Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Home Forums Search Search Results for 'ኢትዮጵያ'

Viewing 15 results - 676 through 690 (of 730 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    የስንፈተ ወሲብ መድኃኒቶች እንደአግባቡ ከሆነ በሀኪም ትዕዛዝ የሚሰጡ መሆናቸውን በመግለጽ፥ ነገር ግን በሕገ-ወጥ መንገድ ያለሀኪም ትዕዛዝ ለኅብረተሰቡ የሚያሰራጩ ሕገ-ወጥ የመድኃኒት ተቋማት እንዳሉ ተጠቅሟል።

    አዲስ አበባ – የኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድኃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን ፈዋሽነቱና ደኅንነቱ ያልተረጋገጠ በንግድ ስሙ “ቪጋ፣” “ቪጎ” እና “ፊካ” (ቪጎ 50፣ ቪጎ 100/ Vigo50/100፣ ቬጋ 50፣ ቬጋ 100/Vega 50/100፣ ፊካ 50፣ ፊካ 100/Fika 50/100) የተሰኙ የወሲብ ማነቃቂያ መድኃኒቶች (የስንፈተ ወሲብ መድኃኒቶች) በሕገ-ወጥ መንገድ በሀገር ውስጥ መሰራጨታቸውንና በተጠቃሚዎች ላይም የጤና እና የኢኮኖሚ ጉዳት እያደረሱ መሆኑን አስታወቀ።

    ባስልጣን መሥሪያ ቤቱ ጥቅምት 22 ቀን 2011 ዓ.ም. በተሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ እንደተገለጸው በድህረ-ገበያ ቅኝት በተደረገው የቁጥጥር ሥራ ለማወቅ እንደተቻለው በተቋሙ ያልተመዘገቡና ጥራት እና ደኅንነነታቸው ያልተረጋገጡ እንዲሁም በሕገ-ወጥ መንገድ ወደሀገር ውስጥ የገቡት የስንፈተ ወሲብ (የወሲብ ማነቃቂያ) መድኃኒቶች በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች በመገኘታቸው ህብረተሰቡ ምርቶቹን ከመጠቀም ራሱን እንዲቆጥብና ጥንቃቄ እንዲያደርግ ባለስልጣን መስሪያቤቱ አሳስቧል።

    ከዚህ በተጨማሪ ችግሩን የከፋ የሚያደርገው የስንፈተ ወሲብ መድኃኒቶች እንደአግባቡ ከሆነ በሀኪም ትዕዛዝ የሚሰጡ መሆናቸውን በመግለጽ፥ ነገር ግን በሕገ-ወጥ መንገድ ያለሀኪም ትዕዛዝ ለኅብረተሰቡ የሚያሰራጩ ሕገ-ወጥ የመድኃኒት ተቋማት እንዳሉ የተደረሰበት ስለሆነ ህብረተሰቡ መሰል ተግባር ሲፈጸም ከተመለከተ በነጻ የስልክ መስመር 8482 በመደወል ለባለስልጣን መሥሪያ ቤቱ እንዲያሳውቅ አስገንዝቧል።

    የባለስልጣን መሥሪያ ቤቱን መግለጫ በመጥቀስ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እንደዘገበው ከላይ የተጠቀሱት ሕገ-ወጥ መድኃኒቶች ለስንፈተ ወሲብ (ፈዋሽነት (በሌላ አባባል፥ ለወሲብ ማነቃቂያነት) ጥቅም ላይ እየዋሉ ሲሆን፥ በአዲስ አበባ፣ በዲላ፣ በወላይታ፣ በወራቤ፣ በሆሳዕና፣ በሀዋሳ፣ በደሴ፣ በኮምቦልቻ እና በጎንደር በስፋት እየተሰራጩ ነው። እነዚህ ሕገ-ወጥ መድኃኒቶች በህብረተሰቡ ላይ እይሳደሩ ያለው ዘርፈ ብዙ ጫና እና ተጽዕኖዎች ከፍተኛ ነው። እንደዘገባው ከሆነ ይህ እጅግ አሳሳቢ ችግር በስፋት ከተከሰተ ሁለት ዓመትና ከዚያ በላይ ቢሆነውም በአሁኑ ጊዜ የተጠቃሚው ቁጥር እየጨመረና እያስከተለ ያለውም ችግር አሳሳቢ ደረጃ ላይ ደርሷል። መግለጫውን መስጠት ያስፈለገውም ስርጭቱ በመስፋፋቱ ህብረተሰቡ ጥንቃቄ እንዲያደርግ እና በድርጊቱ ላይ የሚሳተፉም ከተግባራቸው እንዲቆጠቡ ለማሳሰብ ነው።

    በባለስልጣኑ የመድኃኒት ኢንስፔክሽን ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ገዛኸኝ እንዳለ እንደገለጹት፤ ባለስልጣኑ ባከናወነው የክትትልና ቁጥጥር ስራ በደቡብ ክልል ‹‹ቪጋ› እና ‹‹ቪጎ›› የተባለውን ጨምሮ በህገወጥ መንገድ የገቡ መድኃኒቶች ሲሸጡ የተደረሰባቸው ከ30 በላይ የሚሆኑ የግል መድኃኒት ቤቶች የክልሉ ተቆጣጣሪ አካል እርምጃ እንዲወስድ ስም ዝርዝራቸውን አሳውቋል። በከሚሴና በደሴም በተመሳሳይ የተሰማሩ ወደ 20 ድርጅቶች እርምጃ እንዲወሰድባቸው ማድረጉን ዳይሬክተሩ ገልጸዋል።

    ባለስልጣኑ በተለያየ ጊዜ በህገወጥ መንገድ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገቡ መድኃኒቶችን ከፍትህ አካላትና ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በመውጫ በሮች ላይ ቁጥጥር በማድረግ ህገወጦችን በመከላከል ረገድ ኃላፊነቱን በመወጣት ላይ ቢሆንም የህብረተሰብ ተሳትፎ መኖር እንዳለበት አመልክተዋል። ህብረተሰቡ ያለ ሀኪም ትዕዛዝ ከመውሰድ እንዲቆጠብና ህገወጥነትንም እንዲከላከል ጥሪ አቅርበዋል።

    በባለስልጣኑ የመድኃኒት ምዝገባና ፈቃድ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ አብደላ ቃሶ ባለስልጣኑ ፈዋሽነታቸውና ጥራታቸው የተረጋገጠ መድኃኒቶችን ህብረተሰቡ በቀላሉ የሚለይበትን አሠራር ዘርግቶ ችግሩን ለመቅረፍ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን አስታውቀዋል። ተገልጋዮች ከዚህ በኋላ ሕጋዊና ሕጋዊ ያልሆኑ መድኃኒቶችን በባለስልጣኑ ድረ-ገጽ (http://www.mris.fmhaca.gov.et) ማየት እንደሚችሉና በድረ-ገጹ ላይም ስለመድኃኒቱ ዝርዝር የሆነ መረጃ እንደሚያገኝ አመልክተዋል። ቀደም ሲል እስከ አንድ ዓመት ጊዜ ይወስድ የነበረውን መድኃኒቶችን በዓይነትና በብዛት የመመዝገብ ሥራም በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ እንዲጠናቀቅ ለማስቻል እየሰራ መሆኑንም አስታውቀዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድኃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን እና የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት

    የስንፈተ ወሲብ መድኃኒቶች

    Semonegna
    Keymaster

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊን የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት አድርገው መረጡ። ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ የኢትዮጵያ የሕግ ባለሙያ ሴቶች ማኅበር መሥራች ናቸው።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዛሬ ጥቅምት 22 ቀን 2011 ዓ.ም በሚያካሂደው መደበኛ ስብሰባ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ሹመትን ያጸድቃል ተብሎ ይጠበቃል። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊን የፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት አድርገው መርጠዋቸዋል።

    የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ 5ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፣ 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን፣ 4ኛ መደበኛ ስብሰባ ዛሬ ይካሄዳል። በስብሰባው በሕገ መንግስቱ አንቀጽ 81 ንዑስ አንቀጽ 1 መሰረት ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚያቀርቡትን የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት እጩ ፕሬዚዳንትና ምክትል ፕሬዚዳንት ሹመት መርምሮ እንደሚያጸድቅ ይጠበቃል። ስለዚህ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምርጫ ያቀረቧቸው ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ የጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ሆነው ይሾማሉ ተብሎ ይጠበቃል።

    በአሁኑ ወቅት ፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንትና ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው እያገለገሉ ያሉት አቶ ዳኜ መላኩ እና አቶ ጸጋዬ አስማማው በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተሾሙት ሰኔ 16 ቀን 2008 ዓ.ም ነበር።

    ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ ማን ናቸው?

    ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ  በ1985 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ሕገ መንግስት ኮሚሽን የሕግ አማካሪ ሆነው አገልግለዋል። በ1987 ዓ.ም. የኢትዮጵያ የሕግ ባለሙያ ሴቶች ማኅበርን (Ethiopian Women Lawyers Association/ EWLA) ከሌሎች የሕግ ባለሙያ ሴቶች ጋር በመሆን አቋቁመው በ1988 ዓ.ም. ማኅበሩ በይፋ ሥራ ጀመረ። በዚያም ጊዜ ወ/ሮ መዓዛ የማኅበሩ ሥራ አስፈጻሚ ሆነው እስከ 1997 ዓ.ም. ድረስ ሠርተዋል።

    ወ/ሮ መዓዛ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የምጣኔ ሀብት ኮሚሽን ለአፍሪካ (United Nations Economic Commission for Africa) የተባለው ዓለም-አቅፍ ድርጅትን በ2003 ዓ.ም. በመቀላቀል፥ በዚሁ ድርጅት ውስጥ ከሰኔ ወር 2004 ዓ.ም. ጀምሮ የሴቶች መብት አማካሪ ሆነው ሠርተዋል።

    ከሕግ ባለሙያነታቸው በተጨማሪ በ2003 ዓም ኢትዮጵያ ውስጥ በ13 ጠንካራ ኢትዮጵያውያን ሴቶች ተደራጅነት የተቋቋመው እናት ባንክ (አ/ማ) ሲመሠረት ከመሥራችቹ ውስጥ ጉልህ ሚና የተጫወቱ አባል ነበሩ። ባንኩ ውስጥም ከአራት ዓመታት በላይ የዳይሬክተሮች ቦርድ አባል ሆነው አገልግለዋል።

    ኢትዮጵያ ውስጥ ለሴቶች እኩልነትና ለሴቶች መብት በመታገል ላደረጉት አንጸባራቂ ውጤት ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ በህዳር ወር 1996 ዓ.ም ‘የሀንገር ፕሮጀክት ሽልማት’ (Hunger Project Award) የአፍሪካ ተሸላሚ ሆነዋል። ከዚያም ቀጥሎ (ከሁለት ዓመት በኋላ) የኖቤል የሰላም ሽልማት ዕጩ ሆነው ሊቀርቡ ችለዋል።

    በ2006 ዓ.ም. ዘረሰናይ ታደሰ ተደርሶ የተዘጋጀው (ዳይሬክት የተደረገው) “ድፍረት” የተሰኘውና በዓለም አቀፍ ደረጃ መልካም ተቀብይነትን ያገኘው ፊቸር ፊልም (feature film) ሂሩት አሰፋ የተባለች አንዲት የ14 ዓመት ልጃገረድ ኢፍትሀዊ በሆነ ባህል የሞት ፍርድ ተፈርዶባት ከዚያም የሕግ ባለሙያ (ጠበቃ) የሆነችውን ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊን አግኝታ የሚሆነውን የሚተርክ እንደሆነ ይታወሳል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    መዓዛ አሸናፊ

    Semonegna
    Keymaster

    የኢ.ፌ.ዴ.ሪ የሴቶችና ሕፃናት ጉዳይ ሚኒስቴር በበጎ ፈቃደኛ ኢትዮጵያውያን ሴቶች የተቋቋመውን ጀግኒት የተሰኘ የማህበረሰብ ንቅናቄ በይፋ ለመመሥረት እና አገር አቀፍ የሴቶች የሰላም ጉባዔ ለማካሔድ ዝግጅት መጀመሩን አስታውቋል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – ጀግኒት ንቅናቄ ከኢ.ፌ.ዴ.ሪ የሴቶችና ሕፃናት ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር በመተባበር “ጀግኒት ዓለመች፣አቀደች፣ አሳካች” በሚል መሪ ቃል የሚያዘጋጁትን አገር አቀፍ ጉባዔ አስመልክቶ ዘጠኙ ሴት ሚኒስትሮች፣ እንዲሁም የሁለቱ ምክር ቤት አፈ-ጉባዔና ምክትል አፈ ጉባዔ በተገኙበት ጋዜጣዊ መግለጫ መሰጠቱን ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት (ኤፍ.ቢ.ሲ) ዘግቧል።

    ከዘጠኙ ክልሎች እና ከሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ ሴቶች የሚሳተፉበት አገር አቀፍ የሴቶች የሰላም ጉባዔ የፊታችን ጥቅምት 26 ቀን 2011 ዓ.ም እንደሚካሄድም በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ይፋ ተደርጓል።

    በመግለጫው ላይ ንግግር ያደረጉት የሴቶች፣ ህፃናትና ወጣቶች ሚኒስትር ወ/ሮ ያለም-ፀጋይ አስፋው፥ “ጅግኒት ዓለመች፣ አቀደች፣ አሳካች” በሚል መሪ ቃል የሚደረገው አገር አቀፍ ጉባዔ በሀገሪቱ ውስጥ ዘላቂ ሰላም በማረጋገጥ፤ የሴቶችና ሕፃናትን የአደጋ ተጋላጭነት በመቀነስ መብትና ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ እና ሴቶች ሰላም በአጠቃላይ መከበር ላይ ያላቸውን አስተዋጽዖና ግብዓት ለማሳደግ ነው ብለዋል። እንዲሁም የሴቶችና ሕፃናትን ደኅንነት በዘላቂነት ለማረጋገጥ በየአከባቢው ሴቶች ለሰላማቸው ጠንክረው እንዲሠሩ ለማድረግም ነው በማለት አክለዋል።

    ጀግኒት የተሰኘው የማህበረሰብ ንቅናቄ በአገሪቱ የሴቶችን ጥንካሬ ከተተኪነት በላይ ራሳቸው ለተሻለ ነገር የሚያበቁ እና ብቁ ትውልድ የሚያፈሩ መሆናቸውን ለማሳየት ያስችላል ተብሏል። በአሁን ሰዓት ሴቶች በአገሪቱ ልማትና እድገት ላይ በየደረጃው እየተወጡ ያለው ከፍተኛ አስተዋጽዖ ለሁሉም የኅብረተሰብ ክፍል በማሳወቅና በማሳየት ክብርና ዕውቅና ማግኘት እንዲችሉ ያደርጋል ተብሎ ተብራርቷል።

    ከንቅናቄው በኋላ የሴቶች የልማት ጥምረት ይመሰረታል የተባለ ሲሆን፥ ይህም በሴቶችና ህፃናት ዙሪያ የሚንቀሳቀሱ አካላት ለማጠናከር፣ በዘላቂ ሰላም ማረጋግጥና ሴቶች በልማቱ ያላቸው ተሳታፊነትና ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ዙሪያ የራሱ ድርሻ እንደሚኖረው ተጠቁሟል።

    ከዚህ ጋር በተያያዘ ኢትዮጵያ ውስጥ ከጾታ እኩልነት ጀምሮ እስከ አጠቃላይ ዲሞክራሲ እንዲሰፍን፥ ከቅርብ ወራት ወዲህ በአገሪቱ የተጀመረውን ለውጥ ለማፋጠንም ንቅናቄው አስተዋፅኦው የጎላ ይሆናል ተብሏል።

    በጋዜጣዊ መግለጫው ወቅት ለሚኒስትሮቹ አሁን ያለውን የሴት ሚኒስትሮች ቁጥር ለማስቀጠልም ሆነ በአጠቃላይ በፖለቲካ ውስጥ የሴቶችን ተሳትፎ ለማጎልበት ምን ታስቧል ተብሎ ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ የሰጡት የሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል፥ ብዙ አቅም ያላቸው ሴቶች እንዳሉና ንቅናቄው እስከ ወረዳ ድረስ የሚካሄድ በመሆኑ አቅም ያላቸውን ሴቶች ወደ ከፍተኛ የስልጣን እርከኖች ማምጣት ይቻላል ብለዋል።

    ጀግኒት ንቅናቄን ለመቀላቀል ወይም ደግሞ ስለንቅናቄው የበለጠ ለመረዳት በፌስቡክ ገጻቸው (Jegnit) ወይም በትዊተር አድራሻቸው (@jegnit) ያግኟቸው።

    ምንጭ፦ ኤፍ.ቢ.ሲ እና የጀግኒት ንቅናቄ ማኅበራዊ ገጾች

    ጀግኒት ንቅናቄ

    Semonegna
    Keymaster

    የፈረንሳይ መንግስት በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ጥያቄ መሰረት፥ ለላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያን እድሳት አስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋል፤ የኢትዮጵያ መከላከያን ለማዘመን ተስማምቷል፤ ለአየር መንገድ ከ100 ሚሊዮን ዩሮ በላይ ድጋፍ ያደርጋል።

    ፓሪስ፥ ፈረንሳይ – የፈርንሳይ መንግስት ለላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያን ድጋፍ እንዲያደርግ በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) የቀረበለትን ጥያቄ በፕሬዝዳንቱ ኢማኑኤል ማክሮን (Emmanuel Macron) በኩል ተቀብሎ ተስማምቷል።

    በፈረንሳይ ይፋዊ የሥራ ጉብኝት በማድረግ ላይ የሚገኙት የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ፥ ትናንት ምሽት ነው በፓሪስ ኢልዚ ቤተ መንግስት (Élysée Palace) ከፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ጋር በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ኢትዮጵያ በባህል፣ በእምነትና በቋንቋ ከፈረንሳይ ጋር የነበራትን ወዳጅነት እንድታጠናክር የፈረንሳይ የመጀመሪያ ሥራ በላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያን የደረሰውን ችግር መቅረፍ ሊሆን እንደሚገባ ለፕሬዝዳንት ማክሮን ጥያቄ አቅርበው አዎንታዊ ምላሽ መገኘቱን ሁለቱ መሪዎች በጋራ በስጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ አስታውቀዋል።

    መሪዎቹ በሰላም፣ በዴሞክራሲና በልማት ዙሪያ ዝርዝር ውይይት ማድረጋቸውን የጠቀሱት ዶ/ር አብይ፥ ፈረንሳይ የሀገር መከላከያን ለማዘመን የሰው ኃይል ለማሰልጠን መስማማቷንም  አስታውቀዋል።

    መሪዎቹ በኢኮኖሚው መስክ ባደረጉት ውይይትም ፈረንሳይ የኢትዮጵያ አየር መንገድን ለማዘመን ከ100 ሚሊዮን ዩሮ በላይ በማውጣት የአዲስ አበባ ኤርፖርትን ለመሥራት፣ እንዲሁም የፈረንሳይ ኢንቨስተሮች ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ኢንቨስት እንዲያደርጉ ከስምምነት መድረሳቸውን ጠቅላይ ሚኒስትሩ የገለጹት።

    ኢትዮጵያ የጀመረችውን የኢኮኖሚ ማሻሻያ ከማገዝ አንጻርም ከፈረንሳይ የልማት ኤጀንሲ (ኤ.ኤፍ.ዲ)፣ ከአለም ባንክ እና ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም (አይ.ኤም.ኤፍ) ከምታገኘው የበጀት ድጋፍ በተጨማሪ የፈረንሳይ መንግስት የቀጥታ ድጋፍ ለማድረግ ያለውን ዝግጁነት ፕሬዝዳንት ማክሮን መግለፃቸውን ዶ/ር አብይ አስታውቀዋል።

    የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት እ.ኤ.አ በመጋቢት ወር 2019 ኢትዮጵያን እንደሚጎበኙ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቁመዋል።

    በአፍሪካ ቀንድ በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል የመጣውን ሰላም በማስቀጠል በኤርትራና በጅቡቲ መካከል ሰላም እንዲጠናከር ለማድረግ በጋራ ለመስራት መስማማታቸውንም አስታውቀዋል በማለት ኤፍ.ቢ.ሲ ዘግቧል።

    ፕሬዚዳንት ማክሮን ኢትዮጵያን የሚጎበኙት ከጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ በቀረበላቸው ግብዣ መሰረት መሆኑም ታውቋል። ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ከውይይቱ በኋላ ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ ጋር በሰጡት የጋራ መግለጫ፥ የፊታችን መጋቢት ወር 2011 ዓ.ም ላይ ኢትዮጵያን እንደሚጎበኙ አስታውቀዋል።

    የፈረንሳይ የልማት ኤጀንሲ (ኤ.ኤፍ.ዲ) እ.ኤ.አ በመስከረም ወር 2017 ዓም የአዲስ አበባ ቄራዎች ድርጅትን ለማሻሻልና በአዲስ ቦታ ለማደራጀት ከ70 ሚሊዮን ዩሮ በላይ ድጋፍ ማድረጉን፣ እ.ኤ.አ በሰኔ ወር 2018 ደግሞ ለከተማ ልማት እና የጂኦተርማል ኤሌክትሪክ ኃይል ፕሮጀችት 18 ሚሊዮን ዩሮ ለመደገፍ ከኢፌዴሪ የፋይናንስና ገንዘብ ሚኒስቴር ጋር ስምምነቶችን መፈራረሙን መዘገባችን ይታወሳል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ 

    የፈረንሳይ መንግስት


    Semonegna
    Keymaster

    በአገሪቱ ከ7 ሺህ 800 በላይ አዳዲስ አነስተኛና መካከለኛ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎች እንደሚቋቋሙ የፌዴራል አነስተኛና መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ልማት ኤጀንሲ አስታወቀ።

    አዳማ (ኢዜአ)– በመላ አገሪቱ በዚህ አመት ከ7 ሺህ 800 በላይ አዳዲስ አነስተኛና መካከለኛ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎች እንደሚቋቋሙ በኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ስር የሚገኘው የፌዴራል አነስተኛና መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ልማት ኤጀንሲ (Federal Small and Medium Manufacturing Industry Development Agency) አስታወቀ።

    አዳዲስ ኢንዱስትሪዎቹን ለማቋቋም፣ ነባሮችን ለማጠናከርና በቁሳቁስ ለማደራጀት 14 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር እንደሚያስፈልግ ኤጀንሲው አስታውቋል።

    የአነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዝ ፋይናንስ ፕሮጀክት የ2010 በጀት ዓመት የሥራ ዕቅድ አፈጻጸምን የሚገመግምና በ2011 ዕቅድ ላይ የሚመክር የሁለት ቀን መድረክ ጥቅምት 17 ቀን 2011 ዓም በአዳማ ከተማ ተጀምሯል።

    በኤጀንሲው የፖሊሲ ዕቅድና ፕሮጀክት ዝግጅትና ክትትል ዳይሬክተር ወ/ሮ ገነት አረጋዊ በወቅቱ እንደገለጹት ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ መር ኢኮኖሚ ለሚደረገው መዋቅራዊ ሽግግር አዳዲስ አነስተኛና መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎችን መገንባት አስፈልጓል። ነባሮችንም የማጠናከር ሥራ የትኩረት አቅጣጫ መሆኑን ነው የገለጹት።

    ለእዚህም በበጀት ዓመቱ 7 ሺህ 860 አዳዲስ አነስተኛና መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎችን የማቋቋምና 2 ሺህ 924 ነባር ኢንዱስትሪዎች የማጠናከር ሥራ እንደሚከናወን አመልክተዋል።

    “አዳዲስ ኢንዱስትሪዎቹን ለማቋቋም፣ ነባሮቹን ለማጠናከርና ለእቃ አቅርቦት የሚያስፈልገው 14 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ለሁሉም ክልሎች፣ ለአዲስ አበባና ድሬዳዋ ከተማ መስተዳድሮች በብድር ይቀርባል” ብለዋል ወ/ሮ ገነት።

    የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ወ/ሮ መሰንበት ሸንቁጥን ፕሬዝደንት አድርጎ መርጧል

    አዲስ ከሚቋቋሙት የማምረቻ ኢንዱስትሪዎች መካከል የብረታ ብረትና እንጨት ሥራ፣ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት፣ ቆዳና የቆዳ ውጤቶች፣ የግብርና ምርት ማቀነባበሪያዎች፣ የኮንስትራክሽን ግብዓቶችና ጌጣ ጌጥ ማምረቻዎች እንደሚገኙበት ጠቅሰዋል።

    ዳይሬክተሯ እንዳሉት በሚቋቋሙት ኢንዲስትሪዎች ከ195 ሺህ ለሚበልጡ ዜጎች ቋሚ የሥራ እድል ይፈጠራል ተብሎ ይጠበቃል። አያይዘውም “ኢንዱስትሪዎቹን ውጤታማ ለማድረግ በሀገር ውስጥ የ2 ቢሊዮን ብርና በውጭ አገራት የ194 ነጠብ 5 ሚሊዮን ዶላር የገበያ ትስስር ይመቻቻል” ብለዋል።

    ዘርፉን ለማሳደግ ለባለሀብቶች፣ ለዩኒቨርሲቲ ምሩቃን፣ ለሞዴል አርሶ አደሮችና አርብቶ አደሮች እንዲሁም ለሌሎችም የኅብረተሰብ ክፍሎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና እንደሚሰጥ ዳይሬክተሯ አስታውቀዋል ።

    የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር አቶ አስፋው አበበ በበኩላቸው “የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ልማት የትራንስፎርሜሽኑ መሰረት ስለሆነ በእያንዳንዱ ወረዳ ሊቋቋም ይገባል” ብለዋል።

    ባለድርሻ አካላትን በልዩ ትኩረት በመሳተፍ ዕቅዱን እውን ለማድረግ ኤጀንሲው ከሁሉም ክልሎችና ከሁለት የከተማ መስተዳድሮች ጋር ጥቅምት 17 ቀን 2011 ዓ.ም የስምምነት ሰነድ መፈራረሙንም አቶ አስፋው አመልክተዋል።

    የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ለውጥና ብልጽግና እንዲሁም የቴክኖሎጂ ሽግግር ያለማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪው ዕድገትና ተወዳዳሪነት ሊመጣ ስለማይችል ሁሉም አካላት ለተፈጻሚነቱ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ዋና ዳይሬክተሩ አሳስበዋል ።

    የቀረበው አመላካች ዕቅድ ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ-መር ኢኮኖሚ ለመሸጋገር የሚደረገውን ግብ ለማሳካት ወሳኝ ስለመሆኑ ከመድረኩ ተሳታፊዎች ተገልጿል።

    ለኢንዱስትሪው ልማት ማነቆ የሆኑ በሊዝ፣ በብድር ገንዘብና በኤሌክትሪክ አቅርቦት የሚስተዋሉ እጥረቶችና የተንዛዙ አሠራሮች ሊፈቱ እንደሚገባም በተሳታፊዎቹ ጥያቄ ቀርቧል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    መካከለኛ የማኑፋክቸሪንግ

    Semonegna
    Keymaster

    በአዊ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ፋግታ ለኮማ ወረዳ በደረሰ የመኪና አደጋ የ14 ሰዎች ሕይወት ማለፉን የአማራ ብዙሃን መገናኛ ድርጅት (አብመድ) እና የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) የዞኑ ፖሊስ መምሪያን በመጥቀስ ዘግበዋል።

    የመምሪያው የመንገድ ትራፊክ ደህንነት ባለሙያ ዋና ኢንስፔክተር ወርቅነህ ስዩም በተለይ ለኢዜአ እንደገለጹት ይህ የመኪና አደጋ የደረሰው ጥቅምት 17 ቀን 2011 ዓ.ም፣ ከጠዋቱ 3፡00 አካባቢ ሲሆን፥ ቦታው ደግሞ በወረዳው “ሉሊስታ” በተባለ ቀበሌ ነው። ከዳንግላ ወደ ኮሶበር እየሔደ የነበረ 16 ሰው የመጫን አቅም ያለው የህዝብ ማመላለሻ መኪና (የሰሌዳ ቁጥሩ፦ 3-20705-አማ) እና ወደ ባህር ዳር አቅጣጫ እየሄደ ከነበረ የመከላከያ ሠራዊት ከባድ የጭነት መኪና (የሰሌዳ ቁጥሩ፦ መከ-01335) ክፉኛ በመጋጨታቸው የ1 ሰዎች ሕይወት የቀጠፈው አደጋ ሊደርስ ችሏል።

    ዋና ኢንስፔክተር ወርቅነህ በገለጻቸው “የህዝብ ማመላለሻ መኪናው ከዳንግላ ወደ ኮሶበር በመጓዝ ላይ ሳለ በተቃራኒ አቅጣጫ ወደ ባህር ዳር ይመጣ ከነበረው ከባድ የጭነት መኪና ጋር በመጋጨታቸው አደጋው ሊከሰት ችሏል” ሲሉ፥ በተከሰተው አደጋ 14 ሰዎች ሕይወታቸው ሲያልፍ ሌሎች 12 ሰዎች በጽኑ ቆስለዋል በማለት አክለው ተናግረዋል። ከዚህ በተጨማሪ አደጋው በደረሰበት ወቅት 15 ሰው ብቻ መጫን የነበረበት የሕዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪው 25 ሰዎችን ጭኖ እንደነበር ዋና ኢንስፔክተር ወርቅነህ አያይዘው ገልጸዋል።

    በፋግታ ለኮማ ወረዳ የትራፊክ ተቆጣጣሪ ሳጅን መልካሙ ልየው ለአብመድ ሕይወታቸው ስላለፈው ሰዎች ሲያብራሩ፥ በአደጋው ሹፌሩን እና ረዳቱን ጨምሮ የ14 ሰዎች ሕይወት አልፏል ብለዋል።

    የቆሰሉት ሰዎች በዳንግላና እንጅባራ ሆስፒታሎች ህክምና እየተደረገላቸው ሲሆን ቀላል ጉዳት የደረሰባቸው ሁለት ተጨማሪ ሰዎች ደግሞ በአዲስ ቅዳም ጤና ጣቢያ ሕክምና ተደርጎላቸው ወደ ቤተሰቦቻቸው ተልከዋል።

    የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን የስምንት መንገዶች ግንባታ ሥራ የኮንትራቶችን ከተለያዩ ተቋራጮች ጋር ተፈራረመ

    ከሟቾች መካከል ከሕጻን ልጃቸው ጋር ሕይወታቸው ያለፈው አንዲት እናት እንደሚገኙበት ያስታወቁት ኢንስፔክተሩ፣ የ13ቱ ሟቾች አስክሬን ወደቤተሰቦቻቸው የተላከ ሲሆን ለቀሪው የአንዲት ሴት አስከሬን ቤተሰቦቿን የማፈላለግ ሥራ እየተሠራ መሆኑን ዋና ኢንስፔክተር ወርቅነህ ስዩም ጠቁመዋል።

    ዋና ኢንስፔክተሩ እንዳስታወቁት በአሁኑ ወቅት የአደጋው መንስዔ እየተጣራ መሆኑን አመልክተው፣ የከባድ መኪናው አሽከርካሪ አደጋው ከደረሰ በኋላ በመሰወሩ በቁጥጥር ስር ለማዋል በፖሊስ በኩል ክትትል እየተደረገ ሲሆን፤ ይህ ዘገባ እስከተጠናቀረበት ጊዜ ድርስ አልተያዘም። በየቀኑ እየደረሰ ያለውን የትራፊክ አደጋ ለመቀነስ አሽከርካሪዎች የመንገድ ትራፊክ ደህንነት ህጉን አክብረው ሊያሽከረክሩ እንደሚገባም ኢንስፔክተሩ አሳስበዋል።

    ከዚህ ጋር በተያያዘ ባለፈው ዓመት ሀምሌ 1 ቀን 2010 ዓ.ም የሀገሪቱ ትራንስፖርት ባለስልጣን ባወጣው በ2010 ዓ.ም የበጀት ዓመት ብቻ 5,118 ሰዎች በተሽከርካሪ አደጋ ሕይወታቸው እንዳለፈ፣ ይህም ከ2009 ዓ.ም የበጀት ዓመት ጋር ሲነጻጸር 13.7 በመቶ እንደጨመረ ያስረዳል። የፌደራል ትራንስፖርት ባለስልጣን ባወጣው በዚሁ መግለጫ ላይ በ2010 ዓ.ም የበጀት ዓመት በተሽከርካሪ አደጋ 7,754 ሰዎች ላይ የከባድ፣ 7,775 ሰዎች ላይ ደግሞ ቀላል የመቁሰል አደጋ ደርሷል። በዚሁ የበጀት ዓመት የደረሰው የመኪና አደጋ (የተሽከርካሪ አደጋ) በቁጥር 41,000 ሲሆን ይህም በ2009 ዓ.ም የበጀት ዓመት ከደረሰው የተሽከርካሪ አደጋ ጋር ሲነጻጸር በመቶ እድገት አሳይቷል። ኢትዮጵያ በዓለም ላይ ካሉ ሀገራት በተሽከርካሪ ብዛት ዝቅተኛ ከሚባሉ ሀገራት ብትመደብም በተሽከርካሪ ምክንያት በሰው ላይ በሚደርስ አደጋ ግን አውራ ቦታ ከያዙት ሀገራት ውስጥ ትመደባለች።

    ምንጮች፦ Xinhua፣ አብመድ እና ኢዜአ

    የመኪና አደጋ

    Semonegna
    Keymaster

    ፓዌ ወረዳ (የኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት) – መገኛው ከምስራቅ እስያ እንደሆነ የሚነገርለት አኩሪ አተር አሜሪካንና ቻይናን ጨምሮ በርካታ የአለም አገራት በስፋት በማምረት ለምግብነት ማዋል ከጀመሩ ሁለት ምዕተ ዓመታት ተቆጥረዋል። አኩሪ አተር ከፍተኛ የፕሮቲን መጠን በውስጣቸው ከያዙ የሰብል ዓይነቶች ውስጥ አንዱና ዋነኛው ሲሆን የቪታሚን፣ የማዕድንና ሌሎችም ለጤና ጠቃሚ የሆኑ ንጥረ ነገሮች ይዘቱ ከፍተኛ መሆኑ በሰው ልጅ የአመጋገብ ስርዓት ውስጥ እጅግ አስፈላጊ እንዲሆን ያደርገዋል።

    በሰብሉ ዙሪያ የተካሄዱ ጥናቶች እንደሚጠቁሙት ከሆነም የልብ ህመም፣ የደም ግፊትና ካንሰርን ጨምሮ ለበርካታ የሰውን ልጅ ሊያጠቁ የሚችሉ የበሽታ አይነቶች መፍትሄም ነው። በዚህም አኩሪ አተር በአጭር ጊዜ ውስጥ በ ዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ተፈላጊነትን ሊያገኝ ችሏል። ከዚህ በተጨማሪም አኩሪ አተር በውስጡ የያዘው የዘይት መጠን ከፍተኛ በመሆኑ በአገር ውስጥና በውጭ ኢንዱስትሪዎች እየታየ ያለው የምርት ፍላጎት ከፍተኛ ሲሆን የአፈር ለምነትን ለማሻሻል የሚረዳ የሰብል ዓይነት ነው። ለእንሰሳት መኖነትም በከፍተኛ ሁኔታ ይውላል።

    አገራችን ኢትዮጵያም አኩሪ አተርን ወደ አገር ውስጥ በማስገባት የተስማሚነት ጥናት በማካሄድ፣ በማላመድና በማምረት ለምግብነት ማዋል ከጀመሩ አገራት ውስጥ አንዷ ናት። አኩሪ አተር ወደኢትዮጵያ ገብቶ መመረት ከጀመረ አራት አስርት ዓመታት በላይ ያስቆጠረ እንደሆነ ይነገራል። በሰብሉ ዙሪያ በተደረጉ ምርምሮችም ከ25 በላይ ቴክኖሎጂዎች ማውጣት ተችሏል። ከነዚህም ውስጥ አብዛኛውን ቁጥር የሚይዙት በኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የወጡ ናቸው። አገራችን አኩሪ አተርን በስፋት ለማምረት አመቺ የሆነ ሰፊ መሬትና አየር ንብረት ያላት ከመሆኑ ገር በተያያዘ በርካታ አገራት ያሳዩት የንግድ ፍላጎት ከፍተኛ ቢሆንም በዚሁ ሰብል እተሸ ፈነ ያለው መሬት ስንመለከት እጅግ በጣም አነስተኛ ነው። በመሆኑም በአገሪቱ ውስጥ በፍጥነት እየተስፋፉ ላሉ የምግብ ዘይትና የእንሰሳት መኖ አምራች ኢንዱስትሪዎች የምርት ፍላጎት የሚመጥን ምርት ማቅረብ አልተቻለም።

    በኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የፓዌ ግብርና ምርምር ማዕከል (ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል) ከአኩሪ አተር ሰብል የሚገኘውን ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ከግምት ውስጥ በማስገባትም ለረጅም ጊዜያት ምርምር ሲያካሂድ የቆየ ሲሆን የዝናብ መጠናቸው ከፍተኛ፣ መካከለኛና ዝናብ አጠር ለሆኑ አካባቢዎች ተስማሚ እንዲሁም በሽታንና ተባይን የመቋቋም አቅማቸው ከፍተኛ የሆኑ የአኩሪ አተር ቴክኖሎጂዎችን በማውጣት በአርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ ዘንድ ተቀባይነትን እንዲያገኙ የማስተዋወቅና የማስፋፋት ሥራዎችን ሲሠራ ቆይቷል። ከዚሁ ጋር በተያያዘም ውጤታማና ጥራት ያለው ምርት ለማምረት እንዲቻል የአመራረት ሂደትን የተከተሉ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠናዎችን ሲሰጥ ቆይቷል።

    ቪድዮ፦ ኢትዮጵያ ውስጥ በአማሮ ወረዳ በቡላ ምርት ላይ የተሠማሩ ሰዎች አስፈላጊውን ድጋፍ ስለማይደረግላቸው እየተዳከሙ ነው

    ማዕከሉ በዚሀ ዓመትም በመተከል ዞን በፓዌና ማንዱራ ወረዳዎች የሚገኙ አርሶ አደሮችንና ከፊል አርብቶ አደሮችን በማቀናጀት የማኅበረሰብ አቀፍ የአኩሪ አተር ቴክኖሎጂ መነሻ ዘር ብዜት ሥራዎችን አከናውኗል። ይህንንም ተሞክሮ በማስፋት ሌሎችም የአካባቢው አርሶ አደሮችና አርብቶ አደሮች ተጠቃሚ የሚሆኑበትን ለማመቻቸትና ፍላጎት ለመፍጠር የሚረዳ አርሶ አደር የመስከ ቀን ጥቅምት 4 ቀን 2011 ዓ.ም አካሂዷል። በዚሁ በዓል ላይ ተሳታፊ የነበሩ አንዳንድ የአካባቢው አርሶ አደሮች እንደገለፁትም ሰብሉን ማምረት እያስገኘ ያለውን ጠቀሜታ ከሌሎች አርሶ አደሮች በመረዳታቸው የአኩሪ አተርን ለማምረት ፍላጎት ያደረባቸው ቢሆንም የመነሻ ዘር አቅርቦት ችግር ገጥሟቸዋል። ለዚህም ችግር መፍትሄ እንደሚያገኙ በመተማመን ወደ ምርምር ማዕከሉ እንደመጡ ይናገራሉ።

    በኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የሁለተኛው የግብርና እድገት ፕሮግራም አሰተባባሪ የሆኑት ወ/ሮ ሶፊያ ካሳ በዚሁ የአርሶ አደር መስክ ቀን መርሃ ግብር ላይ በመገኘት የመክፈቻ ንግግር ባደረጉበት ወቅት እንደገለፁት በአኩሪ አተር ዙሪያ የተከናወኑ የማስተዋወቅና የማስፋፋት እንዲሁም ዘር ብዜት ስራዎች የኢንስቲተዩቱ ቴክኖሎጂዎች ያላቸው ተደራሽነተት ምን ያህል ነው የሚለውን ማሳያ ነው ያሉ ሲሆን በአገሪቱ ለረጅም ጊዜያት ሲነሳ የቆየውን የመስራችና ቅድመ መስራች ዘር አቅርቦት እጥረት ችግር ኢንስቲትዩቱ በተያዘው በጀት ዓመት ከክልል ግብርና ምርምር ተቋማትና ከሌሎችም አጋር አካላት ጋር በመቀናጀት አርሶ አደሩe በማደራጀትና ስልጠና እንዲያገኝ በማድረግ የመስራችና ቅድመ መስራች ዘር ብዜት ሥራን በጥራት የማከናወን ተግባር እያከናወነ እንደገኝ ገልፀዋል። ከዚህ በተጨማሪም የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልልና አካባቢው አኩሪ አተርን ጨምሮ ለበርካታ ሰብል ምርት አመቺ የሆነ አካባቢ በመሆኑ በተመሳሳይ የሚታየውን የመነሻ ዘር አቅርቦት ችግር ለመቅረፍ የፓዌ ግብርና ምርምር ማዕከል ከአካባቢው አርሶ አደርና አርብቶ አደር ጋር ያለውን ትስስር በማሳደግ የሰብል ምርትን አስተማማኝ ደረጃ ለማድረስ መስራት ይኖርበታል ሲሉ ይገልፃሉ። ዶ/ር ሶፊያ አያይዘውም አርሶ አደሩ መስኖን በመጠቀም በዓመት ሁለት ጊዜ ማምረት የሚያስችለው አቅም ላይ እንዲደርስ ድጋፍ ማድረግ ይኖርብናል ብለዋል።

    የአኩሪ አተር ቴክኖሎጂ አርሶ አደሩ ዘንድ በስፋት እንዲደርስ ለማድረግም የማስተዋወቅና የማስፋት ስራዎች በተጠናከረ ሁኔታ መሠራት የሚኖርባቸው ሲሆን የአካባቢውን ማኅበረሰብ ተሳትፎ በማሳደግም በክላስተር እንዲደራጁ በማድረግ በባለሞያዎች እገዛም ጥራቱን የጠበቀ የመነሻ ዘር ብዜት በማከናወን በርካታ ቁጥር ያላቸው የአካባቢውን አርሶና አርብቶ አደሮች ተጠቃሚነት ማሳደግ የሚቻል መሆኑ ይታወቃል። ከዚሁ ጋር በተያያዘም የቅድመ-መስራችና መስራች ዘር አቅርቦት ሃላፊነት የምርምር ተቋማት ቢሆንም የአገሪቱ የምርምር ተቋማት ካላቸው የአቅም ውስንነት መነሻነት መነሻ ዘሮችን በስፋት ለተጠቃሚዎች ለማድረስ አይቻላቸውም። በመሆኑም የዘር ብዜት ስራን በሃላፊነት ከሚያከናውኑ ተቋማት በተጨማሪም አርሶ አደሮችን በማደራጀትና ተገቢውን የሰብል አያያዝ ስልጠና በመስጠትና ክትትል በማድረግ ምርትን ማስፋት ከማስቻሉም ባለፈ መነሻ ዘር ላይ የሚፈጠሩ የተለያዩ ችግሮችን በመቅረፍ የሰብል ምርቶችን በስፋት ለኢንዱስትሪ ግብአትነትና ለውጭ ንግድ ማዋል የሚያስችል በመሆኑ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ይሆናል።

    የፓዌ ግብርና ምርምር ማዕከል በሰሜን ምዕራብ የአገሪቱ ክፍል በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መተከል ዞን ፓዌ ወረዳ የሚገኝ ሲሆን፣ ምርምር ማዕከሉ በሰብል በእንሰሳትና ተፈጥሮ ሃብት የምርምር ዘርፎች ለረጅም ጊዜያት የምርምር ሥራዎችን ሲያከናውን ቆይቷል። በዚህም በርካታ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ፣ በማላመድ፣ በማስተዋወቅና የማስፋት ሥራዎችን በማከናወን በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ አርሶ አደሮችና አርብቶ አደሮችን ተጠቃሚ ለማድረግ ሲሠራ ቆይቷል፤ እየሰራም ይገኛል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት

    አኩሪ አተር

    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትና የፌደሬሽን ምክር ቤቶች ጥቅምት 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ባካሄዱት ልዩ ስብሰባቸው አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴን 4ኛው የኢትዮጵያ ርዕሰ ብሄር (ፕሬዝዳንት) አድርጎ በሙሉ ድምፅ መርጧል።

    ፕሬዝዳት ሳህለወርቅ ዘውዴ ቃለ መሃላ ፈፅመው ኃላፈነታቸውን በትጋትና በታኝነት አገርና ህዝብን ለማገልገል ቃል ገብተዋል።

    አምባሳደር ሳህለ ወርቅ ዘውዴ ላለፉት አመስት ዓመታት በፕሬዝዳንትነት ላይ የነበሩትን ዶ/ር ሙላቱ ተሾመን በመተካት አገሪቱን በፕሬዝዳንትነት የሚመሩ ይሆናል። ተሰናባቹ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመም ከተመራጯ ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ጋር የስልጣን ርክክብ አድርገዋል።

    አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ ማን ናቸው?

    ተወልደው ያደጉት አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ሲሆን የመጀመሪያና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን የተከታተሉት በሊሴ ገብረማርያም ትምህርት ቤት ነው። አራት ሴት ልጆች ለነበሯቸው ወላጆቻቸው የመጀመሪያ ልጅ የሆኑት ሳህለወርቅ ዘውዴ ገና በ17 ዓመታቸው ነጻ የትምህርት ዕደል አግኝትው ወደ ፈረንሳይ በማቅናት ሞንትፔልየር (Montpellier) በምትባለው የፈረንሳይ ከተማ በሚገኘው ዮኒቨርሲቲ ኦፍ ሞንትፔልየር (University of Montpellier) የተፈጥሮ ሳይንስን አጥንተዋል። በሀገረ ፈረንሳይ ለዘጠኝ ዓመታት ከቆዩ በኋላ ወደ ኢትዮጵይ በመመለስ በትምህርት ሚኒስቴር ውስጥ የሕዝብ ግንኙነት ክፍልን ማገልገል ጀመሩ። ቆይተውም የሕዝብ ግንኙነት ክፍሉን በበላይነት መርተዋል። ከዚያም ወደ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በመዘዋወር በተለያዩ የሥራ ኃላፊነቶች አገልግለዋል።

    ወሮ ሳህለወርቅ ዘውዴ በአምባሳደርነት ለመሾም ከአምባሳደር ዮዲት እምሩ ቀጥሎ ሁለተኛዋ እንስት ናቸው። በመጀመሪያ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሆነው የተሾሙትም ሴኔጋል ሲሆን የአምባሳደርነት ስልጣናቸውም ሴኔጋልን ጨምሮ ማሊን፣ ኬፕ ቨርዴን፣ ጊዚ ቢሳውን፣ ጋምብያን እና ጊኒን (እ.ኤ.አ 1989–1993) ያጠቃልል ነበር። ቀጥሎም እ.ኤ.አ 1983–2002 በጅቡቲ የኢትዮጵያ አምባሳደርና በኢጋድ (IGAD) የኢትዮጵያ ተጠሪ ሆነው አገልግለዋል። እ.ኤ.አ ከ2002 ጀምሮ እስከ 2006 ድረሰ በፈረንሳይ (ሞሮኮን ጨምሮ) የኢትዮጵያ አምባሳደርና በዩኔስኮ (UNESCO) የኢትዮጵያ ተጠሪ ሆነው አገልግለዋል። እ.ኤ.አ ከ2006 ጀምሮ እስከ 2009 ድረስ በአፍሪካ ህብረት (AU) እና በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (UNECA) የኢትዮጵያ ተጠሪ ሆነው ሀገራቸውን አገልግለዋል።

    ከሀያ ዓመታት በላይ በተለያዩ ሀገራትና ዓለማቀፋዊ ድርጅቶች የኢትዮጵያ አምባሳደርና ተጠሪ በመሆን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤትን ያገለገሉት አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ እ.ኤ.አ በ2009 የተበባሩት መንግስታት ድርጅትን (ተመድ) በመቀላቀል የድርጅቱ በመካከለኛው አፍሪካ ሪፑብሊክ የተቀናጀ ሰላም ግንባታ መሪ (Head BINUCA) በመሆን ማገልገል ጀመሩ። ይህ አገልግሎታቸውም ወደ ሚቀጥለው ኃላፊነት አሸጋግሯቸው እ.ኤ.አ በ2011 ዓም የዚያን ጊዜ የተመድ ጠቅላይ-ጸሀፊ ባን ኪ-ሙን (Ban Ki-moon) አዲስ ለተቋቃመው በናይሮቢ የተመድ ጽህፈት ቤት (UNON) የመጀመሪያዋ ጠቅላይ-መሪ አድርገው ሾማቸው። በዚያም ለሰባት ዓመታት ካገለገሉ በኋላ እ.ኤ.አ በሰኔ ወር 2010 የአሁኑ የተመድ ጠቅላይ-ጸሀፊ አንቶንዮ ጉቴሬስ (António Guterres) አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴን በተመድ ጠቅላይ-መሪ ስር (Under-Secretary-General) የአፍሪካ ህብረት ልዩ ተጠሪ (UN’s Special Representative to the AU) እና በአፍሪካ ህብረት ውስጥ የተመድ ጽህፈት ቤት ዋና ኃላፊ (Head of UNOAU) አድርገው ሾሟቸው እስካሁን ድረስ በዚሁ ሹመታቸው እያገለገሉ ይገኛሉ።

    አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ ባለትዳርና የሁለት ወንድ ልጆች እናት ናቸው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ሳህለወርቅ ዘውዴ


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ኢመባ) – የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን (ኢመባ) 600 ኪ.ሜ ርዝመት የሚሸፍኑ የስምንት መንገዶች ግንባታ ሥራ የኮንትራት ስምምነት ከ13.8 ቢሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ከተለያዩ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ሀገር ተቋራጮች ጋር ተፈራረመ።

    የሁለተኛው የእድገትና ትራንስፎርሜሽን አካል የሆኑና 600 ኪ.ሜ ርዝመት የሚሸፍኑ የስምንት መንገዶች የመንገድ ግንባታ ሥራዎች የኮንትራት ስምምነት ከብር 13.8 ቢሊዮን በላይ በሆነ ወጪ ጥቅምት 14 ቀን 2011 ዓ.ም በሒልተን ሆቴል ተፈራርሟል። የመንገድ ፕሮጀክቶቹ ዝርዝር መረጃ የሚከተለውን ይመስላል።

    1. ጣርማበር–መለያ–ሰፈሜዳ መገንጠያ 1 መለያ–ሞላሌ–መገንጠያ 2 ሞላሌ–ወገሬ መንገድ (ርዝመት 118.87 ኪ.ሜ)

    o የገንዘቡ መጠን፦ 1,906,200,296.75 ብር
    o የግንባታ ጊዜ ሚፈጀው፦ 36 ወራት
    o ኮንትራክተር፦ መከላከያ ኮንስትራክሽን

    2. ጂማ–አጋሮ–ዴዴሳ ወንዝ መንገድ (ርዝመት 79.07 ኪ.ሜ)

    o የገንዘቡ መጠን፦ 1,306,509,305.57 ብር
    o የግንባታ ጊዜ ሚፈጀው፦ 42 ወራት
    o ኮንትራክተር፦ ቻይና ሬል ዌይ 21ኛ ቢሮ ግሩኘ
    o ቀድሞ የነበረው የመንገዱ ደረጃ፦ አስፋልት

    3. መሰል/ሞሲሊ–ኮራ/ቆሪ–84.2 ኪ.ሜ /ኮንት 1/ መንገድ (ርዝመት 84.2 ኪ.ሜ)

    o የገንዘቡ መጠን፦ 1,536,235,563.54 ብር
    o የግንባታ ጊዜ ሚፈጀው፦ 42 ወራት
    o ኮንትራክተር፦ ቻይና ስቴት ኮንስትራክሽን ኢንጂነሪንግ ኮ. ሊሚትድ

    4. መሰል/ሞሲሊ–ኮራ/ቆሪ–84.2–ጠሩ ኪ.ሜ /ኮንት 2/ መንገድ (ርዝመት 73.34 ኪ.ሜ)

    o የገንዘቡ መጠን፦ 1,502,371,329.85 ብር
    o የግንባታ ጊዜ ሚፈጀው፦ 42 ወራት
    o ኮንትራክተር፦ ቻይና ስቴት ኮንስትራክሽን ኢንጂነሪንግ ኮ. ሊሚትድ

    5. አርሲ–ሮቤ–አጋርፋ–አሊ ኮንትራት 1 አሊ ከተማ-ዋቤ ድልድይ መንገድ (ርዝመት 53.5 ኪ.ሜ)

    o የገንዘቡ መጠን፦ 2,153,060,671.98 ብር
    o የግንባታ ጊዜ ሚፈጀው፦ 36 ወራት
    o ኮንትራክተር፦ ቻይና ኮሙኒኬሽን ኮንስትራክሽን ኩባንያ (ሲሲሲሲ)

    6. አዲአርቃይ–ጠለምት መንገድ (ርዝመት 76.6 ኪ.ሜ)

    o የገንዘቡ መጠን፦ 1,981,378,049.64 ብር
    o የግንባታ ጊዜ ሚፈጀው፦ 36 ወራት
    o ኮንትራክተር፦ የንኮማድ ኮንስትራክሽን

    7. እስቴ–ስማዳ መንገድ (ርዝመት 53.08 ኪ.ሜ)

    o የገንዘቡ መጠን፦ 1,925,451,264.41ብር
    o የግንባታ ጊዜ ሚፈጀው፦ 36 ወራት
    o ኮንትራክተር፦ ቻይና ኮሙኒኬሽን ኮንስትራክሽን ኩባንያ (ሲሲሲሲ)

    8. ውቅሮ–አጽቢ–ኮነባ መንገድ (ርዝመት 63 ኪ.ሜ)

    o የገንዘቡ መጠን፦ 1,745,722,493.86 ብር
    o የግንባታ ጊዜ ሚፈጀው፦ 42 ወራት
    o ኮንትራክተር፦ ሱር ኮንስትራክሽን

    የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን በመግለጫው እንዳስታወቀው መንገዶቹ ከዚህ በፊት በጠጠር ደረጃ የነበሩ ሲሆን አሁን ግን በአስፋልት ደረጃ የሚገነቡ ይሆናሉ። ለነዚህም ግንባታ ሙሉ ለሙሉ የኢትዮጵያ መንግስት የሚሸፈን ይሆናል።

    የመንገዶቹ ግንባታ በሚጠናቀቅበት ወቅት እንደ ጤፍ፣ ማር እና ፍየል እንዲሁም ሌሎች የግብርና ምርቶችንም ሆነ ሌሎች ምርቶችን ካለምንም ችግር ወደ ገበያ ለማውጣት ያስችላሉ። በተጨማሪም ከዚህ በፊት በአካባቢው የነበረውን የተቀላጠፈ የትራንስፖርት ችግር በመቅረፍ የአካባቢው ህብረተሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ ወደ ፈለገው ቦታ የሚንቀሳቀስበትን ሁኔታ ያመቻቻሉ።

    እነዚህ መንገዶች በአገሪቱ ካለው ማ ኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ እንዲሁም መንግሥት ከያዘው የድህነትና የኋላቀርነት ቅነሳ ስትራቴጂ አንጻር ከፍተኛ አስተዋጽዖ እንደሚያበረክቱ ይታመናል። የመንገዶቹ ግንባታ በሚጠናቀቅበት ወቅት ከዚህ በፊት በአካባቢው የነበረውን የትራንስፖርት ችግር በመቅረፍ የአካባቢው ህብረተሰብ በቀላሉ ወደ ፈለገው ቦታ የሚንቀሳቀስበትን ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር ከመሆኑም ባሻገር ፣ በኢንቨስትመንት የተሰማሩ ባለሃብቶች ያመረቱትን ምርት ወደ ገበያ ለማውጣት እንዲችሉና ሌሎች ባለሃብቶችም በአካባቢው ኢንቨስት ለማድረግ ተነሳሽነትን ከመፍጠር አኳያ የዚህ መንገድ መገንባት ጉልህ ሚና ይጫወታል።

    ከዚህም በተጨማሪ በአካባቢው የስራ ዕድል እንዲፈጠር በማስቻል ፣ በአካባቢው የሚገኙ ትንንሽ መንደሮች በከተማ ደረጃ እንዲስፋፉና እንዲያድጉ ከማድረግ እንዲሁም የጤና ፣ የትምህርት እና ሌሎች የማህበራዊ አገልግሎት ተቋማት በሰፊው እንዲስፋፉ ከማድረግ አንፃር ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያበረክታሉ ተብሎ ይታመናል። ስለሆነም የመንገድ ኘሮጀክቶቹ በተያዘላቸው የጊዜ ገደብ እንዲጠናቀቁ በአካባቢው የሚገኙ የመስተዳድር አካላትና፣ የክልሉ ነዋሪዎች ከፍተኛ ትብብር እንዲያደርጉ የኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን ያሳስባል።

    የኮንትራት ስምምነቱን የፈረሙት በኢመባ በኩል አቶ ሃብታሙ ተገኝ የኢትዮጵያ መንገዶች ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሲሆኑ በተቋራጮቹ የሥራ ተቋራጮቹ ሥራ አስኪያጆች እና ተወካዮቻቸው ናቸው።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን (ኢመባ)

    የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን

    Semonegna
    Keymaster

    የኢፌዴሪ መንግስት የፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመን የመልቀቂያ ጥያቄ ከተቀበለ ከሀያ ዓመታት በላይ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ስር በአምባሳደርነትና የኢትዮጵያ ተጠሪነት ያገለገሉት አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ ፕሬዝዳንት ሆነው እንደሚሾሙ የተለያዩ የዜና ምንጮች ዘግበዋል።

    አዲስ አባባ – ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ (ዶ/ር) ሀሙስ ጥቅምት 15 ቀን 2011 ዓ.ም. በሚውለው የሕዝብ ተወካዮችና የፌዴሬሽን ምክር ቤቶች 2ኛ አስቸኳይ መደበኛ ስብሰባ የሥራ መልቀቂያ እንደሚያቀርቡ ይጠበቃል። የአስቸኳይ ስብሰባው ዋና አጀንዳ የፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመን የሥራ መልቀቂያ መቀበልና አዲስ ፕሬዚዳንት መምረጥ እንደሚሆን ተገልጿል።

    ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ (ዶ/ር) የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ሆነው የተመረጡት መስከረም 27 ቀን 2006 ዓ.ም ሲሆን ሶስተኛው ፕሬዚዳንትም (ከዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ እና አቶ ግርማ ወልደጊዮርጊስ ቀጥሎ) ናቸው።

    ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ ወለጋ አርጆ ከተማ በ1949 ዓ.ም ነው የተወለዱት፤ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን በቻይና የፖለቲካ ኢኮኖሚ ፍልስፍና፣ ሁለተኛውን በህግና ዲፕሎማሲ ከአሜሪካ፣ 3ኛ ዲግሪያቸውን ከቻይና ቤጂንግ ዩኒቨርስቲ በህግ አግኝተዋል።

    ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ በጃፓንና በቻይና የኢትዮጵያ ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ሆነው ያገለገሉ ሲሆን፤ ከ1993-1994 ዓ.ም የግብርና ሚኒስትር፣ ከጥቅምት 1994-1998 ዓ.ም የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ሆነውም አገልግለዋል። በፕሬዝዳንትነት እስከተመረጡበት ጊዜም በቱርክ የኢትዮጵያ ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ነበሩ።

    ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ የተለያዩ የምርምር ሥራዎችን በተለያዩ መስኮች ያከናወኑና በመምህርነትም ያገለገሉ ሲሆን ከአገር ውስጥ አማርኛና ኦሮምኛ ከውጭ ደግሞ እንግሊዝኛ፣ ቻይንኛና ፈረንሳይኛ ቋንቋዎችን መናገርና መጻፍ ይችላሉ።

    በኢፌዴሪ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 70 ንዑስ አንቀጽ 4 መሰረት የአንድ ፕሬዝዳንት አገልግሎት ጊዜ ስድስት ዓመት ሲሆን፥ አንድ ግለሰብ ከሁለት ጊዜ በላይ በርዕሰ ብሔርነት ሊመረጥ እንደማይችል ይደነግጋል። ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ የመጀመሪያ ቨፕሬዝዳትነት አምስተኛ ዓመታቸው ነው።

    ከዚህ ጋር በተያያዘ የተለያዩ የሀገር ውስጥ ሚዲያዎች ኢትዮጵያን ከሀያ ዓመታት በላይ በሚኒስቴርነትና በአምባሳደርነት ያጋለገሉት አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ ቀጣዩ የኢትዮጵያ ርዕሰ ብሔር (ፕሬዝዳንት) ይሆናሉ ብለው ቅድመ ግምታቸውን እየሰጡ ነው። በዚህም አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ ፕሬዝዳንት ሆነው ከተመረጡ በኢትዮጵያ ታሪክ የመጀመሪያዋ እንስት ፕሬዝዳንት ይሆናሉ ማለት ነው።

    ለመሆኑ አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ ማን ናቸው?

    ተወልደው ያደጉት አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ሲሆን የመጀመሪያና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን የተከታተሉት በሊሴ ገብረማርያም ትምህርት ቤት ነው። አራት ሴት ልጆች ለነበሯቸው ወላጆቻቸው የመጀመሪያ ልጅ የሆኑት ሳህለወርቅ ዘውዴ ገና በ17 ዓመታቸው ነጻ የትምህርት ዕደል አግኝትው ወደ ፈረንሳይ በማቅናት ሞንትፔልየር (Montpellier) በምትባለው የፈረንሳይ ከተማ በሚገኘው ዮኒቨርሲቲ ኦፍ ሞንትፔልየር (University of Montpellier) የተፈጥሮ ሳይንስን አጥንተዋል። በሀገረ ፈረንሳይ ለዘጠኝ ዓመታት ከቆዩ በኋላ ወደ ኢትዮጵይ በመመለስ በትምህርት ሚኒስቴር ውስጥ የሕዝብ ግንኙነት ክፍልን ማገልገል ጀመሩ። ቆይተውም የሕዝብ ግንኙነት ክፍሉን በበላይነት መርተዋል። ከዚያም ወደ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በመዘዋወር በተለያዩ የሥራ ኃላፊነቶች አገልግለዋል።

    ወሮ ሳህለወርቅ ዘውዴ በአምባሳደርነት ለመሾም ከአምባሳደር ዮዲት እምሩ ቀጥሎ ሁለተኛዋ እንስት ናቸው። በመጀመሪያ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሆነው የተሾሙትም ሴኔጋል ሲሆን የአምባሳደርነት ስልጣናቸውም ሴኔጋልን ጨምሮ ማሊን፣ ኬፕ ቨርዴን፣ ጊዚ ቢሳውን፣ ጋምብያን እና ጊኒን (እ.ኤ.አ 1989–1993) ያጠቃልል ነበር። ቀጥሎም እ.ኤ.አ 1983–2002 በጅቡቲ የኢትዮጵያ አምባሳደርና በኢጋድ (IGAD) የኢትዮጵያ ተጠሪ ሆነው አገልግለዋል። እ.ኤ.አ ከ2002 ጀምሮ እስከ 2006 ድረሰ በፈረንሳይ (ሞሮኮን ጨምሮ) የኢትዮጵያ አምባሳደርና በዩኔስኮ (UNESCO) የኢትዮጵያ ተጠሪ ሆነው አገልግለዋል። እ.ኤ.አ ከ2006 ጀምሮ እስከ 2009 ድረስ በአፍሪካ ህብረት (AU) እና በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (UNECA) የኢትዮጵያ ተጠሪ ሆነው ሀገራቸውን አገልግለዋል።

    ከሀያ ዓመታት በላይ በተለያዩ ሀገራትና ዓለማቀፋዊ ድርጅቶች የኢትዮጵያ አምባሳደርና ተጠሪ በመሆን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤትን ያገለገሉት አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ እ.ኤ.አ በ2009 የተበባሩት መንግስታት ድርጅትን (ተመድ) በመቀላቀል የድርጅቱ በመካከለኛው አፍሪካ ሪፑብሊክ የተቀናጀ ሰላም ግንባታ መሪ (Head BINUCA) በመሆን ማገልገል ጀመሩ። ይህ አገልግሎታቸውም ወደ ሚቀጥለው ኃላፊነት አሸጋግሯቸው እ.ኤ.አ በ2011 ዓም የዚያን ጊዜ የተመድ ጠቅላይ-ጸሀፊ ባን ኪ-ሙን (Ban Ki-moon) አዲስ ለተቋቃመው በናይሮቢ የተመድ ጽህፈት ቤት (UNON) የመጀመሪያዋ ጠቅላይ-መሪ አድርገው ሾማቸው። በዚያም ለሰባት ዓመታት ካገለገሉ በኋላ እ.ኤ.አ በሰኔ ወር 2010 የአሁኑ የተመድ ጠቅላይ-ጸሀፊ አንቶንዮ ጉቴሬስ (António Guterres) አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴን በተመድ ጠቅላይ-መሪ ስር (Under-Secretary-General) የአፍሪካ ህብረት ልዩ ተጠሪ (UN’s Special Representative to the AU) እና በአፍሪካ ህብረት ውስጥ የተመድ ጽህፈት ቤት ዋና ኃላፊ (Head of UNOAU) አድርገው ሾሟቸው እስካሁን ድረስ በዚሁ ሹመታቸው እያገለገሉ ይገኛሉ።

    አምባሳደር ሳህለወርቅ ዘውዴ ባለትዳርና የሁለት ወንድ ልጆች እናት ናቸው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ሳህለወርቅ ዘውዴ


    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አባባ – የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ትረስት ፈንድ ጥቅምት 12 ቀን 2011 ዓ.ም በይፋ ገንዘብ መሰብሰብ መጀመሩን የጠቅላይ ሚኒስትር ልዩ ጽህፈት ቤት አስታወቀ።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ከሁለት ወር በፊት ለኢትዮጵያ ዳያስፖራ ማህበረሰብ የትረስት ፈንዱ እንዲቋቋም ንቁ ተሳትፎ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበው እንደነበረ ይታወሳል።

    በይፋ የተቋቋመው ትረስት ፈንድ ጥቅምት 12 ቀን ገንዘብ መሰብሰብ መጀመሩን ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ገልጸዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ትረስት ፈንድ አማካሪ ምክር ቤት ተቋቁሞ በይፋ ሥራ እንዲጀምር ላደረጉት ትጋትና ጥረት አባላቱን በኢትዮጵያ ሕዝብ ስም አመስግነዋል።

    በአሁኑ ወቅት በትረስት ፈንዱ ገንዘብ የማሰባሰብ ሥራ የመጀመሪያ ደረጃ ላይ እንዳለና ከዚህም በኋላ ብዙ ሥራ መሥራት እንደሚገባ ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ የገለጹት።

    ———————————————-

    ———————————————-

    የትረስት ፈንድ አማካሪ ምክር ቤቱ የፈንዱን አቅምና ውጤታማነት ለማሻሻል በትጋት መሥራት እንዳለበትም ዶክተር አብይ ተናግረዋል።

    የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ማህበረሰብ የሚሰጡትን የተወሰነ ገንዝብ በአንድ ወይም በሁለት ጊዜ ጠቅልለው በመክፈል በጣም ወሳኝ ለሚባሉ ፕሮጀክቶች የሚያስፈልገውን ድጋፍ እንዲያፋጥኑም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠይቀዋል።

    በቀን ከአንድ ዶላር በላይ መስጠት ለሚችሉ ዜጎች ድጋፋቸውን በፍጥነት እንዲያድርጉና ዓለም አቀፉ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ማኅበረሰብ ከትረስት ፈንድ ምክር ቤቱ ጋር ትብብራቸውን እንዲያደርጉ ዶክተር አብይ ጥሪያቸውን አቅርበዋል።

    የኢትዮጵያ የዳያስፖራ ትረስት ፈንድ የዳይሬክተሮች ቦርድ የተመረጡ ሲሆን ስም ዝርዝራቸው በቅርቡ ይፋ እንደሚደረግም መጠቆማቸውን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የላከው መግለጫ ያስረዳል።

    ፈንዱ የዳያስፖራውን ተሳትፎ ለማቀናጀትና የልገሳውን ገንዘብ ለማሰባሰብ የሚያስችል እንደሆነ የተገለጸ ሲሆን የባንክ ሒሳብ ቁጥሩም የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 1000255726725 (አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ) ነው። ከዚህ የባንክ የሒሳብ ቁጥር በተጨማሪ ተቋሙ በኢንተርኔትም ገንዘብ እንደሚያሰባስብና ኦፊሴላዊ ድረ ገጹም “https://www.ethiopiatrustfund.org” እንደሆነ ክስር በተመለከተው ጋዜጣዊ መግለጫ አሳውቋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ በተለያዩ አገራት የሚገኙ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን የተሻለች ኢትዮጵያን ለመገንባት በሚደረገው ጥረት የበኩላቸውን እንዲወጡ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርበው ባደረጉት ንግግር ጥሪ ማቅረባቸው ይታወቃል።

    በውጭ አገራት የሚገኙ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን በቀን ቢያንስ 1 የአሜሪካ ዶላር በመለገስ ለተለያዩ የልማት ሥራዎች ድጋፍ እንዲያደርጉ መጠየቃቸው የሚታወስ ነው።

    የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ትረስት ፈንድ ተቋም ምክር ሰጪ ካውንስል መግለጫ (ጥቅምት 10 ቀን 2011 ዓ.ም)

    የኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ዳያስፖራ ፈንድ ተቋም ሰኞ ጥቅምት 12 ቀን 2011 ዓ.ም (October 22, 2018) ለሕዝብ መዋጮ መሰብሰቢያ ይከፈታል።

    የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ፈንድ ተቋም ምክር ሰጪ ካውንስል (ኢዲቲኤፍ) ሰኞ ጥቅምት 12 ቀን 2011 ዓ.ም (October 22, 2018) ለሕዝብ መዋጮ መሰብሰቢያ ያዘጋጀዉን ዝግጅት ለሕዝብ ይፋ አድርጎ ሥራዉን በኦፊሴላዊ ድረ-ገጽ https://www.ethiopiatrustfund.org እንደሚጀምር በደስታ ያስታዉቃል።

    ባለፉት ሳምንታት ካውንስሉ የዲያስፖራ ፈንዱን ሕጋዊና መንግስታዊ ደንቦችን በተከተለ መንገድ ፈንዱን ለመመስረት በትጋት ሠርቷል።

    የፈንዱ ካውንስል ምክር ቤት በዓለም ያሉ ዲያስፖራ ኢትዮጵያውያን ክቡር ጠ/ሚ ዶ/ር አብይ አህመድ በቀን 1 ዶላር ለህዝብ አርዳታ አዋጡ ያሉትን ጥሪ ተመልከቶ መዋጮ ለመስጠትና ፈንዱን በስራ ላይ ለማዋል ከፍ ያለ ጉጉት አንዳላቸው ይገነዘባል።

    ይህን ፍላጎት ለሟሟላትና ፈንዱን በሥነ ስርዓት ሥራ ማስጀመር ምክር ቤቱ ለትርፍ ያልተቋቋመ የበጎ አድራጎት ድርጅት ማቋቋም የባንክ ሂሳብ ቁጥር መክፈት ከኢንተርኔት ክፍያ ስርዓቶች እና ሌሎች የፋይናንስ መድረኮችን ጋር መደራደር አና የተለያዩ ደንቦችን ሟላትና አስተዳደራዊ እና የአፈፃፀም ሂደቶችን ለመቆጣጠር እና ግልጽነትን ለማረጋገጥ ምክር ቤቱ እነዚህን ሥራዎች በፍጥነት መወጣት ችሏል።

    ካውንስሉ ዓለምአቀፍ ዲያስፖራዎች ማኅበረሰቦች ለፈንዱ ላሳዩት መታገስና የማያወላዉል ድጋፍ ከፍተኛ ምስጋናዉን ያቀርባል።

    ካውንስሉ የኢትዮጵያ ዲያስፖራን የኢትዮጵያ ወዳጆች እና ሌሎች ነፃነት ዲሞክራሲ ሰብአዊ መብቶችን እና መልካም አስተዳደርን በኢትዮጵያ ማበልፀግ የሚፈልጉን ሁሉ በቀን 1 ዶላር መዋጮቻቸዉን በአንድ ጊዜ በጠቅላላው 365 የአሜሪካን ዶላር እንዲከፍሉ ባክብሮት ይጠይቃል። ይህንም በማድረግ አስፈላጊ ፕሮጀክቶችን ባፋጣኝ ለማስጀመር ይቻላል።

    ስለ ፈንዱ ለመማር እና መዋጮ ለማድረግ ወድዚህ ድህረ ገፅ ይሂዱ (ይጫኑ) https://www.ethiopiatrustfund.org/

    ልዩ ማስታወሻ – የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ትረስት ፈንድ በሚል ስም አንዳንድ በግል የተደራጁ ሰዎች ገንዘብ ለመሰብሰብ ጥረት እንደሚያደርጉ የፈንዱ ምክር ቤት ይረዳል። ነገር ግን ኦፊሴላዊ የሆነው በክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ እ.ኤ.አ. ነሐሴ 9, 2018 በካውንስሉ የተቋቋመው ኤድቲኤ (EDTF) ብቸኛና መደበኛ በሕግ የታወቀው ነው።

    የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ትረስት ፈንድ

    Semonegna
    Keymaster

    በኢትዮጵያውያን የኪነ ጥበብ አድናቂዎች ዘንድ ተወዳጅነት እያተረፈ የመጣው ለዛ የአድማጮች ምርጫ ሽልማት ዘንድሮ ለስምንተኛ ጊዜ ጥቅምት 13 ቀን 2011 ዓ.ም በሂልተን ሆቴል፣ አዲስ አበባ፣ እጅግ በደመቀ ሁኔታ ተከናውኗል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – በሀገራችን የሙዚቃ ታሪክ እጅግ መቀዛቀዝ፣ የሙዚቃ አልበምም ህትመት መፍዘዝ፣ ፊልም ሠሪዎችም ሥራዎቻችውን ተመልካቾች ፊታቸውን ባዞሩባቸው በዚያ ወቅት እንደ አንድ የኪነጥበብ አባልና የሚዲያ ባለሙያ አቅማቸው በፈቀደ የበኩላቸውን አስተዋጽዖ ለማበርከት፣ እንዲሁም አድማጭ ተመልካቹን ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ለማነቃቃት በማሰብ ነበር ጋዜጠኛ ብርሀኑ ድጋፌ እና ባልደረቦቹ በሸገር ኤፍ ኤም 102.1 ሬድዮ ላይ “ለዛ የአድማጮች ምርጫ ሽልማት” ሥነ ስርዓትን የየጀመሩት።

    በእርግጥ ኪነ ጥበብና ኢትዮጵያ ሀገራችን በባህላዊውም ሆነ በዘመናዊው መንገድ እጅግ ብዙ ዓመታትን ያስቆጠረ ቁርኝት ቢኖራቸውም ቅሉ የኪነ ጥበብ ሙያዉን እንደተከበረ ሙያ ባለሙያዉንም የተከበረ ሙያ እንዳለው ቆጥሮ ወቅት ጠብቆ በተገደበ የጊዜ ኡደት ለሙያውና ለባለሙያው ተገቢውን ዕውቅና፣ ብሎም ክብር የሚሰጥ ቋሚ ተቋም ባለመኖሩ ያለመኖሩን በማስገንዘብ የሥነ ስርዓቱ ሀሳብ ጠንሳሾች “ለምን እኛ የቻልነውን አናደርግም?” በሚል ነበር የኪነ ጥበብ ሰዎችን በዓመት አንድ ጊዜ እያሰባሰቡ ለማወያየት፣ በዓመቱ በሙያውና በሙያቸው ጉልህ አስተዋጽዖ ያደረጉትን “በጎ ሥራ ሠርታችኋል! ይበል!” ለማለት ለዛ የኤድማጮች ምርጫ ሽልማትን በ2003 ዓ.ም የጀመሩት።




    በ2003 ዓ.ም በተደረገው የመጀመሪያ ሽልማት ‘የዓመቱ ምርጥ ነጠላ ዜማ’፣ ‘ምርጥ ተዋናይት’፣ ‘የዓመቱ ምርጥ ተዋናይ’፣ ‘የዓመቱ ምርጥ ፊልም’ እና ‘የዓመቱ ምርጥ አልበም’ በሚሉ አምስት ዘርፎች (ዘውጎች) ኢትዮጵያውያን የኪነ ጠበብ ሰዎች ተመርጠው የተሸለሙ ሲሆን ሽልማቱም ያገኙትም ከያኒት ዘሪቱ ከበደ “አርቴፍሻል” በሚለው ነጠላ ሙዚቃዋ፣ ተዋናይት ሰሃር አብዱልከሪም “ያንቺው ሌባ” በተሰኘ ፊቸር ፊልም ላይ ባሳየችው ትወና፣ ጋሽ አበበ ባልቻ “ሄሮሺማ” በተሰኘ ፊቸር ፊልም ላይ ባሳየው ትወና፣ “ሄሮሺማ” ፊቸር ፊልም በምርጥ በፊልምነት፣ እንዲሁም ከያኒ ናትናኤል አያሌው (ናቲ ማን) በመጀመሪያው አልበሙ በአምስቱ የተዘረዘሩት ዘርፎች አሸናፊዎች ሆነው የሥነ ስርዓቱ የበኩር ተሸላሚዎች ሆኑ።

    በዚህ መልኩ የተጀመረው ለዛ የአድማጮች ምርጫ በየዓመቱ ከጥቅምት ወር ጀምሮ እስከ ሃምሌ ድረስ የሚወጡ የኪነ ጥበብ ሰዎችንና ሥራዎችን በአድማጮች ምርጫ አወዳድሮ ዕውቅና እየሰጠ፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ ተሳታፊዎችን እያበዛ፣ በባለሙያዉም፣ በመራጭነት በሚሳተፈውም ይሁን በየበይ ተመልካችነት በሚከታተለው ኢትዮጵያዊ ዘንድም ተወዳጅነት እያተረፈ ዘንድሮ ለስምንተኛ ጊዜ ጥቅምት 13 ቀን 2011 ዓ.ም በሂልተን ሆቴል፣ አዲስ አበባ፣ እጅግ በደመቀ ሁኔታ ተከናውኗል። ከሁለት ወራት በፊት በተካሔደው ዘጠነኛው አዲስ የሙዚቃ ፌቲቫል ላይ የዓመቱ ምርጥ አርቲስት ተብሎ የተሸለመው ድምጻዊ ሮፍናን ኑሪ በዚህ ሥነ ስርዓትም ላይ ተመሳሳይ ሽልማት፣ ሌሎች ሁለት ሽልማቶችን ጨምሮ አሸንፏል። በስምንተኛው ለዛ የአድማጮች ምርጫ ሽልማት፦

    ● ምርጥ ነጠላ ዜማ፦ “ጨረቃ” (ሮፍናን ኑሪ)፣
    ● ምርጥ አዲስ ድምፃዊ፦ ሮፍናን ኑሪ (“ነፀብራቅ” በተባለው የሙዚቃ አልበሙ)
    ● ምርጥ የሙዚቃ አልበም፦ ነፀብራቅ (ሮፍናን ኑሪ)
    ● ምርጥ የሙዚቃ ክሊፕ፦- የመጀመርያዬ (ናትናኤል አያሌው/ናቲ ማን):-
    ● ምርጥ ተዋናይት፦ አዚዛ አህመድ “ትህትና” በተሰኘ ፊቸር ፊልም ላይ ባሳየችው ትወና፣
    ● ምርጥ ተዋናይ፦ አለማየው ታደሰ “ድንግሉ” በተሰኘ ፊቸር ፊልም ላይ ባሳየው ትወና፣
    ● ምርጥ ፊልም፦ “ድንግሉ”
    ● ምርጥ ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማ፦ ምን ልታዘዝ?

    አሸናፊ ሆነው ተሸልመዋል። በዚህ ሥነ ስርዓት ላይ እጅግ ለበርካታ ሙዚቀኞች የዘፈን ግጥም በመስጠት በኢትዮጵያ ሙዚቃ ውስጥ ስሙ እጅጉን ጎልቶ የሚታወቀው የሙዚቃ ግጥም ገጣሚ (lyricist) ይልማ ገብረአብ “የ2010 ዓ.ም የኪነ ጥበባ በለውለታ” ሆኖ ልዩ የክብር ሽልማት ተሸልሟል። ገጣሚ ይልማ ገብረ አብ ከአንድ ሺህ በላይ የሙዚቃ ግጥሞችን ጽፎ ለተለያዩ ድምጻውያን አበርክቷል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ለዛ የአድማጮች ምርጫ


    Semonegna
    Keymaster

    የአሜሪካ ድምፅ ለባለሞያዎቹ ሥልጠና ሲሰጥ ያገር ውስጥ ጋዜጠኞችንም ቢያካትት ፍላጎታቸው መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ስልጠና ለመስጠት አዲስ አበባ ከሚገኙ የአሜሪካ ድምጽ ጋዜጠኞች ጋር በተገናኙበት ጊዜ አስታውቀዋል።

    አዲስ አበባ – የአሜሪካ ድምፅ ለባለሞያዎቹ ሥልጠና ሲሰጥ ያገር ውስጥ ጋዜጠኞችንም ቢያካትት ፍላጎታቸው መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) አስታውቀዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ የአሜሪካ ድምፅ የአፍሪካ ዲቪዥን ዳይሬክተር አቶ ንጉሤ መንገሻን እና የአፍሪካ ቀንድ ማኔጂንግ ኤዲተር ጋዜጠኛ ትዝታ በላቸውን በቢሯቸው ተቀብለው አነጋግረዋል።

    የአሜሪካ ድምፅ በኢትዮጵያና በጎረቤት ሃገሮች ለሚገኙ ዘጋቢዎቹ እስካለፈው ዓርብ የቆየ የአንድ ሣምንት ሥልጠና አዲስ አበባ ላይ ሰጥቷል።

    በኢሕአዴግ መንግሥትና በአሜሪካ ድምፅ መካከል ላለፉት 27 ዓመታት ከዘለቀ ውጣ ውረድ ያልተለየው ግንኙነት በኋላ አንድ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር የጣቢያውን ኃላፊዎች ተቀብሎ ሲያነጋግር ይህ የመጀመሪያው ነው።

    ለተጨማሪ መረጃ የተያያዘውን የድምፅ ፋይል ያዳምጡ። ዘጋቢ እስክንድር ፍሬው ለአሜሪካ ድምጽ የአማርኛ ዝግጅት ክፍል

    ጋዜጠኛ ንጉሤ መንገሻ
    ትውልደ ኢትዮጵያዊው ንጉሤ መንገሻ ከ2014 (እ.ኤ.አ) ጀምሮ የአሜሪካ ድምጽ የአፍሪካ ዲቪዥን ዳይሬክተር (Africa Division Director) ሆኖ እያገለገለ ይገኛል። ጋዜጠኛ ንጉሤ ወደ አሜሪካ የመጣው እ.ኤ.አ በ1981 ዓም ሲሆን በ1982 የአሜሪካ ድምጽን በሲኒየር ኤዲተርነት ተቀላቅሏል። ቀጠሎም የአሜሪካ ድምጽ የመካከለኛው አፍሪካ ሰርቪስ ቺፍ (Service Chief)፣ የአፍሪካ ዲቪዥን ፕሮግራም ማናጀር (Africa Division Program Manager)፣ አሁን ደግሞ ሆኖ የአፍሪካ ዲቪዥን ዳይሬክተር አገልግሏል/እያገለገለ ይገኛል።

    ጋዜጠኛ ትዝታ በላቸው
    በ ኤሉባቡር ዞን (የቀድሞው ኤሉባቡር ክፍለሀገር) ያዮ ወረዳ ውስጥ የተወለደችው ጋዜጠኛ ትዝታ በላቸው ወደ አሜሪካ የመጣችው እ.ኤ.አ በ1973 ሲሆን፥ ትምህርቷን ዋሽንግተን ዲሲ በሚገኘው ሐዋርድ ዩኒቨርሲቲ (Howard University) ተከታትላ የአሜሪካ ድምጽን የተቀላቀለችው የአማርኛ ዝግጅት ክፍሉ በተመሠረተ በሁለት ዓመቱ (እ.ኤ.አ በ1984) ነበር። በአሜሪካ ድምጽ (የአማርኛ ዝግጅት ክፍሉን ጨምሮ) በተለያዩ የጋዜጠኝነት ሙያ እርከኖች ያገለገለች ሲሆን በአሁኑ ወቅት የአፍሪካ ቀንድ ማኔጂንግ ኤዲተር (Horn of Africa Managing Director) ሆና እየሠራች ነው።

    የአሜሪካ ድምፅ

    Semonegna
    Keymaster

    በምንም ተአምር ለኢትዮያ ሕዝብ ውሸት አልነግርም። ዕድሜዬም፤ ሥነ ምግባሬም አይፈቅድልኝም። ኢንጂነር ስመኘው በቀለ ሕይወታቸው ያለፈው በሰው በደረሰባቸው ጥቃት አይደለም ― ኮሚሽነር ጄነራል ዘይኑ ጀማል

    (ኤስ.ቢ.ኤስ ሬድዮ)–በሜልበርን ከተማ (አውስትራልያ) ተቀማጭነቱን ያደረገው ኤስ.ቢ.ኤስ ሬድዮ (SBS Radio) የአማርኛ ዝግጅት ክፍል ጋዜጠኛ ካሣሁን ሰቦቃ ኢትዮጵያ በነበረበት ጊዜ ከኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን፤ ኮሚሽነር ጄነራል ዘይኑ ጀማል ጋር ቆይታ አድርጎ ነበር። የተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮችን እያነሳም ቃለ ምልልስ አድርጎላቸው ነበር። ቃለ ምልልሱ የተደደረገው በሐዋሳ ከተማ ነበር – የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ደኢሕዴን) ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል ሆነው በተመረጡ ማግስት።

    ዋነኛ ርዕሰ ነገራቸውም ሕግና ሥርዓትን በአገር አቀፍ ደረጃ ማስፈንና ተዓማኒ የምርመራ ውጤቶችን በወቅቱ ለሕዝብ ይፋ ማድረግ ናቸው።

    አቶ ዘይኑ፤ እንደ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጄኔራልነታቸው የሕግ የበላይነት ለዲሞክራሲ እስትንፋስ መሆኑን ጠንቅቀው ያውቃሉ። ለተጀመረው የለውጥ ሂደት እጅጉን ቀናዒ ናቸው።

    “የሕግ የበላይነት ሳይከበር ዲሞክራሲ የሚታሰብ አይደለም። የዲሞክራሲ፣ የሰላምና የነፃነት ሀ ሁ የሕግ የበላይነት ነው” ይላሉ። ይህ ፅንሰ ሃሳብ ነው። ግብሩ የፖሊስ ኃይላቸው ፖለቲካዊ ሁከትን የመግታት ደረጃ ላይ አለመድረሱ ነው።

    የጸጥታ ሥራ ያለ ሕዝብ ትብብር ዕውን እንደማይሆን ስለሚረዱም ፤ ሕዝቡ ከጸጥታ ኃይሉ ጎን ቆሞ ሰላሙን እንዲያስከብር፤ ዲሞክራሲያዊ ሂደቱን እንዲታደግ ጥሪ ያቀርባሉ።

    የሁከት ምንጮችን በሰላማዊ መንገድ ለመታገል ወደ አገር ውስጥ በገቡ ተፎካካሪ ድርጅቶች ላይ በጅምላ ማላከኩ ተገቢ አይደለም በማለትም ያስገነዝባሉ።

    በሳቸው አተያይ ለአገረ ኢትዮጵያ የጸጥታ መደፍረስ ዋነኛ አስባቦች፡ –
    • የሕግ የበላይነትን ጠንቅቆ ካለመረዳት የሚከሰቱ የእርስ በርስ ግችቶች፣
    • ከነፃነት መግለጫ መንገዶች ጋር ተያያዥ የሆኑ የሕግ ግድፈቶችና
    • ጥቅማቸው የተነካባቸውና ያኮረፉ ኃይላት ድርጊቶች እንደሆኑ በዋቤነት ይነቅሳሉ።

    የፌዴራል ፖሊስ የምርመራ ውጤች መጓተትን አስመልክተው “ጥፍር እየነቀልን ምርመራ ስለማናካሂድ ማስረጃዎችን ለማሰባሰብ ጊዜ ይወስዳል” ባይ ናቸው፤ የፖሊስ ኃይሉ አቅም ደረጃም ታክሎበት።

    የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ፕሮጀክት ሥራ አስኪያጅ የነበሩት ኢንጂነር ስመኘው በቀለን አሟሟት አስመልክቶ መግለጫቸው በሕዝብ ዘንድ ሙሉ አመኔታን እንዳላሳደረ ላነሳንላቸው ጥያቄ ሲመልሱ፤

    በምንም ተአምር ለኢትዮያ ሕዝብ ውሸት አልነግርም። ዕድሜዬም፤ ሥነ ምግባሬም አይፈቅድልኝም። ኢንጂነር ስመኘው ሕይወታቸው ያለፈው በሰው በደረሰባቸው ጥቃት አይደለም

    በማለት በእርግጠኛነት ተናግረዋል።

    ለወደመው ንብረት፤ ለባከነው ሐብትና ከኢንጂነሩ ሞት ጀርባ ተጠያቂ ስለሚሆኑ አካላት ሲመልሱ፤ “ከኢንጂነር ስመኘው ሞት ጀርባ ያሉትን ፖሊስ ለፍርድ ያቀርባል። ያ እስከሚሆን ድረስ ፖሊስ ዕንቅልፍ አይኖረውም” ብለዋል።

    አንዱ አንኳር መልዕክታቸው “አንድም ሰው ቢሆን ጠብመንጃ ይዘናል ብለን ተኩሰን መግደል አንፈልግም። ግድያ፣ እስር፣ እንግልት ይበቃናል። ለዘመናት አይተነዋል። ለዘመናት ተሰቃይተንበታል። እዚህ ጋር ሊቆም ይገባል” የሚል ነው።

    ኮሚሽነር ጄነራል ዘይኑ ጀማል ከጋዜጠኛ ካሣሁን ሰቦቃ ጋር ያደረጉትን ቃለ ምልልስ ከተያያዘው የድምፅ ፋይል ያድምጡ።

    ዘጋቢ ካሣሁን ሰቦቃ ለኤስ.ቢ.ኤስ ሬድዮ የአማርኛ ዝግጅት ክፍል

    ዘይኑ ጀማል

    Semonegna
    Keymaster

    ኢታካ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካ የተለያዩ የሴት አልባሳት በማምረት ወደ ተለያዩ የአውሮፓ አገራት መላክ መጀመሩን የፋብሪካው ዋና ሥራ አስኪያጅ ሚስተር ቴድርኮ ፍራንቦኒ (Federico Fraboni) ተናግረዋል።

    መቀሌ (ኢዜአ)–በጣልያኑ ግዙፍ ኩባንያ ካልዜዶንያ ግሩፕ በ15 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ወጪ የተገነባው ኢታካ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካ ተመረቀ።

    በመቀሌ ልዩ ስሙ አሸጎዳ በተባለ አካባቢ የተገነባው ፋብሪካ በወር 22 ሚሊዮን ብር ዋጋ ያላቸው አልባሳትን ለዓለም ገበያ የማቅረብ አቅም እንዳለው በምረቃ ሥነ ስርዓቱ ላይ ተመልክቷል።

    ፋብሪካውን መርቀው የከፈቱት የንግድና ኢንዱስቱሪ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር መብራህቱ መለሰ በክልሉ ከተማ ልማት ንግድና ኢንዳስትሪ ቢሮ የኢንቨስትመንት ጽህፈት ቤት ዳይሬክተር አቶ ሃፍቶም ፋንታሁነኝ እና በኢትዮጵያ የጣሊያን ኤምባሲ ተወካይ ሚስተር ፕትሮ ፓናሮላ ናቸው።




    የንግድና ኢንዱስቱሪ ሚኒስትር ዴኤታው ዶ/ር መብራህቱ በዚህ ወቅት እንዳሉት በጣሊያን ባለሃብቶች ተገንብቶ ለምረቃ የበቃው ኢታካ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካ አገሪቱን ከማልማት አልፎ የኢትዮጵያዊያንን ትክክለኛ ምስል ለዓለም ያስተዋውቃል፤ ፋብሪካው ለዜጎች የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ ለአገሪቱ የኢኮኖሚ እድገት ፋይዳው የጎላ መሆኑንም ተናግረዋል።

    ለሀገሪቱ እድገት ትልቅ ድርሻ ያለውን የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ለማበረታታት ከሁሉም የመንግስት አካላት ትኩረት ሰጥቶ መሥራት እንደሚገባም ዶ/ር መብራህቱ ገልጸዋል።

    ኢታካ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካ የተለያዩ የሴት አልባሳት በማምረት ወደ ተለያዩ የአውሮፓ አገራት መላክ መጀመሩን የተናገሩት ደግሞ የፋብሪካው ዋና ሥራ አስኪያጅ ሚስተር ቴድርኮ ፍራንቦኒ (Federico Fraboni) ናቸው።

    ፋብሪካ በወር 22 ሚሊዮን ብር ዋጋ ያላቸው አልባሳት ለውጭ ገበያ እንደሚያቀርብ እና ቀደም ሲል ለሙከራ ሲያመርት መቆየቱን ገልጻው የመጀመሪያ ምርቱንም በቅርቡ ለውጭ ገበያ መላኩን ጠቁመዋል።

    ———————————————-

    ———————————————-

    በክልሉ ከተማ ልማት ንግድና ኢንዳስትሪ ቢሮ የኢንቨስትመንት ጽህፈት ቤት ዳሬክተር አቶ ሀፍቶም ፋንታሁነኝ በበኩላቸው ፋብሪካው ለአንድ ሺህ ወገኖች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ገልጸዋል።

    በመቀሌ አካባቢ ኢታካ ጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካን ጨምሮ ባለቤትነታቸው የውጭ ባለሀብቶች የሆኑ ሦስት የጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካዎች ግንባታቸው ተጠናቅቆ ወደ ምርት መሸጋገራቸውንም አቶ ሀፍቶም ተናግረዋል።

    ሌሎች አስር የአገር ውስጥ ባለሀብቶችም በዘርፉ ለመሰመራት የኢንቨስትመንት ፍቃድ ወስደው በተለያዩ የግንባታ ሂደት ላይ ይገኛሉ።

    በክልሉ የኢንዱስቱሪ ዘርፍ እንቅስቃሴ ከዚህም በላይ እንዲያደግ የመንግስት ጥረት ሊጠናከር እንደሚገባም አቶ ሀፍቶም ተናግረዋል።

    በፋብሪካው ምረቃ ላይ የተገኙት በኢትዮጵያ የጣሊያን ኤምባሲ ተወካይ ሚስተር ፕትሮ ፓናሮላ ክልሉ ሰላም የሰፈነበትና ለሥራ የተነሳሳ የሰው ኃይል ያለው መሆኑ በጣሊያን ባለሀብቶች ተመራጭ እንዲሆን አድርጎታል።

    “በኢትዮጵያና በኢጣሊያ የቆየውን የሁለቱን አገራት ታሪካዊና ልማታዊ ግንኙነት በሁሉም ዘርፍ ለማጠናከር በጋራ እንሠራለን” ብለዋል።

    በፋብሪካው የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው ዜጎች መካከል ከመቀሌ ዩኒቨርሲቲ በኢንዱስትሪያል ኢንጂነሪንግ የተመረቀው ወጣት ልኡል ኃይሉ አንዱ ነው።

    ፋብሪካው በአካባቢው በመከፈቱ እሱን ጨምሮ በርካታ ወጣት ምሩቃንን የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ማድረጉን ተናግሯል።

    “ኢታካ የጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ፋብሪካ ወደምርት ሥራ በመግባቱ የሥራ እድል አግኝቺያለሁ” ያለው ደግሞ ወጣት አወጣሀኝ አለነ ነው።

    በምረቃ ስነ ስርዓቱ ላይ ከጣሊያን አገርና ከኢትዮጵያ የመጡ ባለሀብቶችና ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)

    ኢታካ

Viewing 15 results - 676 through 690 (of 730 total)