Search Results for 'ፓለቲካ'

Home Forums Search Search Results for 'ፓለቲካ'

Viewing 8 results - 16 through 23 (of 23 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    “ሀገራችንን ኢትዮጵያን አጣብቆ የያዘውን መንግሥታዊ ኃይል ቢዳከም፣ እነዚህ የታሪክም የፓለቲካ መሠረት ያላቸው ልዩ ልዩ ቅራኔዎች በየቦታው ቢፈነዱ፣ በሕዝብ መካከል የእርስ በእርስ ግጭቶች ቢበራከቱ በብዙ አቅጣጫና ውስብስብ የብሄር ቅራኔዎች፣ ሌሎች ፓለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና፣ ማኅበራዊ ችግሮች የተጠመደች ሀገራችንና የኢትዮጵያ ሕዝብ ወዴት ሊወስዱ እንደሚችሉ ከግምት ማስገባት አስፈላጊና ወሳኝ ይሆናል።”

    ሳይቃጠል በቅጠል
    በጋራ ሀገራችን ላይ ያጠላውን የመበታተንና የሕዝብ ለሕዝብ እልቂት ለመቀልበስ የመፍትሄዎች አካል እንሁን!
    (ነአምን ዘለቀ)

    በሀገር ውስጥ ለምትገኙ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ በሙሉ፣ የአማራ፣ የኦሮሞ፣ የልዩ ልዩ የቋንቋና ባህል ማኅበረሰቦችን ለምትወክሉ ልሂቃንና ምሁራን፣ የሃይማኖትና የፓለቲካ ድርጅቶች መሪዎች፣ በሀገር ውስጥና በዲያስፓራ ለምትገኙ ኢትዮጵያውያን ወገኖች፣ አክቲቪስቶች፣ የሚዲያ ባለሙያዎችና የማኅበራዊ ሚዲያ ተሳታፊዎች በሙሉ፦

    ሰሞኑን በአገራችን በኢትዮጵያ ልዩ ልዩ አካባቢዎች በደረሱ ጥቃቶች ሳቢያ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰላማዊና ንጹሃን ወንድሞች፣ እህቶች፣ አባቶች፣ እናቶች፣ አዛውንት፣ ሕጻናት ሳይቀሩ፣ የሃይማኖት አገልጋዮች ጭምር በግፍ ተገድለዋል፣ ቆስለዋል፣ ተፈናቅለዋል። አብያተ ክርስቲያናትና መስጊዶችም ተቃጥለዋል። ብዙ ግፍ ተፈጽሟል። ሕይወታቸውን ላጡ ንጹሃን ዜጎች ወገኖቼና ለቤተሰቦቻቸው፣ ለዘመዶቻቸው በአጠቃላይ ለኢትዮጵያ ሕዝብ የተሰማኝን ጥልቅ ሃዘን እገልጻለሁ።

    የሰው ልጆችን ከእንስሳት የሚለየን ረቂቅ ሕሊናን፣ ርሕራሄን፣ ሰብዓዊነት ነው። ከአራት አስር ዓመታት በላይ በተሰበኩ፣ ላለፉት በርካታ ወራት ደግሞ በተካረሩና ጥላቻን መሠረት ባደረጉ የተዛቡና ቁንጽል የታሪክና የፓለቲካ ትርክቶች ሳቢያ ለደረሰው እጅግ አሳዛኝ ጥቃትና የኢትዮጵያውያን ሕይወት መቀጠፍ የራሳቸው ሚና እንደነበራቸው የሚያጠያይቅ አይደለም።

    እነዚህን አሰቃቂና ዘግናኝ ድርጊቶች የፈጸሙ ሁሉ ተጠያቂ መሆን አለባቸው፣ መንግሥት እነዚህን ኢ-ሰብዓዊ ወንጀል የፈጸሙ ግለሰቦች በሕግ ፊት ማቅረብ አለበት።

    ከጥቂት ወራት በፊት በልዩ ልዩ ሚዲያዎች በተደጋጋሚ ሃሳቤን ለመግለጽ እንደሞከርኩት ከአንዳንድ የኦሮሞና የአማራ፣ የሕብረ ብሔር ኢትዮጵያውያን ልሂቃን፣ እንዲሁም በልዩ ልዩ ሚዲያዎችና ሶሻል ሚዲያዎች፣ አክቲቪስቶች፣ የብሔርም የሕብረ ብሔርም የፓለቲካ ድርጅት መሪዎች ሲሰነዘሩ የቆዩ ትንኮሳዎች፣ ጠብ አጫሪ ተግባራት፣ እንቅስቃሴዎች በልዩ ልዩ ማኅበረስቦች መካከል ለዘመናት የነበረውን ተጋምዶ፣ ትስስር፣ ትብብር፣ ፍቅር፣ ወልዶ ተዋልዶ አብሮ መኖር የነበረውን እንዳልነበር እያራከሰ እያኮሰሰ የደረሰበትን አሳዣኝ ዝቅጠት ከንፈር እየመጠጥን ስንታዘብ ሰንብተናል። በእኔ እበልጥ እኔ እበልጥ፣ እልህ ተጋብተውም እንዱ እንዱን ለመብለጥ የቃላት ጦርነቶችና፣ ከሁሉም ጎራ የሚሰራጩ የተዛቡ ትርክቶች፣ በሶሻል ሚዲያ የቃላት ሰይፍ መማዘዝ፣ ጥላቻን በሕዝብ መካከል መርጨት በስፋት ሲደረጉ የቆዩበት ሁኔታ፣ በስፋት በተሰራጩ የታሪክም የፓለቲካም የተዛቡ ትርክቶች፣ እጅግ ሲጋነኑ የነበሩ ቁንጽል መረጃዎች፣ ፊው የተዛመቱ የፈጠራ ወሬዎችን ጨምሮ በማኅበረሰቡ መካከል፣ በተለይም ለዘመናት ኢትዮጵያን እንደ ሀገር በመገንባት ትልቅ ድርሻ ያላቸውን በኦሮሞና የአማራ ሕዝቦች መካከል ትልቅ ክፍተት እንዲፈጠር፣ የተወሰኑ የሕዝብ ክፍሎች ውስጥም ጥላቻ አየሰፋ፣ እየተጠናከረ እንዲመጣ አፍራሽ አሰተዋጽኦ በማድረግ ከሰሞኑ ለተቀሰቀስው ከጥላቻ የመጣ ጥቃት፣ እጅግ አሳዛኝና እሰቃቂ ድርጊቶች ሚና እንደነበራቸው መታወቅ ያለበት ይመስለኛል።

    በተለይ በሕዝብ ቁጥር ትልቅ በሆኑት ብሔሮች በአማራና በኦሮሞ መካከል ቅራኔን፣ ጥላቻን፣ ጥርጣሬን የሚያጠናክሩ ትንኮሳዎች፣ በየመድረኩ፣ በጀርመን በእሥራኤል፣ በሌሎችም የዲያስፓራ የተቃውሞ ሰልፎች የተሰነዘሩ የጥላቻ፣ እንዱ ሌላውን በንቀት የሚያንኳስሱ ቃላቶችና ድርጊቶች፣ የተሳሳቱና የተዛቡ ትርክቶች በስፋት ሲካሄዱ እንደነበር የሚካዱ ሊሆኑ አይችሉም። ከዚህ አፍራሽና እጅግ ስስና ተሰባሪ የሆነውን የሀገሪቱን ሁኔታ፣ ተዋናዮቹ ግለሰቦች ብቻ ሳይሆኑ፣ ከግለሰቦች ጀርባ የሚገኙ የዶ/ር መረራ ጉዲናን አጠቃቀም ለመዋስ “የሚጋጩ ህልሞች” እንዲሁም ቅዠቶች፣ ሃሳቦችና ትርክቶች፣ በእነዚህ ትርክቶች ዙሪያም የተሰለፉ ሚሊዮኖች መኖራቸውን እነዚህ ሚዲያዎች፣ ሶሻል ሚዲያዎችና፣ አክቲቪስቶችና የፓለቲካ ልሂቃን ከግምት ውስጥ ሊያስገቡት አልቻሉም፤ ለማስገባትም አልተፈለገምም ነበር።የሴራ መልዕክቶች፣ ባልተጣሩና ለማጣራትም ምንም ጥረት ባልተደረገባቸው በዜና መልክ የሚቀርቡ የፈጠራም የተጋነኑም ወሬዎች በተለይ ሀገር ውስጥ በመሬት ላይ ለሚገኘው የገፈቱ ቀማሽ ሰላማዊ ሕዝብ የማይበጀው መሆኑ መረዳት ያስፈልግ ነበር።

    ያደራጁት ኃይል በእጃቸው በሌለበት፣ አማራጭ ራዕይና ፕሮግራም ባላዘጋጁበት፣ አገርን ሊያረጋጋ፣ ሕዝብን ከጥቃት ሊከላከል የሚችል ወታደራዊና የጸጥታ ኃይሎችን ባላሰለጠኑበት፣ በማይመሩበት፣ ለዚህ ደግሞ መንግሥታዊ አቅሙም፣ ችሎታም፣ ስትራቴጂካዊ ጥናቶች ሆነ ቅደመ ዝግጅቶች ማንም ምንም በወጉ ባላሰቡበት፣ ባልተዘጋጁበት ሁኔታ በስልጣን ላይ የሚገኘውን ብዙ ተግዳሮቶች የገጠመው ነገር ግን ለውጥን ለማምጣት ደፋ ቀና ሲል የቆየውን የለውጡን አመራር በከፍተኛ ርብርብ ለማዋከብና ለመሸርሸር የተሄደበት ርቀት ትልቅ ታሪካዊ ስህተት ይመስለኛል።

    ሀገራችንን ኢትዮጵያን አጣብቆ የያዘውን መንግሥታዊ ኃይል ቢዳከም፣ እነዚህ የታሪክም የፓለቲካ መሠረት ያላቸው ልዩ ልዩ ቅራኔዎች በየቦታው ቢፈነዱ፣ በሕዝብ መካከል የእርስ በእርስ ግጭቶች ቢበራከቱ በብዙ አቅጣጫና ውስብስብ የብሄር ቅራኔዎች፣ ሌሎች ፓለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና፣ ማኅበራዊ ችግሮች የተጠመደች ሀገራችንና የኢትዮጵያ ሕዝብ ወዴት ሊወስዱ እንደሚችሉ ከግምት ማስገባት አስፈላጊና ወሳኝ ይሆናል። እንደ ሀገር መኖር አለመኖር፣ እንደ ሀገር መቀጠል ወይንም አለመቀጠል የምንችልበት ወይንም የማንችልበት የታሪክ መጋጠሚያ ላይ ደርሰናል። በአንድ አካባቢ የሚጀመር እሳት፣ ወደ ሌላ አካባቢ ሊዛመት እንደሚችል ወደ ሰደድ እሳት ሊያድግ፣ ሊሸጋገር ወደሚችል ደረጃ እንደሚደርስ ብዙ እውቀትና ማሰብ የሚፈልግ አይመስለኝም። በሌላም በኩል ደግሞ የእርስ በእርስ ግጭቶች እየተቀጣጠሉ፣ አድማሳቸው እየሰፋ ሊሄድ እንደሚችል፣ በአንድ አካባቢ የተነሳ ግጭትና የግጭቱ ጥቃት ስለባ የሆኑ ወገኖች በሌላ አካባቢ በሚገኙ የአጥቂዎች ወገኖች ላይ የብቀላ ጥቃት፣ የብቀላ ብቀላ አድማሱ አየሰፋ፣ እየተዛመተ፣ ማንም ምድራዊ ኃይል ሊቆጣጠረው ወደማይችል ምድራዊ ሲኦል ሊለወጥ የማይችልበት ምክንያት አይኖርም።

    ውድ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ፦

    ዛሬ ትላንት አይደለም። ትላንት የሁሉም የኢትዮጵያ አካባቢዎች፣ የአብዛኛው የዲያስፓራ ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን ትኩረትና የትግሉ ግብ፣ የትግሉም ዒላማ በሕዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ ሲዘወር በነበረ ግፈኛና ጨካኝ አገዛዝ ላይ ያነጣጠረ እንደነበር የሚካድ አይደለም። ከጎንደር እስከ ሐረር፣ ከባሌ ዶሎ እስከ ወሎ፣ ከሐረር እስከ ባሕር ዳር የኢትዮጵያ ሕዝብ ከኦሮሞ እሰክ አማራው፣ ከጋምቤላ እሰከ ሶማሌ፣ ከአዲስ አባባ እስከ አምቦ ትግሉ ከመንግሥት ኃይሎች፣ ከጨቋኝና ግፈኛ ገዥዎችና የመጨቆኛ መሥራሪያዎቻቸው፣ ተቋማቶቻቸው ጋር ሲያፋፍም የነበረ፣ አለፍ ካለም የእነሱ ጥቂት ደጋፊዎች ላይ ያነጣጠረ እንደነበር የማይረሳ ነው።

    ዛሬ ግን ቅራኔው፣ ግጭቱ፣ ጥላቻው የጎንዮሽ በሕዝብ መካከል ሆኗል፤ በማኅበረሰቦች መካከል ሆኗል። ትልቁ አደጋ ይህ ከሰሞኑ የተከሰተውና ነጥሮ የወጣው እውነታ ከዚህ ጋር የተያያዘ መሆኑ የሚያጠራር፣ የሚያሻማ ሊሆን አይችልም። ዛሬ ቅራኔው ለዘመናት አብረው በኖሩ ማኅበረሰቦችና በሕዝብ መካከል መሆኑ ነው። ይህ እውነታ በስፋትና በጥልቀት በበርካታ የአገሪቱ አካባቢዎች የሚታይ እጅግ አደገኛ ሂደት መሆኑ ግልጽ አየሆነ ነው።

    ይህን ልዩና እጅግ አስጊ ሁኔታ ለመለወጥ ከፍተኛ ጥንቃቄ፣ ዘዴዎች፣ ብልሃቶች ይጠይቃል። መንግሥታዊ የማድረግ አቅም የመኖር አለመኖር ብቻ ሳይሆን የመንግሥት እርምጃዎች፣ የመንግሥት ድርጊቶች ሊፈጥሩ የሚችሉትን አሉታዊ የሆነ የአንድ ወይንም የሌላ ወገን የአጸፋ ምላሽ ለመቋቋም የሚያስችል፣ ያልተጠበቁ ትላልቅ አደጋዎች በሕዝብ ላይ እንዳይደርሱም እስቀድሞ ችግሮቹ በቀጥታ የሚመለከታቸውና ከችግሩ ጋር ተፋጠው የሚገኙ የመንግሥት መሪዎችና ልዩ ልዩ የመንግሥታዊ ተቋማት ሃላፊዎች ሊደረግ ብቻ የሚችል የቢሆንስ ትንታኔም የሚያስፈልገው ነው። የመንግሥት መሪዎች ወደ ስልጣን ያመጣቸው ፓርቲና ሕዝብ ውስጥ ያላቸው ቅቡልነት፣ ስትራቴጂካዊ አስተሳሰብ ዝግጁነት፣ በየጊዜው የሚፈተሽ ዕቅድና ይህንኑ የማስፈጸሚያ/የ ማድረግ አቅም የሚሰጡ ልዩ ልዩ የመሣሪያዎች ሳጥን በአግባቡና በብቃት ማዘጋጀትን የሚጠይቁ ናቸው። ድርብርብና በየደረጃው የሚከናወኑ ተግባራት ያሉበት ውስብስብ ሁኔታ ነው። በመንግሥት ብቻ ሳይሆን፣ በአገር ሽማግሌዎች፣ በሃይማኖት አባቶች፣ በልሂቃን፣ በልዩ ልዩ ኃይሎችና ባለድርሻዎች በጋራም፣ በተናጠልም ሥራዎችን ይጠይቃሉ።

    የኢትዮጵያን ሰላምና፣ ደህንነት፣ መረጋጋት የሚፈልጉ ዜጎች ሁሉ ይህን አስጊና አደገኛ በሕዝባችን ደህንነት፣ በሕዝባችን አብሮነት፣ በኢትዮጵያ ሃገራዊ ህልውና ላይ የተደነቀረ ከባድ አደጋ ለመሻገር ከተፈለገ ይህን አደጋ ከሚያባብሱ፣ ከሚቀጣጥሉ ቃላት፣ ቅስቀሳዎች፣ ቁንጽልና በቅጡ ያልታሰቡባቸው፣ ያልተጠኑም በርካታ የሀሰትም ወሬዎች፣ የተዛቡና በምንም መልኩ መቼም ሙሉና ሁለንተናዊ እይታን ሊሰጡ የማይችሉ ትርክቶች በሚዲያና በማኅበራዊ ሚዲያዎች ከማሰራጨት መቆጠብ የግድ ይሆናል። በምትኩ የሚዲያዎች ሚና ለኢትዮጵያ ሕዝብ ተስፋ መስጠት፣ ማኅበረሰቦች እንዲቀራረቡ የበኩላቸውን ሚና መጫወት ያለባቸው ይመስለኛል። ግጭት ሳይሆን ውይይት፣ ቅራኔን ሳይሆን መግባባት እንዲመጣ ገንቢ ጥረቶች ማድረግ የሁሉም የፓለቲካ ልሂቃንና የሚዲያዎች፣ በሀገር ቤትም በውጭ ሀገርም የሚገኙ የብሄርም የሕብረ ብሄርም ዓላማ ያነገቡ አክቲቪስቶች ታሪካዊ ሃላፊነት ነው ብዬ አምናለሁ። በተለይም እሳቱ የማይደርስባቸው፣ በእነሱም በቤተሰቦቻቸው፣ በዘመዶቻቸው ላይ ጭምር ሊደርስ የሚችል የማይመስላቸው በውጭም በሀገር ውስጥም የሚገኙ የየብሔሩ ልሂቃን፣ የየብሔሩና በሕብረ ብሔርም ኢትዮጵያዊነትና ዜግነት ፓለቲካ የተደራጁ አክቲቪስቶች ሁሉ ቆም ብለው ማሰብ የሚገባቸው ወቅት አሁን መሆኑን በጥብቅ ለማሳሰብ እፈልጋለሁ።

    የሚቀጥለው እሳት ወደ ሰደድ እሳት እንዳያመራ ሳይቃጠል በቅጠል እንዲሉ ለትላልቆቹ የፓለቲካ ልዩነቶች መፍትሄ ማፈላለግ ያስፈልጋል። የተጀመረው አዝጋሚና ብዙ ተግዳሮቶች የገጠመው የለውጥ ሂደት ከእናካቴው እንዳይቀለበስ ሁሉም የድርሻውን ማበርከት አለበት ብዬ አምናለሁ። ይህን አጋጣሚ ለመጠቀም ያቆበቆቡ፣ ይህን ሁኔታ ለመጠቀም ሰሞኑን በሀዘን የተመለከትነውን ጥቃት በማጦዝ፣ በማራገብ ጮቤ የረገጡ፣ ልዩ ልዩ ዘዴዎችንም በመጠቀም ከተለያዩ የፓለቲካም፣ የሚዲያም ተዋናዮች ጀርባም በመሆን ቅራኔዎችና ችግሮች እንዲሰፉ፣ እንዲባባሱ የእነማን ዘርፈ ብዙ ጥረት እንደሆነ የሚጠቁሙ በርካታ መረጃዎች በየጊዜው እንደሚያሳዩ ለአብዛኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ ግልጽ ይመስለኛል። ከመሸጉበት ለማንሰራራት፣ ብሎም የኢትዮጵያን ሃገረ መንግሥት ማዕከል ዳግም ለመቆጣጠር ያላቸውን ቀቢጸ-ተስፋ ዕውን ለማድረግ፣ የለመዱትንም ግፈኛ መንግሥታዊ ሽብርና መንግሥታዊ ዘረፋ በመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ኪሳራ ለማስቀጠል ሙከራቸውን ከማድረግ ወደ ኋላ የማይሉ እኩይና ከታሪክ የማይማሩ ያረጁ ያፈጁ ከ21ኛው ክፍለ ዘመን የፓለቲካ አስተሳሰብ ጋር እራሳቸውን ማለማመድ፣ ካለፈው ወንጀሎቻቸውና ውድቀታቸው መማር የማይችሉ ድኩማን የፓለቲካ ድርጅች እንዳሉ ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ፍንትው ብሎ የሚታይ ሃቅ ነው ብዬ እገምታለሁ።

    እነዚ ህይሎች የራሳቸውን ጥቅምና ያጡትን የበላይነትና ፈላጭ ቆራጭነት ከማየት በስቲያ፣ በሕዝብ ላይ ጭነው ከነበሩት የበላይነት ባሻገር ለሕዝብ መከራ፣ ለሰው ልጆች ጉስቁልና ቁብ የማይሰጣቸው ናቸው። የሚሊዮኖች ኢትዮጵያውያን ደምና እንባ ለ27 ዓመታት አንደ ጎርፍ እንዲፈስ ያደረጉት እነዚህ የፓለቲካ ዓመታት ይህን እኩይ ዓላማቸውን ለማሳካት የጋራ አገራችን ኢትዮጵያ አገራዊ ትርምስ ውስጥ ብትገባ ፈጽሞ የማይጨነቁበት መሆኑን ሲጀምሩም የተነሱበት የፓለቲካ ዓላማ፣ ታሪካቸው፣ እስካሁንም የቀጠሉበት አንደበታቸው፣ የተካኑበት መሰሪነትና ተንኮል ያረጋግጣል። “እኛ የኢትዮጵያ አዳኞች ነን” በሚል ሽፋንና ነገር ግን የማዕከላዊ መንግሥትን ሙሉ በሙሉ የመቆጣጠር ቀቢጸ-ተስፋቸው እሁንም በትዕቢትና በትምክህት ተወጥረው በሚያደርጉት እንቅስቃሴ አገራችንን ወደ ሁለንተናዊ ትርምስ ጎዳና ሊያስገባ የሚችል ዕድል እንዳንሰጣቸው የኢትዮጵያ ሕዝብ ሁሉ ነቅቶ መጠበቅ እንዳለበት በጽኑ አምናለሁ።

    የኢትዮጵያ ምድር ከጥንት ከሺህ ዓመታት በፊት ዛሬ የሚገኙ ሕዝቦች ያልነበሩበት፣ አንዱ በአንድ ዘመን ከደቡብ ተነስቶ ሌሎችን ማኅበረሰቦች አስገብሮ መሬት ሲይዝ፣ በሌላ ዘመን ሌላው ይህኑ አጸፋ ሲያደርግ፣ ሲስፋፋ፣ በአመዛኙ ደግሞ የየብሔሩ ገዢዎች፣ በዓለም ላይ እንደነበሩ ገዥዎች ሁሉ የተደረጉ ሂደቶች ናቸው። ሌሎች የዓለም ሃገሮች ከተመሠረቱበት የሀገራት ምሥረታ ሂደት ምንም የሚለየው የለም። ባርያ ፈንጋዩና አስገባሪው ደግሞ የአንድ ብሔር አንድ ቋንቋ የሚናገሩ ብቻም አልነበሩም። በልዩ ልዩ የታሪክ ምዕራፎች የየማኅበረሰቡ/ብሄሩ ንጉሶችና ገዢዎች፣ አስገባሪዎች፣ ተስፋፊዎች በመሆን ተፈራርቀዋል። የልዩ ልዩ ብሔሮች/ማኅበረሰቦች ገዢዎች ከመሃል ወደ ደቡብ፣ ከደቡባዊ ከምሥራቃዊ ኢትዮጵያ ተነስቶ እስከ መሃላዊ የዛሬዋ ኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን እስከ ሲሜናዊና ሰሜን ምሥራቃዊ የሀገሪቱ ክፍሎች በመዝመት በመስፋፋት ሲፈራረቁበት የቆዩበት የረጅም ዘመናት ሂደት ነው። የረጅም ዘመናት ታሪካችን እያንዳንዱ ማኅበረሰብና በየዘመኑ፣ በሰፊው የታሪካችን ምዕራፎች የነበሩ የብሔርም የሕብረ-ብሔርም ገዥዎች በቀደሙት ዘመናት አጣኋቸው ያላቸውን መሬቶች ለማስመለስ ዳግም በኃይል ሲስፋፋ የነበረበት ውጥንቅጥና አባይን በጭልፋ እንደሚባለው ረጅምና ተጽፎ ያላለቀ፣ ተጽፎም ሊያልቅ የማይችል፣ የብዙ ዘመናት የመጥበብ፣ የመስፋት ሂደቶችና ተደጋጋሚ ኡደቶች ብቻም አልነበሩም። የንግድ ልውውጥ፣ የማኅበራዊ ግንኙነቶች፣ የቋንቋና ባህል መወራርስና መዳቀል የነበሩበትም ሂደት ነበር። ለዳር ድንበርና ለሕዝብ ክብር ለኢትዮጵያ አገራዊ ግንባታ በኦሮሞም፣ በአማራም፣ በአፋር፣ በትግሬ፣ በወላይታ፣ ጉራጌ በሌሎችም የቋንቋና የባህል ማኅበረሰቦች ባፈሯቻቸው በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሀገራዊ እርበኞች፣ አንጸራቂ ጀብድ በፈጸሙ፣ ታላላቅ ጀግኖችና የጦር መሪዎች መስዋዕትነት የተገነባ ሕብረ-ብሔራዊ ኢትዮጵያ ማንነትና ሃገራዊነት የታሪክ ሂደትም ነው። ይህ ውስብስብ የታሪክ ሂደት በ150 ዓመት ታሪክ ትንሽ አጭር መነጽር ሊታጠር፣ ሊገደብ የማይችል ሰፊ የዘመናት የታሪክ ባህርን በጭልፋ በሰፈረ፣ እጅግ ቁንጽል የሆነ የነፍጠኛ የሰባሪ የገባር/የአስገባሪ ትርክትና እንድምታ የማያይወክለው፣ የማይገልጸው ሰፊና ጥልቅ የሆኑ የታሪኮቻችን ገመዶችና ክሮች የልዩ ልዩ ማኅበረስቦች መስተጋብሮች፣ ግንኙነቶችና፣ የሂደቶች ውጤት ነው።

    ዋናው፣ ትልቁ ሃቅ ግን ከዚህም ከዚያም ወገን ማንም የታሪካችን ሙሉ እውቀት፣ ሙሉ መረጃ እንኳን በዚህኛው በወዲያኛውም ሕይወቱ ሊኖረው አይችልም። ታላላቆቹና በዓለም ደረጃ የሚታወቁት የታሪክ ጸሐፍት እነ አርኖልድ ቶዬንቢ (Arnold J. Toynbee)፣ ኤድዋርድ ጊበን (Edward Gibbon)፣ ዘመናዊና ትላልቅ ስም ያላቸው ኒያል ፊርግሰን (Niall Ferguson)፣ ፈርናንድ ብራውዴል (Fernand Braudel)፣ ሌሎችም ታዋቂ የታሪክ አጥኚዎች የሀገራቸውንም ሆነ የዓለምን ታሪክ በሚመለክት የጻፏቸው ሁሉንም የታሪክ ምዕራፎች፣ ሁሉንም ታሪካዊ ክንውኖች፣ ሁሉንም ታሪካዊ መረጃዎች፣ ሁሉንም ታሪካዊ ሂደቶች አጣርተው በሙሉ፣ ፍጹም በሆነ እውቀት/ዩኒቨርሳል የታሪክ ዘይቤም የታሪክ ሙሉ እይታ ሊኖራቸው እንደማይችል የታወቀ ሃቅ ነው። የብዙ አገሮች ታላላቅ የታሪክ ጸሐፊዎች በእያንዳንዱ የታሪክ ምዕራፍ አስከ ዛሬ የሚወዛገቡባቸው በርካታ የታሪክ ኩነቶች፣ የታሪክ ትርጓሜዎች፣ የታሪክ ዘይቤዎች እንዳሉ ራሱ የኢትዮጵያን ታሪክ በራሳቸው ልክ ለሚፈልጉት የፓለቲካ አጀንዳ ቀንጭበውና ቆንጽለው የሚያቀርቡ የየብሔሩ ልሂቃን የሚያጡት ሃቅም አይደለም።

    እነዚህ አጨቃጫቂ፣ አወዛጋቢ የሆኑት በሁሉም ወገን ቁንጽል የሆኑና ማንም በምንም መልኩ ሙሉ በሙሉ በሚያስብል ደረጃ እንደበርክታ የታሪክም የማኅበራዊ ሳይንስ የመነጩ ጥናትችና ትርክቶች ሙሉ እይታ፣ ሙሉ እውቀት፣ ሙሉ ግንዛቤ፣ እንደሌላቸው ይታወቃል። የተፈጥሮ ሳይንስ በተለይም ከአንስታይን የሬላቲቪትይ የፊዚክስ ቲዎሪ (Albert Einstein’s Relativity Theory) ግኝት በኋላ ሁሉን አዋቂና ሁሉን ተንባይ ነኝ የሚለው ማንነቱ ላይ በደረሰብት ቀውስ ሳቢያ የሳይንሱ ማኅበረሰብ የሚቀበለው በአመዛኙ ፍጹም የሆነ፣ ሙሉ የሆነ እውቀት፣ ዩኒቨርሳል የሆነ እርግጠኝነት፣ የትንበያ አቅምም እንደሌለ ነው። ሌሎች ታላላቅ የሳይንስ ፈላስፎች ኢ-እርግጠኝነት (Uncertainty principle) የሚል ስያሜ የሰጡት የተፈጥሮ ሳይንስ ንጉስ የሆነው ፊዚክስ ተፈጥሮን ሙሉ በሙሉ፣ ሁሉን ለማወቅና የሚሆነውንም ለመተንበይ የማይችል፣ በእጅጉ ያለውን ውሱንነት ያጠናከሩ፣ ልዩ ልዩ የእውቀት ዘርፎችም ከኢኮኖሚክስ እስከ የፓለቲካ ሳይንስ የእውቀት ዘርፎች ጠቅላይ ሊሆኑ፣ ሙሉና የወድፊቱንም በፍጹም እርግጠኝነት ሊተነብዩ እንደማይችሉ፣ ልዩ ልዩ የእውቀት ዘርፎች በተወሰነ አውድ፣ በተወሰነ ካባቢ ውሱን ለሆነ ግንዛቤና እውቀት፣ ለውሱን ችግሮች መፍቻ ዘይቤዎች/መሣሪያዎች ብቻ እንደሆኑ፣ የወደፊቱም የመተንብይም ሆነ ያልፈውን የታሪክም የማኅበረሰብን ውጥንቅጦች በሁለንተዊና ጠቅላይ/ዩኒቨርሳል በሆነ መልኩ ለማወቅ እንደማይቻል እንዱ ሌላውን ሲገለብጡ፣ የኖሩ ንደፈ ሃሳቦች፣ ጽንሰ ሃሳቦች (theories)፣ የዓለም እይታዎች (paradigms)፣ ልዩ ልዩ የማኅበረሰባዊና የተፈጥሮ ሳይንስ ፍልስፍናዎች፣ እንዲሁም የዘይቤዎች (methods/models) የትየለሌ መሆናቸው የሚያረጋግጡት ይህንንኑ ነው። በብዙዎች ዘንድ በዚህ ጉዳይ ላይ ሰፊ ግንዛቤና መግባባት የተደረሰ ይመስለኛል።

    ስለዚህ የኢትዮጵያ ልሂቃን በተለይ በፓለቲካው ትልቅ ሚና ያላችሁ የታሪክና የህብረተሰቡን ችግሮች ሁሉ በሚመለከት አለን የምትሉት ግንዛቤ ውሱንነት መቀበል። ትህትና ብትህውትነት (humbleness and humility) እኛ ሁሉን እናውቅለታለን ብለው ለሚገምቱት ሕዝብና ማኅበረሰብም የተሻለው ምልከታ ይመስለኛል። ምክንያቱም ፍጹም እወቀት፣ ፍጹማዊ እውነት አለኝ ለማለት በማይቻልበት እጅግ ሰፊና ጥልቅ የተፈጥሮ፣ የታሪክ፣ የማህብረሰብም ሂደቶች፣ ጉራማይሌዎች፣ ጓዳ ጎድጓዳዎች፣ ጉራንጉሮች፣ ዥጉርጉር ሁኔታዎችና ሂደቶች የነበርን ሕዝቦች በመሆናችን። የሰው ልጆች ሕይወትም ሆነ የዓለም ሕዝቦች ታሪክ አካል የሆነ የኢትዮጵያ ታሪክ (ታሪኮች) ግራጫ ቀለም ያላቸው እንጂ ነጭና ጥቁር ባለመሆናቸው የኋላ ታሪኮቻችን፣ የሚጋጩ ትርክቶች ያን ወይንም ይህን ቁንጽል የታሪክ ጠብታ ይዞ ሙሉ እውቀት ባለቤት ነኝ፤ በሞኖፖል እውቀት እኔ ጋር ብቻ የሚል ስሜት ያላቸው የየብሄሩ ልሂቃን ቁንጽ የታሪክ ትርጉሞች/ትርክትን መሠረት አድርገው የሚሰነዘሩ ሽኩቻዎች የሕዝብ፣ የማኅበረሰብ ቅራኔዎች፣ ጥላቻና፣ ግጭቶች፣ ጥቃቶች መንስዔም እየሆነ የመጣበት ይህ እጅግ አሳዛኝ ሁኔታ እሁን ላይ መቆም ይገባዋል። ለአገርና ለሕዝብ የተሻለው፣ የሚበጀው መንገድም ይህ ይመስለኛል። ሁለተኛው አማራጭ ሕዝብን ማጫረስ፣ ሀገርን ማፍረስ፣ ሁሉም በእሳት የሚጫወት ተዋናይ በሰደድ እሳቱ ወላፈን እራሱም ሆነ በምድር ላይ የሚገኙ የሚወዳቸውም ሳይቀሩ የመለብለብ፣ የሚጠበስ ምድራዊ ገሃነም ብቻ ናቸው።

    የኦሮሞም የአማራም ከዚያም የደቡባዊና የምሥራቃዊ ኢትዮጵያን፣ እንድሁም የኦሮሞን ታሪክ በአግባቡ አላካተተም ወይንም አይወክልም የሚባለው የግዕዝ ስልጣኔ ታሪክ፣ ሌላም ካለ ሁሉም ወገን የኔ የሚላቸው ትርክቶች፣ ልዩ ልዩ ታሪኮች ወይንም የሚጣጣሙበት ወይንም የሚቀራረቡበት መንገዶችና ዘዴዎች መፈለግ፤ ወይንም ደግሞ ተመሳሳይ የታሪክ አረዳድ ያልነበራቸው አገሮች፣ የሚጋጩ ትርክቶች አገራዊ ትርምስ የፈጠሩባቸው የሌሎች ሀገሮችን ሕዝቦች ልምድ ቀስሞ ከሁሉም የተውጣጣ፣ ይህንኑ የሚያጠና ባለሙያዎች የሚገኙበት ኮሚሽን የሚቋቋምበት ሁኔታ ቢመከር ምናልባት አንዱ የመፍትሄ አካል ሊሆን ይችላል። ምክንያቱም ቀደም ሲል እንደተነሳው የአገራችን ትላልቅ የፓለቲካ ቅራኔዎች አንዱ ከአለፉ ታሪኮቻችን የታሪክ አረዳድና አተረጓጎም ልዩነቶች፣ የሚጋጩ ትርክቶች ላይ የሚመነጩ በመሆናቸው ከፍተኛ ትኩረትና ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል እላለሁ።

    ሁሉም አሸናፊ የሚሆንበት፣ ማንም ተሸናፊ የማይሆንበት በሀገሪቱ ዋና ዋና ችግሮች ዙሪያ መፍትሔ ተኮር ውይይቶች በየደረጃው የሚደረጉበት ሁኔታዎች መፈለግ አስፈላጊ ይሆናል። ሁሉም ባለድርሻዎች አገሪቷን እሁን ላይ ከገጠማት የህልውና አደጋ ለመታደግ ከለውጡ መሪዎች ጋር በመነጋገር፣ በለውጡ መሪዎችም በኩል ጉልህ ድምጽ ያላቸውን ባለድርሻዎች፣ የየብሄሩን ልሂቃንና የፓለቲካ ኃይሎች ሁሉ ፍላጎታቸውን በግልጽ ወደ ጠረጴዛው እንዲያቀርቡ፣ ውይይቶች እንዲደረጉ፣ ሰጥቶ የመቀበል፣ ብሎም ሀገራዊና ብሄራዊ መግባባት ላይ መድረስ እንዲቻል መድረኮችን የማመቻቸት ጊዜው አሁን ነው የሚል የሚል ሃሳብ አቀርባለሁ።

    የሁሉም ዜጎችና የቋንቋና የባህል ማኅበሰቦች ጥቅምና መብቶች ያልተከበሩባት ኢትዮጵያ የማንም የየትኛውም ብቸኛ ማኅበረሰብ/ወይንም ብሔር መብት፣ ፍትህና ጥቅም ለዘለቄታው ሊከበርባት እይችልም። የአማራ፣ የኦሮሞ፣ የሌሎችም ማኅበሰቦች ልሂቃንና የፓለቲካ ኃይሎች ቆም ብለው የማንም የማትሆን አገር ሁላችንም ወደ ምድራዊ ሲኦል የሚወስድ መንገድ ከመግፋት እጅግ የተሻለው አመራጭ ለሁሉም ጥቅም፣ ለሁሉም እኩልነት፣ መብቶች፣ ለሁሉም ድምጽና ክብር፣ ለሁሉም የምትመች ኢትዮጵያን እንድትሆን ተነጋግሮ፣ ተግባብቶ፣ ፍኖተ ካርታውን፣ የጨዋታውን ሕግ፣ ሂደቱን፣ የሥነ ምግባር ደንቡን… ወዘተ የሚመለከቱ እንዲሁም ዋና ዋና ፓለቲካዊ ልዪነቶች ላይ ዉይይቶች በማድረግ፣ ወደ መግባባት ላይ ለመድረስ ማሰብ ያለባቸው ጊዜ አሁን ይመስለኛል። ይህ ጥሪ ለኦሮሞ፣ ለአማራ፣ ለሶማሌ፣ ለአፋር፣ ለትግራይ ለሌሎችም ማኅበረሰቦች ልሂቃን፣ የፓለቲካ ኃይሎች፣ እንዲሁም የሕብረ ብሔር የኢትዮጵያዊነት የዜግነት የፓለቲካ ኃይሎች በሙሉ ለህሊናም፣ ለታሪካችሁም እጅግ የተሻለው አማራጭ መሆኑን በአንክሮ ማሰብ ወቅቱ አሁን ይመስለኛል።

    በሁሉም አካባቢዎች የሚገኙ ሕብረ ብሔር ኢትዮጵያውያን የዜግነት መብቶችና ጥቅሞች ፍትሃዊ በሆነ መልኩ እንዲስተናገድ፣ እንዲከበሩ፣ እንዲረጋገጡ የሚያስችል ሂደት መጀመርም አለበት። የየትኛውም ብሔር የበላይነት (hegemony)፣ በየትኛውም አካባቢ ይህ የኔ ለእኔ ብሔር ብቻ ነው ሌላው ዜጋ መጤ ነው፣ ሰፋሪ ነው… ወዘተ የሚሉ የተዛቡና ብዙ ሚሊዮን ዜጎችን በገዛ አገራቸው ባይተዋር ያደረጉ፣ ስጋትን፣ የነገን ተስፋ አለማየት፣ ከሰሞኑ ደግሞ በንጹሃን ዜጎች ላይ ያነጣጠሩ ጥቃቶች ሕይወት ያስቀጠፉ አስተሳሰቦችና ሥነ ልቦናዎች የሚለወጡበት ሁኔታ በቅጡ መታሰብ፣ መፍትሔም ማግኘት አለባቸው። በተጨማሪም ይሄ “የኔ ብሔር፣ ይሄ የኔ አካባቢ ብቻ ነው”፣ የሚሉ ኢ-ፍትሃዊ የሆኑ ጸረ-ዴሞክራሲያዊ አመለካከቶች “የኔ” ለተባለውም ብሔር ሕዝብ ጥቅምንም መብቶችንም ለዘላቂው ሊያስከብርና ሊያስቀጥል አይችልም። ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት በሌለበት፣ የሕግ የበላይነት ባልተረጋገጠበት፣ ተጠያቂነትና ግልጽነት የሌሉዋቸው የፓለቲካ ስርዓቶች በስመ ብሄር፣ ወይንም በሀገራዊ ብሄርተኝነት ስም ወደ ስልጣን የመጡ ፈላጭ ቆራጭ አምባገነኖች ብሄሬ በሚሉት ሕዝብ ላይ ያደረሱትን መከራ፣ ስቃይና፣ እልቂት በታሪክም አሁን ላይ በዘመናችንም ከበቂ በላይ ሁላችንም የታዘብን፣ ያየን ይመስለኛል።

    በአንድ ሀገር ውስጥ ግማሹ የበኩር ልጅና አንደኛ ዜጋ፣ ገሚሱ የሀገሪቱ ሕዝብ ደግሞ የእንጀራ ልጅና ሁለተኛ ዜጋ፣ ከዚያም ወረድ ብሎ በስጋት በፍርሃት፣ ያለዋስትና እየኖረ የሚቀጥልባት ኢትዮጵያ እንደ እንድ የጋራ አገር፣ በጋራ አብሮ ለመኖር ሊያዘልቁ የሚያስችሉ አይሆኑም። ይህን እስከፊና ለ26 ዓመታት የተንሰራፋ፣ ዛሬም ሊደገም፣ ተጠናክሮ ሊቀጠልበት የሚሞከርበት፣ ብዙ ሚሊዮኖች አማርኛ ተናጋሪ ይሁኑ እንጂ ከኦሮሞ፣ ከጉራጌ፣ ከወላይታ፣ ከትግሬ፣ ከከንባታ፣ ጋሞ፣ ከሶማሌ አፋር፣ ከሌሎችም ማኅበረሰቦች ቅይጥና ቅልቅል የሆኑ፣ ወይንም በሥነ ልቦናም፣ በአመለካከትም፣ የትኛውም ብሔር ሳጥን ውስጥ ሊገፉና ሊከተቱ የማይችሉ፣ ነገር ግን ሁሉንም ብሔሮች/ማኅበረሰቦች የሚወዱ፣ አብሮ የኖሩ፣ አፍቅሮ፣ ተጋብቶና ተዋልዶ፣ በልዩ ልዩ ማኅበራዊና ሰዋዊ ገመዶች የተሳሰረ፣ በደም በአጥንት የተለሰነ የልዩ ልዩ ማኅበረሰቦች የተገኙ “ከአስገባሪነት”፣ “ከነፍጠኝነት”፣“ከሰባሪነት” ጋር ምንም ግኙነት የሌላቸው፣ ከኢትዮጵያዊነት ሌላ ቤት የሌላቸው፣ ብዙ ሚሊዮን ዜጎቻችን በአዲስ አበባ አካባቢዎች፣ በሐረር፣ በድሬ ዳዋ፣ በባሌ፣ በአዳማ፣ በአሰላ፣ በአዋሳ፣ በልዩ ልዩ ሌሎች የሀገሪቱ የከተማ፣ ከተማ ቀመስና የገጠር አካባቢዎች ሁሉ ሙሉ መብቶቻቸው፣ ደኅነታቸው፣ በሁሉም የኢትዮጵያ አካባቢዎች በተለይም በኦሮሞ፣ በደቡብ በሌሎችም አካባቢዎች መከበር፣ መረጋገጥ የሚቻልበት ሁኔታዎች፣ ውይይቶች፣ ድርድሮች፣ መግባባቶች መደረስ ይኖርበታል።

    በሀገርም ውስጥ በውጭም የምትገኙ የምታውቁኝም የማታውቁኝም ወድ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ፦

    ታላቁ የአሜሪካን ፕሬዝደንት አብረሃም ሊንከን (Abraham Lincoln) የአሜሪካ ጥቁ ር ሕዝቦችን ከባርነት ለማላቀቅ በተደረገው የደቡብ ባሪያ አሳዳሪ ኮንፌደሬት ሠራዊትና የሰሜኑ የአንድነት ሠራዊቶች ከዛሬ 160 ዓመታት በፊት ባደረጉት የእርስ በእርስ ጦርነት ወቅት እንደተናገረው እርስ በእርሱ ተከፋፈለ ቤት ሊቆም/ሊዘልቅ አይችልም (“A house divided against itself cannot stand”)። አሁን እየታየ ባለው በሕዝብ ውስጥ የሚገኝ ቅሬኔና ትላልቅ ህመሞችና ስንጥቆች ሳቢያ የሁላችንም የጋራ ቤት የሆነችው ሀገረ ኢትዮጵያ በዚህ ሁኔታ ህልውናዋ መቀጠል አይችልም። ፍትሃዊነትና ልከኝነትን (just and fair) ማዕከል አድርገን አገራዊ የፓለቲካ ችግሮቻችንን ካልፈታን፣ ይህ ብዙ ሚሊዮን ዜጎቻችንን መብት አልባና አንገት አስደፊ ያደረገ፣ እስከፊና አሳፋሪ ሁኔታ እንደ አገር አብሮ ለመኖር አያስችለንም። ይህን አስከፊና ከሀገሪቱ ችግሮች አንዱ የሆነ አስተሳሰብና ሕጎች ለመለወጥ ሂደቶች መጀመር አለባቸው። ተጠያቂነት፣ ግልጽነት፣ ስልጣን የተገደበበት፣ ሕዝብ በርካታ አማራጮች ቀርበውለት በነጻ ርዕቱአዊ ምርጫ ሊወስን የሚችልበት የሕግ የበላይነትና ለአገራችን ውስብስብ ችግሮች መድኅን ሊሆን የሚችል ፌደራላዊም ዴሞክራሲያዊም የሆነ የፓለቲካ ሥርዓት ለዘላቂው ለሁሉም የቋንቋና የባህል ማኅበሰቦች፣ ለሁሉም ኢትዮጵያውያን ዜጎች ሊበጅና ሊጠቅም የሚችለው። በአንድ ጎን በየአካባቢው የሚገኙ የማኅበረሰቦች የስልጣን ምንጭነት፣ የባህል ቋንቋቸው እኩልነት የሚረጋገጥበት፣ በሌላ በኩል ደግሞ ሁሉም የኢትዮጵያ ዜጎች በሁሉም የአገሪቱ አካባቢዎች ሙሉ መብቶች የሚከበሩበት፣ የሚረጋገጡበት መንትዮሽ ግብ ሊያጣጥም፣ ሊያስታርቅ የሚችሉ የመፍትሔ ሃሳቦች፣ ሌሎች መሰል አመራጮችንም ማፈላለግ የአገሪቱ የፓለቲካ ልሂቃንና የተደራጁ ኃይሎች በጥልቀት ሊያስቡበት የሚገባ አንገብጋቢና ከቀዳሚዎቹ የፓለቲካ ችግሮቻችን አንዱ ይመስለኛል።

    የ20ኛ ክፍለ ዘመን ታላቁ የሳይንስ ሊቅ አልበርት አንስታይን (Albert Einstein) ከእምሮዋዊ አቅምና እውቀት፣ የወደፊቱን የማለም ምናባዊ ኃይል የበለጠ ነው (“Imagination is more important than knowledge”) እንዳለው ወቅቱ እውቀት አለን የምትሉ ልሂቃን ምናባዊ አቅማችሁን በመጠቀም የሀገራችንን የፓለቲካ ችግሮችና ተግዳሮቶች በውይይት፣ በድርድር፣ ለመፍታት ማሰብን በረጅሙ ማለምን ይጠይቃችሁሃል። ፓለቲካ የዕድሎች ጥበብ (“politics is the art of the possible”) ጭምር ነው ይባላል። ይህ አሻግሮ ማየትን፣ ተግዳሮቶችን ወደ መልካም ዕድሎች፣ አደጋዎችን ወደ ጥሩ አጋጣሚዎች ለመለወጥ ምናባዊ እቅምን መጠቀምንም የሚጠይቅም ጭምር ስለሆነ ይመስለኛል። ዊኒስተን ቸርችል (Winston Churchill) ታላቅ ከመሆን ጋር ታላቅ ኃላፊነትነትም አብሮ ይመጣል፣ ትልቅ ዋጋም ያስከፍላል (“The price of greatness is responsibility”) እንዳለው የብሄርና የሕብረ ብሄር የፓለቲካ ልሂቃን የሀገራችን የፓለቲካ ኃይሎች ለሀገራዊ ሰላም፣ ለሕዝብ መረጋጋት፣ ለፍትሃዊ የፓለቲካ ሥርዓት ምሥረታ፣ እናንተም ትልቅ ለመሆን ለምትችሉበት፣ በርዕቱአዊ ነጻ ምርጫ አማራጭ የፓለቲካ ፕሮግራሞቻችሁን አቅርባችሁ ካሸነፋችሁ 105 ሚልዮን ሕዝብ ለመምራት ለምትችሉበት ዴሞክራሲያዊ የፓለቲካ ሥርዓት በጋራ መሥርቱ። ቆምንለት ለምትሉት ብሄር/ብሄረሰብም ደኅነትና ሰላም፣ ጥቅምና መብቶች፣ እንዲሁ ለመላው ሕዝብ፣ ለሁሉም ኢትዮጵያውን ዜጎች፣ ለሁላችንም የጋራ ሀገር በታላቅ ኃላፊነት መንገድ ለመንቀሳቀስ መወሰን ብልህነትና አስተውሎት ነው። በታሪክ ፊት፣ በሕግም ፊት፣ በህሊናችሁም ተጠያቂ አያደርጋችሁም። በሰማይም እንዲሁ። ሀገር ከሌለ፣ ሀገር ውስጥ ሰላም መረጋጋት ከጠፉ ስልጣንም፣ ጥቅምም፣ ታላቅነትም፣ ማንም ምንም የሚያገኝበት ሁኔታ ሊኖር እንደማይችል፣ ሁሉም ሊጠፋፋ የሚችልበት ሀገራዊ ትርምስ ውስጥ እንደ ዋዛ ፈዛዛ ሊገባ እንደሚቻል በዛሬ ዘመን የተወለዱ የሊቢያን፣ የሶርያን፣ የመንን ሕዝቦች መከራና ስቆቃ እያዩ ያደጉ ታዳጊ ወጣቶች እንኳን የሚገነዘቡት እውነታ ነው።

    ሀገራችን ኢትዮጵያ የምትገኝበት አጠቃላይ ሁኔታ እጅግ እንደሚያሳስበው እንድ ኢትዮጵያዊ ዜጋ፣ ሰሞኑን በተከሰተው የንጹሃን ዜጎቻችን ሕይወት መቀጠፍ፣ መቁሰልና መፈናቀል እንደሚያሳዝነው አንድ ሰብዓዊ ፍጡር፣ ለአማራ ወይንም ለኦሮሞ ብቻ ሳይሆን ለሁሉም የቋንቋና የባሕል ማኅበረሰቦች፣ ዜጎች በፍትህ፣ በሕግ የበላይነት፣ በማኅበራዊ ፍትህ፣ በዴሞክራሲ ፌደራላዊ የፓለቲካ ሥርዓት የሚኖሩባት ኢትዮጵያ እውን እንድትሆን የበኩሉን አስተዋጽኦና ትግል እንዳደረገ አንድ ኢትዮጵያዊ ዜጋ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ዶ/ር አብይ አህመድ፣ ለምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንንለአቶ ለማ መገርሳለአቶ ገዱ አንዳርጋቸው፣ ሌሎችም ለውጡን የመሩና በመምራት ላይ የሚገኙ የኢህአዴግ አመራሮች ይህን ጉዳይ በጥብቅ እንዲያስቡበት ከሀገሪቱ ልዩ ልዩ ባለድርሻ አካላት፣ የብሔርም/ዘውግም፣ የሕብረ ብሔራዊ የፓለቲካ አመለካከትና ፕሮግራም ያላቸው ልሂቃንና ተጽዕኖ ፈጣሪ ባለድርሻዎች ሁሉ በአግባቡ የሚሳተፉበት ብሔራዊ የውይይት፣ የምክክር መድረኮች ማመቻቸት ሰዓቱ የደረሰ ይመስለኛል። መግባባትና እርቅ የሚደረስበት፣ እንዲሁም ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ሊያራምዱ የሚችል ፍኖተ ካርታ በሁሉም ባለድርሻዎች ተሳትፎ ወደ ስምምነት የሚያደርሱ መድረኮች የማመቻቸት ሂደት እንዲጀመር የግሌን ሃሳብ እንደ እንድ ኢትዮጵያዊ ለማቅረብ እወዳለሁ።

    የሀገራችንን ችግሮችና ወቅታዊ ሁኔታ በሚመለከት በማዘጋጀት ላይ ያለሁትን የግሌን ሰፋ ያለ ምልከታ በቀጣይ አቀርባለሁ። ፍትህ፣ ሰላም፣ የሕግ የበላይነት፣ የሕዝብና የሀገርን ጥቅም ማስቀደም በሀገራችን እንዲሰፍን፣ መቻቻልና አብሮ መኖር እንዲለመልም ቸሩ አምላክ ይርዳን!!

    ነአምን ዘለቀ
    ቨርጂኒያ፡ አሜሪካ

    ሀገራችን ኢትዮጵያ ያለችበት የፓለቲካ ቀውስ የሚያሳስበው ሁሉ ሊያነበው የሚገባ

    Anonymous
    Inactive

    አክሱም ዩኒቨርሲቲ ኤርትራዊያን ተማሪዎችን አስመረቀ
    —–

    አክሱም ዩኒቨርሲቲ ኤርትራዊያን ተማሪዎችን አስመረቀ። ዩኒቨርሲቲው ዛሬ ያስመረቃቸው 14 ኤርትራዊያን በመጀመሪ ዲግሪ ያሰለጠናቸውን ናቸው። አስተያየታቸውን ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) የሰጡ ኤርትራዊያን ተመራቂዎች እንዳሉት በቀጣይ የሁለቱን ሀገራት የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት ለማጠናከር ኃላፊነታቸውን ይወጣሉ።

    በፓለቲካ ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ትምህርት የተመረቀው ዮናስ አሸብር እንዳለው የሁለቱ ሀገራት የሕዝብ ለሕህዝብ ግንኙነት ብዙ ዓመታት ያስቆጠረ ነው።

    ሀገራቱ በመካከላቸው ተፈጥሮ በነበረው አለመግባባት ከ20 ዓመታት መለያየት በኋላ ዳግም ግንኙነታቸውን ማደሳቸውን አስታውሶ፥ “በቀጣይ የሀገራቱን የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት ለማጠናከር ድልድይ ሆነን እንሠራለን” ብለዋል።

    ከዩኒቨርሲቲው በቢዝነስ ማኔጅመንት የተመረቀው ዮሐንስ ጉዕሽ በበኩሉ፥ በኢትዮጰያ መንግስት የትምህርት ዕድል በማግኘቱ ደስታ እንደተሰማው ገልጾ “የጋራ ባህልና እሴት ያላቸው የኢትዮጰያና የኤርትራን ህዝቦችን ማለያየት አይቻልም” ብሏል።

    በቀጣይም የሁሉቱ ሀገራት የጋራ ልማትና ተጠቃሚነት ለማሰቀጠል የበኩልን እንደሚወጣ ተናግሯል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ

    Semonegna
    Keymaster

    ማለቂያ የሌላቸው ብዙ ብዙ የውሽት ትርክቶች ሰፊውን የአማራ ሕዝብ ጥቅምም ሆነ ኢትዮጵያን እንደ ሀገር ለማስቀጠል ፈጽሞ የማይበጅ፣ እንዲያውም በአማራው ክልልም ሆነ በበርካታ አካባቢዎች በጎጥና በአካባቢም ጭምር ወርዶ የእርስ በእርስ ግጭቶች ሊወልድ የሚችል አደጋ ያዘለ ሁኔታ እያደገ መሆኑን የሰሞኑ ክስተት ያመላክታል።

    ኢትዮጵያ ሀገራችንን ከጥፋትና ከእልቂት ለማዳን ቆም ብለን በሰከነ ሁኔታ ማሰብና መራመድ እጅግ አስፈላጊና ወሳኝ ጊዜ ላይ እንገኛለን።
    (ነአምን ዘለቀ)

    የአማራ መሰረት ያላችሁ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ፣ ኢትዮጵያውያን ወገኖቼ ሁሉ፥

    ዛሬ ከፊታችን ያፈጠጠው መሰረታዊ ጥያቄ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድን እንደግፍ ወይንም አንደግፍ የሚለው አይደለም። የዛሬው ማዕከላዊ ጥያቄ፣ የዛሬው ዋና ጥያቄ ‘ኢትዮጵያ እንደ ሀገር ትቀጥል ወይንስ አትቀጥል’ የሚለው ነው። አብይ መጣ፣ ከበደ፣ ዋቅጅራ፣ ወይንም ግደይ፣ እቺ ታሪካዊት ሀገር፣ እቺ መከረኛ ሀገር፣ እትብታችን የተቀበረባት፣ የምንወዳት፣ ሌት ተቀን የምንጨነቅላት ኢትዮጵያ ሀገራችን፣ በተማሩ ልጆቹ በተደጋጋሚ የተከዳና የተበደለ፣ በድህነትና በችጋር የሚማቅቀው፣ ነገር ግን ጨዋና ኩሩ የሆነው እብዛኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ አብሮነት እንዴት ይቀጥል ነው ዋናው፣ መሰረታዊው፣ ማዕከላዊው ጥያቄ፣ የዛሬው ጥያቄ፣ የአሁን ሰዓት ዋነኛ ጥያቄ ይሄው ነው።

    ሰሞኑን “ኣማራው ተጠቃ፣ ተበደለ፣ ተገፋ” በሚል ሽፋን፣ በአብይ አህመድ “የኦሮሞ/ የኦዴፓን የበላይነት” ለመጫን እየሠራ የሚገኝ የትሮጃን ፈረስ ተደርጎ በሰፊው የሚነዛው ጥላቻ፣ የሚረጨው ሰፊ መርዝና ቅስቀሳ ሰፊው የአማራ ሕዝብን ጥቅም (በአማራው ክልል ብቻ ሳይሆን በኦጋዴን፣ በሀረር፣ በባሌ፣ በአርሲ፣ በኢሉባቡር፣ በወለጋ፣ ወዘተ… በሌሎች አካባቢዎች የሚገኘውን ከ10 ሚሊዮን በላይ አማራኛ ተናጋሪ ማኅበረሰብ) የአማራውን ሕዝብ ደህንነትና ዋስትና ለማረጋገጥ ምን ያህል እንደሚጠቅም፡ ህልውናውንም እንደምን አርጎ ለማረጋገጥ እንደሚያገለግል ቆም ብሎ የታሰበበት አለመሆኑ ግልጽ ነው።

    በትናንሽና ፍጹም የማይናበቡ፣ የጋራ ራእይ፣ የጋራ ስልት (strategy) በሌላቸው በየጎጡ የተደራጁና አማራን እንወክላለን በሚሉ እንደ አሸን የፈሉ ቡድኖች የሚደረገው ይሄው በጣም የከረረ ጥላቻ፣ ማለቂያ የሌላቸው ብዙ ብዙ የውሽት ትርክቶች ሰፊውን የአማራ ሕዝብ ጥቅምም ሆነ ኢትዮጵያን እንደ ሀገር ለማስቀጠል ፈጽሞ የማይበጅ፣ እንዲያውም በአማራው ክልልም ሆነ በበርካታ አካባቢዎች በጎጥና በአካባቢም ጭምር ወርዶ የእርስ በእርስ ግጭቶች ሊወልድ የሚችል አደጋ ያዘለ ሁኔታ እያደገ መሆኑን የሰሞኑ ክስተት ያመላክታል። ይህ ደግሞ የሶማሊያ፣ የሊቢያ፣ የሶሪያን እልቂትና መበታተን የሚደግም፣ የሚያስከነዳም የምድር ሲኦል እንደሚፈጥር በተረጋጋ አዕምሮ ልብ ያለው ሁሉ ልብ ሊል ይገባል።

    ይልቅዬ በዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ የአማራው ዘላቂ ጥቅም የሚጠበቅበት፣ የሁሉም ሕዝቦች አብሮነት የሚረጋገጥበት፣ የኢትዮጵያ እንድነት የምናስቀጥልበት ሁኔታዎችና መንገዶችን፣ ሰከን ብሎ ማሰብ፣ በስሜት ሳይሆን በስትሪቴጂያዊ አስተሳሰብ፣ በጥበብና በስልት፣ በጋራ፣ ሰጥቶ በመቀበል እንጂ፣ ሰሞኑን በሶሻል ሚዲያ እንደሚራገበው አማራውን እንወክላለን የሚሉ በልዩ ልዩ ቡድኖች የተደራጁም ያልተደራጁም አክራሪ ብሄርተኞች እጅግ በሚያጦዙት መንገድ ፈጽሞ ሊሆን እንደማይችል የሮኬት ሳይንስ አውቀት የማያስፈልገው ሃቅ ይመስለኛል።

    ሰደድ እሳቱ ሲጀመር እያንዳንዱ ቤት አንደሚያንኳኳ ቆም ብሎ ማሰብ፣ ከሌሎች ሀገሮች ውድመት፣ ውድቀትና፣ ምስቅልቅል መማር ሰዓቱ ከመድረሱ በፊት ቆም በሎ ማሰብ ብልህነት፣ አስተውሎትም ነው። ስለዚህ ሰላም፣ መረጋጋት፣ ማዕከላዊ መንግስት የተከፈተውን ምህዳር ተጠቅሞ በሰላማዊ፣ ሕጋዊ፣ ስልታዊና ስትራቴጅካዊ አካሄድ በሰላማዊና በተደራጀ መልክ የአማራውን ሕዝብ ጥቅም፣ ደኅንነት ለማሰጠበቅ መንቀሳቀስ እንጂ፥ የሰፈር የጦር አበጋዞች (በሶማሊያና በሊቢያ እንዳየነው “warlords”)፣ ከሕግና ከስርዓት ውጭ የራሳቸውን ፍላጎት በጉልበት ለመጫን የሚፈልጉ አፈንጋጮችን (በሶሪያ እንደተከሰተው “rogue military commanders”) በማጀገን የአማራውን ሕዝብ ተገፍቻለሁ፣ ተጠቅቻለሁ ብሎ እንዲነሳሳ ሰፊ ቅስቀሳ ማድረግ ታሪክ ይቅር የማይለው፣ የአማራውን ሕዝብንም ሆነ፣ የአማራው ማኅበረሰብ በደም፣ በሕይወቱ፣ በላቡ ገብሮ፣ ለግንባታዋ ብዙ የተዋደቀላት ትላቋና ታሪካዊቷ ኢትዮጵያን የማይበጅ፣ ወደ ጥፋት፣ ወደ እርስ በእርስ ጦርነት፣ አልፎም ወደ ውድመትና ወደ መበታተን ሊያደርሰን የሚችል ሂደት እየተመለከትን ነው።

    በዚህ ሁሉ ትርምስ ደግሞ ዛሬ የሚፈነጥዘው፣ ይህን ሰፊ ትርምስ (turmoil) ለራሱ በሚገባ እየተጠቀመ የሚገኘው፥ እንደ አንድ ሰው የቆመው፣ እስከ አፍንጫው የታጠቀውም ሕዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ (ሕወሃት) ብቻ ነው። ሌላው ተከፋፍሏል፣ በአብይ አህመድ ላይ በሚወርደው የጥላቻ ውርጅብኝም ሀገሪቷን እንደ ሙጫ አጣብቆ ደካማ ቢሆንም የያዘውን ስርዓተ መንግስት (state)፣ ማዕከላዊ መንግስቱንም ለማዳከም ብዙ የድንጋይ ናዳ አየወረደ ነው። በየዕለቱ በተደራጀም በአልተደራጀም መልኩ እየተደረገ የሚገኘው ይሄው ነው።

    ሕዝብን እርስ በእርስ ሊያባላ፣ ሊያጫርስ የሚችል፣ ምንም አማራጭ ሃሳብ፣ ራእይና፣ ድርጅትም ሆነ ስትራቴጂ ለማቅረብ የማይችሉ፣ ነገር ግን አማራውን እንወክላለን የሚሉ፣ እንዲሁም በአብይ አህመድ ላይ የግል ጥላቻና ጥርጣሬ ያላቸው በርካታ ግለሰቦችና ቡድኖች ጭምር ተሳታፊ የሆኑበት ይሄው በከፍተኛ ስሜት በማጦዝ፣ የተገፊነትን ስሜት በመቀስቀስ ላይ የተመሰረተ ሰፊ ዘመቻ ያነጣጠረውና እየሄደ ያለው በዚሁ ግብ ላይ ነው። የእነዚህ ቡድኖች ምንም መናበብም ሆነ፣ የጋራ አማራጭ፣ እንዲሁም ለሀገራችንና ለሕዝባችን አሻግሮ የሚያይ ራእይ ማቅረብ ያማይችሉ፣ እርስ በእርሳቸው እንኳን ተቀምጠው በአግባቡ በምክኒያታዊነት መነጋገርና መደማመጥ የማይችሉ፣ ግለሰቦች፣ ቡድኖችና ኃይሎች የሚገፋውና የሚረጨው መርዝ ሁሉንም (እነሱንም ጨምሮ) ወደ ፍጹማዊ ኪሳራ፣ የዜሮ ድምር ፓለቲካ (zero-sum game) የሚወስድ፣ ማንም ምንም ወደማያተርፍበት የሲኦል መንገድ አገራችንንና ሕዝባችንን እየገፋ መሆኑን ሁሉም ኢትዮጵያዊ ዛሬ ላይ በሚገባ መገንዘብ አስፈላጊ የሆነበት ወቅት ላይ የደረሰን ይመስለኛል። ነገ በጣም ይዘገያል የዘገየ (too little too late) ይሆናል።

    ከዚህ አሳፋሪና ለሀገራችን ህልውና ብሎም ለኢትዮጵያ 105 ሚሊዮን ሕዝብ አብሮነት፣ ለኢትዮጵያ አንድነት ቀጣይነት እጅግ አስጊ ሁኔታ በተፈጠረበት በአሁኑ ወቅት አሸናፊ የሚሆነው ማነው? ሁሉንስ ድልና ወርቅ አፋሽ የሚሆነው ማነው? ብቸኛ ተጠቃሚስ ይኖራል ወይ? በሰላም ደሴት በደስታና በፍሰሃ ሊኖር የሚችለውስ ማነው? ስለእውነት፡ ስለሀቅ ለመናገር ማንም እንደማይሆን፣ ማንም እንደማይተርፍ በእርግጠኝነት መተንበይ ይቻላል። ሁላችንም ተያይዘን ወደ እልቂት፣ ወደ ሁለንተናዊ ውድቀት፣ ወደ ሲኦል እያዘገምን ይመስለኛል።

    ስለዚህ ወግኖቼ፥ ቆም ብለን ማሰብ ብልህነት ነው። ነገን ማሰብ፣ በተረጋጋና በምክንያታዊነት ዛሬን በትዕግስትና በስልት መራመድ አሰፈላጊና ወሳኝም ናቸው። የአማራውንም ጥቅምና ደኅንነት፣ የሌላውን ኢትዮጵያዊ ማኅበረሰቦች/ብሄሮች፣ አብሮነት፣ የአማራውንም ሆነ የሌላውን እኩልነት፣ መብት፣ ደህንነት፣ ለማምጣት በጥንቃቄ፣ በሕግ አግባብ፣ በሰላማዊ መንገድ፣ አስቦ፣ በአስተውሎ መራመድ የነገን ውድመት፣ የሀገር መበታተን፣ የሕዝብንም እልቂት የሚከላከል ሁሉም ሕዝቦች በጋራ በሰላም፡ በዴሞክራሲ፣ በሕግ የበላይነት፡ በእኩልነት የሚኖሩባት ኢትዮጵያን የሚያረጋግጥልን ብቸኛ መንገድ መሆኑን ሁሉም ኢትዮጵያዊ ዜጋ፣ ሁሉም የአማራ መሰረት ያለው ኢትዮጵያዊ ሁሉ በውጭም በሀገር ውስጥም ሊያጤነው የሚገባ ይመስለኛል። የመጨረሻው ደወል እያቃጨለ መሆኑ እየተሰማኝ ነው። ኢትዮጵያ እንደ ሀገር፣ ሁሉም ሕዝቦች፣ ማኅበረስቦች፣ በእኩልነት፣ በፍትህ፣ በሕግ የበላይነት የሚኖርባት ኢትዮጵያን ሁሉም ኢትዮጵያዊ፣ የአማራ መሰረት ያለው ኢትዮጵያውያን ሁሉ በጥሞና አስበን፣ አስተውለን፣ አቅደን መንቀሳቀስና ሀገራችንን ከጥፋት የማዳኛው ወቅት አሁን ነው፣ ዛሬ ነው።

    እግዚአብሔር ሀገራችንና ሕዝባችንን ይጠብቅልን፤ ስላሙን ያውርድልን።
    ነአምን ዘለቀ

    የአማራ ሕዝብ


    Anonymous
    Inactive

    አቶ ነአምን ዘለቀ የኢሳት የሥራ አስፈጻሚ ቦርድ አባል በግላቸው የሰጡት መግለጫ

    ሶሻል ሚዲያ ላይ ለምትገኙ ኢትዮጵያውያን ሁሉ፦

    ኢሳትን በሚመለከት የውስጥ “መረጃ” በሚል በማኅበራዊ ሚዲያ የተሰራጩ ነገር ግን ከሃቁ፣ ከእወነታው ከሂደቱ የራቁ፣ ሕዝብን ለማወናበድ፣ ኢሳትንም ለማፍረስ ሆነ ተብሎ የተደረገ መሆኑ እንዲታወቅ እንወዳለን። የወጣው ስም ዝርዝር ከሀቁ የራቀ፣ መሰረተ ቢስ መሆኑን ለማሳወቅ እወዳለሁ።

    ማንኛውም ተቋም ገቢውን የሚያገኝበት ሁኔታ ሲለወጥ የማስተካከያ እርምጃዎች ይወስዳል። በእኔ በኩል ለአለፉት 4 ዓመታት አራት ሌሎች አባላት የሚገኙበት የኢሳት የሥራ አስፈጻሚ ቦርድ ሆነን ስንሠራ እንዳደረግነው ሁሉ ኢሳትን የሕዝብ ዓይንና ጆሮ ሆኖ እንዲቀጥል ለማድረግ የማዋቀርና የማስተካከል በርካታ እርምጃዎች ስንወስድ የቆየን ሲሆን አሁንም ተጨማሪና ተከታታይ እርምጃዎችን እንደሚወስድ በአፕሪል 18 ቀን 2019 (ሚያዝያ 10 ቀን 2011 ዓ.ም.) ለሕዝብና ለኢሳት ቤተስቦች ይፋ ማድረጉ ይታወሳል።

    በተጨማሪም ኢሳት ከለውጡ በፊት በነበረው አቅምና ሁኔታ ማስቀጠል እንደማይቻል ለኢሳት ባልደረቦች ስናሳስብና ለወራት ያህል ብዙ ዝርዝሮች የሚገኙበት ውይይቶች ስናደርግ ቆይተናል፤ መፍትሄዎችም ለማፈላለግ ብዙ ጊዜ በርካታ ስብሰባዎች ተደርገዋል። ካስፈለገ ሁሉንም ጉዳይ ከጅምሩ እስካሁን የነበረውን በተለያዩ ደረጃዎች የተደረጉትን ሁሉ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ይፋ ለማድረግ እንደሚቻል መታወቅ አለበት።

    ይህ “መረጃ” ተብዬ የወጣው ኢሳትን ለማፍረስ በዚህም ተጠቃሚ ለመሆን በታቀደ መልኩ ሆን ተብሎ የተሠራና ከዶ/ር ብርሃኑም ሆነ ዶ/ር አብይ አህመድ ጋር በመሆን የተወሰነ የፓለቲካ አስተሳሰብ ያላቸውን ለማጥቃት የታለመ እንደሆነም የተሰራጨው “መረጃ” መሰረተ-ቢስ መሆኑን ለኢትዮጵያ ሕዝብ ለማረጋገጥ እወዳለሁ።

    “ቅጥረኛ” በሚልም እኛን ለመወንጀል የደፈሩ ግለሰቦችም ሆነ “መረጃው”ን የሰጧቸው ሰዎች በዚህ ሸፍጥ የሚያሸንፉና ሕዝብን የሚያወናብዱ ከመሰላቸው ይህ እንደማይሳካላቸው፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ ማን ምን እንደነበር፣ ከየትስ እንደመጣ፣ መቼ ወደ ኢሳት እንደመጣ፣ ማንስ እንዳመጣው፣ እኛም ምን እንዳደረግን፣ ከየት ወዴት እንደተጓዝን፣ ሁሉንም እስካሁን ድረስ የተደረገውን ጉዞ ከማስረጃና ከሰነዶች ጋር ለማቅረብ ስለሚቻል ሕሊናቸውን እንዲመረምሩና ከዚህ የአደባባይ ነውር ቢታቀቡ የተሻለው መንገድ ነው በማለት በግሌ ሁሉንም ለማሳሰብ እወዳለሁ።

    እዩኝ፣ እዩን ስለተባለ ብቻ “እኛ ብቻ ጋር ሀቅም፣ እውነትም፣ የትግል ባለቤትነትም፣ ዕውቀትም፣ አልፎሞ አሁን ደግሞ ኢሳትም ‘የእኔ’ ብቻ ነው” ባዩ የበዛበት ዘመን ላይ ስለሆንን፣ ነውር ውስጥ እየገቡ እኛን ምላሽ እንድንሰጥ፣ ህዝብም እንዲያዝን የሚያስገድዱን ማናቸውም ወገኖች ሁሉ በድጋሚ፣ ባለፈው እንደሆነው ስም ወደማንሳትና ጭቃ መወራወር እንደተገባው እንዳይሆን በጥብቅ ለማሳሰብ በግሌ እወዳለሁ።

    እውነት ያወጣሀል እንደሚባለው ሃቁን፣ ሂደቱን፣ እውነቱን በዝርዝር ለማውጣት ምንም የምንቸገርበት፣ የምናፍረበትም፣ ለማንም ለምንም ኣንደማንመለስ፣ እንደ አንዳንዶች “ቅጥረኛ’ ሳንሆን 26 ዓመታት ለኢትዮጵያ ህዝብ ፍትህን፣ ነጻነት፣ ለማምጣት ሁለንተናዊ ትግል ያደረግን፣ ሁሉንም ነጋራችንን የሰጠን፣ ከማንም ምንም የማንፈልግ ግለሰቦች እንደምንገኝበት ለህሊናችን ያደርንና ይህንኑ ይዘን እስከ ዕለተ ሞታችን እንደምንቀጥልም ሆዳቸው የሚያውቁ፣ ነገር ግን ይህን ርካሽ ተግባር የትም የማያደርሳቸው ግለሰቦች እንዲያስቡበት፣ ወደ ህሊናቸው እንዲመለሱ በግሌ በጥብቅ ለማሳሰብ እወዳለሁ። ለሁሉም ጎራ ስናሳስብ፣ በግልም፣ በቡድንም፣ በአደባባይ ስም ሳይጠቀስም ለሁለት ሳምንታት እንደተጻፈውና ፣ ለበርካታ ወራት ኢሳት ውስጥ የተፈጠሩ ችግሮችን ለመፍታት ጥረት ስናደርግ እንደከረምነው።

    አቶ ነአምን ዘለቀ የኢሳት የሥራ አስፈጻሚ ቦርድ አባል (በግል)

    Semonegna
    Keymaster

    ከኢሳት (ESAT TV) የሥራ አስፈጻሚ ቦርድ የተሰጠ መግለጫ

    ጉዳዩ፦የኢሳትን (ESAT TV) መዋቅርና አሠራር ማስተካከልን ይመለከታል

    ጊዜው ኢሳትን የመሰሉ የኢትዮጵያዊነትና የዲሞክራሲ ድምጾችን አገራችን ኢትዮጵያ ከመቼውም ጊዜ በላይ የምትፈልግበት ነው። ኢሳትም (ESAT TV) ለዚህ አገራዊ ጥሪ መልስ ለመስጠት በአገር ውስጥም ሆነ ከአገር ውጭ ተጠናክሮ ለመሥራት ቃል መግባቱን በድጋሚ ለማስታወስ እንፈልጋለን።

    የኢሳት ቦርድ (ESAT TV Executive Board) ባለፈው ኤፕሪል ወር (April 2019) ውስጥ ይህንን ጥሪ በወጉ ለመመለስ በስድስት አስፈላጊ የሆኑ ኢሳትን የማጠናከሪያና የማሻሻያ አቅጣጫዎች ከተቋሙ ሠራተኛና የድጋፍ ኮሚቴ ተወካዮች ጋር በመመካር መወሰን እንደሚጀመር አስታውቆ ነበር። በዚህ መሰረት ሜይ 28፣ 2019 (ግንቦት 20 ቀን 2011 ዓ.ም.) ቦርዱ ከመላው ዓለም አቀፍ የኢሳት ባልደረቦች ጋር በመሰብሰብ የመጀመሪያውን ውሳኔ ይፋ አድርጓል።

    ይህ ውሳኔ ያተኮረው ኢሳት ኢንተርናሽናልን በባጀት፣ በሰው ኃይል፣ በፕሮግራሞች ይዘትና አቅጣጫዎች እንዲሁም በአስተዳደር አቅም ከዘላቂነት ጋር እንዲጣጣም ማድረግን ይመለከታል። ውሳኔው እንደማንኛውም ተቋማዊ የመዋቅር የማስተካከያ እርምጃ ጊዜያዊ ችግሮችን ሊፈጥር ቢችልም በዘላቂነት ግን ኢሳትን (ESAT TV) በሁሉም ዘርፍ አቅሙንና ሕዝባዊነቱን በማጠናከር የተመሰረበትን መሰረታዊ ዓላማ እውን ማድረግ ነው።

    ይህንን መሰረተ ሃሳብ በደንብ ተገነዘቦ በሚሠራ የኢሳት አስተዳደርና ባለሙያዎች የተወሰነን ውሳኔ የፖለቲካ ፉክክር ጨዋታ ውስጥ እያስገቡ መተርጎም ትክክል አይሆንም። ይህ ውሳኔ በማህበራዊ ሚዲያ ላይ ሰሞኑን እንደሚወራው በኢሳት ውስጥ ያሉ የጋዜጠኞች የሃሳብ ልዩነቶች ጋር የተያያዘ አይደለም። ኢሳት የፖለቲካ ፓርቲ አይደለም። በባለሙያዎቹ ውስጥ እንደማንኛችንም የህብረተሰብ አባላት የተለያየ የግል እምነትና የፓለቲካ አመለካከቶች እንደሚንጸባረቁ ግልጽ ነው። ሆኖም እንደ ሚዲያ ተቋም የኢሳት ሚና የመንግሥትን ወይም የማንንም አንድ ወገን ፍላጎትን መቃወም ወይም መደገፍ ሳይሆን ሙያዊ ብቃት ያለው አስተማማኝና የተጣራ መረጃ የሚያቀርብ የህዝብ ሚዲያ ሆና ማገልገል ነው።

    የኢሳት ግብ በነጻነት፣ በሙያዊ የጋዜጠኝነት ሥነ-ምግባር፣ እንዲሁም በሕዝባዊ ዓላማ ላይ ተመስርቶ የሚዲያ ምርቶችን በማምረት፡ በፓለቲካዊ፣ በኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊና፣ ባህላዊ ርዕሰ ጉዳዮች እንዲሁም የተጣሩ መረጃዎች በማቅረብ ሕዝብን ማገለገል ነው። በተለይ አሁን ሀገራችን ባለችበት ሁኔታ ደግሞ የኢትዮጵያን ሕዝብ አንድነት ማበረታታት፣ የሀገሪቱም ችግሮችና ተግዳሮቶች በዲሞክራሲያዊ መንገድና በውይይት የመፍታትን ባህል እንዲስፋፋ መርዳት ነው።

    ይህንን መሰረተ ሃሳብ በደንብ ተገነዘቦ በሚሠራ የኢሳት አስተዳደርና ባለሙያዎች የተወሰነን ውሳኔ የፖለቲካ ፉክክር ጨዋታ ውስጥ እያስገቡ መተርጎም ትክክል አይሆንም። ዛሬ የተጀመረው የኢሳት ማጠናከሪያ በቅርቡም በቦርድ፣ በአስተዳደር፣ በኤዲቶሪያልና በአጠቃላይ የኢሳት አሠራር ላይ ይቀጥላል። ኢሳት በመጀመሪያ የሥራ ምዕራፉ ማለትም በሀገራችን ከ 27 ዓመታት በላይ የተሰራፋውን አፋኝና ዘረኛ ስርዓት በማስወገድ ሂደት ያበረከተውን አስተዋጽኦ በሚቀጥለውም የሀገርና የሕዝብ አንድነትና የዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ሥራ ምዕራፍ ውስጥም እንደሚቀጥል ጥርጥር የለንም። ለዚህም የኢሳት ቤተስቦችና የድጋፍ ኮሚቴዎች እንደወትሮው ኢሳት የህዝን ዓይንና ጆሮ ሆና እንዲቀጥል የበኩላችሁን እንድታደረጉ ትብብራችሁን በአክብሮት እንጠይቃለን።

    ጁን 1 ቀን፣ 2019 (ግንቦት 24 ቀን 2011 ዓ.ም.)፣ ዋሺንግተን ዲሲ
    የኢሳት (ESAT TV) ቦርድ ሥራ አስፈጻሚ
    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ኢሳት (ESAT TV)


    Semonegna
    Keymaster

    ከዴሞክራሲና ከነጻነት ጋር የተቆራኙ እሴቶች
    (ነአምን ዘለቀ)

    ከዴሞክራሲና ከነጻነት መብቶች ጋር ተያያዥነት ያላቸው እሴቶችና ከእነዚህ ጋር የተገናኙ ንድፈ ሃሳቦች ከፍልስፍና አኳያ መነሻቸው አንዱ የሰው ልጅ ክቡርነትና የግለሰብ ሉዓላዊነት መከበር ጋር የተጋመዱና የተያያዙ መሆናቸው ነው። ዴሞክራሲም ሆነ ነጻነት የሰው ልጆችን ክብር፣ የእያንዳንዱን ሰው ሰብዓዊ ክቡርነት (dignity) ከልብ ካልተቀበለ፣ አንዱ ሌላውን ሰው እንደመጠቀሚያ፣ ለአንድ ግብ ማስፈጸሚያ መሣሪያ (means to an end/instrument) የሚመለከት ከሆነ፥ ለምሳሌ በፓለቲካም ሆነ በሌላ “እገሌን ለዚህ ጉዳይ ተጠቀምኩበት” እንደሚባለው ከሆነ ስር የሰደደ የእሳቤው፣ የእሴቶች፣ እንዲሁም የፍልስፍናው ግንዛቤ ላይ ከፍተኛ እጥረት አለ ማለት ነው። ይህንንም በጥልቀት በንድፈ ሃሳብ (theory)፣ እንዲሁም በጽንሰ ሃሳብ (concept) ደረጃ በጥልቀት ማወቅ ቢቻልም፣ ከልባችን ጋር አልተዋሃደም (internalized አልሆነም) ማለት ነው።

    ሰዎችን የግብ ማስፈጸሚያ አድርጎ ማየት ብዙ ጊዜ የግራም ሆነ የቀኝ ርዕዮትን ያነገቡ በጣም ጨካኝና ጠቅላይ ከሆኑ (totalitarian) ርዕዮቶች/ፍልስፍናዎች ፣ የነዚህ ውላጅ ከሆኑ የፓለቲካ ስርዓቶችም የሚመነጭ ነው። በምዕራባውያኑ ዘንድ በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ላይ በሰፊው የተጻፈበትና ልዩ ልዩ አመለካከቶች ያሉ ቢሆንም ከሊበራሊዝም አኳያ በርሊን፣ ከፕራግማቲዝም ሪቻርድ ሮርቲ (Richard Rorty)፣ ከሰብዓዊነት ላይ የተመሠረተ የማርክሳዊ ፍልስፍና አመለካከቶች እንደ ኤሪክ ፍሮም (Erich Fromm) እንዲሁም ሌሎችም ፈላስፎችና ሃያሲዎች የእነዚህ ጠቅላይ ርዮተ ዓለሞች ቅድመ መነሻ/መሠረት ከጥንታዊ ግሪክ ከፕሌቶ ፍልስፍና መሆኑን ተንትነውበታል። ነገር ግን የምዕራባዊ ስልጣኔና አካል ባልሆኑ፣ የእኛንም ማኅበረሰብ ጨምሮ ይህ አመለካከት በቅድመ ዘመናይ (pre-modern) ስርዓተ መንግሥታት የፓለቲካ፣ የባህልና ፣ ማኅበራዊ ግንኙነቶች ውስጥም ሰፍኖ የነበረ መሆኑ ግልጽ ነው።

    በርካታና እጅግ አንገብጋቢ ሃገራዊ ጉዳዮች ቢኖሩም ቅሉ፣ አንዱ የችግሮቻችን ምንጭ ከአስተሳሰብ ጋር፣ ከአመለካከቶች ጋር የተያያዙ ጎጂ የአስተሳሰቦችና እሴቶች (values) መሆናቸው ቀላል ግምት የሚሰጠው አይደለም። የሰው ልጅ ውስብስብ ፍላጎቶች ያለን ፍጥረቶች ነንና ወደ ውስጥ መመልከትና የትኛው ፍላጎት ለምን አላማ የሚለውን ራስን መሞገት ወደ ተሻለ በበጎ የሞራል እሴቶች ላይ የተመሠረተ የፓለቲካ ማኅበረሰብ ለማጠናከር የራሱ አስተዋጽኦ ያደርጋል። የፓለቲካ ጉዳይ ከስልጣን ጋር የተያያዘ መሆንና፣ በዴሞክራሲም ሆነ ዴሞክራሲያዊ ባልሆኑ የፓለቲካ ስርዓቶች ውስጥ ስልጣን (power) የሰው ልጆችን ‘ኮራፕት’ [corrupt] (በጥቅም ብቻ ሳይሆን ስልጣን ላይ ያሉትንም ሆነ ወደ ስልጣን የሚመጡትን ሰዎች የሞራል እሴቶን በማዳከም ጭምር) የማድረግ አቅሙ በጣም ከፍተኛ መሆኑ ቢታወቅም፥ ፍትህ፣ ዴሞክራሲና ነጻነት በሀገራችን እንዲመጣ ከልብ ከተፈለገ ደግሞ ከነዚህ ዓይነት አመለካከቶች ለመጽዳት መሞከር አንዱ የቤት ሥራ መሆን አለበት ማለት ነው።

    የሰውን ልጅ ክቡርነት (dignity) ከልብ ማመን፣ ይህ እሴት እንዲዋሀደን ማድረግ፣ ለዲሞክራሲያዊ ባህል መስፈን፣ ፍትሃዊና ሰብአዊነት የነገሰበት ስርዓት እውን እንዲሆን ለማድረግ በጣም ወሳኝ ከሆኑ እሴቶች አንዱና ዋነኛው ነው። ቅዱሳን መጻህፍትም የሚሉት ‘በአንተ ላይ ሊደረግ የማትፈልገውን በሌላው ሰው ላይ አታድርግ’ ይመስለኛል። ፓለቲካው በርካታና አስፈላጊ የሞራልና የስነ-ምግባር እሴቶች ያስፈልጉታል የሚለው ዋናው ጭብጥ ነው – በተለይ በፓለቲካ ልሂቃን (political elites)። በቀጣይነት ተያያዥነት ያላቸው ጉዳዮች ይኖራሉ። በቸር ይግጠመን።

    አቶ ነአምን ዘለቀን ፌስቡክ ገጻቸው ላይ ይከተሏቸው (Like ያድርጓቸው)፦ Neamin Zeleke
    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ከዴሞክራሲ እና ከነጻነት ጋር የተቆራኙ እሴቶች


    Semonegna
    Keymaster

    ግልጽ ደብዳቤ ለኢትዮጵያ ሕዝብ በአቶ ነአምን ዘለቀ ― አቶ ነአምን ዘለቀ ራሳቸውን ከአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ አገለሉ
    ———

    ለአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ አባላት፣ የሠራዊት አባላት፣ ደጋፊዎችና፣ በልዩ ልዩ መደረኮች ለምታውቁኝ ኢትዮጵያውያን በሙሉ፦

    በሀገራችን የመጣውን ለውጥ ተከትሎ የአርበኞች ግንቦት 7 የዴሞክራሲና የአንድነት ንቅናቄ (አግ7) አመራር አባላት እ.ኤ.አ. በሀምሌ (July) ወር 2018 በአሜሪካን ሀገር ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) ጋር በተደረገ ስብሰባ ላይ ከተደረሱት የስምምነት ነጥቦች መካከል አንዱ የአግ7 ንቅናቄ ሠራዊት ከኤርትራ በርሃና ከሀገር ውስጥም የነበሩት የአግ7 ታጣቂዎች ወደ ሀገር ወደ ሰላማዊ ኑሮ መመለስና ማቋቋምን የሚመለከት ነበር። በዚህም መሠረት በኤርትራ የነበሩ የንቅናቄው ሠራዊት አባላት እንዲሁም በየበረሃው የነበሩ የንቅናቄው ታጣቂዎች ወደ ልዩ ልዩ ካምፖች በየጊዜው እንዲገቡ መደረጉ ይታወቃል። በብዙ መቶ የሚቆጠሩ የንቅናቄው አባላትም ከልዩ ልዩ እስር ቤቶች ቀደም ሲል በተከታታይም እንደተለቀቁ ይታወቃል። በኃላፊነት ስመራ በቆየሁት በውጪው ዘርፍ ስር የማኅበራዊ ፈንድ ኮሚቴ እንዲቋቋም በማድረግ በውጭው ዓለም በሚገኙ በንቅናቄው አባላት፣ በደጋፊዎች፣ እንዲሁም አገር ወዳዶች ትብብር መጠነ ሰፊ ገንዘብ በማሰባሰብ በየእስር ቤቱ የነበሩት ተጋዮች ለሦስት ተከታታይ ወራት እንዲረዱ እንዲሁም ከኤርትራ በረሃ ለመጡትና በካምፕና ከካምፕ ውጭ ለሚገኙትም በልዩ ልዩ መንገዶች እርዳታዎች እንዲያገኙ ለማድረግ ተችሏል።

    ከኤርትራ በረሃ ወደ አገር ቤት እንዲገቡ የተደረጉትን የአርበኞች ግንቦት 7 የቀድሞ ታጣቂዎች እንዲሁም የሌሎች የፓለቲካ ድርጅቶች ታጣቂዎችን መልሶ የማቋቋሚያ ፕሮጄክት ጽ/ቤት በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት ስር ከ7 ወራት በፊት የተመሠረተ ሲሆን፥ የውጭ መንግስታትም በተለይም የጀርመን መንግስት ለዚሁ የሚውል ገንዘብ ለመስጠት ከበርካታ ወራት በፊት ተስማምተው ነበር። ሆኖም ከተቋቋመው ጽ/ቤት አቅም ማነስ እንዲሁም ጉዳዩ ተገቢውን ውሳኔዎች ሳያገኝ እየተጓተተ በመቆየቱ ሳቢያ የአርበኞች ግንቦት 7 ሠራዊት አባላት (በተለይም ከካምፕ ውጪ እንዲቆዩ ተደርገው መልሶ የማቋቋሚያ ድጋፍ እንዲጠብቁ የተነገራቸው ጭምር) ለከፍተኛ ችግር መዳረጋቸው ለህሊና እረፍት በሚነሳ ሁኔታ ውስጥ እራሴን አግኝቼ ነበር።

    የንቅናቄው ሊቀመንበር ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ እንዲሁም ዋና ጸሃፊ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ችግሩ መፍትሄ እንዲያገኝ በየጊዜው ከጠቅላይ ሚንስትሩና ከሌሎች የመንግስት ኃላፊዎች ጋር የሚያደርጉት ግንኙነትና ክትትል እንደተጠበቀ ሆኖ፤ በችግር ላይ የነበሩ የሠራዊት አባላት ሁኔታ አየተደራረበ የጭንቀት ድምጾች እየተበራከቱ በመምጣታቸው፣ ይህ ጉዳይ የንቅናቄውን ሊቀመንበርና ዋና ጸሐፊውን ብቻ የሚመለከት ሳይሆን አባላትና ሠራዊቱ የመረጡን የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላትን በሙሉ በተናጠልም ሆነ በጋራ የሚያስጠይቅ፣ ለሠራዊቱም ሆነ ለአባላት ኃላፊነት አለብን በሚል መንፈስ ይህ ለውጡን ለሚመራው መንግስትም የጸጥታና የፓለቲካ ችግር የሚፈጥር ሁኔታ፣ ከሞራልም ሆነ ከፓለቲካ እኳያ የንቅናቄውንም ውስጣዊ ጤንነት እየተፈታተነ የነበረ ትልቅ ችግር እየሆነ በመምጣቱ፣ ለችግሩ አፋጣኝ መፍትሄ እንዲሰጥ እርዳታ ለመስጠት ቃል ከገቡና ለመርዳት ፈቃደኛ ከሁኑ መንግስታት በተለይም ከጀርመን አምባሳደር፣ ከስዊድን መንግስት ኃላፊዎችና የፓርላማ አባላት፣ ከልዩ ልዩ የመንግስት ኃላፊዎችና ከመንግስት መዋቅር ውጭ የሚገኙ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሚቀርቡ ግለሰቦች ጋር በመገናኘት ለማስረዳትና መፍትሄ እንዲያገኝ የበኩሌን አስተዋጽዖ ለማድረግ ጥረቶች ሳደርግ ቆይቻለሁ።

    ብዙ ዝርዝሮች ያሉትና ወራት ያስቆጠረ ሂደት ቢሆንም፣ በዚህ አጋጣሚ ለዚህ ችግር መፍትሄ በማፈላለግ ሊያዳምጡን በራቸውን ለከፈቱ የልዩ ልዩ የመንግስት ተቋማት ኃላፊዎች፣ በተለይም የብሄራዊ አደጋና መከላከል ኮሚሽነር ምትኩ ካሳ፣ አምባሳደር ብርቱካን አያኖ፣ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት አማካሪ አምባሳደር ግርማ ብሩ፣ ጠቅላይ አቃቤ ሕግ አቶ ብርሃኑ ጸጋዬ፣ እንዲሁም ከመንግስት መዋቅር ውጭ ያሉና ከለውጡ በኋላ ከጠቅላይ ሚንስትሩ ሊያገኙን እንደሚፈልጉ በላለቤቴ በኩል መልክት የላኩብኝ የጠቅላይ ሚኒስሩ የአርቅ ኮሚቴ አባል አቶ ብርሃን ተድላ፣ በበርካታ የሕዝብና የሀገር ጉዳዮች ያላሰለሰ አስተዋጽኦ የሚያደርጉትና የረጅም ጊዜ ወዳጄ ለሆኑት ዶ/ር አምባሳደር ካሳ ከበደ፣ በጉዳዩ ላይ ትኩረት ሰጥተው ለመርዳት ለተንቀሳቀሱት፣ በእርዳታና በመልሶ ማቋቋም ከፍተኛ ልምድና ዕውቀት ያላቸው ለሻለቃ ዳዊት ወልደ ጊዮርጊስ፣ እንዲሁም ለመለሶ ማቋቋም የተቋቋመው መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ኣፍሪድ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ቴዎድሮስ ይልማ፣ ሌሎችም ለችግሩ መፍሄ ለማግኘት ያገኘኋቸውን ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ሁሉ እስከአሁኑ ቀን ድረስ ለከፍተኛ ችግር ተዳርገው በሚገኙት የሠራዊት አባላት ስም ምስጋና ሳላቀርብ አላልፍም፡፡ በአንጻሩ ደግሞ ትላንት ከለውጡ በፊት እንኳን እነሱን ደጅ ልንጠና ቀርቶ አጠገባቸው ለመድረስ እንኳን የምንጸየፋቸው፣ የተቀመጡበት የኃላፊነትና የአማካሪነት ቦታ የሀገርና የህዝብ ችግሮች ለመፍታት መሆኑ እምብዛም የሚያስጨንቃቸው የማይመስሉ፣ ራሳቸውን የኮፈሱ አድርባዮች፣ ከንቱና ግብዝ የመንግስት ባለሟሎች በዚህ ሂደት ለመታዘብ ችያለሁ።

    የሆነ ሆነ ይህ ከፍተኛ ችግር መፍትሄ እንዲያገኝና በውጭ የሚገኙትም ሆኑ በካምፕ ውስጥ የሚገኙት የንቅናቄያችን ሠራዊት አባላት ቢያንስ አቅም ባለው፣ ሠራዊቱ የሚገኝበትን ችግር ለማቃለል ብቃትና ተቋማዊ ቁመና ለዓመታት ባካበተ የመንግስት ኮሚሽን በኩል እንዲሆን የሚያስችል እርምጃ እንዲወሰድ በቅርብ ቀን መወሰኑን አዲስ አበባ በነበሩኩባቸው አራት ሳምንታት ከሚመለከታቸው የመንግስት ኃላፊዎች ጋር በተደረገ ውይይት አረጋግጫለሁ። ይህም እርምጃ ለወራት የቆየን ከባድ የህሊና ሸክም ያቃለለ ቢሆንም፣ አሁንም ከካምፕ ውጭ የሚገኙ የሠራዊቱ አባላት የሚገኙበትን ዘርፈ ብዙ ማኅበራዊ ችግሮች አስመልክቶ በየዕለቱ በርካታ መረጃዎች እየደረሰን በመሆኑ ከካምፕ ውጭም ሆነ ከካምፕ ውስጥ የሠራዊቱ አባላት ቃል የተገባላቸው እርዳታ እንዲደርሳቸው፣ የመልሶ ማቋቋሙ ሂደት በቶሎ እንዲጀመር፣ የንቅናቄው የሥራ አፈጻሚ ኮሜቴ እንዲሁም ጉዳዩ የሚመለከታቸው የመንግስት ኃላፊዎች የሚያስፈልገው ያልተቋረጠ ትኩረትና ክትትል እንዲያደርጉ በድጋሚ ለማሳሰብ እወዳለሁ።

    ሀገራችን ኢትዮጵያ ዘርፈ ብዙ ተግዳሮቶችና ህልውናዋን የሚፈታተኑ ስጋቶች የተጋረጡባት ከመሆኗም በሻገር ከምንጊዜውም በባሰ መልኩ መስቀለኛ መንገድ ላይ የምትገኝ መሆኑን በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ሁሉ የሚስማሙ ይመሰለኛል። ይህን አደጋ ለመቋቋም ደግሞ በርካታና ዘርፈ ብዙ ሕዝብ አቀፍ እንቅስቃሴዎች ያስፈልጋሉ። ስለዚህም ውስብስብ በሆኑና ስር በሰደዱ መጠነ ሰፊ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፓለቲካዊ ችግሮች አውድና ከባቢ ውስጥ ተዘፍቀው ለኢትዮጵያ ዴሞክራሲ፣ ፍትህና፣ የሕግ የበላይነትን ለማስፈን እየተደረገ በሚገኘው የለውጥ ጅማሮ እንዳይቀለበስ የለውጡን አራማጆች፣ ለውጡን ለማስቀጠል በተጨባጭ እርምጃዎች እስከተንቀሳቀሱ ድረስ ማገዝ አማራጭ የሌለው ነው ብዬ አምናለሁ።

    ሀገራችንን ቅርጫ ለማድረግ ሲሉ የ100 ሚሊዮን ህዝብ ዕጣ ፈንታ ላይ ቁማር የሚጫወቱ፣ የሕዝብን የተሻለ ህይወት፣ ለሁሉም የኢትዮጵያ ልጆች የታገሉለትን፣ የሚመኙትን ፍትህ፣ ነጻነትና የነገን ተስፋ እየረጋገጡ የሚገኙ እጅግ ራስ ወዳድ፣ ስግብግብ ህሊና ቢሶች፣ የኢትዮጵያን ልዩ ልዩ ማኅበረሶቦች አብሮነት አጥፍተው ለራሳቸው ጠባብ ብሄረተኝነት እጀንዳ ጥቅምና ስልጣን ለማምጣትም ሆነ ለማስቀጠል በየአካባቢው ትርምስ የሚፈጥሩ፣ ክቡር የሆነውን ሰብዓዊነት ረግጠው ወደ አራዊትነት በተጠጋ የለየለት ጽንፈኝነትና አክራሪነት የታወሩ ጥቂቶች፣ ከራሳቸው ግላዊ ፍላጎትና ጥቅም ውጭ ለሕዝብና የሀገር ደህንነት፣ ለሰላም፣ ለፍትህና፡ ለሕግ የበላይነት ምንም ቁብ የማይሰጡ የጥፋት ኃይሎች በአብዛኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች እንደአሸን በፈሉበት ሁኔታ ከኢትዮጵያዊነት ውጪ፣ ከፍትህ፡ ከእኩልነትና፣ ከሕዝብ አብሮነት የተለየ ሌላ አማራጭ እንደሌለ፣ ሌላ ሀገር፣ ሌላ ምድርም አለመኖሩን በሚገባ የተረዱ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ሁሉ በየአካባቢያቸው እያፈጠጠ፣ እያገጠጠ ከሚገኘውን የህልውና አደጋ ከእነዚህ አክራሪና ጽንፈኛ የጥፋት ኃይሎች ሊያመጡት ከሚችሉት የሀገራችንን የመኖር አለመኖር ህልውና የሚፈታተን የሲኦል ጎዳና ራሳቸውን፣ ቤተስባቸውንም ለመከላከል፣ ተከላካይ በሆነ መልኩ እርስ በእርስ መደራጀት፣ እንዲሁም ራስን በራስ ማደራጀትና፣ ብሎም ነቅቶ መጠበቅ ሌላው አስፈላጊና ወቅታዊ ተግባር ነው ብዬ አምናለሁ።

    ለአገራችን ሕልውና፣ ለሕዝባችን ሰላም፣ ፍትሕና ዴሞክራሲያዊ ስርዓት የሰፈነባት ኢትዮጵያ እንድትኖር የሚያስችል የፓለቲካ ስርዓት እንዲረጋገጥ የሚጨነቁ ኢትዮጵያውያን ሁሉ እልህ አስጨራሽ ሁኔታ ውስጥ ብንገኝም ከዚህም ከዚያም የሀገሪቱን ህልውና አደጋ ላይ እየጣሉ የሚገኙ አክራሪና ጽንፈኛ ብሄረተኞችና የለውጥ ቅልበሳ ቡድኖች ወጥመድ ሰላባ ላለመሆን በስልት፣ በሰከነ ጥበብና በሃገራዊ ኃላፊነት መንቀሳቀስ የግድ ነው ብዬ አምናለሁ። ለኢትዮጵያዊነት፣ ለሁሉም ኢትዮጵያዊያን ዜጎች እኩልነትና ሁለንተናዊ መብቶች የቆሙ የፓለቲካ ኃይሎች፣ የሲቪክ ተቋማት፣ እንዲሁም የፕሬስ ድርጅቶችን ማጠናከር እንዲሁ ሌላቅ የወቅቱ ዐቢይ ተግባራት ይመስሉኛል።

    በሀገራችን የተጀመረው ለውጥ ከመጣ ከጥቂት ወራት በኋላ ንቅናቄው የፓለቲካ ፓርቲ እንደሚሆን ስምምነት በተደረሰ ጊዜ የፓለቲካ ፓርቲ አመራርም ሆነ አባል ሆኜ ለመቀጠል ፍላጎት እንደሌለኝ በአመራሩ ላይ ለሚገኙ ሁሉ በተለያዩ ጊዜያት ገልጬ ነበር። እስካሁንም ድረስ የቆየሁት ከመሪዎች አንዱ ሆኜ እንዳገለግል ለመረጡኝ አባላትና የሠራዊት አባላት ባለኝ ኃላፊነትና ተጠያቂነት ቢያንስ ከኤርትራ በርሃና በኢትዮጵያም ውስጥ ሆነው በጨለማው ዘመን ለኢትዮጵያ አንድነትና ለሕዝብችን ነጻነት ህይወታቸውን ለመገበር ለቆረጡ እነዚህ ዛሬ በካምፕ ውስጥና ከካምፕ ውጭ የሚገኙ የሠራዊት አባላትና ታጋዮች ህይወት ተገቢውን መስመር እስኪይዝ ነበር።

    ቀደም ሲል መልቀቂያ አስገብቸ የነበረ ቢሆንም እንኳን የንቅናቄው ዋና ጸሀፊ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ጨምሮ የተለያዩ የንቅናቄው አመራሮች በኃላፊነቴ እንድቆይ በነበራቸው ፍላጎት፣ እኔም ከነሱ ጋር ባደረኳቸው ውይይቶች በቦታው መቆየቴ ሠራዊቱን ይጠቅማል ብዬ ስላመንኩ እስካሁን ድረስ በተሰጠኝ የኃላፊነት ቦታ ላይ የምችለውን እያገዝኩ ቆይቻለሁ። ሆኖም ለቆሙለት ዓላማ፣ ለንቅናቄያቸውና ለሀገራቸው ክብር መተኪያ የሌላት ህይወታቸውን ለመክፈል የቆረጡ የትግል ጓዶቸ ላለፉት 7 ወራት በከፍተኛ ችግሮች ውስጥ ወድቀው ማየት ለኔ እንቅልፍ የሚነሳ ጉዳይ መሆኑ አልቀረም።

    ለኢትዮጵያ አንድነት፣ ለዴሞክራሲና ለኢትዮጵያ ሕዝብ ሁለንተናዊ መብቶች መረጋገጥ የበኩሌን አስተዋጽኦ ሳደርግ ቆይቻለሁ። ባለፉት ሁለት አስርት አመታት በላይ በውጭው ዓለም በተደረገው ትግል ልዩ ልዩ የትግል መድረኮችን በመሥራችነት፣ በአባልነት፣ በአስተባባሪነት፣ እንዲሁም በአመራር ኃላፊነቶች የዜግነት ግዴታዬን ከሚጠበቅብኝ በላይ አስተዋጽኦ በማድረግ ለ26 ዓመታት ያልተቋረጠ የትግል አስተዋጽኦ አድርጌያለሁ። የኢትዮጵያ ሳተላይት ቴሌቭዥንን(ኢሳት) በማቋቋም፣ በመገንባት ሂደትና እስከ 2015 ድረስም በዋና ሥራ አስፈጻሚነት ፣ እሰከአሁኑ ድረስም በቦርድ ሥራ አስፈጽሚ አባልነት የበኩሌን አስተዋጽኦ ተወጥቻለሁ።

    ባለፉት 8 ዓመታት የአርበኞች ግንቦት 7 የአንድነትና ለዴሞክራሲ ንቅናቄ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባልና ልዩ ልዩ የሥራ ኃላፊነቶች ላይ በመሰማራት፣ እ.ኤ.አ ከመስከረም (September) ወር 2017 ከተደረገው የንቅናቄው ጉባኤ ላይ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል ሆኜ ከተመረጥኩኝ በኋላም የንቅናቄው የውጪው ዘርፍ ኃላፊ በመሆን እስካሁን ድረስ በቅንነትና በምችለው እቅም ኃላፊነቴን ተወጥቻለሁ። በአሁኑ ወቅት ከአርበኞች ግንቦት 7 የሥራ አስፈጻሚ ኮሜቴ አባልነት፣ እንዲሁም ንቅናቄው የውጭ ዘርፍ ኃላፊነት በገዛ ራሴ ፈቃድ መልቀቄን ለአርበኞች ግንቦት 7 አባላት፣ ደጋፊዎች፣ በልዩ ልዩ የትግል መድረኮች ለምታውቁኝ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ለማሳወቅ እወዳለሁ።

    የአርበኞች ግንቦት 7 ንቅናቄ በቅርብ ጊዜ ጉባኤ በማድረግ ይከስማል። አዲስ ሀገራዊና በኢትዮጵያዊነት፣ በዜግነትና በማኅበራዊ ፍትህ ላይ የቆመ የፓለቲካ ፓርቲ የምሥረታ ሂደት ወደ ማገባደጃው በመድረሱ በአዲሱ ፓርቱ ለሚመረጡ አመራሮች እንዲሁም አባላትና ደጋፊዎች ሁሉ ያለኝን ጽኑና መልካም ምኞቴን እገልጻለሁ። ለወደፊቱ ለኢትዮጵያ ሀገራችን እንዲሁም ለዓዝባችን ፋይዳና ጥቅም በሚያስገኙ ልዩ ልዩ ተግባራት ላይ በመሳተፍ እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ ዜጋ ድርሻዬን እንደምወጣ ለምታከብሩኝ፡ ለምትወዱኝና ለማከብራችሁና ለምወዳችሁ ወገኖቼ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ለማረጋገጥ እወዳለሁ። እዚህ ላይ የንቅናቄው ወዳጆችም ሆናችሁ ሌሎች እንድታውቁት ላሰምርበትም የምፈልገው በንቅናቄው አጠቃላይ የፓለቲካ ራዕይና ተልእኮ፣ በሚመሠረተው የፓለቲካ ፓርቲ ዓላማና ተልዕኮ፣ እንዲሁም ከማንም የንቅናቄው አመራር አባላት ጋር በግል ሆነ በፓለቲካ ምንም ዓይነት ቅራኔ የሌለኝ መሆኑን ለማረጋገጥ እወዳለሁ። ዘለአለማዊ ክብርና ሞገስ ለኢትዮጵያ አንድነት፣ ለዓባችን ነጻነትና፣ ለፍትህ ሲሉ አይተኬ የህይወት መስዋዕትነት ለከፈሉ የኢትዮጵያ ልጆች ሁሉ! ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!

    ነአምን ዘለቀ ቦጋለ
    ቨርጂኒያ፣ ዩናይትድ ስቴትስ ኦፍ አሜሪካ
    ማርች 18 ቀን፣ 2019

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ነአምን ዘለቀ


    Semonegna
    Keymaster

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ የምርጫ ቦርዱ ሰብሳቢ ተደርጋ መሾም የሀገሪቱን የምርጫ ሂደት ለማሻሻል የተገባውን ቃል ለማጠናክር እና ለ2012 ዓ.ም. ምርጫ ዝግጅት ገለልተኛ የምርጫ ቦርድን ለማጠናከር ያለውን የፓለቲካ ቁርጠኝነት ምስክር ነው ብለዋል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የኢ.ፌ.ዲ.ሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ኅዳር 13 ቀን 2011 ዓ.ም. ባካሄደው 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 7ኛ መደበኛ ስብሰባው ወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳን የብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ አድርጎ በአራት ተቃውሞ፣ ሦስት ድምፅ ተዐቅቦ በአብላጫ ድምጽ ሾሟል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ (ዶ/ር) የዕጩዋን ሹመት ባቀረቡበት ወቅት መንግስት የምርጫ ቦርድ ሰብሳቢን በአዲስ መልክ ለመተካት የወሰነው የተጀመረውን አገራዊ ለውጥ ዳር እንዲደርስ ለማድረግ የተጀመረው የጥረት አካል መሆኑን ተናግረዋል።

    በተለይም የዲሞክራሲ መገለጫ የሆነው ምርጫ ቦርድ ተዓማኒና ገለልተኛ ለማድረግ ተቋሙን የማዘመንና ማሻሻል ከማድረግ በተጨማሪ ብቁ የሆነ መሪ እንደሚያስፈልገው በማመን ወ/ሪት ብርቱካን ለዕጩነት ቀርበዋል ብለዋል ጠቅላይ ሚንስትሩ።

    ዶ/ር ዐብይ ወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ የምርጫ ቦርዶ ሰብሳቢ ተደርጋ መሾም የሀገሪቱን የምርጫ ሂደት ለማሻሻል የተገባውን ቃል ለማጠናክር እና ለ2012 ዓ.ም. ምርጫ ዝግጅት ገለልተኛ የምርጫ ቦርድን ለማጠናከር ያለውን የፓለቲካ ቁርጠኝነት ምስክር ነው ብለዋል።

    በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ አቅራቢነት የብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ሆነው የተሾሙት ወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ ሹመት የተከናወነው የቀድሞዋ ሰብሳቢ አምባሳደር ሳሚያ ዘካሪያ በፈቃዳቸው ኃላፊነታቸውን መልቀቃቸውን ተከትሎ ነው።

    ወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ ማን ናቸው ?

    በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በህግ የመጀመሪያ ዲግሪ ያላቸው፣
    ከሀርቫርድ ዩኒቨርሲቲ ኬኔዲ ስኩል ኦፍ ገቨርንመንት የሁለተኛ ዲግሪ ያላቸው፣
    – በፌደራል ፍርድ ቤቶች በዳኝነት ያገለገሉ፣
    – የሰብዓዊ መብት ተከራካሪ፣
    – በውጪ ሀገር በናሽናል ኢንዶውመንት ፎር ዲሚክራሲ በተባለ ድርጅት ተመራማሪ ሆነው የሠሩ፣
    – የፓርቲ አመራርና ተወዳዳሪ (ቅንጅት) ሆነው የሠሩ፣
    – በምርጫ ሂደት ሰፊ ልምድ ያላቸው ናቸው።

    Interview: Birtukan Mideksa, who shook Ethiopian court system, is back to Ethiopia from exile

    ወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ በአሁኑ ሰዐት የማንኛውም የፖለቲካ ፓርቲ አባል ያልሆኑና ገለልተኛ መሆናቸውን ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ ለምክር ቤት አባላት ተናግረዋል። የምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ተጠሪነቱ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መሆኑ ይታወቃል።

    ወ/ሪት ብርቱካን ሚደቅሳ ከቀድሞ ቅንጅት ለአንድነትና ለዲሞክራሲ ፓርቲ (ቅንጅት) ጋር በተያያዘ ለእስራትና ለእንግልት ከተዳረጉ በኋላ ከሀገር ወጥተው በሀገረ አሜሪካ ለሰባት ዓመታት በስደት የኖሩ ሲሆን፥ በቅርቡ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚታየውን ሁለንተናዊ ለውጥ ተከትሎ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ባቀረቡላቸው ጥሪ መሠረት ጥቅምት ወር መጨረሻ ላይ ወደ ኢትዮጵያ መመለሳቸው ይታወሳል።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ብርቱካን ሚደቅሳ PHOTO: Abebe Abebayehu


Viewing 8 results - 16 through 23 (of 23 total)