሱ፣ ሲያስፈራሩ እና ሊያሸማቅቁ ሲሞክሩ ማየት እጅግ ያማል።

    አቶ አዲሱ አረጋ፥ ያ’ኔ!

    እነ ቄሮ፣ ፋኖ፣ ዘርማ እና ሌሎችም የመንደር ነጻ አውጪ ቡድኖች ሳይፈጠሩ ወይም መኖራቸው ሳይታወቅ በፊት ከወያኔ ጋር የነበረውን የሃያ ሰባት ዓመት ትንቅንቅ እና እልህ አስጨራሽ ትግል ብቻቸውን የተጋፈጡት እስክንድርን ጨምሮ በጣት የሚቆጠሩ ጋዜጠኞች፣ የመብት አቀንቃኞች እና ተሟጋቾች፣ ጥቂት ምሁራን እና ጥቂት የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓሪቲ ድርጅቶች አመራር እና አባላት ናቸው። የዛሬዎቹ ሹማምንት የህወሃት ጥርስ እና ክርን ሆነው የገዛ ሕዝባቸውን ይገዘግዙ እንደነበር እንዲህ በአጭር ጊዜ መዘንጋታቸው የሚያስገርም ነው። ከህወሃት ጫና ተላቀው ዛሬ እንደልብዎ እንዲናገሩ ያደረገችዎት ነጻነት ከእነ እስክንድር ነጋ እና ሌሎች ለዜጎች መብት መስዋዕትነት የከፈሉ ኢትዮጵያዊያን በመከራ ጊዜ ከሸከፏት ፌስታል መመንጨቷን ያወቁ አልመሰለኝም።

    የእስክንድር እና የጃዋር ኢትዮጵያን ሳስባት

    ቄሮ ነጻ ያወጣው እስክንድር ነጋን ሳይሆን እድሜያቸውን ሙሉ የህወሃት ተላላኪና ማላገጫ ሆነው የኖሩትን አቶ አዲሱ አረጋን እና ሌሎች የኢህአዴግ (የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ግንባር) ካድሬዎችን ነው። እስክንድር ነጋ እና ሌሎቹ በግፍ ታስረው የነበሩ የመብት ታሟጋቾች እና የነጻነት አቀንቃኞች ነጻ የወጡት ራሳቸው በከፈሉት መስዋዕትነት ነው። ያጣጣሏት የእስክንድር ነጋ ፌስታል ለእርሶም ነጻ መውጣት ትልቅ ድርሻ አላት።

    የመብት ተሟጋቾችን፣ በክፉ ቀን ለሕዝብ ነጻነት ዋጋ የከፈሉ ጋዜጠኞችን፣ ሲታሰሩና ሲሰቃዩ የኖሩ የፖለቲካ መሪዎችን፣ ምሁራንን እና የአገር ባለውለተኛ የሆኑ ግለሰቦችን ባልተገራ የካድሬ አንደበት መዝለፍም ሆነ ክብራቸውን መንካት እና መብታቸውን ማፈን ለውጥ እንመራለን ከሚሉ አካላት አይጠበቅም።

    ያሬድ ኃይለማርያም

    አቶ አዲሱ አረጋን ነጻ ያወጣችው የእስክንድር ፌስታል


    #11158
    Anonymous
    Inactive

    አቶ አዲሱ አረጋ የዛሬ ሁለት ዓመት፥ ሕዝባዊ እንቢተኝነቱ እንዳይቀጥል “አይደገምም” በማለት ታሳሪዎችን በማስተማር¡¡ የተጀመረው ሕዝባዊ እንቅስቃሴ ኒዮሊበራሎች በአገራችን “የቀለም አብዮት” ለማስነሳት እንደሆነ፣ የተፈጠውን የመልካም አስተዳደር ችግር ለመፍታት ጥረት እየተደረገ እንደሆነ ነግረውን ነበር።

    አቶ አዲሱ አረጋ፥ ያ’ኔ!
    (ይድነቃቸው ከበደ)

    የህወሃት መራሹ የኢህአዴግ የአገዛዙ ሥርዓት በሕዝባዊ እንቢተኝነት የዛሬ ሦስት እና ሁለት ዓመት በሚናጥበት ወቅት፤ መስከረም ወር 2009 ዓ.ም. የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በማወጅ ሕዝባዊ ትግሉን ለመቀልበስ፣ በአገዛዙ በኩል የመጨረሻ እና ትልቁ የተባለ አፋኝ አዋጅ ታውጆ ነበር።

    የአዋጁን መውጣት ተከትሎ፤ ቁጥሩ ቀላል የማይባል ዜጎች በተለያዩ ቦታዎች በኃይል በማስገደድ እስራት ተፈጽሟል። በአዋሽ አርባ፣ አዋሽ ሰባት፣ ብርሸለቆ፣ ጦላይ፣ ሰንከሌና ሌሎች ካምፖች ውስጥ ለ‹ተሃድሶ ስልጠና› በሚል ለመግለፅ የሚከብዱ ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት በእነዚህ ካምፖች ውስጥ ተፈጽሟል። በተለይ ከአዲስ አበባ ተይዘን ወደ አዋሽ 7 ከገባን ታሳሪዎች በፊት አንድ ወር ቀድመው እዚሁ ካምፕ የገቡ ከኦሮሚያ ክልል የተያዙ ወጣቶች የደረሰባቸው በደል ለመግለጽ እጅግ በጣም የሚከብድ ሰቅጣጭ ነው።

    በማጎሪያ ካምፖች ውስጥ በሺዎች በማሰር ይፈጸም የነበረው ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት፣ በዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተቆርቋሪ ተቋማት፣ በአገር ወዳደ ኢትዮጵያዊያን ዘንድ ትልቅ መነጋገሪያ ሆነ። ይህ ደግሞ በወቅቱ በአገዛዙ ሥርዓት ላይ ጫና በመፍጥር የተጀመረው ሕዝባዊ እንቢተኝነት ሌላ ተጨማሪ ጉልበት ሆነ።

    ከጥቂት ቀናት በኋላ የሰብዓዊ መብት ጥሰት መኖር አለመኖሩን እናጣራለን ያሉ “በመንግስት” ፍቃድ ታጉረን የምንገኝበት ካምፕ እንዲመጡ ተደርጓል። እንዲያናግራቸው ከተመረጡ ታሳሪዎች ጋር እኛን ወክለው ያዩትን እና የደረሰባቸውን የመብት ጥሰት ተናግሯል። በወቅቱ የመንግስት ሚዲያዎች ዜና ሲያቀርብ መሠረታዊውን የመብት ጥሰት ወደ ጎን በመተው፣ በጥሩ ሆኔታ ላይ እንደምንገኝ እና ስልጠና እየተከታተልን እንደሆነ ይገልጹ ነበር።

    በዚያን ጊዜ አቶ አዲሱ አረጋ፥ ያ’ኔ በአዋሽ አርባ፣ አዋሽ ሰባት፣ ብርሸለቆ፣ ጦላይ፣ ሰንከሌና ሌሎች ካምፖች ውስጥ በመዘዋወር፤ ‘መንግስት’ ወጣቶችን አላሰረም ‹ተሃድሶ ስልጠና› እየሰጠ ነው¡¡ ለማስባል በሚደረገው ጥረት፣ መንግስታዊ ድራማ አስመስሎ ለመከወን የአንበሳውን ድርሻ በታታሪነት ከፈጸሙት መካከል አቶ አዲሱ አረጋ አንዱ ናቸው።

    በተለይ እኔ በነበርኩበት ካምፕ አዋሻ 7፤ “አይደገምም” ኢትዮጵያ ካስመዘገበችው ዕድገት አንፃር አሁን የገጠማት “ሁከትና ብጥብጥ” አይገባትም፤ የሚል እንድምታ ያለው፣ “እኛ ታሳሪዎች” ሁከትና ብጥብጥ ማቆምና ማስቆም እንዳለብን የሚያትት። ሌላኛው ደግሞ “የቀለም አብዮት” ኒዮሊበራሎች፣ ግብጽ እና ኤርትራ ኢትዮጵያ ውስጥ ብጥብጥ እና አለመረጋጋት ለመፍጠር ስለሚፈልጉ “እኛ ታሳሪዎች” ከዚህ “የቀለም አብዮት” እራሳችንን እንድንጠብቅ የሚያሳስብ “የስልጠና” አርዕስት ላይ አቶ አዲሱ አረጋ ስልጠና በመስጠት በእኛ ታሳሪዎች ላይ “እጅግ በጣም” ጎብዘውብን ነበር¡¡

    አቶ አዲሱ አረጋ፥ ያ’ኔ ማለትም የዛሬ ሁለት ዓመት፥ ሕዝባዊ እንቢተኝነቱ እንዳይቀጥል “አይደገምም” በማለት ታሳሪዎችን በማስተማር¡¡ የተጀመረው ሕዝባዊ እንቅስቃሴ ኒዮሊበራሎች በአገራችን “የቀለም አብዮት” ለማስነሳት እንጂ፣ መጪው ጊዜ የኢትዮጵያ ሕዳሴ መሆኑ፣ ኢትዮጵያ ቁጥር አንድ ጠላቷ ድህነት እንደሆነ እና በወቅቱ የተፈጠው የመልካም አስተዳደር ችግር ለመፍታት ጥረት እየተደረገ እንደሆነ። አቶ አዲሱ ለመናገር እንጂ ለማዳመጥ ወይም ለመጠየቅ ቅንጣት ፍላጎታ ሳይኖራቸው እሳቸው እና “መንግስታቸው” ብቻ የሚፈልጉትን ነግረውን ያ’ኔ ሄደዋል።

    እኚህ ሰው አሁን ላይ “የለውጥ ኅይል” ከሚባሉት ውስጥ አንዱ ናቸው።

    ይድነቃቸው ከበደ

    አቶ አዲሱ አረጋ


    Semonegna
    Keymaster

    ሰናይ መልቲሚዲያ በበሳል ባለሙያዎችና በፕሬስ እድገት ውስጥ ከፍተኛ ሚና በተጫወቱ አንጋፋና ወጣት ጋዜጠኞች አስተባባሪነት የተቋቋመ የሕዝብ የሚዲያ ነው።

    ትላንት፣ ዛሬ እና ነገን እንደ ድልድይ የሚያስተሳስር ፣ የኢትዮጵያን ታሪክ፣ የዛሬን ተጨባጭ ሁኔታ ከግምት አስገብቶ፣ ነገ ላይ የተሻለች ኢትዮጵያን ለመፍጠር የሚረዱ አዳዲስ መርሀግብሮችን (ፕሮግራሞች) እና አቀራረቦችን ማስተዋወቅና አሁን በሥራ ላይ ያሉ የመገናኛ ብዙኃን ክፍቶችን መሙላት ዋንኛ ዓላማዉ በማድረግ፣ ሕዝብ በእኩልነት ሃሳቡን መግለጽ የሚቻልበት ሚዲያ ነው። ለዚህም “ሰናይ” ብለን ብዙኃኑ ባለው አቅሙ የድርሻው ባለቤት ሆኖ የእኔ የሚለውን ታላቅ የመልቲሚዲያ ተቋም ይፋ ለማድረግ እንወዳለን።

    ሰናይ መልቲሚዲያ የሕዝብ፣ ለሕዝብ፣ በሕዝብ የሆነ የመጀመሪያ ሚዲያ፤ እያንዳንዱ ዜጋ ያለብሔር ልዩነት፣ ያለጾታ፣ ያለእድሜና ክልል ገደብ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በሰናይ ቴሌቪዥን (ሰናይ ቲቪ)፦

    • የተሻለ ፕሮግራም የሚሰራበት የራሱ ቲቪ አክስዮን ባለድርሻ ይሆናል ፤ምርትና አገልግሎት የሚያስተዋውቅበት ቲቪ አክስዮን ባለድርሻ ይሆናል፤የመረጃ፣ የቁም-ነገር እና የመዝናኛ ፍላጎትንና ጥምን የሚያረካ ቲቪ አክስዮን ባለድርሻ ይሆናል፤
    • የሰናይ ቲቪ የመጀመሪያው የሕዝብ ሚዲያ ኔትወርክ (network) ሲሆን በመጀመሪያ በቴሌቭዥን ሳተላይት ስርጭት ጀምሮ በመቀጠል ወደ ሬድዮ፣ ድረ-ገፅ እና በሶሻል ሚዲያ (social media) የሚያካትት ይሆናል፤
    • በሰናይ ቲቪ እያንዳንዱ ዜጋ ካለበት ቦታ የኔ በሚለው መልኩ በቀጥታ እንዲሳተፍና እቅድ ውስጥ መካተት የሚችልበትን ሁኔታ ይፈጥራል፤ እውነተኛና ነፃ አማራጭ ሚዲያ ይሆናል። ድምፅ አልባ ለሆነውም ለኢትዮጵያ ሕዝብ ሃሳቡን በነፃነት የሚገልጽበት መንገድ ይከፈታል፤ የተለያዩ አመለካከቶችና መልዕክቶች የሚተላለፉበት ጭምር ይሆናል።

    ሰናይ መልቲሚዲያ የተመሰረተው እየታሰሩ፣ እየተፈቱ ለሕዝብ መሰዋዕትነት ሲከፍሉ በቆዩ ነባር የነፃው ፕሬስ ጋዜጠኞች አስተባባሪነት፤ ብዙኃኑ ሕዝብ ሊገዛው በሚያስችል መልኩ ሰላሳ አምስት ሺህ (35,000) አክስዮኖችን በማቅርብ ሲሆን፤ እያንዳንዳቸው አንድ ሺህ ብር ዋጋ ያላቸው በአጠቃላይ የሰላሳ አምስት ሚሊዮን ብር ዕጣ ለሽያጭ አቅርበዋል። በዚህም መሰረት የአንድ አክስዮን ዋጋ 1,000.00 (አንድ ሺህ) ብር ሲሆን፤ ዝቅተኛውና አንድ ሰው ሊገዛ የሚችለው የአክስዮን መጠን 5,000.00 ብር (አምስት ሺህ ብር) ዋጋ ያላቸው አምስት ዕጣዎች ሲሆን፤ አንድ ሰው ሊገዛ የሚችለው ከፍተኛው የአክስዮን ብር መጠን 2,800,000.00 ( ሁለት ሚሊየን ስምንት መቶ ሺህ ብር) ዋጋ ያላቸው 2,800 ( ሁለት ሺህ ስምንት መቶ) የአክስዮን ዕጣዎች ናቸው። ይህ ማለት፤ ማንም ወገን ከስምንት ከመቶ በላይ አክስዮን አንዳይገዛ ገደብ አለበት። ሰናይ መልቲሚዲያ በአንድ ወገን ቁጥጥር ስር እንዳይወድቅ የሚደረግበት ማዕቀፍ ተበጅቷል።

    ሰናይ ቲቪ የማንኛውንም የፖለቲካ ወገንተኝነትን የማያስተናግድ፣ የግለሰቦች የፖለቲካ እምነት የማያንጸባርቅ፣ ፍጹም ገለልተኛ ሚዲያ ነው። በመሆኑም፤ ማንኛውም ሰው፣ ከፖለቲካ ፓርቲዎች እና የሃይማኖት ተቋማት በስተቀር፣ የአክስዮን ባለድርሻ መሆን ይችላል። ለበለጠ መረጃ የፕሮጀክት አማካሪውን “ጌት አማካሪዎች” (GET Business & Investment Consultants) የንግድና ኢንቨስትመንት ማማከር፣ ድርጀቱን በግንባር በመቅረብ ወይም በስልክ-ቁጥር +251 (011) 8 12 12 33/34 በመደወል መረጃ ማግኘት ትችላላችሁ።

    ምንጭ፦ ጌት አማካሪዎች/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ሰናይ መልቲሚዲያ


    Semonegna
    Keymaster

    ‹‹የንባብ ባህላችንን እናዳብር፤ ምክንያታዊ ትውልድ እንፍጠር›› በሚል መሪ-ቃል የመጽሐፍት ሽያጭ፣ ዓወደ-ርዕይና ሲምፖዚየም አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ተማሪዎች፣ መምህራን፣ ሠራተኞችና ሌሎች እንግዶች በተገኙበት ተካሂዷል።

    አርባ ምንጭ (AMU) – በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ቤተ-መጽሐፍትና መረጃ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት አዘጋጅነት “የንባብ ባህላችንን እናዳብር፤ ምክንያታዊ ትውልድ እንፍጠር” በሚል መሪ-ቃል የመጽሐፍት ሽያጭ፣ ዓወደ-ርዕይና ሲምፖዚየም ለመጀመሪያ ጊዜ ከሰኔ 3 ቀን እስከ ሰኔ 8 ቀን 2011 ዓ.ም. ተካሂዷል።

    የዝግጅቱ ዓላማ በዩኒቨርሲቲውና በአካባቢው ማኅበረሰብ ዘንድ በንባብ ባህል ዙሪያ ሰፊ ግንዛቤ በመፍጠር እውቀት እንዲስፋፋ እና ልምድ እንዲዳብር ለማድረግ እንዲሁም ማኅበረሰቡ የመጽሐፍትን ጥቅም ተረድቶ ከሌሎች ወጪዎች በመቀነስ የመግዛት ልምድ እንዲቀስም ለማስቻል መሆኑን በዩኒቨርሲቲው የቤተ-መጽሐፍትና መረጃ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ዓለምሰገድ ካሣሁን ገልፀዋል።

    የዕለቱ የክብር እንግዳ ገጣሚ፣ ደራሲና መምህር ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ የንባብ ጅማሮ፣ ጥቅምና የመምህራን ሚናን አስመልክቶ ባቀረቡት አንኳር ሀሳብ ንባብ ሊለካ የሚችለው በአንባቢው ላይ በሚያመጣው ዘርፈ ብዙ ለውጥ እንደሆነ ገልጸዋል። ንባብ የተለያየ ነገር ግን የተዋሀደ ይዘት ያለው እንደመሆኑ ማኅበራዊ ተግባቦት እንዲጨምር፣ ተአማኒ እውቀት እንዲዳብር ብሎም ባልኖርንበት ዘመንና ቦታ በምናብ እንድንኖር የሚያደርግ ጥልቅ ምስጢር አለው ብለዋል።

    ጥሩ አንባቢ የአፃፃፍ ስልትና የቃላት አመራረጥን ከመረዳት ባለፈ በሚያነበው ጉዳይ ራሱን የሚመለከትና የሚፈትሽ እንዲሁም የሌሎችንም ስሜት መረዳት የሚችል እንደሆነ ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ ተናግረዋል። ለዚህም መምህራን ከመጽሐፍት ምርጫ አንስቶ መልካም ልምዶችን ለትውልዱ በማካፈል በመረጃ የዳበረና ያወቀ ማኅበረሰብ እንዲፈጠር የበኩላቸውን መወጣት እንደሚገባቸው አስገንዝበዋል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝደንት ዶ/ር ዳምጠው ዳርዛ በበኩላቸው ለአንድ ማኅህበረሰብ እድገት የተማረ ማኅበረሰብ መፍጠር ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ እንደመሆኑ ላለፉት በርካታ ዓመታት በአገሪቱ ከመሠረተ ትምህርት ጀምሮ እስከ ከፍተኛ ትምህርት ዘርፍ ጥረት ሲደረግ መቆየቱን አውስተዋል።

    ማንበብና መጻፍ ከግለሰብ ባለፈ ለማኅበረሰብ ሁለንተናዊ እድገት ወሳኝ ናቸው ያሉት ፕሬዝደንቱ፥ የንባብ ባህል እንዲዳብር አስፈላጊውን ቁሳቁስ በማሟላት፣ አቅምና ጊዜ በተገቢው በመጠቀም፣ ተፈላጊውን የአዕምሮና የአስተሳሰብ ለውጥ በማምጣት እንዲሁም ምክንያታዊ ትውልድ በመፍጠር ከግለሰብና ከማኅበረሰብ ባለፈ ለአገር ዕድገት አስተዋጽዖ ማበርከት እንደሚቻል ገልፀዋል። በመሆኑም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለንባብ ባህል መዳበር አጽንዖት ሰጥተው ሊሠሩ ይገባል ሲሉ ተናግረዋል።

    የዩኒቨርሲቲው አካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝደንት ዶ/ር የቻለ ከበደ በበኩላቸው በአገሪቱ ተጨባጭ ሁኔታ ምንም እንኳ ጥንታዊ የሆኑና የተለያየ ዘውግ ያላቸው የስነ-ጽሑፍ ውጤቶች እንዲሁም ወቅታዊ አዕምሯዊ ውጤት የሆኑ የህትመት ውጤቶች ቢኖሩም ከጊዜ ወደ ጊዜ የሚታየው የንባብ ባህል መቀዛቀዝ በመረጃ የበለጸገና ምክንያታዊ የሆነ ዜጋ ከመፍጠር አኳያ እንደ አገር ከፍተኛ ተጽዕኖ የሚያሳድር እንደሆነ ተናግረዋል። በአገሪቱ ለንባብ የሚውለው ጊዜ በዓለም አንባቢ ዜጋ ካላቸው አገራት አንጻር በሣምንት ለንባብ ከሚያውሉት አማካይ ጊዜ በእጅጉ መራቁን የተለያዩ ዓለም አቀፍ ጥናቶች እንደሚያስረዱም ዶ/ር የቻለ ገልፀዋል።

    በማኅበረሰቡ ዘንድ መጽሐፍትን ገዝቶ ከማንበብ ይልቅ የማኅበራዊ ድረ-ገጽ ምርኮኛ መሆን፣ የወረቀትና የህትመት ዋጋ መጨመርና ሌሎችም ለችግሩ መባባስ በምክንያትነት ይጠቀሳሉ። ይሁን እንጂ የንባብ ባህል መዳበር ወሳኝ ጉዳይ በመሆኑ ባህሉ እንዲያንሰራራና መሻሻሎች እንዲመጡ ጠንከር ያለ ጥረትን ይጠይቃል።

    በንባብና ሚዲያ ቴክኖሎጂ ዙሪያ የሚያጠነጥን የውይይት መነሻ ጽሑፍ የዶክትሬት (PhD) ተማሪ በሆኑት አቶ ተመስገን ካሣዬ ቀርቦ ከተሳታፊዎች ጋር ሰፊ ውይይት ተደርጓል። በዚህም ዘመኑ የቴክኖሎጂና የመረጃ ከመሆኑ ባሻገር የሚዲያ ተግባቦት ባህሎችን ከሌላው ጋር የመቀየጥ አቅም ከፍተኛ እየሆነ መምጣቱ ተገልጿል።

    ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት ንባብ የአንድ ወቅት ሂደት ስላልሆነ በየደረጃው ያለው ሁሉም ማኅበረሰብ ከዋና ሥራው ጎን ለጎን መጽሐፍት ማንበብን ልምድ በማድረግ ከራሱ አልፎ ለሌሎችም መትረፍ የሚያስችል አቅም ማጎልበት እንደሚገባው ገልጸዋል። በተለይም በአገራችን ያሉ ደራሲያን መጽሐፍት ስነ-ጽሑፋዊ ይዘታቸውን ሳይለቁ፣ ታሪክን ሳያዛቡ እንዲሁም በሥነ-ምግባር ረገድ የተሻለ አቀራረብ እንዲይዙ በማድረግ ንቁ ማኀበረሰብ በመፍጠር ለአገራዊ ለውጥ የበኩላቸውን እንዲወጡ ጥሪ አስተላልፈዋል።

    በመጽሐፍት አውደ ርዕይና ሲምፖዚየሙ የዩኒቨርሲቲው አመራሮች፣ መምህራንና ተማሪዎች እንዲሁም ከአርባ ምንጭ ከተማ እና ከአዲስ አበባ የመጡ የቤተ-መጽሐፍት ባለሙያዎችና የመጽሐፍት ሽያጭ መደብሮች ተሳታፊ ሆነዋል።

    ምንጭ፦ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የንባብ ባህል


    Anonymous
    Inactive

    ኢትዮጵያ ቡና ከመቐለ 70 እንደርታ ባዶ ለባዶ ተለያዩ
    —–

    አዲስ አበባ – በኢትዮጵያ ወንዶች ፕሪምየር ሊግ በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው ኢትዮጵያ ቡና እና መቐለ 70 እንደርታ ሰኔ 11 ቀን 2011 ዓ.ም. ያደረጉት ጨዋታ ባዶ ለባዶ ተጠናቋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም ከቀኑ 9 ሰዓት ጀምሮ የተደረገው 27ኛ ሳምንት ተስተካካይ ጨዋታ ያለምንም ግብ በሰላም ተጠናቋል።

    መቐለ 70 እንደርታ ዛሬ ያለምንም ግብ አቻ መለያየቱን ተከትሎ ሊጉን በ52 ነጥብ እየመራ ከለው ፋሲል ከነማን ተከትሎ በ50 ነጥብ በሁለተኛ ደረጃ ተቀምጧል። በ34 ነጥብ በሊጉ 11ኛ ደረጃ ተቀምጦ የነበረው ኢትዮጵያ ቡና በበኩሉ ነጥቡን ወደ 35 በማሳደግ በሊጉ ያለዉን ደረጃ ወደ 9ኛ ከፍ ማድረግ ችሏል።

    የፕሪምየር ሊጉ 28ኛ ሳምንት ቀጣይ መርሃ ግብር የፊታችን ቅዳሜና እሁድ የሚቀጥል ሲሆን ቅዳሜ ጅማ አባጅፋር ከኢትዮጵያ ቡና፣ ሀዋሳ ከተማ ከመከለከያ፣ ስሁል ሽሬ ከደደቢት፣ ባህር ዳር ከተማ ከወላይታ ድቻ ጋር ይጫወታሉ።

    እሁድ ሰኔ 16 ቀን 2011 ዓ.ም. የፕሪሚየር ሊጉ መሪ ፋሲል ከነማ ከሜዳው ዉጭ ከአዳማ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ፣ ሲዳማ ቡና ከድሬደዋ፣ መቐለ 70 እንደርታ በጥሎ ማለፉ ከደቡብ ፖሊስ ጋር እንደሚጫወቱ ከፌዴሬሽኑ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን

    Anonymous
    Inactive

    ኤርሚያስ ሊታሰር የሚችለው ከፈጠራና ሙግቱ በተያያዘ እንደሆነ ትልቁን ግምት መውሰድ ይቻላል። የኤርሚያስ ትልቁ “ወንጀል” ገዥዎቹና ገዥዎችን ተጠልለው የከበሩትን በእውቀት ላይ ተመስርቶ ስለሚሞግትና ስለሚወዳደራቸው፣ ስጋት ስለሆነባቸው ይመስለኛል።

    ኤርሚያስን የትኛው “ወንጀል” ሊያሳስረው ይችላል?
    (ጌታቸው ሽፈራው)

    ኤርሚያስ አመልጋን የማውቀው ሚዲያ ላይ ነበር። 2008 ዓ.ም. ክረምት ላይ ያልጠበኩት ቦታ አገኘሁት። ማዕከላዊ ጠባብ ክፍል ውስጥ። ትኋን ከጣራው የሚዘንብበት “ሸራተን” የሚባል አስቀያሚ እስር ቤት ውስጥ ነው የሆነች ጥግ ይዞ ያገኘሁት። ሀብታሞች እስር ቤት ሲገቡ ትሁት ለመሆን ጥረት ያደርጋሉ። የኤርሚያስ ግን ሳይለይ አይቀርም። የምሩን ይመስለኛል። ብዙ ሰው ጓደኛው ነው። ወጣቶች ጓደኞቹ ናቸው። ሀብታሞቹ ፈልገውት ይመጣሉ። እሱ ግን በአብዛኛው ውሎው ከሌሎቹ ጋር ነው።

    ከምንም በላይ የገረመኝ በዛን ወቅት የነበረው የፖለቲካ ዝንባሌው ነው። ወቅቱ 2008 ዓ.ም. ነው። በዚህ ወቅት ብዙ ጉዳይ ይበላሽብኛል የሚል ሀብታም የማይነካውን አጀንዳ ኤርሚያስ አይፈራውም። ውሎው በሽብር ከተከሰሱት ጋር መሆኑ አይደለም። ሰላይ በሞላበት እስር ቤት በወቅቱ በሽብር የተፈረጁት የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች መካከል “ማን ሊጠቅመን ይችላል? እንዴትስ ከግብ ይደርሳሉ? ምን ይደረግ?” የሚል ውይይት ላይ በቀጥታ ይሳተፍ ነበር። በፖለቲካ አመለካከታቸው የተለያየ ጠርዝ ላይ የተቀመጡ የፖለቲካ ድርጅት አመራሮችንና አባላትን፣ ግለሰቦችን ሰብስቦ ያወያይ ነበር። የውይይት መሪው ራሱ ነበር። ያከራክር ነበር። በዛ ጠባብና ማንም ውይይቱን በሚሰማበት ቤት መድረክ መሪው ኤርሚያስ ነው።

    በአንድ ክፍል ውስጥ በነበረችን ጥቂት ቆይታ እንዳጫወተኝ አቶ ኤርሚያስ መለስ ዜናዊንም በኢኮኖሚ ፖሊሲው በደንብ ሞግቶታል። መለስ የኤርሚያስን ፈጠራ ችሎታ ባይክድም ሙግቱን አልወደደለትም። እየቆዩ ግን ገዥዎቹ ፈጠራውንም አልወደዱለትም። አብዛኛው አሠራራቸው ጋር ይጋጫል። ለአብነት ያህል ዘመን ባንክን የመሰረተው ብዙ የግንባታ ወጭ ሳያወጣ በቴክኖሎጅው የትም እንዲያገለግል ነው። ኢህአዴግ ግን የትኛውም ባንክ በዓመት 5 በመቶ የሚሆን የቅርንጫፍ ማስፋፊያ እንዲያደርግ የሚያስገድድ ፖሊሲ አውጥቷል። ከዛም ሲያልፍ ብዙ ሴራዎች እንዳሉ ኤርሚያስ በግልፅ ይናገራል።

    ኤርሚያስ በእስሩ ወቅት ችግር ቢገጥመውም በቀላሉ ሲያልፋቸው አይቻለሁ። ሌላው ቀርቶ ዐቃቤ ሕግ ሚሊዮን ብሮችን የሚያስይዘበትን የዋስትና መብቱን (መጨረሻ ላይ በአንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን መሰለኝ የተለቀቀው) ሲነፍገው እስረኞች እንደሚሰማቸው ብስጭትና ንዴት አይታይበትም። እስረኞች በግፍ ፍትሕ ለተከለከለ እንደሚቆጩት ለእሱም ሲቆጩና ሲናደዱ “ምን አናደዳችሁ?” እያለ የሚቀልድ ሰው ነው። ብርታቱ በፖለቲካ ጉዳይ የሚታሰሩ የተወሰኑ ብርቱዎች የያዙትን እንጅ ከገንዘብ ጋር በተያያዘ ተከሰው እስረኛውን እንቅልፍ ከሚከለከሉት ብዙሃን ነጋዴዎች ጋር የሚመሳሰል አልነበረም።

    ዘመን ባንክ እንደ ይሁዳ – (ኤርሚያስ አመልጋ – ከቂሊንጦ ማረሚያ ቤት)

    ኤርሚያስ ለብዙ ነገሮች ተስፋ ቆርጦ “ሽብርክ” አለማለቱ በገዥዎች የተወደደለት አይመስለኝም። ፈጠራው የተወደደለት አይመስለኝም። በእርግጥ ብዙ የፈጠራ ባለሙያዎች፣ ጎበዝ ነጋዴዎች ይኖራሉ። ነገር ግን ከእነዚህ መካከል አብዛኛዎቹ የራሳቸውን ፈጠራ፣ ብቃትና ሀብት በሌላ ይሁንታ ጭምር እንዲተዳደር የሚፈልጉ ናቸው። ኤርሚያስ ይህ የሚፈቅድ ሰው አይመስልም። በትንሽ ትዝብቴ ፈጠራውን በገዥዎች ይሁንታ የሚያስተዳድር እንዳልሆነ ተገንዝቤያለሁ።

    ከራሱ ፈጠራ ባለፈ ቤተ መንግስት ገብቶ እነ መለስን ፖሊሲያዎቸው ኢኮኖሚውን የማያራምድ፣ ለሀገር ኪሳራ መሆኑን ሞግቷል። በዚያ ጨለማ ወቅት፣ በዚያ ብዙ ባለሀብት ባሽቃበጠበት ወቅት እነ መለስን የሞገተ ሰው የዛሬዎቹን ከመሞገት ወደኋላ እንደማይል ግልፅ ነው። በፖሊሱ ጉዳይ ከመተቸት ባለፈ የወቅቱ ገዥዎችም እንደ ድሮዎቹ ባለሀብቱ ወደራሳቸው ቀየ እንዲጎርፉ ፍላጎት ነበራቸው። ሆኖም ኤርሚያስ ፍላጎት የነበረው አይመስልም። ኤርሚያስ መዋለ ንዋይ ለማፍሰስ የመረጣቸው ቦታዎች እንደነበሩ ሲነገር ቆይቷል። ኤርሚያስ በዚህ የእፎይታ ይመስል የነበረ “የለውጥ” ወቅት በአዲስ ፈጠራ ለመምጣት ጥረት እያደረገ እንደነበር ተገልጿል። ብዙ ዕቅዶች እንዳሉት ያወራ ነበር። ለብዙዎቹ ሀብቶች ፈተና ነው። ገዥዎችንም ይሞግታል። እነሱ ወደፈለጉት ቦታ መዋለ ንዋይ ለማፍሰስም ፈቃደኛ አይመስልም። የኤርሚያስን እስር ሳስታውስ የሚመጡልኝ እነዚህ የገዥዎቹ ወጥመዶች ናቸው። እንጂማ ኤርሚያስ ከአረብ ባለሀብት የተሻለ ሀገሩን መጥቀም የሚያስችል እውቀት አለው። ገንዘቡን ባያፈስ እንኳ ከእነ ፍራንሲስ ፉኩያማ የተሻለ የሀገሩን ባህልና ጥቃቅን ክፍተቶች የሚረዳ ጥሩ አማካሪ መሆን ይችል የነበር ሰው ነው። በኤርሚያስ ላይ እንደ ችግር የተወሰደበት በውጥንቅጥና በኪሳራ ወቅትም እሠራለሁ የሚልበት ሥነ-ልቦናው ይሆናል።

    በአንድ ወቅት ስንከራከር ሊያሳምነኝ ያልቻለ ሙግት ነበረው። የገዥዎቹን ድርጅቶች አቅልሎ ነው የሚያያቸው። ሜዳው ከአፈና እና ወከባ ከተላቀቀ በቀላሉ ከስረው የሚወጡ እንደሆኑ ነው የሚናገረው። በመንግስት ድጎማ፣ ሙስና፣ ሌሎቹን በማፈን እና በገዥዎች ትብብር ትርፍ የሚያግበሰብሱት ተቋማት እውነተኛው ስርዓት ሲመጣ አፍታ ሳይቆዩ ከሜዳው እንደሚወጡ ነው የሚናገረው። የሰው ኃይልን በገፍ አስገብተው ጉልበት እየበዘበዙ የሚያጋብሱት ድርጅቶች የሰለጠነና በእውቀት የሚመራ ጋር ተወዳድረው እንደማይዋጣላቸው ነበር የሚናገረው። በወቅቱ የኢፈርትን ጡንቻ እያሰብኩ ኤርሚያስ የዋህ የሆነ ይመስለኝ ነበር። ከእነዚህ ግዙፎች ጋር ተወዳደሮ ማሸነፍ እንደሚችል በድፍረት ሲናገር ወኔውን አድንቄያለሁ። ይህ ወኔ ግን አግበስብሰው ለሚያተርፉትና አትራፊዎቹን ለያዙት ፈተና ይሆናል። ሳስበው ኤርሚያስ ትክክል ነበር። እነ ሜቴክን እንደምሳሌ መጥቀስ ይቻላል። ዛሬም ሌሎች ባለሜቴኮች አሉ። ኤርሚያስ ለእነዚህ ገንዘብ ከየትም አምጥተው በገዥዎች እገዛ ለሚያተርፉት ሰዎች ስጋት ነው። ኤርሚያስ ከእስር እንደተፈታ ሊያደርጋቸው የሚችላቸውን ጉዳዮች ያወራ ነበር። አንደኛው የኢኮኖሚ ተንታኝ ቡድን ማዋቀር ነው። መሰል ቡድን አዋቅሮ በተሻለ ሜዳ ልወዳደር ቢል በገዥዎቹ እገዛ ሚያተርፈው ስጋት ሊሆን ይችላል። ኤርሚያስን ሊያሳስረው ከሚችሉት ነገሮች መካከል ሳብሰለስል የሚመጡልኝ መሰል ጉዳዮች ናቸው።

    ሁሉም እስረኛ ነፃ ነው ብሎ መደምደም አይቻልም። ሆኖም በዚህ ዘራፊ የገዥዎቹ ቀኝ እጅ ሆኖ በሚኖርበት ሀገር ኤርሚያስ መታሰር አይገባውም ለማለት ሞራል አናጣም። ዘራፊዎች የገዥዎች መመኪያ ሆነው በሚኖሩበት፣ ዘራፊዎች የገዥዎች ከለላ በሚደረግላቸው ሀገር ኤርሚያስ በወንጀል ታሰረ ለማለት ክፉ ሕሊና ይጠይቃል። ቢያንስ ገዥዎችንና ገዥዎችን ታክከው ያገኙትን ገንዘብ እንጅ እውቀታቸውን ተማምነው፣ በእውቀት ተመርተው መነገድ ከማይችሉት አጎብዳጆች የተሻለ መሆኑን መካድ አይቻልም። ቢያንስ ቢያንስ የውጭ ባለሙያዎችን ያህል “አማክረን” ተብሎ ብዙ ሳይለመን ምክር የሚለግስ፣ ለሀገር የሚጠቅም መሆኑን መካድ አይቻልም። ከውጭ እንደሚመጡት አማካሪዎች ብዙ ገንዘብ ሳይጠይቅ የወልስትሬት (Wall Street) ልምዱን በቀናነት ለሀገሩ ሊያካፍል እንደሚችል መካድ አይቻልም። ኤርሚያስ ሊታሰር የሚችለው ከፈጠራና ሙግቱ በተያያዘ እንደሆነ ትልቁን ግምት መውሰድ ይቻላል። የኤርሚያስ ትልቁ “ወንጀል” ገዥዎቹና ገዥዎችን ተጠልለው የከበሩትን በእውቀት ላይ ተመስርቶ ስለሚሞግትና ስለሚወዳደራቸው፣ ስጋት ስለሆነባቸው ይመስለኛል። ኤርሚያስን የፈለገ ወንጀል ሠራ ቢሉን ወንጀለኞች በሚሸለሙበት ሀገር፣ ዘራፊዎች ለገዥዎች በማጎብደዳቸው “ነፃ ሆነው” በሚኖሩበት ሀገር የሚያሳስረው ወንጀልን ለመገመት የሚከብድ ነው።

    ኤርሚያስ ነፃ ይመስለኛል። ነፃ እንኳን ባይሆን ከአጎብዳጆቹ አንፃር ሊሸለም የሚገባው ሰው እንደሆነ አምናለሁ። ኤርሚያስ ባይታሰር ለገዥዎቹ ባይጠቅም፣ ለሀገሩ ብዙ ብዙ ይጠቅማል።

    ኤርሚያስን ፍቱት!

    ጌታቸው ሽፈራው

    ኤርሚያስ አመልጋ


    Anonymous
    Inactive

    የጉራጌ ሕዝብ አውራጃውን ከራሱ በተወለዱ አበጋዞች ያስተዳድር የነበረው ኦሮሞ በገዳ መተዳደር ከመጀመሩ ቢያስ ከ208 ዓመታት በፊትና ኦሮሞ ደቡብ፣ ምዕራብ፣ ምስራቅና መካከለኛው ኢትዮጵያን መውረር ከመጀመሩ ከ200 በላይ ዓመታት በፊት ነበር።

    የጉራጌ ሕዝብ ከ158 ዓመታት በፊት…
    (አቻምየለህ ታምሩ)

    ሰማዩም ምድሩም የኛ ነው የሚሉን ኦነጋውያን የሚይዙት ቅጣምባሩ ጠፍቷቸዋል። ከሰሞኑ ደግሞ ባሰራጩት በምስል የታገዘ ዜና በጉራጌ ምድር ከ158 ዓመታት በፊት ተቋርጦ ነበር ያሉን የገዳ ስርዓት ማስጀመራቸውን ነግረውናል። እንዲህ ዓይነት ዜና ሲሰማ ዝም ማለት ተገቢ ባለመሆኑ ከ158 ዓመታት በፊት የጉራጌ ሕዝብ ከኢትዮጵያ ማዕከላዊ መንግሥት ጋር ስለነበረው ግንኙነት፣ የነበረውን የውስጥ አስተዳደር ታሪክና “ገዳ” የሚባለው የወረራና የዘመቻ ስርዓት ወደ በአካባቢው በደረሰበት ወቅት ስለተከተሉ ሁኔታ ሳነብ ከተማርሁት የሚከተለውን ጀባ ብያለሁ።

    የጉራጌ ምድር ከጥንት ጀመሮ የኢትዮጵያን መንግሥት ያቆሙ ዋና ዋና የጦር መሪዎችን ያፈራ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ አውራጃ ነበር። ተመዝግቦ ከምናገኘው ታሪክ ብንነሳ እስከ ሞቃድሾ ድረስ የነበረውን የኢትዮጵያ ግዛት ባስተዳድሩት ዐፄ ዐምደ ጽዮን [እ.ኤ.አ. ከ1314 ዓ.ም.–1344 ዓ.ም. ድረስ የነገሡ] ዜና መዋዕል ውስጥ ጉራጌ ከኢትዮጵያ ማዕከላዊ መንግሥት ጋር ቅርብ ቁርኝት የነበረው ሕዝብ እንደነበር ተጽፎ እናገኛለን። በዘመኑ የጉራጌ አውራጃ የውስጥ አስተዳደር ይመራ የነበረው በጉራጌ ተወላጅ አበጋዞች ነበር።

    ጉራጌ አውራጃውን ከራሱ በተወለዱ አበጋዞች ያስተዳድር የነበረው ኦሮሞ በገዳ መተዳደር ከመጀመሩ ቢያስ ከ208 ዓመታት በፊትና ኦሮሞ ደቡብ፣ ምዕራብ፣ ምስራቅና መካከለኛው ኢትዮጵያን መውረር ከመጀመሩ ከ200 በላይ ዓመታት በፊት ነበር። የኦሮሞ ብሔርተኛው ፕሮፌሰር መሐመድ ሐሰን “The Oromo and the Christian Kingdom of Ethiopia” በሚል ባሳተመው መጽሐፉ ገጽ 158 ላይ እንደጻፈው ኦሮሞ በገዳ መመራት የጀመረው እ.ኤ.አ. በ1522 ዓ.ም. እንደሆነና የመጀመሪያው ገዳ “ገዳ መልባ” እንደሚባል ነግሮናል። ጉራጌ ግን ኦሮሞ ገዳ ከጀመረበት ከ1522 ዓ.ም. በመቶዎቹ በሚቆጠሩ ዓመታት በፊት ቆዬት ብዬ የማቀርብላችሁ ከገዳ ጋር ምንም ግንኙነት የሌላው የራሱ የውስጥ አስተዳደር ስርዓት ነበረው።

    የጉራጌ ምድር ክርስትና ቀድሞ በሰፊው ከተሰበከበትና ከጸናበት የኢትዮጵያ አውራጃዎች አንዱ ነበር። በወቅቱ የተጻፈው ድርሳነ ዑራኤል ይህንን ያረጋግጣል። ከድርሳነ ዑራኤሉ በተጨማሪ ራሳቸው የጉራጌ ተወላጆችም ይህንን ታሪክ ጽፈዋል። የጨቦ ኡዳደ ኢየሱስ ሕዝብ ታሪክ ጸሐፊው አቶ ምስጋናው በላቸው “የጨቦ ኡዳደየሱስ ሕዝብ አጭር ታሪክና ባሕል” በሚል በመጋቢት 1985 ዓ.ም. ከጀርመን በጻፉት የታሪክ መጽሐፋቸው ገጽ 66 ላይ እንደጻፉት አይመለል በሚባለው የጉራጌ ምድር የሚኖረው «ክስታኔ» የሚባለው ሕዝብ መጠሪያ «ክስተነ» ከሚል ከቦታው ቋንቋ የመጣ መሆኑንና ትርጉሙም ክርስቲያን ማለት እንደሆነ ነግረውናል። አይመለል የመጀመሪያዎቹ ክስታኔዎች ወይንም ክርስቲያኖች የሰፈሩበት ምድር ነው።

    ክስታኔ፣ ጉራጌ በመባል በወል ከሚጠሩት የቤተ ጉራጌ ማኅበረሰቦች ውስጥ አንዱ ሲሆን ሶዶ ጉራጌ እየተባለም ይጠራል። የክስታኔ ሕዝብ ቋንቋ ክስታኒኛ ይባላል። አቶ ምስጋናው በላቸው በመጽሐፋቸው ገጽ 63 እንደነገሩን በጨቦ ምድር ብቻ ከግራኝ ወረራ በፊት 40 ጥንታዊ አብያተ ክርስቲያናት የነበሩ ሲሆን ከወረራው በኋላ የተረፉት ግን 13 ስደተኛ ታቦቶች የተዳበሉበት ታሪካዊው የዋሻ ሥላሴ ቤተክርስቲያንና በወንጭት ደሴት ላይ የነበረው የቅዱስ ቂርቆስ ቤተክርስቲያን ብቻ መሆናቸውን ነግረውናል። አቶ ምስናጋው ጨምረው እንደጻፉት የዋሻ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን በዐፄ ካሌብ ዘመነ መንግሥት የተሠራ መሆኑን ከጉራጌ ታሪክ አዋቂ አባቶች አገኘሁት ያሉትን ታሪክ ነግረውናል። ይህ የጉራጌ ሕዝብ ክርስትናን ከተቀበሉ ቀደምት የኢትዮጵያ ነገዶች መካከል መሆኑን ያሳየናል።

    ጉራጌ የኢትዮጵያን ሰለሞናዊ መንግሥት በሸዋ ምድር ካቆሙ የኢትዮጵያ ዋና ዋና ነገዶች መካከል ቀዳሚው ስለመሆኑ ሌላው ማስረጃ በዐፄ ናዖድ ዘመነ መንግሥት የተጻፈው ድርሳነ ዑራኤል ነው። በዘመኑ ድርሳነ ዑራኤል እንደተጻፈው እግዚአብሔር መስፍንነት ከጉራጌ፥ ከመንዝና ከወረብ እንዳይወጣ ለአጼ ናዖድ [የንግሥና ዘመናቸው እ.ኤ.አ. ከ1494–1508 ዓ.ም. ድረስ ነው] ቃልኪዳን ገባለት ይለናል። ይህ በድርሳነ ዑራኤሉ ከገጽ 311–315 ተጽፎ የሚገኝ ሲሆን ሙሉው ቃል እንዲህ ይነበባል፦

    ወእምድኅረ፡ ዝንቱ፡ ወሀቦ፡ ለናዖድ፡ እግዚእነ፡ ኢየሱስ፡ ክርስቶስ ኪዳነ ምሕረት፡ ከመ፡ ኢይጥፋእ ምስፍና፡ ወምልክና፡ በምድረሸዋ፡ ወመንዝህ ወበሀገረ፡ ጐራጌ፡ ዘይብልዎ ምድረ፡ ወረብ፡ ወምሁር።

    ትርጉም፦

    ከዚሀ፡ በኋላ፡ ጌታ ኢየሱስ፡ ክርስቶስ፡ ከምድረ፡ ሸዋ፡ ምሁርና፡ ምድረ፡ ወረብ፡ ከሚባለው ከጐራጌ፡ አገር፡ ከመንዝም፡ አገዛዝና፡ መስፍንነት፡ አንዳይጠፋ፡ ለናዖድ፡ ቃል፡ኪዳን፡ ሰጠው።

    በድርሳኔ ዑራኤሉ እንደተገለጠው የጉራጌ ሕዝብ በዘመኑ የኢትዮጵያ መስፍን ሆነው እንዲሾምላቸው ከተወሰነላቸው ሦስት የኢትዮጵያ አካባቢዎች መካከል አንዱ ነበር። በዚህ መልክ እስከ መካከለኛው ዘመን የማዕከላዊው የኢትዮጵያ መንግሥት ዋልታ የነበረው ጉራጌ ከግራኝ ወረራ በኋላም ለኢትዮጵያ ቤተመንግሥት በጣም ቅርብ ነበር። ከግራኝ ወረራ በኋላ ዋናኞቹ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት ራሶች ጉራጌዎች ነበሩ።

    ከግራኝ ወረራ በኋላ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ከፍተኛ የመንግሥት ስልጣን ከነበራቸው አራጊ ፈጣሪ ጉራጌዎች መካከል በዐፄ ያዕቆብ [እ.ኤ.አ. ከ1597 ዓ.ም.–1603 ዓ.ም.፤ እንዲሁም ከ1604 ዓ.ም.–1607 ዓ.ም. ድረስ የነገሡ] እና በዐፄ ዘድንግል [ እ.ኤ.አ. ከ1603 ዓ.ም.–1604 ዓ.ም. ድረስ የነገሡ) ዘመናት የነበሩትን ራስ ዘሥላሴን ለአብነት መጥቅስ ይቻላል። የጉራጌ ተወላጁ ራስ ዘሥላሴ ዐፄ ዘድንግል “መልከ ሐራ” በሚል ያቋቋሙትን የንጉሥ ሠራዊት ይመሩ ነበር። ዐፄ ሰርጸ ድንግል እ.ኤ.አ. በ1597 ዓ.ም. ከሞቱ በኋላ ደግሞ ለሚቀጥሉት 10 ዓመታት ኢትዮጵያን የገዙት ራስ ዘሥላሴ ነበሩ ማለት ይቻላል።

    ራስ ዘሥላሴ በዐፄ ሰርጸ ድንግል ዘመን «ቁርባንና ሚዛን» የተባለው ደምብያ የሰፈረው ሠራዊት መሪ ነበር። ዐፄ ዘድንግል ለወታደሩ አመጽ ምክንያት የሆነ ገባሩን ነጻ የሚያወጣ አዋጅ አውጀው ነበር። ይህ አዋጅ ወታደሩንና ገባሩን ወይም ዜጋውን እኩል ያደረገ አዋጅ ነበር። በዚህ ምክንያት ራስ ዘሥላሴና ቁርባንና ሚዛን የተባለው ሠራዊት በንግሡ ላይ አምጾ ደምብያ ውስጥ ባርጫ ከተባለ ስፍራ ዐፄ ዘድንግልን ገደሉት። ጣሊያናዊው የታሪክ ተመራማሪ ኮንቲ ሮሲኒ (Carlo Conti Rossini) ያሳተመው በዘመኑ የተጻፈው ታሪከ ነገሥት መንግሥት በጉራጌው በራስ ዘሥላሴ እጅ ገብቶ ነበር ይላል። ኮንቲ ሮሲኒ ያሳተመው ታሪከ ነገሥት ውስጥ የሚገኘው ይህ ታሪክ የሚከተለውን ይመስላል፦

    ወበውዕቱ ፩ ዓመት ተጻልዕዎ ሐራሁ ለሐጼ ዘድንግል እለ ይብልወሙ ቁርባን፥ ወሚዛም ወእርስ ዘሥላሴ በምክንያተ ዝንቱ አዋጅ ዘአንገረ ውእቱ እንዘ ይብል ሰብእ ሐራ፤ ወገብራ ምድር። እስመ ዓመፁ ኩሉ ዜጋሆሙ ወቀተልዎ በኵናት ማዕከለ ደምብያ ዘውእቱ ባርጫ [1604 ዓመተ ምኅረት] ። […] ወእምድኅረ አዘዘ እራስ ዘሥላሴ ከመ ያንስእዎ ለሐጼ ዘድንግል ወአንሥእዎ ወወሰድዎ ውስተ ደሴተ ዳጋ ወቀበርዎ ህየ። ወነበረት መንግሥት በዕዴሁ ለጉራጌ ራስ ዘሥላሴ።” [ምንጭ፦ C. Conti Rossini, C. (1893). Due squarci inediti di cronica etiopica. Rendiconti della reale accademia dei Lincei. Classe di Scienze Morali, Storiche e Filologiclre; Page 807.

    ትርጉም፦

    በአንድ ዓመት ውስጥ ቁርባንና ሚዛን የተባሉት ወታደሮች እንዲሁም ራስ ዘሥላሴ “ሰው ነጻ ነው፤ ምድር ገባር ነው” በሚለው አዋጅ ምክንያት ዐፄ ዘድንግልን ተጣሉት። ዜጎች [ንጉሡን ደግፈው አመጹ]። በደምብያ መካከል ባርጫ ውስጥ በጦር ወግተው ገደሉት። ከዚህ በኋላ ራስ ዘሥላሴ ዐፄ ዘድንግልን እንዲያነሱት አዘዘ፤ አንስተው በዳጋ ደሴት ቀበሩት። መንግሥት በጉራጌው በራስ ዘሥላሴ እጅ ነበረች።

    ከዚህ የምንረዳው በዘመኑ በኢትዮጵያ ማዕከላዊ መንግሥት አራጊ ፈጣሪ የነበሩት የጉራጌ ተወላጁ ራስ ነበሩ።

    ወደ ውስጥ አስተዳደሩ ስንመጣ የጉራጌ ሕዝብ አውራጃውን የሚያስተዳድረው ከተወላጆቹ በሚመረጡ አበጋዞች ነበር። የጨቦ ተወላጁ አቶ ምስጋናው በላቸው የጉራጌ ሕዝብ አካል የሆነውን የጨቦ ሕዝብ የውስጥ አስተዳደር በሚመለከት “የጨቦ ኡዳደየሱስ ሕዝብ አጭር ታሪክና ባሕል” በሚለው መጽሐፋቸው ከገጽ 85–89 የሚከተለውን ጽፈዋል፤

    “አበጋዙ የሕዝቡ ጠቅላይ አስተዳዳሪ ሆኖ እንደ አባት የሚታይ መሪ ነው። አበጋዙ እንደኃላፊነቱ ሥፋትና የሥራው ክብደት ከእጩነት አስንቶ እስከተሾመበት ድረስ በጥልቅ ተጠንቶ የሚመረጥበት ሁኔታ ጥንቃቄ የተሞላበት ነው። ይህም የሚሆነው በየሁለት ዓመት ግፋ ቢል በሦስት ዓመት አንድ ጊዜ ነው። የአንድ አበጋዝ የአገልግሎት ዘመኑ ለሁለት ዓመት ብቻ ሲሆን በዚሁ ሁለት ዓመታት ውስጥ ዳኝነቱና ተወዳጅነቱ ከፍ ያለ ምስክርነት ካገኘ ያለ ምንም ተቃውሞ አንድ ዓመት ተመርቆለት ለሦስት ዓመታት ያስተዳድራል። ድጋሚ መመረጥ የለም።…

    አበጋዝ ሲመረጥ በጊዜው ሥልጣን ላይ ያለው የአመራር አካል ሥልጣን ከመልቀቁ ከብዙ ወራት በፊት አበጋዝ መመረጥ የሚገባው ሰው ስም ከየጎሣው በሚስጥር ይጠየቃል። አበጋዝ መሆን ይችላል ተብሎ ከየጎሳው ከየአካባቢው የተጠቆመውን አዛውንት የእያንዳንዱን ሁኔታ ማለት ባኅሪው፣ ተቀባይነቱና የማስተዳደር ችሎታውን በሚስጥር አጥንቶ አበጋዝ ይሆናል ብሎ ያመነበትን ለጠቅላላው የሕዝብ ጉባዔ ያቀርባል።

    ሕዝቡ ካመነበት በኋላ የሹመቱ ሥነ ስርዓት የሚፈጸምበትን ቀን ራቅ አድርጎ ይቀጥራል። ቀጠሮው ራቅ የሚለው በሕዝቡ ጥያቄ ሆኖ እንደተለመደው በስርዓተ ሹመቱ ቀናት ሕዝቡ በፈቃዱ የሚደሰትበትን የእርድ በሬዎች፣ የሚበላና የሚጠጣውን ከየጎሳውና ከየአካባቢው አጠራቅሞ ለማምጣት እንዲመቸው ብሎ ነው። የተሿሚው ጎሳ አብዛኛውን ያቀርባል።

    በስርዓተ ንግሡ ቀን አበጋዙ በሻሽ ጥምጥም ዘውድ ሰሠርቶላቸው፣ የአበጋዙ ባለቤት በፀጉራቸው ጉንጉን ዘውድ ተሠርቶላቸው አበጋዙ በሠንጋ ፈረስ፣ ባለቤታቸው “እቴ” ተብለው [እቴጌ ማለት ይመስላል] በሰጋር በቅሎ ላይ ተቀምጠው በጎሳቸው እጀብና ሆታ ሰንበት ወራቡ ሲደርሱ እዚያ ተሰብስቦ የሚጠብቃቸው ሕዝብ በዘፈንና በእልልታ ይጠብቃቸዋል። ሰንበት ወራቡ የመጀመሪያ ስርዓተ ንግሥ የሚፈጸምበት ቦታ ነው። እዚያ ቦታ ከመድረሳቸው ቀደም ብሎ አበጋዙና “እቴ” የሚቀመጡበት በሦስት ድርብ የተሰራ የእንጀራ መደብ ይዘጋጃል። እንጀራ ላይ የሚቀመጡበት ምክንያት እነሱ በሚያስተዳድሩበት ክልል ጥጋብ እንዲሆን ተመኝተው ነው ተብሎ ይታመናል።

    ተሿሚዎቹ የክብር ሥፍራቸውን ከያዙ በኋላ በገንዙና በአባጅልባዎች አማካኝነት ሕዝብ በተሰበሰበበት ሥርዓተ ንግሡ ይፈጸማል። ወዲያውኑ ቃለ መሐላ ሲፈጸም ወይፈኖች፣ በሬዎች ታርደው ፈንጠዝያው ይቀጥላል። ይህ የደራ ድግስ በየደረጃው እየተበላ አምስት ቀን ይቆያል። በአምስተኛው ቀን አበጋዙና “እቴዋ” ዋሻ ሥላሴ ቤተክርስቲያን እንደዚያ ታጅበው ሄደው የመጨረሻ ሥርዓተ ንግሥ ከተፈጸመ በኋላ አበጋዙ ወደ ጅሎት ቦታው ተመልሶ አገልግሎቱን ከፈጸመው አበጋዝ መንበሩን ይረከባል። አንዴ አበጋዝ ሆኖ የተመረጠ አዛውንት መንበሩንና አስተዳደሩን በፍቅርና ራሱ ቃለ ቡራኬ ሰጥቶ ለአዲሱ አበጋዝ ሲያስረክብ በትረ መንግሥቱ [በእጁ ይይዘው የነበረው ዘንድ] ለክብሩ ሲባል በእጁ ይቀራል። የአገልግሎቱ ዋጋም ዕድሜውን ሙሉ አበጋዝ ተብሎ መጠራት ሆኖ ይኸው የማዕረግ ስሙና የሚይዘው አንድ ነበሩ።”

    የጉራጌ ሕዝብ የውስጥ አስተዳደር በዚህ መልክ የተገለጸውን ይመውላል። አበጋዞቹ በሕዝብ ፊት ሥርዓተ ንግሥና ከፈጸሙ በኋላ የሥርዓት ንግሥናው ፍጻሜ የሚሆነው አበጋዙና እቴዋ በጥንታዊው ዋሻ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ሄደው የመጨረሻውን ሥርዓተ ንግሥ ከፈጸሙ በኋላ ነው። በዚህ መልክ አውራጃውን ሲያስተዳድር የኖረው የጉራጌ ሕዝብ ከኢትዮጵያ ማዕከላዊ መንግሥት ጋር የነበረው ግንኙነት የተቋረጠው በኦሮሞ ወረራ ምክንያት ነው። በኦሮሞ ወረራ ምክንያት ከማዕከላዊው የኢትዮጵያ መንግሥት ጋር የነበረው ግንኙነት የተቋረጠው የጉራጌ ሕዝብ በተለይም የጨቦ ክስታኔና ምሑር ሕዝብ በኦሮሞ ወረራ ምክንያት ክሥታኔና ምሑር የነበረውን ቋንቋውን በአባገዳዎች ተገዶ እንዲተውና ኦሮምኛ እንዲናገር በመገደዱ ብዙ ስቃይ እንደደረሰበት አቶ ምስጋናው በመጽሐፋቸው አትተዋል። አቶ ምስጋናው በመጽሐፋቸው ገጽ 50 ላይ እንደጻፉት ኦሮሞ በገዳ ስርዓት እየተመራ የጉራጌን ምድር ሲወር የነበረውን ጥፋት እንዲህ ይገጹታል፦

    በዚህ ጊዜ [ኦሮሞ ወደ ጉራጌ ምድር በተስፋፋበት ወቅት ማለታቸው ነው] ስለ ቋንቋ የነበረው እምነት ኦሮምኛ የሚናገር “ቢርመዱዳ እንጡቂና” ኦሮምኛ የማይናገር “ዲና በሌሣ” የሚል ሆነ። ትርጉሙም ኦሮምኛ የሚናገር ወገናችን ነው ይገብር፤ ኦሮምኛ የማይናገር ጠላታችን ነው ይጥፋ” ማለት ነው።

    እንግዲህ! ኦነጋውያን በጉራጌ ምድር ከ158 ዓመታት በፊት ነበረ ያሉትን ገዳ ለማቋቋም እየተንቀሳቀሱ ያሉት ገዳ የሚባለው የወረራ ስርዓት ሳይመሰረት የራሱ የውስጥ አስተዳደር የነበረውን የጉራጌ ሕዝብ “ኦሮምኛ የሚናገር ወገናችን ነው ይገብር፤ ኦሮምኛ የማይናገር ጠላታችን ነው ይጥፋ” እያሉ አባገዳዎች የጉራጌን ሕዝብ ያጠፉበትን፣ ከርስቱ ያፈለሱበትን የወረራና የጦርነት ስርዓት መልሰው ለመትከል ነው። አባገዳዎች ወደ ጉራጌ ምድር ብቻ ሳይሆን ወደ ምዕራብ፣ መካከለኛውና ደቡብ ኢትዮጵያ የተስፋፉት “ኦሮምኛ የሚናገር ወገናችን ነው ይገብር፤ ኦሮምኛ የማይናገር ጠላታችን ነው ይጥፋ” እያሉ የዘር ማጥፋትና የዘር ማጽዳት እየፈጸሙ ነው። ኦነጋውያን በጉራጌ ምድር መልሰው ሊተክሉ እየፈለጉት ያለው የገዳ ስርዓትም “ኦሮምኛ የሚናገር ወገናችን ነው ይገብር፤ ኦሮምኛ የማይናገር ጠላታችን ነው ይጥፋ” እያሉ አባገዳዎች ዘር ያጠፉበትን፣ ባላመሬቱን ከርስቱ ያለፈሉበትን የወረራና የዘር ማጥፋት ስርዓት ነው።

    የጨቦ ተወላጁ አቶ ምስጋናው በላቸው በመጽሐፋቸው ገጽ 66 እንደነገሩን አባገዳ አካባቢውን ከወረረው ጀምሮ የነበረው ስቃይ፣ ጭቆና መከራ ተወግዶ በጨቦ ምድር ፍቅርና ሰላም የወረደው ዳግማዊ ምኒልክ ሲደርሱላቸውና ከአባገዳ ባርነት ሲያላቅቋቸው እንደሆነ ጽፈዋል። «የሰላሙ ዘመን» ያሉት የዐፄ ምኒልክ ፀሐይ በጨቦ ምድር መውጣት ከጀመረችበት ጊዜ ጀምሮ የጨቦ ካህናት ከዐፄ ምኒልክና ራሶቻቸው ጋር እየዞሩ በኦሮሞ ወረራ ምክንያት ተቋርጦ የነበረውን የጥንቱን ወንጌል የማስፋፋት ተግባራቸውን በመቀጠል እስከ ዳር አገር ድረስ እየዞሩ ክርስትና መነሳት የሚፈልገውን ክፍል እንዳጠመቁና ከመሀል ኢትዮጵያ እስከ ኖኖና ጡቁር ምድር ድረስ በመሄድ አዳዲስ አማኞችን ያጠምቁት የጨቦ ቄሳውስት እንደነበሩ አውስተዋል።

    ባጭሩ የጉራጌ ሕዝብ ለሺህ ዘመናት የኢትዮጵያ ማዕከላዊ መንግሥት ዋልታ የነበረ፣ የራሱ የሕዝብ አስተዳደር ስርዓት የነበረው ሠራተኛ ሕዝብ እንጂ ገዳ የሚባል ከዲሞክራሲ ጋር የስናፍጭ ቅንጣት ታህል ግንኙነት የሌለው የወረራ፣ የጦርነት፣ የመስፋፋት ዘመቻና የዘር ማጥፋት የተካሄደበት ስርዓት ባለቤት አልነበረም!

    አቻምየለህ ታምሩ

    የጉራጌ ሕዝብ


    Anonymous
    Inactive

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ከብሔራዊ ቤተ-መዛግብትና ቤተ-መፃሕፍት ኤጀንሲ፣ ከትግራይ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ባህልና ቱሪዝም ቢሮ እና ከመቐለ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመቀናጀት “ግዕዝ እና ሥነ-ፈውስ” በሚል ቃል የተዘጋጀው 5ኛው ሀገር አቀፍ የግዕዝ ጉባዔ ለሁለት ተከታታይ ቀናት በመቀሌ ዩኒቨርሲቲ አዲሐቂ ካምፓስ ሲካሄድ ቆይቶ ቀጣይ አቅጣጫዎችን በማስቀመጥ ሰኔ 2 ቀን 2011ዓ.ም. ተጠናቋል።

    በጉባዔው መክፈቻው ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት ክብርት ወ/ሮ ብዙነሽ መሠረት የባህል ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ያስተላለፉት መልዕክት “አገራችን ከ80 በላይ ቋንቋዎች የሚነገሩባት ብዝሃ-ባህል ያለን ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ሀገር መሆናችን እንደአፍሪካ አህጉር መልካም አጋጣሚዎች ቢኖረንም ያሉንን ባህላዊ እሴቶችና ሀገር በቀል ዕውቀቶችን አስተዋውቀን በሚገባ አልተጠቀምንባቸውም። የራሳችን የሆነ ፊደልና የግዕዝ ቋንቋ ያለን ሲሆን፣ እነዚህ ልዩ ጥበቃና እንክብካቤ የሚያስፈልጋቸው በጥናትና ምርምር እየተደገፈ በመሰነድ ለትውልድ ማስተላለፍ የሁላችን ኃላፊነት ሆኖ ይገኛል ካሉ በኋላ የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ላለፉት አራት ዓመታት ተመሳሳይ የጥናትና ምርምር መድረኮች የተካሄዱበት አግባብና ውጤታማነት ሲገመግም ጉባዔዎች በተባባሪ የባለድርሻ አካላት ተሳትፎ በጋራ የሚካሄዱ መሆናቸው እንደ ጥሩ ጅምር የሚወሰድ ነው ብለዋል።

    አክለው ክብርት ሚኒስትር ዴኤታዋ ከዚህ ቀደም በተካሄዱ ጉባዔያቱ በቋንቋው ጥናት ዙሪያ ያሉ ጠቃሚ ልምዶች፣ በቋንቋው ጥናት አስፈላጊነት በቂ ግንዛቤ ያገኘንባቸው ነው ብሎ መውሰድ ይቻላል። የዘንድሮው የመቀሌ ጉባዔ ለየት የሚያደርገው ከግዕዝ ወጣ ብሎ በሥነ-ፈውስ ላይ ትኩረት ማድረጉ ጭምር መሆኑ ነው። የግእዝ ቋንቋ በሥነ-ፈውስ ደረጃ ምን ይላል የሚለው ጥያቄ መልስ የሚሰጥባቸው፣ አቅጣጫና መፍትሄ የሚቀርብባቸው ጥናታዊ ጽሑፎች በጉባዔው የሁለት ቀን ውሎ ይቀርባሉ ተብሎ ታሳቢ ተደርጓል።ሥነ-ፈውስ ኅሊናዊ፣ ሥነ-ፈውስ ሥጋዊ፣ ሥነ-ፈውስ መድኃኒታዊ፣ ሥነ-ፈውስ መንፈሳዊ፣ እያልን ብዙ ነጥቦችን ማንሣት እንችላለን። ሰው በጎ አስተሳሰብ እንዲኖረው፣ ለአገር፣ ለወገን፣ እንዲኖር ጤናማና ያልተዛባ አእምሮ እንዲኖረው ያስፈልጋል። ሁሉን ጎጂ አድርጎ የሚመለከት አእምሮዊ ህልውናዊ እንደሚያስፈልገው አምናለሁ። በዚህ ጉባዔ የስነ-ፈውስ ደረጃ ምንድነው የሚለውን ጥያቄ መልስ የሚሰጡ አማራጮችን በስፋት መዳሰስና በጉባዔው ማጠቃለያም የተሳታፊዎች ንቁ ተሳትፎና ውይይት ለቋንቋው ልማት ለምናካሂደው ተግባራዊ እንቅስቃሴዎች ሊያግዙ የሚችሉ ምክረ-ሀሳቦች እንደሚመጡ ያለኝ ተስፋ ላቅ ያለ ነው በማለት መልዕክታቸውን በማስተላለፍ ጉባዔው በይፋ አስጀምረዋል።

    5ኛው ሀገር አቀፍ የግዕዝ ጉባዔ በተያዘለት መርሃ-ግብሮች መሠረት በግእዝ ላይ የተደረጉ የተለያዩ የጥናትና ምርምር ስራዎች ቀርበው ገለፃና ውይይት ተደርጎባቸዋል። እነዚህም ግዕዝና ሥነ-ፈውስ በመጋቤ ምስጢር ፍሬስብሃት ዱባሌ (ከኢ.ኦ.ተ. ቤተ ክርስቲያን)፣ ግዕዝና ለፈውስ የሚደረስ ጸሎት በዶ/ር አባ ዳንኤል አሰፋ (ከፍራንቺስኮ ካቶሊክ ዩኒቨርሲቲ)፣ ግዕዝና የባህል መድሃኒት በመጋቤ ምስጢር ስማቸው ንጋቱ (ከባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ)፣ ዘይትረከቡ በውስጠ ልሳነ ግዕዝ ሕቡኣነ ስመ እግዚአብሔር ዘይህቡ ፈውሰ ድኅነት በአቶ ሃፍተ ንጉስ (ከአዲግራት ዩኒቨርሲቲ)፣ ግዕዝ (The General Features of the Geez Magical Texts) በአቶ ጉኡሽ ሰለሞን (ከአዲግራት ዩኒቨርሲቲ)፣ ጸበልና ማየ ጸሎት በግዕዝ ባህል ወፊዚክስ በዶ/ር ሀጎስ አብርሃ (ከመቐለ ዩኒቨርሲቲ) ይገኙበታል።

    ምንጭ፦ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የግዕዝ ጉባዔ


    Anonymous
    Inactive

    በ60 ሚሊዮን ብር የተገነባው የመደ ወላቡ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል በይፋ ተመረቀ
    —–

    በባሌ ዞን በመደ ወላቡ ወረዳ በ60 ሚሊዮን ብር የተገነባው የመደ ወላቡ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ባሳለፍነው ሳምንት በይፋ ተመርቋል።
    ሆስፒታሉን በይፋ የመረቁት የኦሮሚያ ክልል ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ ናቸው፡፡

    ኤክስ ሬይን ጀምሮ በርካታ የህክምና ቁሳቁሶችን ያሟላው ሆስፒታል ለ150 ሺህ የአካባቢው ነዋሪዎች አገልግሎት መስጠት ይችላል ሲል የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ዘግቧል።
    በ2005 ዓ.ም. ግንባታው የተጀመረው ሆስፒታሉ በ2009 ዓ.ም. በከፊል ተጠናቆ ሥራ እንደጀመረ በምረቃ ፕሮግራሙ ላይ ተገልጿል።

    ምንጭ፦የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን

Viewing 15 results - 436 through 450 (of 730 total)