Search Results for 'አብይ አህመድ'

Home Forums Search Search Results for 'አብይ አህመድ'

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 68 total)
  • Author
    Search Results
  • Anonymous
    Inactive

    የሰሞኑ “ቃል በተግባር” የተሰኘው የጠቅላይ ሚኒስትሩ ዘጋቢ /ገላጭ/ ፊልም በሁለት ኢትዮጵያውያን አተያይ
    [ቃል በተግባር ― በዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ እና በአቶ ያሬድ ኃይለማርያም አተያይ]

    • ቃል በተግባር ― ኢትዮጵያን ሀገር ሆና አየኋት
      [በድሉ ዋቅጅራ (/)]

    ኢትዮጵያን እንደሀገር ያገለገልኳት፣ ያፈቀርኳት በ1970ዎቹ መጨረሻ (1976-79) ባለው ጊዜ ነበር፤ በመጀመሪያው ዙር የብሔራዊ ውትድርና አገልግሎት ዘመኔ። ከትምህርት ቤት በግዴታ ታፍሼ የገባሁበት የብሔራዊ ውትድርና ከሀገሬ ጋር ልብ ለልብ አስተዋወቀኝ፤ አፈቀርኳት።

    ግዳጄን ፈጽሜ፣ ዩኒቨርሲቲ ተምሬ፣ በ1983 አ.ም. ወደ ሥራ ስሰማራ ኢትዮጵያን አጣኋት። በብሔር ፖለቲካ ሴራ የተካኑ፣ ስሟን መጥራ የሚዘገንናቸው መሪዎች እጅ ወድቃለች። ለጎሳና ቋንቋ ድንበር ከልላ፣ ባንዲራ [ሰንደቅ ዓላማ] ሰቅላ እሷ ፈዝዛለች።… ለብሔረሰቦችና ለቋንቋዎች እኩልነትና ለሰብዓዊ መብት መከበር ዝም ብዬ አላውቅም፤ እሟገታለሁ። ባንዲራቸው ሲከልላት፣ የምትተነፍሰው አየር ሲያጥራት፣ ኢትዮጵያን ሲረሷት ግን አዝናለሁ፤ ያመኛል።

    ከረዥም ጊዜ በኋላ በትላንትናው ዘጋቢ ፊልም ውስጥ ኢትዮጵያን ሀገር ሆና አየኋት። ዘመንን መስላ፣ ተስፋ አዝላ አነበብኳት። በሦስት ዓመት፣ ያለጥላቻና ግጭት ዜና ነግቶ በማይመሽበት ሀገር፣ ‘የእኔ ሀሳብ ካልሆነ ሀገሬ ትበተን’ በሚል ጽንፍ ረገጥ ፖለቲካዊ መርገምት ውስጥ፣ እንኳን በልዕልና መሥራት፥ በትክክል ማሰብስ ይቻላል ወይ? ያውም ይህ ሁሉ ኃላፊነት ለተጫነበት መሪ?!

    የእያንዳንዳችን አመለካከትና እይታ የሚመነጨው ከቆምንበት ቦታ ነው!

    አዎ፣ ሀገራችን የብሔር ፖለቲካው ካጣባት ደዌ አልተፈወሰችም። አዎ አሜሪካ ማእቀብ ጥላብናለች። አዎ ሱዳን ድንበራችንን ተሻግራ መሬታችንን ይዛለች። አዎ የትግራይ ወገኞቻችን በከፍተኛ ሰብዓዊ ችግር ላይ ናቸው። አዎ የኤርትራ ወታደሮች ከሀገራችን ጨርሶ አልወጡም። አዎ ሸኔና የጁንታው ርዝራዦች በሚሰነዝሩት ጥቃት አሁንም ዜጎች ህይወታቸውን እያጡ ነው። አዎ የኑሮ ውድነት ጣራ ነክቷል።… ሀገራችን ውስጥ በርካታ ችግሮች፣ በርካታ ያልተመለሱ ጥያቄዎች አሉ።

    እነዚህ ሁሉ ችግሮች እያሉ እነዚህ አስደናቂ ፕሮጀክቶች መሠራታቸው አግባብ አይደለም በማለት ሰዎች ለጥላቻቸው የሰበብ ድር ያዳውራሉ። እኔን የሚገርመኝ በዚህ ሁሉ ችግር ውስጥ መሠራት መቻላቸው ነው።

    መሠራት የነበረበት ያልተሠራ አለ። ካልተሠራው የበለጠ የተሠራው የወደፊት መንገዳችንን ያሳያል። ጠቅላይ ሚንስትሩ ከሀገሪቱ ባጀት ሳይነካ፣ የተሸለመውን የግል ገንዘብ ሳይሰስት፣ ወዳጆቹን ለምኖ በሦስት ዓመት፣ ጥላቻና ዘለፋን ቁብ ሳይል ይህንን ሠራ። ባለቤቱ ቀዳማዊ እመቤት ዝናሽ ታያቸው እንዲሁ ከሀያ በላይ ትምህርት ቤቶችን በገጠር ቀበሌዎች ገነባች። ለመሆኑ እነዚህን ሰዎች የማናደንቀው ከእነማን ጋር እያወዳደርናቸው ነው? እንኳን በሦስት ዓመት፣ በሦስት አስርታት ውስጥ የዚህን ግማሽ የሠራ መሪ ኖሮን ያውቃል?

    እንደመሪ እነሱ ይህን ሠሩ፤ ያልመለሷቸው ችግሮችም አሉ። እኛስ! እንደ ዜጋ ባለፉት ሦስት ዓመታት ምን ሠራን? እኛ እንደዜጋ ያለነው የት ነው? የሠሩት በጎ ተግባር ወይስ ያልመለሷቸው ችግሮች አካል ነን? በዋናነት የእያንዳንዳችን አመለካከትና እይታ የሚመነጨው ከቆምንበት ቦታ ነው። ሀገራችን በውስጥና ውጭ ችግር ተተብትባለች፤ ፈተና ላይ እንደሆነችም እናውቃለን። ዋናው፣ እያንዳንዳችን ማወቅ ያለብን ጉዳይ ግን ሀገራችንን የተበተባት ችግር፣ የተጋረጠባት ፈተና አካል አለመሆናችንን ነው። እና እንጠይቅ! እንደዜጋ የቆምነው የት ነው?!

    /ር በድሉ ዋቅጅራ ደራሲና ገጣሚ ሲሆኑ፥ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ የሂዩማኒቲስ፤ የቋንቋዎች ጥናት የጆርናሊዝምና የኮሚኒኬሽን ኮሌጅ ውስጥ ደግሞ መምህር ናቸው። ከዚህ ቀደም ለህትመት ከበቁላቸው ሥራዎች ውስጥ የማይፃፍ ገድል፣ የራስ ምስል፣ ያልተከፈለ ስለት፣ የወይራ ስር ጸሎት፣ የማይጻፍ ገድል፣ የተስፋ ክትባት፣ እና ፍካት ናፋቂዎች የጠቀሳሉ። በተጨማሪም በብሔራዊ ቲያትር ቀርቦ በተመልካች ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነትን ያገኘውደብተራውየተሰኘው የሁለት ገጸባሕርያት ቲያትር (two-handler theater) ደራሲ ናቸው።

    • ቃል በተግባር ― እያደነቅን ስጋታችንንም እንገልጻለን፤ አቧራው መሬት ላይ ያለ ግፍ፤ ሃሜቱም ሃቅ ነው
      [አቶ ያሬድ ኃይለማርያም]

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በአዲስ አበባ የሠሯቸውን እና እየሠሯቸው ያሉ ድንቅ ነገሮችን አደንቃለሁ። ለዚህ ሥራቸው ሊመሰገኑ ይገባል። ከሠሯቸው ሥራዎቹ አንዱ የሆነውን የእንጦጦ ፖርክን የመጎብኘት ዕድል ገጥሞኛል። የሚያስደምም ድንቅ ሥራ ነው።

    ከትላንት መግለጫቸውም ሁለት ነገር መረዳት ይቻላል። አንደኛው ሀገር ለማልማት ብዙ እቅድ እና ህልም እንዳላቸው ነው። ሁለተኛው ደግሞ ይህን ህልማቸውን እውን ለማድረግ አንባገነን እሰከመሆን የሚሄዱ መሆናቸውን ነው። አገሪቱ አሁን ያለችበትን ውጥንቅጥ እና አሳሳቢ ችግር፣ የተቃዋሚዎቻቸውን ቅሬታ እና በመንግሥታቸው ላይ የሚሰነዘሩ ቅሬታዎችን ‘አቧራ’ በሚል ገልጸውታል። “ሀሜት አቧራ እንጂ አሻራ መሆን አይችልም። አቧራውን ንቀን አሻራ ማኖራችንን እንቀጥላለን” የምትለዋ ንግግራቸው አለቃቸው የነበሩትን መለስን [የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊን] አስታወሱኝ። ባጭሩ የመለስን የመታበይ ንግግር ነው የደገሙት። መለስ ‘ውሾቹ ይጮኻሉ፤ ግመሎቹም ጉዟቸውን ይቀጥላሉ’ ነበር ያሉት?

    ታቃዋሚዎቻቸውን ውሻ አድርገው እና ተቋውሟቸውንም እንደ ውሻ ጩኸት ቆጥረው እሳቸው ከጉዟቸው ምንም አይነት ምድራዊ ኃይል እንደማያስቆማቸው ሊያውም በፓርላማ ፎክረው ነበር። የመሠረት ድንጋይ ጥለው ያስጀመሩትን የሕዳሴ ግድብ መጨረሻ ለማየትና ሪባን ለመቁረጥ ግን አልታደሉም። ግመሎቹስ ዛሬ ወዴት አሉ? አብይም ያች በሽታ እየታየችበት ነው። ሀገሪቱ ውስጥ ያለውን ያፈጠጠ እና አሳሳቢ ችግር እንደ አቧራ መቁጠር መጥፎ መታበይ ነው። አቧራው እንዲሰክን የሚቀርቡ ምክርና ወቀሳዎችንም እንደ ሀሜት መቁጠር ሌላው አሳሳቢ የክሽፈት ምልክት ነው።

    ሕዝብ እየተራበ ነው፤ የኑሮ ውድነት ሌላ የቀውስ ምንጭ ነው፤ ያልተረጋጋ ፖለቲካም የልማት ጸር ነው፤ ጦርነትም አውዳሚ ነው፤ የመብት ጥሰቶች መበራከት የአፈና ሥርዓት መሳለጫ ነው። እነዚህ ችግሮች አቧራ አይደሉም። በእነዚህ ጉዳዮች ዙሪያ የሚቀርብብዎት ወቀሳና ነቀፌታዎች ሀሜት አይደለም። ልማቱን ግፉበት፤ መታበይዎን አቁመው ለዲሞክራሲ፣ ለሕግ የበላይነት፣ ለሰብዓዊ መብቶች እና ለፍትህ ቀናዕይ በመሆን እንደ ልማቱ አፋጣኝ መልስ ይስጡ። ካልሆነ ግን መካር እንደሌለው ንጉሥ… ይሆናሉ።

    አቶ ያሬድ ኃይለማርያም መቀመጫውን ጄኔቭ ከተማ፥ ስዊዘርላንድ ያደረገ ስብስብ ለሰብዓዊ መብቶች በኢትዮጵያ (Association for Human Rights in Ethiopia) የተባለ ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ናቸው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    ቃል በተግባር

    Anonymous
    Inactive

    የብልፅግናው ታዬ ደንደዓ … ስለማያወቀው ታሪክ የሚጽፈው ነገርስ ምን ይሉታል?
    (ጋዜጠኛ ፋሲል የኔዓለም)

    ለታላቋ ኢትዮጵያ ተብሎ ዝም ቢባል አሁንስ በዛ። ታዬ ደንደዓ፣ የብልፅግናው ባለስልጣን፣ ስለማያውቀው ታሪክ እየጻፈ የአብይ አህመድን መንግሥት አጣብቂኝ ውስጥ እየከተተው ነው። አብይ አህመድ ህወሓት የቀደዳትን ኢትዮጵያን እንቅልፉን አጥቶ ለመስፋት ይሞከራል፤ ታዬ ደንደዓ እና መሰሎቹ ደግሞ በጎን ይተረትራሉ።

    አብይ አህመድን ለማመስገን የኢትዮጵያን ታሪክ ማጠልሸት አይስፈልግም። አብይ በተደጋጋሚ እንዳለው ነው፤ ኢትዮጵያ ከሱ በፊት በነበሩ መሪዎች እየተገነባች እዚህ የደረሰች አገር ናት።

    ታዬ ደንደዓ ስለ ቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አክሊሉ ሀብተወልድ የተሳሳተ ታሪክ ጻፈ። በዚህ ስህተቱ ሳያፍር ቀጥሎ ደግሞ የዛግዌንና የዶ/ር አብይን መንግሥት አወዳድሮ ሌላ የማይሆን ታሪክ ጫረ። “ሞኝ ባያፍር፣ የሞኝ ዘመድ ያፍር” ነው ነገሩ።

    ታዬ ከዛገዌ መጨረሻ እስከ አፄ ኃይለሥላሴ ዘመን የነበረውን የነገሥታቱን ዘመን ምንም ሥራ እንዳልሠራ አድርጎ ረገመው። በአጭሩ የደርግን ፕሮፓጋንዳ ደገመው። ዓላማው እነሱ የአማራ መንግሥት የሚሉት የሰሎሞናዊው መንግሥት ምንም እንዳልሠራ በማሳየት አማራን መወረፍ ነው።

    አላዋቂነት የወለደው ድፍረትና ስልጣን የወለደው ትዕቢት ታዬን እያቅበዘበዘው ነው።

    ከዛገዌ በኋላ ሸዋ ላይ የተመሠረተው ታላቅ ስልጣኔ በማን እንደፈረሰ ታዬ የሚያውቅ አይመስልም። አክሱም፣ ዛግዌና የሰሎሞናዊው ስርወ-መንግሥት ስልጣኔዎች የማይነጣጠሉ፣ ተያያዥነትና ተደጋጋፊነት ያላቸው የኢትዮጵያ ታሪኮች መሆናቸውን ለማወቅ የልብ ብርሃን ያስፈልጋል።

    ደግሞ የታሪክ ሒሳብ ማወራረድ ውስጥ ከተገባ በማን እንደሚከፋ ታዬና ቢጤዎቹ ያወቁትም ያሰቡበትም አይመስልም። ደርግ እንዳስወራውና ታዬ እንደደገመው ሳይሆን፥ የኢትዮጵያ ነገሥታት ለእደ ጥበብ ሰዎች አክብሮት ነበራቸው። በሄዱበት ሁሉ ይዘዋቸው ከሚዞሩ ሰዎች መካከል የእደ ጥበብ ባለሙያዎች ይገኙበት ነበር። የኢትዮጵያ ነገሥትታና የሙስሊም ነጋዴዎች ቁርኝት በታሪክ ተመዝግቦ የሚገኝ ነው። ይህ ሲባል እንከን አልነበረም ማለት አይደለም፤ እንኳንስ ትናንት ዛሬም ብዙ እንከኖች አሉ።

    የመካከለኛው ዘመን ነገሥታት የሠሩትን ሥራ ለማወቅ እኮ የዛሬዋን አዲስ አበባ ቆፈር ቆፈር ማድረግ ነው። አንቶን ዲ አባዲ የተባለው ፈረንሳዊው አሳሽ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የቆመበት ቦታ ላይ የነበረውን በመካከለኛው ዘመን የተሠራውን የቤተ ክርስቲያን ፍርስራሽ ዓይቶ አግራሞቱን እንዲህ ሲል ገልጾ እንደነበር Abba Emile Foucher እንዲህ ሲል ጽፏል፦

    Who could have been the architect of such a building? … People who constructed such a building with well-cut stone, linked with mere clay, must have been of another type of civilizations.

    የረርን፣ በራራን፣ ፈጠጋርን፣ ጋሞን፣ ጉራጌን በአጠቃላይ የሸዋን የጥንት ታሪክ ያጠና ሰው፣ የኢትዮጵያ ነገሥታት የኢትዮጵያን ሕዝብ አንድነት ለማጥናት እየዘመቱ፣ በጎን ደግሞ ታላቅ ስልጣኔ ገንብተው እንደነበር ይረዳል። ያው እነዚህ ስልጣኔዎች እንዴት እና በእነማን እንደፈረሱ ዝርዝር ውስጥ አልገባም። ታሪካችን ስለሆነ ከመቀበልና ወደፊት ከመጓዝ ውጭ በታሪክ ‘እኘኘ…’ ስንል አንገኝም። እንደ ታዬ ደንደዓ ዓይነት አምቦጫራቂዎች ከበዙ ግን እውነቱን ከመናገር ወደ ኋላ አንልም።

    ታዬ የዛግዌ መንግሥትን ከአብይ አህመድ መንግሥት ጋር ሲያነጻጻር በተዘዋዋሪ መንገድ የአብይን መንግሥት የኦሮሞ መንግሥት አድርገን እንድንቀበለው እየነገረን ነው። አብይን የሚደግፈው አብዛኛው ሰው የአብይን መንግሥት የኢትዮጵያ መንግሥት እንጅ የኦሮሞ መንግሥት አድርጎ አያየውም። ከተሳሳትኩ እታረማለሁ። እንዲህ ከሆነማ አንዳንዶች “ተረኝነት አለ!” የሚሉት ትክክል ነው ማለት ነው።

    አብይ አህመድ የራሱን መንግሥት የኢትዮጵያ መንግሥት እንጂ የኦሮሞ መንግሥት ብሎ ሲጠራው ወይም ተራው የኦሮሞ ነው በሚል አስተሳሰብ ስልጣን እንደያዘ ሲናገር ሰምቼ አላውቅም። አብይን የደገፉት ሰዎች ሁሉ አብይን በኢትዮጵያዊነት እንጂ በኦሮሞነት የሚስሉትም አይመስለኝም። አብይ ከኦሮሞ ነገድ ቢወጣም፥ ስልጣን የያዘው በኢትዮጵያዊነቱ እንጂ የስልጣን ተራው የኦሮሞ ስለሆነ አይደለም። ስልጣን በብሔር ተራ ተከፋፍሎ ከሆነማ ኦሮሞ በየትኛው የዕጣ ድልድል ነው ከሶማሌ፣ ከአፋር፣ ከጋምቤላ፣ ከአማራ ወይም ከጉራጌ ቀድሞ ስልጣን የያዘው? እስኪ ዕጣው መቼ እንደወጣና እንዴት እንደወጣ ንገሩን?

    የእነ ታዬ ደንደዓ አመለካከት በጣም አደገኛ የሚሆነው በምርጫ ቢሸነፉ፣ እንደ ህወሓቶች ሁሉ፣ “ኦሮሞ መሪ ካልሆነ ወይም በእጅ አዙር ካልገዛ ስልጣን አንለቅም” የሚሉ መሆናቸው ነው። ስልጣንን በብሔር መንጽር ማየት ኢትዮጵያዊነትን ማዳከም ብቻ ሳይሆን፣ የብሔር አምባገነንነትም ይፈጥራል። ዋ!

    የታዬ አስተሳሰብ ያላቸው ብዙ የኦሮሞ ብሔርተኞች መንግሥት ውስጥ እንዳሉ ይታወቃል። ዶ/ር አብይ አህመድ ከእነዚህ በብሔር ከሚያስቡ ሰዎች በላይ ከፍ ብሎ የሚበር ስልጡን ሰው እንደሆነ በግሌ አስባለሁ። ስለኢትዮጵያ ታሪክ ያለው አመለካከትም ከብዙዎቹ የተለየና በእውቀት ላይ የተመሠረተ ነው። አብይ እንደነ ታዬ ደንደዓ በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ አያላግጥም። በአላዋቂነት ድፍረትም ሆነ በስልጣን ግብዝነት የማያውቀውን ታሪክ ሲዘባርቅ ሰምቼው አላውቅም። አብይ ንባብ ከአላዋቂነት ድፍረት ነጻ ያወጣው ሰው ነው።

    የኦሮሞ ብልፅግና ውስጥ እንደ አብይ አህመድ ንባብ ነጻ ያወጣቸው አርቀው የሚያዩ ስንት ሰዎች አሉ? ስለአንድ አብይ ብለን የኦሮሞ ብልፅግናን ሁሉ ይቅር እንበለው ወይስ ስለኦሮሞ ብልፅግና ብለን አንድ አብይ አህመድን እንርገመው የሚለውን ጥያቄ መመለሱ ከባድ እየሆነ ነው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    የብልፅግናው ታዬ ደንደዓ

    Anonymous
    Inactive

    በፊትም፣ አሁንም እስትንፋሷ በመሪዋ ላይ ብቻ የሆነባት ሀገር
    (ጋዜጠኛ መላኩ ብርሀኑ)

    እንደአለመታደል ሆኖ የዚህች ሀገር ሰላምና ደህንነት ተጠቃሎ በመሪዎቿ በሰላም ውሎ በሰላም የማደር መዳፍ ውስጥ የገባው ዛሬ አይደለም።

    እንኳን በሰላም ጊዜ ሀገርን መምራት ቀርቶ በጦርነት የማሸነፍና ወጥሮ የመዋጋት ነገር እንኳን የንጉሡን በህይወት መኖር የሚታከክ ነገር ነበር – እዚህ ሀገር። እልፍ ሆኖ ተሰልፎ ድል በእጁ መግባቱን እንኳን እያወቀ ንጉሡ ከተመታ ጦሩ በቀላሉ ይፈታል። ሕዝቡ ንጉሡ ከሌሉ ሀገር የለም እየተባለ ሲሰበክ ነው የኖረው።

    እናቶች ንጉሥ ከሌለ የሚመጣውን መአትና እልቂት በመፍራት ለንጉሡ ረጅም ዕድሜ ከመመኘት በላይ “ከንጉሡ በፊት እኔን አስቀድመኝ” ብለው ይጸልዩም ነበር። ምኒልክ ሲሞቱ የሞታቸው ዜና ለሕዝብ ሳይነገር ስንት ዓመት ፈጀ? መልሱ ይኸው ነው። አጼ ኃይለሥላሴ አንድ ነገር ቢሆኑ ሀገር ያበቃላታል ብለው የሚያምኑ ኢትዮጵያውያን ደርግ በቮልስዋገን ከቤተ መንግሥት ይዟቸው ሲወጣ ሲያዩ ነው ወደሩሃቸው የተመለሱት።

    መንግሥቱ ኃይለማርያም በተራው በኢህአፓ የመግደል ሙከራ ሲደረግበት “ሞተ” ተብሎ አብዮቱ የእልቂት እንዳይሆን (ላይቀርለት ነገር) አደባባይ ወጥቶ ነው እግሩን እጥፍ ዘርጋ እያደረገ ነው “አለሁ” ያለው። መለስ ዜናዊ ሞተ ሲባልም በርካቶች በዚሁ “ሀገር ያበቃላታል” ፍርሃት ውስጥ ነበሩ። እነበረከት አደባባይ ወጥተው “ታጋይ ያልፋል ሀገር ይቀጥላል” ዓይነት ነገር ተናግረው ስጋት ቀንሰዋል።

    የዛሬው መሪ አብይ አህመድ ጉዳይ ግን ከነገሥታቱ በኋላ ካሉት መሪዎች ሁሉ በብዙ ይለያል። ጊዜው ጥቂት ቢሆንም ቅሉ ሃሳቡንና አመራሩን ተቋማዊ ማድረግና ግለሰባዊ ተጽዕኖውን በጥቂቱም ቢሆን ለመቀነስ አልቻለም። ስለዚህ አብይ ተወደደም ተጠላ አሁን ባለው አስተዳደር ውስጥ ብቸኛና መተኪያ የሌለው መሪ ነው።

    አብይ አህመድ እና ጓዶቹ ሲሠሩለት እና ሲያስተዳድራቸው የኖረውን ኢህአዴግ የተባለ ተቋም ከውጭ በነበረ ተቃውሞ ታግዘው ከውስጥ በመፈርከስ ቀንብሩን ከላያቸው ገርስሰው የጣሉ የግለሰቦች ስብስብ እንጂ የተደራጀ ተቋም አልነበሩም። የለውጡ መሪዎች ናቸው የተባሉ ሰዎች በመሃል እየተንጠባጠቡ አብይ ብቻ ሲቀር፣ ቀርቶም ብዙዎች ያደነቁትን ለውጥ እያመጣ ሲቀጥል ብቻውን ገንኖ ወጣ።

    አብይ ከመጣበት ማኅበራዊ መሠረቱ አካባቢ የገጠመው ተግዳሮት አሁን ድረስ በብርቱ ቢገርመኝም በሰሜን አካባቢ ካሉ ሰዎች ዘንድ የተጠላ ሰው መሆኑ ግን አይደንቀኝም። በካልቾ ብሎ ከወንበራቸው ላይ ያባረራቸው ሰዎችና “ገዢነት ካለኛ ለማን!?” ያሉ ጀሌዎቻቸው ሊወዱት አይጠበቅም። ይህም ከዚያ ሰፈር በአብይ ጥላቻ ሳቢያ ሀገር እንድትበተን የሚሠሩና የሚመኙ ድኩማን እንዲፈለፈሉ ምክንያት ሆኗል። መተከል ላይ እየሆነ ባለው “መሪና አቀነባባሪ” ብለው እሱ ላይ ጥርስ የነከሱበት፣ “ወለጋ ላይ ቢገኝ እኔን አያርገኝ” ያሉ የበረከቱበት፣ በመጋቢት መጥቶ በሰኔ ሞቱ የተደገሰለት ሰው ነው አብይ።

    ሰውየው የሀገሪቱን ፖለቲካ ብቻውን እየዘወረ፣ በዚህም በዚያም ሁሉን ነገር ብቻውን እየሠራ፣ አውቆም ይሁን ሳይታወቀው ያለምንም ቀሪ ብቻውን የቆመ፣ የማይካፈል ቁጥር ሆኖ ወጣ። ዛሬ በሰሜን ለተፈጠረውም፣ በደቡብ ላለውም፣ በመሃል ለሆነውም፣ በምዕራብ ለተከሰተውም ችግር ሁሉ ተጠያቂው አብይ ነው የሚል አቋም ባላቸው በርካታ አካላት ሲሰደብ ውሎ የሚያድረው ሰውዬ ወዲህ ጦር እያዘዘ፣ ወዲህ ሀገርና ከተማ እየለወጠ ብቻውን ሲሠራ አጠገቡ የሚተካው ቀርቶ የሚመስለው እንኳን አለማየታችን ፈሪ አድርጎናል።

    [ሰሞኑን] አብይ [ሞተ/ታመመ] ምናምን ሲባል ድንጋጤው የበረታው ከርሱ ሞትም በላይ ነገ ሊሆን የሚችለውን እያሰበ ሁሉም ሰላምና ደህንነቱ ስላስጨነቀው ነው፤ ይህ አለመታደል ነው።

    በግሌ ኢትዮጵያን በከረጢት ውስጥ እንዳለ የተፈጨ ዱቄት፣ አብይን ደግሞ ከረጢቱን የዝቅዝቆሽ አዝሎ ጫፉን በእጁ ጨምድዶ እንደያዘው ተሸካሚ ዓይነት ነው የምመስላቸው። የከረጢቱ ጫፍ ከተለቀቀ ዱቄቱ ከአፈር ይደባለቃል። ይሄ ነው የሚያስፈራኝ።

    አብይን በብዙ የማደንቀው መሪ ቢሆንም በዚህ “the one and only” አካሄዱ ግን ቅሬታ አለኝ። ስለዚህ የእርሱን ደህንነት አጥብቄ የምመኘው በግል ለርሱ ባለኝ ጥሩ ስሜት እና ከፍ ያለ አድናቆት ብቻ ሳይሆን በዋናነት ለዚህች ሀገር ሰላምና መረጋጋት፣ ሲቀጥል ለሕዝቡ በሰላም ወጥቶ በሰላም መግባት፣ ጠበብ ሲል ለቤተሰቤ ደህንንት፣ በጣም ሲጠብ ለራሴ ደህና ወጥቶ ደህና መግባት ብዬ ነው።

    ሰሜኑ አቅሙ ከነሞራሉ ቢደቅቅም ቂሙ ግን ከምንጊዜውም በላይ ጠንኖ ሀገር ብትፈርስ ደስ እንደሚለው በአደባባይ በሚናገርበት፣ ምዕራቡ በፈሪ ዱላ ጫካ ለጫካ እየተሯሯጠ የተሸከመውን መሣሪያ አፍ እያስከፈተ ንጹኃንን በሚረፈርፍበት፣ ከውጭ ግብጽና ሱዳን ቤንዚን በጀሪካን ይዘው እሳታችን ላይ ለመድፋት አጋጣሚ በሚቋምጡበት፣ ብቻ በየትኛውም መስመር ለዚህች ሀገር መልካም የሚመኝ በታጣበት በዚህ ጊዜ አብይ አንድ ነገር ቢሆን ስርዓት ሲናድና ነገር እንዳልነበር ሲሆን ሰዓት የሚፈጅበት አይመስለኝም። ሌሊት እንኳን ቢሆን በርህን ለመስበር እስኪነጋና ከእንቅልፍህ እስክትነቃ እንኳን የሚጠብቅህ የለም!

    በበኩሌ በመሪ ደህንንት ላይ የተንጠለጠለች ሀገር ይዘን ዛሬ ድረስ መኖራችንን ስታዘብ ያለመታደል እለዋለሁ።

    ሰውየውን መደገፍና መቃወም ሌላ ነገር ሆኖ የማንክደው ሃቅ ግን አሁንም ሰላማችን በዚህ ሰው ደህና መሆንና አለመሆን የተወሰነ ሆኖ መዝለቁ ነው። ስለዚህ የተወራበት እንኳን ሀሰት ሆነ! አሹ! ብያለሁ። እንደሰው ሳስብ ደግሞ አብይን ሞት ቀርቶ ጭረት እንዲነካው አልመኝም። [እርሱም ቢሆን] እንደማናችንም የሰላም እንቅልፍ ተኝቶ ማደር አይጠላም። ሀገር ብሎ መሰለኝ የጋለ ምጣድ ላይ የተቀመጠው።

    በግሌ ግን መንግሥት ይሁን አስተዳደር ተቋማዊ ሆነው “ሰዎች ያልፋሉ፣ ሀገር ግን ትቀጥላለች” የምንልበትን ዘመን እናፍቃለሁ።

    ጋዜጠኛ መላኩ ብርሀኑ

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    እስትንፋሷ በመሪዋ ላይ ብቻ የሆነባት ሀገር

    Anonymous
    Inactive

    የህወሓቶች እብሪት ― የህወሓቶች ውድቀት ― እንደሀገር፣ እንደዜጋ የሚያስተምረን ትምህርት
    (አቶ ነአምን ዘለቀ)

    ጆርጅ ሳንታያና (George Santayana) የተባለው ፈላስፋ “ታሪክን የማያስተውሱ ታሪክን በመድገም ይረገማሉ” (‘Those who cannot remember the past are condemned to repeat it.’) እንዳለው፥ አምባገነኖች ከሂትለት እሰከ ሳዳም ሁሴን – ካለፈው መማር ሳይችሉ ያንኑ ሲደጋግሙ ኖሩ። የህወሓቶች እብሪት፣ ትእቢት፣ ለኢትዮጵያ ሕዝብ የነበራቸው ንቀት የዚሁ እብሪተኞች ካለፈው ለመማር አለመቻልና የፍትህን ማዕከላዊነት ጥሎ ልከኝነት ረግጦ የመራመድ ቅጥያ ውጤት ነው።

    ለ27 ዓመታት ፍጹም ሊባል በሚችል የበላይነት የመንግሥት፣ የኢኮኖሚ፣ የወታደራዊና የደህንነት ቦታዎች ላይ የአንበሳ ድርሻውን ይዞ የነበረው ህወሓት፥ ከ2018ቱ (እንደ አውሮፓውያን አቆጣጥር) ለውጥ በኋላ በእኩልነት ለመኖር የተሰጠውን ዕድል መቀበል እንዳልቻለ ግልጽ የነበረው የዛሬ ሁለት ወር ተኩል ገደማ በትግራይ በሚገኘው የሰሜን እዝ ሠራዊት አባላት ላይ ያደረሰው መብረቃዊ ጥቃትና ጭካኔያዊ እርምጃ ያን ተከተሎ በተደረገው ሕግን የማስከበር ወታደራዊ ዘመቻ የተጀመረ ሳይሆን ከሁለት ዓመት ተኩል ጀምሮ አንደ ነበር ግልጽ ነው ።

    ያ የነበረውን ሁለንተናዊ የበላይነት ሲያጣ የሞት ሞት ሆነበትና እንዴት ያድርገው!? መላ ቅጡ ጠፋው። ከጅምሩም የያዙትን ስልጣን ለፍትህ፣ በልከኝነት፣ ለሕዝብና ለሀገር ጥቅም ለማስከበር ሳይሆን በሀገርና በሕዝብ ኪሳራ የራሳቸውን፥ አለፍ ሲልም የአንድ ብሔር ሊሂቃን የበላይነት ለማረጋገጥ የተቀሙበት የዘረፋ፣ የዘረኝነትና የመንግሥታዊ ሽብር መሣሪያቸው ነበር። ህወሓቶች ስለራሳቸው ልዩ መሆን፣ ከሌላው ኢትዮጵያዊ የተለየ ጀግንነት፣ ብቃትና ክህሎት ራሳቸው በፈጠሩት የሀሰት ትርክት በእብሪትና በትእቢት የተወጠረው አእምሮአቸው አዲሱን የኢትዮጵያ የለውጥ መንገድ እንዲሁም ከለውጡ ጋር ተከትሎ የመጣውን ነባራዊ እውነታ ሊቀበሉ አልቻሉም።

    እነ ስዩም መስፍን ኢትዮጵያን “ሶርያና የመን እናደርጋታለን” ብለው በአደባባይ አወጁ። እነ ጌታቸው ረዳ “ትግራይ ሀገር መንግሥት መሆን እንዳለባትና እና በቀጣይም ከኢትዮጵያ ጋር ሶማሌላንድ ከሞቃድሾ ጋር እንዳላት ግንኙነት ነው የምንፈልገው” በማለት በድፍረት ለኢትዮጵያ ሕዝብ ነገሩ። “ተራራን ያንቀጠቀጥን”፣ “የደርግን ሠራዊት የደመሰስን”፣ “ከወርቅ ሕዝብ የተገኘን”፣ “ኢትዮጵያን እንደ አዲስ የሠራን”፣ “የብሔር ብሔረሰቦችን መብት ያረጋገጥን”፣… ብለው ለአስርት ዓመታት የሰበኩት ህወሓቶች የሀሰት ትርክቶቻቸውንም አብጠው አብጠው በአምሮአቸው ውስጥም ተገንብተው፣ ጠጥረውና ደድረው እውነታን ለማየት የማያስችል ግርዶሽ ሆነው ቆዩ። በርካታ የትግራይን ወጣቶችንም በዚሁ ትርክት እወናበዱ። መሬት ላይ ካለው ከነባራዊው እውነታ ጋር ፍጹም በተቃራኑ ቆሙ። እውነታውን ተቀብለው ለመሄድም በትዕቢት፣ በእብሪት፣ በዘረኝነት የተተበተበው ልቦናቸውና ህሊናቸው ፈጽሞ አልፈቅድላቸው አለ።

    በመሆኑም ህወሓቶች ማድባትና መዘጋጀት ጀመሩ። ለሁለት ዓመታት ሲደራጁ፣ ሲዘጋጁ ቆይተው ማዕከላዊ መንግሥቱን ዳግም ለመቆጣጠር፥ ይህ ካልሆነም ኢትዮጵያን አተራምሰውና በታትነው “የትግራይን ሀገር መንግሥት” ለመመሥረት “በመብረቃዊ ጥቃት” በሰሜን እዝ ላይ ክህደትና ጭካኔ የተሞላበት ግፍ ፈጸሙ። በስልጣን ዘመናቸውም ግፍና መከራ ለሕዝብ ሲሰፍሩ ኖሩ። በሰፈሩት ቁና መስፈር አይቀርምና የሚሊዮኖች እምባ፣ የብዙ ሺዎች ደም፣ ዋይታና ሰቆቃ፣ በህወሓቶች ግፍ የተሰደዱ የአስር ሺዎች ኢትዮጵያውያውን መከራ ፈጽሞ ይሆናል ብለው ባልጠበቁትና ባልተዘጋጁበት የበስተርጅና እድሜያቸው፣ በመጦሪያ ዘመናቸው እጅግ የመረረ ዋጋ ጠየቃቸው። በመጨረሻም መራሩን ውድቀትና ውርደት አከናነባቸው። የኢትዮጵያ ሕዝብም ‘አክ እንትፍ!’ እንዳላቸው ሊከሰትላቸው ፈጽሞ ሳይችል ቀርቶ በስተርጅና እድሜያቸው ለውድቀትና ለውርደት፣ ገሚሶቹ ደግሞ በመደምሰስ ፍጻሜያቸው ባጁ።

    የኢትዮጵያ አምላክም በእነዚህ ግፈኞች ላይ መብረቃዊ ጥቃት ያደረሰ ይመስለኛል። ስልጣንና ሀብት ደደብና ደነዝ አድርጎ ለውርደት ከዳረጋቸው ከህወሓቶችና ካለፉ አምባገነኖች ታሪክ ለመማር ያልቻሉ፥ አሁንም በያዙት ስልጣን መከታ በማድረግ በሕዝብ ጫንቃ ለመናጠጥ የሚሞክሩ፣ ፍትህን፣ ሰላምን፣ ለሀገር የሚበጀውን፣ የዜጎችን ህይወት የሚለውጥ ተግባር ላይ ከማተኮርና ከመትጋት ይልቅ ሕዝብን ከሕዝብ የሚከፋፍሉ፣ የብሔር ካርድ ለስልጣን ማጠናከሪያ የሚመዙ፣ የሕዝብ ሰላም የሚያውኩና ሀገሪቱ እንዳትረጋጋ የሚደነፉ፣ በየመድረኩም የሚፎክሩ አፍራሽ በየብሔሩ ስም የተደራጁ ኃይሎችና ቡድኖች በገዢው ፓሪቲ የሚገኙ እንዳንድ መሪ ካድሬዎች ከዚህ ታሪክ ይማሩ ይሆን?

    ከስልጣን ጋር በሚመጣ እብጠትና ማን አለብኝነት ብዙ ርቀት የማያስኬድ መሆኑን ማጤን ትልቅ አስተውሎ ነው። ከፋፋይና ሕዝብን በጭንቀት ውስጥ እንዲኖር ከሚያደርጉ የማኅበራዊ ሚዲያዎችና በየሚዲያው ከሚሰነዘሩ መርዛማና ከፋፋይ አሰተያየቶች ለመሰንዘር ከመሽቀዳደም በጎ በጎውን፣ ለሀገር የሚበጀውን፣ ለሕዝብ ተስፋ የሚሆንውን፣ ለሥራ-አጡ ሥራ የሚፈጥረው፣ ኢትዮጵያን የሚያለማውን፣ ሕዝብ ከሕዝብ የሚያቀራርቡ ተግባራት ላይ ማተኮርና መትጋት በኃላፊነት ላይ ለሚገኙ እነዚህ የገዥው ፓርቲ መሪ ካድሬዎች ቅድሚያ ሊሰጡት ይገባል።

    የሕዝብን ጥቅም ማስቀደም፣ የሕግ የበላይነትና ፍትህን ያማከለ ብሎም ለእያንዳዱ ዜጋ በየትኛውም ክልልና ቦታ ለሚኖር ኢትዮጵያዊ/ት የደህንነት ዋስትናው የሚጠበቅበት፣ ሠርቶ ለፍቶ በሰላም መኖሩ የሚረጋገጥበት፣ የዜጎችን ህይወት የሚቀይሩ እንቅስቃሴዎች ላይ በማተኮር ሕዝብን የሚጠቅም ሥራ ሠርቶ ጊዜው ሲደርስ ስልጣን ማስተላለፍ መሆን ይገባዋል። ስልጣንን ለማቆየት የብሔር ካርድ በየዕለቱ መምዘና ህወሓቶች እንዳደረጉት የሕዝብም አብሮነት የሚሸረሽሩ፣ ብሔር ለብሔር የሚያጋጩ ተግባራት ላይ መጠመድ ዋና ሥራ ሆኖ መቀጠል የለበትም። ከሶማሌ ክልል ፕሬዝዳንት ከሙስጠፋ ኦማርና ከጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ እና ከሌሎችም ሊማሩ ይገባል።

    ሕዝብ በአግባቡና በቅጡ ማገልገል ቅድሚያ መስጠቱ በህወሓቶች ውድቀትና ውርደት ዋዜማ ትልቁ ትምህርት ይህ እንደሆነ መቀበል ብልህነት ነው ። ለሀገርና ለሕዝብም ብቸኛው መንገድ የሕዝብን ሰላም፣ ደህንነት፣ ፍትህ፣ መብቶችና ጥቅሞች እንዲሁም አስከፊውን ድህነት ለማስወገድ አካታችና ዘላቂ ልማትን ማስቀደም መሆን አለባቸው። የህወሓቶች ውድቀት ዋዜማ እንደ ሀገር ምን እንማራለን ለሚለው አንዱ አስተምሮና አስተውሎ ይህ ይመስለኛል።

    አቶ ነአምን ዘለቀ

    የህወሓቶች እብሪት ― የህወሓቶች ውድቀት

    Anonymous
    Inactive

    በህወሓትና በውጭ ኃይሎች የተቃጣውን የእብሪት ጦርነት በጋር ከመመከት ውጭ ሌላ አማራጭ የለም
    ነአምን ዘለቀ

    በሀገራችን አንድነትና በኢትዮጵያ ሕዝብ ደህንነት ላይ በህወሓትና በውጭ ኃይሎች የተቃጣውን የእብሪት ጦርነት በጋር ከመመከት ውጭ ሌላ አማራጭ የለም።

    ሀገራችን ኢትዮጵያ ከባድ የህልውና አደጋ፣ ከባድ ፈተና ውስጥ እየገባች ነው። በእብሪት፣ በበታችነት፣ በዘረኝነት በሽታ የተለከፈው፣ በኢትዮጵያ ላይ የነበረውን ሁለንተናዊ የበላይነት ያጣው የመሰሪው የህወሓት መሪዎች ትግራይ ወስጥ በሚገኘው የሰሜን እዝ የመከላከያ ካምፕ ላይ የኃይል እርምጃ በውሰድ ሀገሪቱን ወደ ጦርነት ለመውሰድ የመጀመሪያ እርምጃቸውን እንደወሰዱ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት የተላለፈው መልዕክት ያሳያል።

    1ኛ) የኢትዮጵያ ሕዝብ ከዳር እስከ ዳር በጋራ ከመቆም ሌላ አማራጭ የለም። በልዩ ልዩ የህገሪቱ ችግሮች ከመንግሥት ጋር የሚገኙ ልዩነቶች ሁሉ ወደ ጎን ማድረግ አማራጭ የለውም።

    2ኛ) በሀገራችን አንድነትና በሕዝብ አብሮነት ላይ የተቃጣውን የህወሓት እብሪት በጋር ከመመከት ውጭ ሌላ አማራጭ የለም።

    3ኛ) የህወሓቶች ዒላማ የፌደራሉ መንግሥት ብቻ አይደለም፤ ይህ ጥቃት የተቃጣው በኢትዮጵያ ህልውና፣ በሕዝባችን ሰላም፣ ደህነትና አብሮነት ላይ ነው።

    4ኛ) የህወሓቶች ጥቃት በመከላከያ ሠራዊትበብልጽግና ፓርቲና እና በመንግሥት ላይ ብቻ አይደለም፤ የህወሓቶች እብሪትና ጠብ አጫሪነት እነሱ ያልገዟት ኢትዮጵያ እንድትፈርስ፣ ብሎም እነሱ የሚያስታጥቁትና የሚደግፉዋቸው ኃይሎች በቤኒሻንጉል፣ በወለጋ እንደተደረጉት እጅግ ዘግናኝና አረመኔያዊ ግድያዎች በሁሉም የኢትዮጵያ አካባቢዎች እንዲደደገሙ በማድረግ ኢትዮጵያን ማፍረስ ነው። ይህን በጋራ ህልውናችውን ላይ የተቃጣ ከባድ አደጋ ኢትዮጵያውያን ሁሉ በጋራ ሆነን መመከት አለብን።

    5ኛ) ሕወሓት፣ ኦነግ ሸኔ፣ ግብጽ፣ እና በዲያስፓራም በሀገር ውስጥ የሚገኙ ቅጥረኖቻቸው ኢትዮጵያን ለማተራመስ ከቻሉ ማዕከላዊ መንግሥቱን ዳግም ለመቆጣጠር፥ ካልቻሉም ደግሞ ህወሓት አባይ ትግራይን ይመሠርታል፤ ግብጽም የአባይን ግድብ ህልውና እና አገልግሎት ለማምከን ትችላለች፤ ኦነግ ሸኔም የኦሮሚያ ሪፑብሊክ ይመሠርታል። አነዚህን ዋና ዒላማቸው አድርገው በጋራ እየተንቀሳቀሱ መሆኑ ግልጽ ነው። ከዚያ ስለሚከተለው ምድራዊ ሲኦል ህወሓትና የኦነግ ሽኔ የሞራልና የስብዕና ድኩማኖች ፈጽሞ ሊረዱ የሚችሉት አይደለም።

    ኢትዮጵያውያን ሁሉ፥ በዲያስፓራ የምንገኝ ሀገር ወዳዶች ሁሉ፥ በሀገር ውስጥም ወጣቱ፥ ጀግናው የቀድሞ ሠራዊት አባላት ሁሉ ከዳር አስከ ዳር በጋራ ሆነን፣ በጋራ ቆመን ከማዕከላዊ መንግሥትና ከመከላከያ ሠራዊቱ ጀርባ በመሰለፍ፣ አሰፈላጊውን ድጋፍና መስዋዕትነት መክፈል አለብን። የሀገራችንን ህልውና፣ የሕዝብን ሰላምና ደህነት፥ የጥፋት፣ የዘረኝነት፣ የእብሪት ክምችት ከሆነው ከህወሓትና ግብረ-አበሮቹ ለመታደግ በጋራ መቆም፣ በጋራ መሰለፍ የወቅቱ [ዋና ተግባራችን መሆን አለበት።]

    ይህን የማያደርግ የታሪክ ተወቃሽ ብቻ ሳይሆን የራሱንም፣ የቤተሰቡንም ዕጣ ፈንታ ለህወሓቶች ዳግማዊ የክረፋው ዘረኝነት፣ ጭካኔና ባርነት መዳረግ ይሆናል፤ ከዚያም ሲያልፍ ሀገር-አልባ መሆንም ይከተላል።

    ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድም ሆነ ከብልጽግና ጋር ያለ ማናቸውም ልዩነት ወደ ጎን አድርገን የመጣብንን የህልወና አደጋ በጋራ መመከት የወቅቱ አብይ ተግባር ነው!!

    ነአምን ዘለቀ (ከአሜሪካ)

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    በህወሓት የተቃጣው የእብሪት ጦርነት

    Anonymous
    Inactive

    የወቅቱ አብይ ጥያቄ – የህወሓትን ሀገር አፍራሽ፣ ሕዝብ አጫራሽ ሴራ በጋራ ቆመን፣ በአንድነት በመንቀሳቀስ ማምከን ነው
    አቶ ነአምን ዘለቀ

    ሰላም ወገኖቼ፥

    የወቅቱ አብይ ጥያቄ ኢትዮጵያ ሀገራችንንና ኢትዮጵያዊነት ከህወሓት ሀገር አፍራሽ፣ ሕዝብ አጫራሽ ሴራ በጋራ ቆመን፣ ከዳር እሰክዳር በአንድነት በመንቀሳቀስ ማምከን ነው። መሆን ወይንም አለመሆን ነው ለእያንዳዱ ዜጋ የቀረበው ጥያቄ!

    የክፋት፣ የነውር፣ የመሰሪነት ጥግ የሆኑት፣ ይህ ነው የማይባል ዘረፋ፣ ዘረኝነትና ግፍ በሚሊዮኖች ዜጎች ላይ የፈጸሙ፣ በእውነቱ ቃላትም የማይገልጻቸው የህወሓት መሪዎች ኢትዮጵያን በበላይነት ካልገዛን ትፈርሳለች የሚል ለዘመናት የቆየ ቅዠት እውን ለማድረግ እየተቅበዘበዙ መሆናቸውን የሰሞኑ ዋና መነጋገሪያ መሆኑ ይታወቃል። ከነበራዊ እውነታ ጋር የተጣሉ፣ የሞራልም የእእምሮም በሽተኞች በመሆናቸው የ27 ዓመት የክፋት፣ የዘረፋ፣ የከረፋ ዘረኝነታቸው ውስጥ ፍዳውን ሲያይ የነበሩ አብዛኛው ኢትዮጵያዊ ዜጎች የሚረዳው መሆኑ ግልጽ ነው።

    ከለውጡ በኋላ ወደ ስልጣን የመጣው አመራር የነዚህን ጉዶች ባህርይና ለዘመናት የተተበተበ በሽታ በሚገባ ተገንዝቦ፣ ስትራቴጂም ነድፎ ህወሓትን የማዳከም ልዩ ልዩ እርምጃዎችን መወሰድ ይገባው ነበር። ያ ግን አልተደረገም። በተለይም ወንጀለኛውን ጌታቸው አሰፋ ሕግ ፊት እንዲቀርብ የፌደራል መንግሥቱ ሲጠይቅ አናስረክብም ባሉ ጊዜ፥ በሀገሪቱ ልዩ ልዩ ክፍሎችም ግጭት ለመፍጠር በርካታ የሳቦታጅ ሥራዎች ማደራጀታቸው፣ መቆስቆሳቸው በሚገባ የሚታወቁ ሆነው ሳለ፥ ፈዴራል መንግሥቱ ከጦርነት በመለስ ሁሉንም የመንግሥት ማድረግ አቅም መጠቀምና ህወሓትን አይቀጡ ቅጣት መቅጣት ነበረበት። በቅርብ ሳምንት በቤኒሻንጉል-ጉሙዝ ክልል በአማራ ማኅበረሰብ አባላት ላይ የተደረገውን አሰቃቂ ጭፍጨፋ በገንዘብና በመሣሪያ ያገዙ፣ በክልሉ ሰፊ መሬት ያላቸው የህወሓት አባል የሆኑ ባለሃብቶች መሆናቸው የክልሉ መንግሥት ባለስልጣን ለኢሳት ጋዜጠኛ መሳይ መኮንን የተናገረውን ልብ እንበል።

    በመንግሥት አካባቢ ብቻ ሳይሆን በሌሎችም ተንሠራፍቶ የነበረ ‘የት ይደርሳሉ?’ መሰል የተዛባና አደጋውን የመረዳት የማይመጥን አመለካከት ሳቢያም፣ ህወሓትን የልብ ልብ ሰጥቶ ኢትዮጵያን ወደ ጦርነት ለመክተት፣ በዚህም የትግራይንም ሆነ የሌላውን ኢትዮጵያዊ በጦርነት እሳት ለመማገድ ዛሬ ላይ የደረሰበት የለየለት እብደት እንዲደርስ ዕድል ባልተሰጠው ነበር፤ አጥፍቶ ከመጥፋትም አይመለሱም። ያ በሀገርና በሕዝብ ላይ የነበራቸውንም ዓይን ያወጣ የጥቂት ዘረኞች የበላይነት፣ ፈልጭ ቆራጭነት እንዳይመለስ አጥተውታልና አዲሱን እውነታ ፈጽሞ ተቀበለው በእኩልነት፣ በአቻነት ሊኖሩ በዘረኝነት፣ በትምክህትና በትእቢት የታጨቀው አእምሮአቸው አይፈቅድላቸውም።

    ለሁለት ዓመት ተኩል የተዘጋጁበት፣ ከጅምሩም ህወሓትና አጋሮቹ እንደ ጊዜ ቦንብ እንዲፈነዳ ቀብሩውት የነበሩት ሰፋፊ የማንነት ስንጥቆች፣ የብሔር ቅራኔዎችን ተጠቅመው ሀገሪቱን በቀውስ ውስጥ ለመክተት፣ ብሎም ለመበታተን ላሰፈሰፉ በየክልሉ ያደፈጡ ጽንፈኞችም ምቹ ሁኔታዎችንም ፈጥሯል። የህወሓት መሪዎች ለበርካታ ዓመታት የነደፉትን መሰሪ ‘ፕላን B’ የሆነውን አባይ ትግራይ-ትግራይ ትግሪኝ፣ ወዘተ… ለመመሥረት የሚችል መስሏቸው እየተንፈራገጡ ይገኛሉ። ለሀገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን ሁሉ ግልጽ መሆን ያለበት የጦርነት እሳት ኢንዲቀጣጠል፣ ብሎም በመላው ኢትዮጵያ እንዲዛመት ያላቸውን ሁሉ በማድረግ ላይ የሚገኙት መሰሪዎቹ ጸረ-ኢትዮጵያ የህወሓት መሪዎች በጠላትነት የፈረጁት ጠ/ሚ ዐቢይ አህመድን ብቻ እንዳልሆነ ግልጽ መሆን ይገባዋል፤ ወይንም ፈደራል መንግሥቱ፣ የብልጽግና ፓርቲ አይደሉም።

    ይልቅስ ዓይን ቀቅሎ የበላው የሀሰትና የነውር ቋት የሆነው የስዩም መስፍንና ሌሎቹ የህወሓት መሪዎች መሠረታዊ ግብ ኢትዮጵያን የማፈራረስ ነው። በፍርስራሹም ላይ በዘረኝነት የታጨቀው የትግራይ ትግርኝ ሀገር መንግሥት የመመሥረት ቀቢጸ-ተስፋ እውን የማድረግ ግብ ነው። ይህ ነው አብይ ግባቸው። ለምን ቢባል የህወሓት መሪዎች ኢኮኖሚውን፣ መከላከያውን፣ ደህንነቱን፣ የውጭ ጉዳዩንና ባጠቃላይም በኢትዮጵያ ሀገረ መንግሥት ላይ በበላይነት የማያሸከረክሩባት፣ ፈላጭ ቆራጭና ሁሉን አድራጊ ፈጣሪ፣ ሌላው የእነርሱ አጎብዳጅ፣ ፈርቶና ተጎናብሶ የማይኖርባት የ27 ዓመቷ ኢትዮጵያ ማስቀጠል የማይችሉበት ነባራዊ ሁኔታን እንዴት ተቀብለው ሊኖሩ ይችላሉ?

    ልብ እንበል፤ ቆም ብለን በቅጡ እናስብ፤ ያቺ ኢትዮጵያ ዛሬ ላይ የለችም። ይህን እጅግ መራር እውነታ ሊቀበሉ ሊውጡት ደግሞ ፈጽሞ አልቻሉም። የእነ ስዩም መስፍን “ዓይናችሁን ጨፍኑና እናሞኛችሁ” የለየለት ውሸቶች፣ ማስመሰሎች፣ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም ቆመው፣ ሠርተው እንደነበር፣ ለሕዝብ ጥቅም የታገሉና ሲሠሩ እንደነበሩ ለቀባሪው ማርዳት ሙከራዎች ሁሉ ከዚህ ሃቅ የሚመነጭም ጭምር ነው። ይህን ሃቅ አስምረን ግልጽና ፍንትው አድርገን ማየት ቀዳሚው ተግባር ነው። ህወሓት ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ እውነተኛ ፍትህ፣ እኩልነት፣ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅሞች የቆመበትና የሠራበት ሁኔታና ጊዜስ መቼ ነበሩ? ብለን ብንጠይቅ፣ እነ ስዩም መስፍን ነጋ ጠባ ሊያጭበረብሩን ከሚሞክሩት ውጭ ማንም አፉን ሞልቶ ሊመሰክር የሚችል ኢትዮጵያዊ የሚገኝ አይመስለኝም። ሀገሪቱን እንደ ቅኝ ተገዢ ሲመዘብሩ፣ በከረፋ ዘረኝነታቸውም ትግርኛ ተናጋሪ ያልሆነውን ኢትዮጵያዊ ሁሉ እንደ የበታችና 3ኛ ዜጋ ሲያንገላቱ፣ ሲገፉ፣ በንቀት ሲመለከቱ፣ ሲዘርፉና ሲገድሉ የነበረው መራራ ታሪክ ሁሉም ያለፈበት የቅርብ ጊዜ አስነዋሪውና አሳፋሪው ትሪካቸውና የእኛም የኢትዮጵያውያን ቁስል ነውና።

    ለምን? ምክንያቱም ከጅምሩም የተነሱበት መሠረት በመሆኑ ለአያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ግልጽ መሆን ይገባዋል፤ መወናበድ ማክተም አለበት። ለአወናባጆችና ውዥንብር ነዥዎችም ሰለባ መሆን የለብንም፤ ብዙዎች ከዳር ቆሞው ጉዳዩ የዐቢይ አህመድ እና የህወሓት ጠብ አድርጎ መመልክት በሀገርና በሕዝብ ላይ ትልቅና ከባድ አደጋ፣ እንደ ሀገርና ሕዝብ ለውድቀትም ሊዳርግ የሚችል፣ ይህ ነው ተብሎ ሊገመት የማችል ዋጋ የሚያስከፍል ስህተት ይሆናል። አለፍ ሲልም ቅጥረኞችና ከራሳቸው ጥቅም በላይ ለጋራ ሀገር፥ ለኢትዮጵያ ሰፊ ሕዝብ ማሰብ የማይችሉ፣ ዐቢይን ሰለጠሉ ኢትዮጵያም ሆነች ሀገረ መንግሥቱ ቢፈርስ፣ በፍርስራሹ ላይ ስልጣን የሚያገኙ የሚመስላቸው እኩዮች “ፓለቲካ ሊያስተምሩን” እንደሚዳዱት የህወሓትና የፌደራል መንግሥቱ/የብልጽግና ጠብና ግጭት ተደርጎ መወሰድ የለበትም። የህወሓት መሪዎች እንቅስቃሴ በሀገራችን ኢትዮጵያና በሕዝብ ሰላም፣ ደህነትና መረጋጋት ላይ የመጣ የህልወና አደጋ ተደርጎ መወሰድ ያለበት ነው።

    የዛሬው አብይ ጥያቄ ኢትዮጵያ ሀገራችንንና ኢትዮጵያዊነት ከህወሓት ሀገር አፍራሽ፣ ሕዝብ አጫራሽ ሴራ ማምከን ነው። መሆን ወይንም አለመሆን ነው ለእያንዳዱ ዜጋ የቀረበው ጥያቄ።

    ነአምን ዘለቀ

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

    የወቅቱ አብይ ጥያቄ የህወሓትን ሀገር አፍራሽ ሴራ በአንድነት በመንቀሳቀስ ማምከን ነው

    Anonymous
    Inactive

    በእነ አቶ ጃዋር መሐመድ መዝገብ የቀዳሚ ምርመራ ሂደት በተመለከተ የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ
    የኢፌዲሪ ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ

    በዛሬው ዕለት (ነሐሴ 11 ቀን 2012 ዓ.ም.) አቶ ጃዋር መሃመድ ጨምሮ ስምንት ተጠርጣሪዎች ላይ የዐቃቤ ሕግ የቀዳሚ ምርመራ ምስክሮችን ለመስማት የተያዘው ቀጠሮ አቶ ጃዋር መሐመድ አሞኛል በማለታቸው ተስተጓጉላል። ከዚህም የተነሳ ፍርድ ቤቱ ምስክሮቹን የመስማት ሂደቱን ለማካሄድ ለሦስተኛ ጊዜ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።

    በዚህ አጋጣሚ ለሕዝብ እና ጉዳዩን ለሚከታተሉ ሁሉ ግልጽ ለማድረግ የምንፈልገው፥ እነ አቶ ጃዋር መሃመድ በከባድ ወንጀል ተጠርጥረው በሕግ ቁጥጥር ስር እንደመሆናቸው፥ ጤናቸውን ለመጠበቅ ባለው አሠራር አስፈላጊውን የጤና ክትትል እና አገልግሎት የሚያገኙ እና እያገኙ ያሉ ሲሆን ጤናቸውም በመልካም ሁኔታ ላይ ይገኛል።

    ለዚህም ማሳያ ከተደረገላቸው የሕክምና በተጨማሪ ዛሬ (ነሐሴ 11) በዋለው ችሎት ምስክር መሰማት እንዳይጀምር የተለያዩ ምክንያቶችን እያነሱ ለረጀም ሰዓት ሲከራከሩ ከቆዩ በኃላ በክርክሩ ላይ ፍርድ ቤቱ ብይን ሰጥቶ ምስክር መሰሚያ ሰዓት ሲደርስ ወጣ ገባ ማለታቸው የሚፈለገው የምስክሮችን የማሰማት ሂደቱን ለማስተጓጎል እና በግብረ አበሮቻቸው ሁከት እና አመጽ ለመቀስቀስ ነው።

    የተጠርጣሪው ግብረ አበሮች በተለያየ መንገድ ምስክሮችን በማስፈራራት የፍትህ ሂደቱ እንዲስተጓጎል ከፍተኛ ጥረት እያደረጉ መሆኑም ታውቋል። ከዚህም በተጨማሪ ፍጹም አግባብነት በሌላቸው መነሻዎች እና በተለያየ ሰበቦች ምስክሮች በቀዳሚ ምርመራ የሚሰሙበተ ሂደት እንዲራዘም እና እንዲሰናከል ለማድረግ ጥረት እያደረጉ በመሆኑ እንደ ወትሮም ሁሉ ተቋማችን ለምስክሮች ተገቢውን የሕግ ጥበቃና ከለላ የሚያደረግ መሆኑን በዚህ አጋጣሚ ለመግለጽ እንፈልጋለን።

    ከምንም በላይ በተለያዩ ጥቃቅን ጉዳዮች አላግባብ ከሚቀርቡ አቤቱታ እና ይግባኞች ጀምሮ፣ አልተዘጋጀንም ተለዋጭ ቀጠሮ ይሰጠን፣ ዳኛው ፌገግ ብሏል እና ይቀየርልን በማለት በሰበብ አስባቡ የፍርድ ሂደቱን ለማደናቀፍ በተጠርጣሪዎቹ በኩል የሚደረግ ጥረት እንዳለ ግልጽ ሆኗል። ይህን እውነታ ሕዝቡም ሆነ የሚመለከታቸው አካላት እንዲገነዘቡ እና በአፋጣኝ ፍትህ እንዲረጋገጥ ከምናደርገው ጥረት ጎን እንዲሰለፉ ጥሪያችንን እያቀረብን፥ ማንም ይሁን ማን ከሕግ በላይ መሆን የማይቻል መሆኑን በአጽንኦትት ለመግለጽ እንወዳለን።

    የኢፌዲሪ ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ
    ነሐሴ 11 ቀን 2012 ዓ.ም
    አዲስ አበባ

    ተያያዥ ዜናዎች

    ጃዋር መሐመድ እና በቀለ ገርባ

    Semonegna
    Keymaster

    ከ200 ሚሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ እየተገነባ ያለው መርካቶ የአውቶቡስ ተርሚናል እየተጠናቀቀ ነው

    አዲስ አበባ (ኢዜአ) – ከ200 ሚሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ እየተገነባ ያለው መርካቶ የአውቶቡስ ተርሚናል በሦስት ወራት ጊዜ ውስጥ ሥራ እንደሚጀምር የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ አስታወቀ። በቀጣዩ ዓመት ተጨማሪ 3 ሺህ የከተማ አውቶቡሶችን ለማሰማራት የግዥ ሂደት ላይ መሆኑንም የትራንስፖርት ቢሮው አክሎ አስታውቋል።

    በቢሮው የፕሮጀክቱ አስተባባሪ መሀንዲስ ኢ/ር ናትናኤል ጫላ ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) እንደጠቆሙት፥ መንግሥት በመደበው ከፍተኛ በጀት መርካቶ የአውቶቡስ ተርሚናል ግንባታው ከነሐሴ ወር 2010 ዓ.ም. ጀምሮ በመከናወን ላይ ይገኛል። በአሁኑ ወቅት ግንባታው ከ87 በመቶ በላይ መድረሱንም ኢ/ር ናትናኤል አመልክተዋል።

    በዘመናዊ መልኩ እየተገነባ ያለው መርካቶ የአውቶቡስ ተርሚናል የተለያዩ አገልግሎት መስጫ ማዕከላት ያሉት መሆኑንም ኢ/ር ናትናኤል ጨምረው ጠቅሰዋል። ከነዚሁ አገልግሎት መስጫ ማዕከላት መካከል ዘመናዊ የትኬት መቁረጫ፣ የደህንነት መቆጣጠሪያ፣ የተገልጋይ ማረፊያ፣ ለአቅመ ደካሞችና አካል ጉዳተኞች አገልግሎት የሚውል ዘመናዊ አሳንሰር፣ የመረጃ ማዕከልእና የተገልጋይ መጸዳጃ ቤቶች ይገኙበታል።

    በመሀል ገበያ 4 ሺህ ካሬ ስፋት ባለው ቦታ ላይ የሚገነባው የአውቶቡስ ተርሚናል ባለ ሁለት ወለል ከፍታ ያለው መሆኑን ኢ/ር ናትናኤል አስረድተዋል። በአፍሪካ ትልቁ ክፍት የገበያ ማዕከል በሆነው መርካቶ በአንድ ቀን ብቻ ከ50,000 እስከ 80,000 ገበያተኛ ሕዝብ እንቅስቃሴ እንደሚያደርግበት የሚገመት ሲሆን የአውቶቡስ ተርሚናሉ በዚህ የገበያ ማዕከል አቅራቢያ መገንባቱ ትልቅ ጠቀሜታ ይኖረዋል።

    በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ስር የትራንስፖርት ፕሮግራሞች ማስተባብሪያ ጽሕፈት ቤት በከተማዋ ውስጥ አራት (ማለትም፥ መርካቶ፣ ፒያሳ፣ ሰሚት እና መገናኛ አካባቢዎች) ዘመናዊ የአውቶቡስ ተርሚናሎችን ለመገንባት ከ2008 ዓም ጀምሮ እንቅስቃሴ መጀመሩ ይታወቃል።

    ከሚገነቡት ተርሚናሎች ውስጥ አስተዳደሩ በ2013 ዓ.ም በመገናኛ አካባቢ ከ2.5 ቢሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ አንድ ዘመናዊ የብዙኃን ትራንስፖርት ተርሚናል ለመገንባት እንቅስቃሴ መጀመሩን ኢ/ር ናትናኤል ጠቁመዋል። ይህ የአውቶቡስ ተርሚናል ተገንብቶ ሲጠናቀቅዘመናዊ ተርሚናሉ የአንበሳ አውቶቡስ፣ ሸገር ባስንና ታክሲዎችን ጨምሮ የተለያዩ የብዙኃን ትራንስፖርት አገልግሎቶችን በማጣመር በአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጠት እንዲችሉ የሚያደርግ መሆኑንም አስረድተዋል።

    ኢ/ር ናትናኤል እንዳሉት የመገናኛው የአውቶቡስ ተርሚናል በአንድ ሄክታር ቦታ ላይ የሚገነና እና ባለስምንት ወለል ሲሆን አራቱ ወለሎች የብዙኃን ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጥበት ነው። በተጨማሪም የፈጣን አውቶቡስ፣ የታክሲ እና የቀላል ባቡር አገልግሎቶች በጣምራ የሚሰጥበት መሆኑንም አብራርተዋል።

    ፕሮጀክቱ ለእግረኞች አገልግሎት የሚውል አንድ ዘመናዊ ድልድይና 200 መኪኖችን በአንድ ቦታ ለማስቆም በሚያስችል የመኪና ማቆሚያ ቦታ (ፓርኪንግ) እንደሚኖረውም ጠቁመዋል።

    የብዙኃን ትራንስፖርትን ለማሻሻል በርካታ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የጠቀሱት ኢንጅነር ናትናኤል፥ በቅርቡ በጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ (ዶ/ር) እና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ታከለ ኡማ (ኢ/ር) የመሠረት ድንጋይ የተጣለበትን የፈጣን አውቶቡስ አገልግሎት ግንባታን ለአብነት ጠቅሰዋል።

    ከእነዚህ ሥራዎች ጎን ለጎን በከተማዋ አሁን በሥራ ላይ ያሉትን 1 ሺህ የከተማ አውቶቡሶች ቁጥር ለማሳደግ በቀጣዩ ዓመት 3 ሺህ አውቶቡሶችን ግዥ ለመፈጸም እተሠራ መሆኑንም ኢ/ር ናትናኤል ጨምረው ገልጸዋል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    መርካቶ የአውቶቡስ ተርሚናል

    Anonymous
    Inactive

    በኦሮሚያ ክልል፣ አዲስ አበባ፣ ሐረር እና ድሬ ዳዋ ከተሞች በሰኔ ወር 2012 ዓ.ም. የተፈጸመውን ፍጅት ለመጣራት መረጃ ለመሰብሰብ የተላለፈ ጥሪ

    ሰላም ኢትዮጵያውያን ወገኖች፥

    በዓለም አቀፍ ደረጃ የተመሠረተው የኢትዮጵያውያን ለሰላም፣ ለፍትህና፣ ለአንድነት ኔትወርክ በሰሜን አሜሪካ የሚገኙ የሕግ ባለሞያዎች ቡድን የራሱን መግለጫ እንደሚያወጣ በገለጸው መሠረት፥ የሕግ ባለሞያዎች የሚገኙበት ቡድን በኦሮሚያ ክልል፣ አዲስ አበባ፣ ሐረር እና ድሬ ዳዋ ከተሞች በሰኔ ወር 2012 ዓ.ም. የተፈጸመውን ፍጅት ለመጣራት መረጃ ለመሰብሰብ የተላለፈ ጥሪ እቅርቧል። ይህን ጥሪ ሀገር ቤት ለሚገኙ ወገኖች በማስተላለፍ ሁሉም ዜጎች እንዲተባበሩ ጥሪውን ያስተላልፋል።

    በኦሮሚያ ክልል፣ አዲስ አበባ፣ ሐረር እና ድሬ ዳዋ ከተሞች በሰኔ ወር 2012 ዓ.ም. የተፈጸመውን ፍጅት
    ለመጣራት መረጃ ለመሰብሰብ የተላለፈ ጥሪ

    በሰኔ ወር 2012 ዓ.ም. የተፈጸመውን የሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል፣ አዲስ አበባ፣ ሐረር እና ድሬ ዳዋ ከተሞች ሰፊ ተቃውሞ መቀስቀሱ ይታወሳል። እነዚህ ተቃውሞዎች በአብዛኛው በታዋቂው የባህልና የፖለቲካ ትግል ፋና ወጊ በነበረው ሃጫሉ ግድያ የሕብረተሰቡን ድንጋጤ ያንጸባረቁና ሰላማዊ ነበሩ። ሆኖም በተወሰኑ አካባቢዎች፣ የተወሰኑ ቡድኖች በሰላማዊ ዜጎች ላይ የኃይል እርምጃ ወስደዋል። በዚህ እርምጃም የተወሰኑ የብሔርና የሃይማኖት ቡድን አባላት እና ጎረቤቶቻቸውን ለማዳን የተንቀሳቀሱ ንጹሃን የኦሮሞ ተወላጆች ላይ የሕይወት መጥፋት፣ አካል መጉደልና ንብረት ውድመት ደርሷል። የተለያዩ የዜና ማስራጫ ዘገባዎች እንድሚያስረዱት የኃይል እርምጃው በድንገት በተወሰኑ ቦታዎች ብቻ የተፈጸሙ እርምጃዎች አለመሆናቸውን ነው። ጥቃቶቹ በመረጃ፣ በሰው ኃይልና በገንዘብ በቂ ዝግጅት ተደርጎባቸው በእቅድ፣ በመዋቅርና በሰፊው በኦሮሚያ ክልል ነዋሪ በሆኑ የተወሰኑ የብሔርና የሃይማኖት ቡድኖች አባላት ላይ ያነጣጠሩ ይመስላሉ። የእነዚህ ጥቃቶች እጅግ አሳሳቢ የሚያደርጋቸው ነገር ውሰጥ አንዱ በመንግሥት የጸጥታ ኃይልና አስተዳደራዊ መዋቅር ድጋፍ የተፈጸሙ መሆናቸው ነው።

    ስለሆነም የእነዚህ ጥቃቶች ሁኔታና ያደረሱት የጉዳት ዓይነትና መጠን እውነቱ መታወቅ ያለበት ጉዳይ ነው። እንደዚህ ያለ ፍጅት እንዳይደገም እርምጃ መወሰድ ይኖርበታል። በዚህ ድርጊት የተሳተፈ ወይም ድርጊቱ እንዲፈጸም ያደራጀ፣ የቀሰቀሰ፣ በገንዘብ የደገፈ ማንኛውም ሰው ተጠያቂ መሆን ይኖርበታል። በወንጀሎቹ ጉዳት ደረሰባቸውን ወገኖች የፍትሕ ጥያቄ በከንቱ እንዳይቀር ወንጀለኞቹን ተጠያቂ ማድረግ፤ እንዲሁም ተጎጂዎቹን መልሶ ለማቋቋም አስፈላጊ ነው።

    እውነትን የማግኝትና ፍትሕን የማረጋገጥ ጉዳይ ለመንግሥት ብቻ የሚተው አይደለም። እነዚህን አሰቃቂ ወንጀሎችን የመመርመርና የመሰነድ ሥራ ሙያዊና ተዓማኝነት ባለው መለኩ መከናወን አስፈላጊነቱ የሚያጠያይቅ አይደለም።

    እነዚህን ጉዳዮች ከግምት በማስገባት፥ በሰሜን አሜሪካ በጥብቅና (ሕግ) ሙያ በተሰማሩ ባለሙያዎች የሚመራ የበጎ ፋቃደኞች ቡድን የሰኔውን ጥፋቶች (ፍጅት) በሚመለከት መረጃ በማሰባሰብ የተሟላ ሪፖርት ለማዘጋጀት ተቋቁሟል። ይህ ሪፖርት ለወንጀሎቹ ተጠያቂ የሆኑ ሰዎች፣ ቡድኖች ተቋማት ከፍትህ እንዳያመልጡ ለሚደረገው ጥረት ይረዳል።

    የዚህ ቡድን አባላት ከማንኛውም ድርጅት ጋር ንክኪ ያለን አለመሆኑን እየገለጽን፥ የዓላማችን ደጋፊ ከሆኑ ግለሰቦችና ተቋማት ድጋፍ ለመቀበል ግን ዝግጁ መሆናችንን እንገልጻለን።

    በዚህም መሠረት፥ ማንኛውም ወንጀሎቹን በቀጥታ የተመለከተ ወይም ስለወንጀሎቹ አስተማማኝ መረጃ ያለው ሰው ምስክርነት እንድትሰጠን(ጭን) ወይም የሰነድ ወይም የኦዶቪዡዋል ማስረጃዎችን እንድትልክልን(ኪልን) ጥሪ እናቀርባለን። ምስክርነት የሚሰጠን ወይም ሌሎች ዓይነት ማስረጃዎችን የሚሰጠን ሰው ራሱ(ሷ) ተጎጂ የሆነ(ች) ወይም የተጎጂው(ዋ) የቤተሰብ አባል፣ ዘመድ፣ ጓዳኛ፣ ጎረቤት ወይም መንደርተኛ የሆነ(ች) መሆን አለበት(ባት)። የምስክሮችን ማንነት በሚስጥር የሚያዝ ሆኖ፥ በሪፖርቱ ላይ ሊጠቀስ የሚችለው በግልጽ በተሰጠ የምስክሩ ፈቃድ ብቻ ይሆናል።

    ምስክርነት ለመሰጠት በቡድናችን የኢሜል አድራሻ forallethiopia@gmail.com ያሳውቁን። ከቡድናችን አንዱ አባል በስልክ ወይም እርስዎ በሚመርጡት የመገናኛ መንገድ ግንኙነት በማድረግ የምስክርነት ቃልዎን እንቀበላለን።

    በተጨማሪም የፎቶና የቪዲዮ ማስረጃዎችንም በኢሜል አድራሻችን forallethiopia@gmail.com የምንቀበል መሆኑን እንገልጻለን። ማንኛውም የምንሰበስበው ማስረጃ እውነተኝነትና አስተማማኝነትን የምናጣራ መሆናችንን እንገልጻለን።

    ይህንን መልዕክት በእንግሊዝኛ ለማንበብ እዚህ ጋር ይጫኑ

    በኦሮሚያ ክልልና አዲስ አበባ ከተማ በሰኔ ወር 2012 ዓ.ም.  የተፈጸመውን ፍጅትን የሚያጣራ – በሰሜን አሜሪካ የሕግ ባለሙያዎች ቡድን
    ሐምሌ 11 ቀን፥ 2012 ዓ.ም.

    [caption id="attachment_15116" align="aligncenter" width="600"]Call for evidence regarding June/July 2020 massacre in Oromia, Addis Ababa, Harar and Dire Dawa በኦሮሚያ ክልል፣ አዲስ አበባ፣ ሐረር እና ድሬዳዋ ከተሞች የተፈጸመውን ፍጅት ለመጣራት መረጃ ለመሰብሰብ የተላለፈ ጥሪ Call for evidence regarding June/July 2020 massacre in Oromia, Addis Ababa, Harar and Dire Dawa[/caption]

    Anonymous
    Inactive

    በየአካባቢያችን የሚገኙ የግጭት ነጋዴዎችን በጋራ እንክላከል ― የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት

    በሀገራችን በየአካባቢው የሚገኙ የግጭት ነጋዴዎችን በጋራ እንከላከል ሲል የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ጥሪውን አቀረበ። የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት በወቅታዊ ሀገራዊ ጉዳዮችን ዙሪያ ዛሬ መግለጫ አውጥቷል።

    ሙሉ መግለጫው እንደሚከተለው ቀርቧል:-

    የተከበራችሁ የሀገራችን ሕዝቦች፥
    ክቡራትና ክቡራን፥

    ባለፈው ሰሞን የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ሞት ተከትሎ ግጭት ጠማቂዎች ባስነሱት ሁከት አያሌ ወገኖቻችን ሕይወታቸው አልፏል፤ የጸጥታ አካላት ተገድለዋል። በመቶ ሚሊዮኖች የሚቆጠር የግለሰቦች፣ የሕዝብና የመንግሥት ንብረት ወድሟል።

    በቅድሚያ በሁከቱ ሕይወታቸው ላለፈው ወገኖቼ የተሰማኝን ሀዘን መግለጽ እወዳለሁ። ለቤተሰቦቻቸውም መጽናናትን እመኛለሁ። መንግሥት ከማኅበረሰቡ ጋር በመሆን የተጎዱትን ለማቋቋም እንደሚሠራ፤ ወንጀለኞቹንም ለፍርድ የማቅረቡን ሂደትና የሕግ የበላይነትን ማስከበሩን እንደሚቀጥል በዚሁ አጋጣሚ በድጋሚ ላረጋግጥላቸው እወዳለሁ።

    ሁላችንም እንደምናውቀው የፖለቲካ መዝገበ ቃላችን የተሞላው ‹ምታው፣ ደምስሰው፣ ቁረጠው እና ፍለጠው› በሚሉ የሞት ቃላት ሲሆን፥ በመሳደድና ማሳደድ ዙሪያ መሽከርከር ከጀመረ ዘመናት ተቆጥረዋል። “ድርጊት ሲደጋገም ልማድ ይሆናል” እንዲሉ አሁን ያለው የፖለቲካ ባህላችን የተቀዳው ባንድ ወቅት እንደቀልድ በጀመርናቸው የሴራ፣ የመገዳደልና በጎራ ተከፋፍሎ ድንጋይ የመወራወር አጉል ልማዳችን ነው። በየአጋጣሚው ሲነገር፣ ሲጻፍና ሲዜም የኖረው ይሄ የተበላሸ ፖለቲካችን በትውልድ ጅረት ተንከባልሎ እነሆ ዛሬ ላይ ደርሷል።

    ይሄው እኛም እንደ መልካም ውርስ የመጠላለፍና የመገዳደል ባህልን ተቀብለን የየዕለት ኑሯችን በቆምንበት መርገጥ፣ ዛሬም ነገም አንድ ቦታ መሽከርከር ሆኗል። ሀገራችንን ወደፊት ለማራመድ የምንሻ ከሆነ ይሄንን ክፉ ውርስ አሽቀንጥረን መጣል ይኖርብናል፤ በመጥፎ ባህል ያደፈ ካባችንን አውልቀን በምትኩ በጋራ የምንበለጽግበትን ካባ ልንደርብ ይገባል። ለውጥ ሰዎችን በሰዎች፣ መሪዎችን በመሪዎች የመቀየር ሂደት ብቻ አይደለም። የተበላሸውን የፖለቲካ ሥነ ልቡና፣ የፖለቲካ ባህልና የፖለቲካ ሥርዓት ጭምር በአዲስ የመቀየር ጉዞ ነው። ተቋሞቻችንን፣ የእርስ በርስ ግንኙነታችንና የፖለቲካ ቋንቋችንን ጭምር መለወጥ ይገባናል። ይሄን ማድረግ ከቻልን እንደሀገርና እንደ ሕዝብ ወደ ምናስበው የብልጽግና ሠገነት እንሻገራለን። ካልሆነም የኋቀርነት አዘቅት ውስጥ ስንደፋደፍ ዘላለም መኖራችን ነው።

    ሁላችንም ልብ ካልን ምንጊዜም ከመከራ የሚያተርፉ አካላት በዙሪያችን እንዳሉ እንረዳለን። የከብት እልቂት ለገበሬ መከራ ቢያመጣም ለጅብ ግን ሠርግና ምላሽ ነው። የዶሮ እልቂት ለባለቤቱ ኪሳራ ለሸለምጥማጥ ደግሞ ትርፍ ነው። የሁለት በጎች ጠብ ጥቅም ካስገኘ የሚጠቀመው ተኩላውን ነው። የሁለት ርግቦች ግብግብ አንጋጦ ለሚጠብቃቸው ድመት በረከት ነው። ምንም መልፋት ሳይጠበቅባቸው ድመቱና ተኩላው በርግቦቹና በበጎቹ ጸብ ምክንያት በቀላሉ ሆዳቸውን ይሞላሉ። በተመሳሳይ በሰዎች ጸብም የሚያተርፉ ሞልተዋል። በእኛም ሀገር አሉ። አሁንም እርስ በእርሳችን እያጋጩን ከፍተኛ ጥቅም የሚያገኙት እነዚሁ ከቅርብም ከሩቅም ሆነው የሚጠብቁ የግጭት ነጋዴዎች ናቸው።

    ለለውጥ ስንታገል ዋነኛው ዱላ የሚሠነዘርብን ከመከራችን ሲያተርፉ ከነበሩ አካላት እንደሆነ ግልጽ ነው። በሁላችንም ቤት ለዘመናት የተዘራ የልዩነት መርዝ አለ። አሁን እዚህም እዚያም ሲፈነዳ የምናየው እሱን ነው። ፈንጂው ዛሬ ቢፈነዳም ከተቀበረ ግን ቆይቷል። የግጭት ፈንጁ ምን እንደሆነ፣ የት የት እንደተቀበረ፣ በማን እንደተቀበረ ማወቅ ለአንድ አካል የሚተው የቤት ሥራ ሳይሆን የእያንዳንዳችን ኃላፊነት ነው። ማወቅም ብቻውን በቂ አይደለም፤ አንድ በአንድ እየተቀለቀመ መክሸፍ ይኖርበታል። ሕዝብ እንዲበጣበጥ፣ አንዱ ብሔር በሌላው ላይ እንዲነሳ፣ አንዱ ሌላውን እንዲገድል፣ ኢትዮጵያውያን የኢትዮጵያውያንን ንብረት እንዲያወድሙ፣ የጥላቻና የሞት ድግስ ቅስቀሳዎች በየሚዲያው እንዲካሄዱ የሚያደርጉት ፈንጂ ቀባሪዎቹ የግጭት ነጋዴዎች ናቸው። አንዳንዶች ከእነሱ ጋር ተባብረው በሕዝብ ላይ ፈንጅዎቹን ያፈነዳሉ። ሳያውቁ ቆመውበት የሚፈነዳባቸውም ይኖራሉ። አንዳቸውም ጉዳትን እንጂ ጥቅም አያስገኙልም። ከእንግዲህ ይበቃል፤ በጉያችን ይዘን ዘወትር መሰቃየት የለብንም።

    የሀገሬ ልጆች፥

    አንገትን እንደ ሰጎን አሸዋ ውስጥ በመቅበር መፍትሔ የምናገኝበት ጊዜ ላይ አይደለንም። አጥፊዎቹን ፊት ለፊት እስካልተጋፈጥናቸው ድረስ የሚያደርሱትን ችግር በመሸሽ ብቻ አናመልጠውም። ላለማየት ጭንቅላትን ጎሬ ውስጥ በመቅበር ዘላቂ መፍትሔ ይገኛል ማለት ዘበት ነው። ዛሬ ጎረቤታችንን የጎበኘ እሳት ነገ ቤታችንን ማንኳኳቱ አይቀርም። ተነጣጥሎ አንድ ባንድ ማገዶ ከመሆን ይልቅ ተባብሮ የተለኮሰውን እሳት እስከወዲያኛው ማሰናበት ይበጃል። ለዚያም ነገሮችን በጥንቃቄ መመልከት፣ ትዕግሥትና አርቆ አስተዋይነት በተሞላበት መልኩ መገምገምና ጥበብ ባለው ሁኔታ ተንቀሳቅሶ ዘላቂ መፍትሔ መስጠት ከእያንዳንዳችን ይጠበቃል።

    ማን ነው በየአካባቢያችን ሰላም እየነሣን ያለው? ከእነማን ጋር ሆኖ ነው የሚበጠብጠን? ለምንድን ነው የሚበጠብጠን? ጥቂት ነውጠኞች የጫሩት እሳት ብዙኃኑን ሲለበልብ ለምንድን ነው እኛስ ማስቆም ያልቻልነው? ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ ማግኘት ከእያንዳንዳችን ይጠበቃል። እሳት ለኳሾቹ እነማን እንደሆኑ፣ ማገዶ እያቀበሉ እሳቱን የሚያባብሱት እነማን እንደሆኑ፣ ዳር ቆመው የሚያዩትና አብረው የሚሞቁት ጭምር እነማን እንደሆኑ ልናውቅ ይገባል። በመንግሥት በኩል እነዚህን ጥያቄዎች በየደረጃው ለመመርመርና አስፈላጊውን ሕግ የማስከበር ርምጃ ለመውሰድ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ቁርጠኞች ነን።

    እሳቱን ማጥፋት ሲገባቸው በቸልታ የሚያልፉት ሰዎች በአንድም በሌላም መንገድ መከራችንን የሚያበዙብን መሆናቸው አያጠያይቅም። የሚወድመው የሀገር ሀብት፣ የሚሞተው የሁላችንም ወገን ነውና ሕጋዊና ሞራላዊ ኃላፊነት እያለባቸው አይተው እንዳላዩ የሚያልፉ አካላት ፈጽሞ ከተጠያቂነት አያመልጡም።

    የተጋረጠብን ችግር እስከወዲያኛው እንዲወገድ ወላጆች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶች እና የየአካባቢው የባህልና የሐሳብ መሪዎች አስተዋጽኦችሁ ከፍተኛ ከመሆኑ አኳያ ያለማመንታት ሚናችሁን እንድትወጡ ጥሪዬን አስተላልፋለሁ። ከምንም በላይ ሕዝባችን አስፈላጊውን ሁሉ ከማድረግ መቆጠብ እንደሌለበት ሊታወቅ ይገባል። እያንዳንዱ ዜጋ ጥፋተኞቹ በማስረጃ ለፍርድ እንዲቀርቡ የበኩሉን ኃላፊነት መወጣት አለበት፤ ከሕግ አስከባሪዎች ጋር ተባብሮ መሥራት፣ የመንደሩንና የከተማውን ሰላምና ልማት ተደራጅቶ መጠበቅ አለበት። በየአካባቢው የተለየ እንቅስቃሴ ስናይ ለምን? ብለን ልንጠይቅ፤ እነማን እንደሆኑ ልናውቅ፤ ከጸጥታ አካላት ጋር በመሆን አጥፊዎችን ለሕግ ልናቀርብ ይገባል። ጎረቤቶቻችንን፣ የልማት ተቋማትን፣ የንግድ ድርጅቶችን፣ ሕዝባዊ ንብረቶችን፣ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶችን፣ የእምነት ተቋማትን፣ የትምህርትና የጤና ተቋማትን በጋራ እስካልጠበቅናቸው ድረስ ነገ የጉዳቱ የመጀመሪያ ሰለባዎች እኛው ስለመሆናችን ነጋሪ አያሻንም።

    ለሚያልፍ ጊዜ የማያልፍ ጠባሳ እንዲቀመጥብን መፍቀድ የለብንም። የትላንቶቹ ጠበሳ ስላቆዩልን እኛ የዛሬዎቹ ምን ያህል አበሳ እያጨድን እንደሆነ ሁላችንም የሚገባን ይመስለኛል፤ ስለሆነም ከዚህ ስህተት ተምረን ዳግም አበሳው ወደ ልጆቻችን እንዳይሻገር ማድረግ የእያንዳንዳችን ኃላፊነት ነው። በጉያችን ታቅፈናቸው የሚዘርፉን፣ የሚያቃጥሉን፣ የሚያበጣብጡንና የሚያገዳድሉን ሰዎች የጊዜ ጉዳይ እንጂ የእጃቸውን ማግኘታቸው፤ ከእነሱ አልፎ በልጆቻቸው በኩል ብድሩን መክፈላቸው አይቀሬ ነው።

    ውድ ኢትዮጵያውያን፥

    ሀገሩንና ሕዝቡን እንደሚወድ ዜጋ ከእያንዳንዳችን ሁለት ነገሮች ይጠበቁብናል። ከተጎዱ ወገኖቻችን ጎን መቆምና አለኝታነታችንን ማሳየት አለብን። የቦታ መቀያየር ይሆናል እንጂ እኛም አንድ ቀን በተጎጂዎች ቦታ የማንቆምበት ምንም ምክንያት የለም። ስለሆነም በሞራል፣ በኢኮኖሚና በባህላዊ መንገድ ደግፈን ተጎጂዎችን ወደነበሩበት እንመልሳቸው። የተቃጠለና የወደመ ንብረታቸውን ለመተካት አጋርነታችን እናሳያቸው፤ ቁስላቸው ጠገግ እስኪል እናክማቸው፤ የፈረሰ ቤታቸውን እንገንባላቸው። የማይተካ ሕይወታቸውን ለተነጠቁ ዜጎቻችን ጸሎት፣ ለሟች ቤተሰቦች መጽናናት እንዲያገኙ እናድርግ። በሁሉም ዘርፍ ያሉ መሪዎች ለዚህ ዓይነቱ እንቅስቃሴ ግንባር ቀደም ሆነው መልካም አርአያነታቸውን እንደሚያስመሰክሩ እተማመናለሁ።

    ሰላማችንን ለማስጠበቅ ደፋ ቀና ሲሉ የተሰዉት ፖሊሶችና የጸጥታ አስከባሪዎች ያለእነሱ ትጋትና መሥዕዋትነት የሚደርሰውን አደጋ በቀላሉ መቆጣጠር ባልቻልን ነበር። ለሀገርና ለሕዝብ ደኅንነት ሲሉ የቆሰሉና የሞቱ የሕግ አስከባሪዎች የከፈሉት የሕይወት ዋጋ በእያንዳንዳችን ልብ ውስጥ በክብር የሚታተም ስለመሆኑ አልጠራጠርም። ለሟች ቤተሰቦቻቸው፣ ለወላጅና ለልጆቻቸው ጭምር ተገቢውን ክብር እንሰጣለን።

    በመንግሥት በኩል ዐቅም በፈቀደ መጠን የተጎዱትን ንጹሃን ዜጎችና የሕግ አስከባሪዎች ለመደገፍና ለማቋቋም ይሠራል። በሌላ በኩል የችግሩን ነዳፊዎች፣ ጠንሳሾች፣ ተልዕኮ ተቀባዮችና ፈጻሚዎችን በየደረጃው መርምሮና አጣርቶ ለሕግ ያቀርባል። ይሄን መሰል ክስተት ዳግም እንዳይፈጠርም ማኅበረሰቡን ያሳተፈ የጸጥታ አካላት ሥምሪትን አጠናክሮ ይቀጥላል።

    ከዚህ በተረፈ ሁላችንም ውድመትና ጥፋት ከእንግዲህ በሀገራችን ላይ እንዳይደገም አምርረን እምቢ ማለት ይኖርብናል። ከሰሜን እስከ ደቡብ፣ ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ ለፖለቲካ ትርፋቸው ሲሉ በየሚዲያው ‹በለው፣ በለው› የሚሉ አካላትን አሁን በግልጽ ነቅሰናቸዋል። በየአካባቢያችን የሚገኙትን የግጭት ነጋዴዎች በሚገባ አውቀናቸዋል። መረባቸውን እየበጣጠስነው ነው። ለጊዜው የተደበቁ የሚመስላቸውም በቅርቡ አደባባይ ይወጣሉ። እሳቱን ለኩሰው ጢሱ እንዳይሸታቸው መሸሽ፤ ፈንጂውን ወርውረው ፍንጣሪ ሳይነካቸው እስከመጨረሻው ማምለጥ አይችሉም። ሰላም ወዳዱ ሕዝባችን በእሳት እየተቃጠለና ሕይወቱን እየተነጠቀ ከእንግዲህ ይቀጥላል ማለት ዘበት ነው። አብሮነትን የሚፈልገው ዜጋችን፣ ለማደግና ለመበልጸግ ሌት ተቀን ደፋ ቀና የሚለው ሕዝባችን እየተጎዳ የግጭት ነጋዴዎቹ በምቾት አይቆዩም።

    በሕዝብ መከራ ካላተረፍን ለሚሉ፤ በምስኪን ዜጎች ሞት ሥልጣን ለመያዝ ለሚቋምጡ ራስ ወዳዶች ‹አሻንጉሊት› መሆን ከእንግዲህ ይበቃል። ሰላማችንና ልማታችን፣ ዕድገታችንና ብልጽግናችን ደንታቸው ከሆኑ አካላት ጋር አበሳን እንጂ መልካም ነገርን ስለማናጭድ ከጉያችን ፈልቅቀን ብቻቸውን ይቆማሉ። ምክር ካልመለሳቸው መከራውን ፈልገዋልና በሚገባቸው መንገድ እንዲጓዙ እንተዋቸዋለን።

    ክቡራትና ክቡራን፥

    የሐሳብ ልዩነት ጌጥ እንጂ እርግማን አይደለም። የተሰማንን መግለጽና ጥያቄዎቻችንን ያለ ስጋት ማንሳት እስካዛሬ የታገልንለት ወሳኙ መብታችን ነው። የዚያኑ ያህል በሀገራችን ነገሮች በሥርዓት እንዲከናወኑ፣ የአንዱ ጥቅም የሌሎችን መብት እንዳይጋፋ እና ዜጎች ሰላምና ደኅንነታቸው ተጠብቆላቸው በሀገራችን እንዲኖሩ ማስቻል የሁሉም ኢትዮጵያዊ ምኞት ነው። ኃይል እስካልተቀላቀለበት ድረስ የሐሳብ ልዩነትን በሰላማዊ መንገድ ማስተናገድ ለዘመናት የታገንለትን መብት ከማጎናጸፍ ባለፈ የሌሎች ዜጎችን ሰላምና ደኅንነት እንዲጠበቅ ያደርጋል። ሐሳብ የሚሞገተውም የሚሸነፈውም በሌላ ሐሳብ እንጂ በጉልበት፣ በነውጥና በአመጽ አይሸነፍም፤ ተሸንፎም አያውቅም። መነጋገር፣ መከራከርና መወያየት እንጂ መጠፋፋት ሥልጣኔን አምጥቶ እንደማያውቅ ማገናዘቢያ አዕምሮ ያለው ሰው ሁሉ በቀላሉ የሚረዳው ሐቅ ነው። ወገኖቼ፣ ሌላው መታወቅ ያለበት ጉዳይ የምንገኝበት ወቅት ብዙ ጊዜ የማይሰጡ ፈተናዎች ከፊታችን የተደቀኑበትና ወሳኝ ድሎችን የምናሳካበት ወቅት እንሆነ ሊረሳ አይገባም። የግብርና ሥራችን ሳይስተጓጎል መከናወን አለበት። ምርታማነትን በመጨመር ከውጭ የምናስመጣውን የምግብ እህል ጭምር ሊተካ በሚቻልበት አኳኋን ሥራችንን መቀጠል ይኖርብናል። ከገጠር ግብርናችን በተጨማሪ የከተማ ግብርና ላይ የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ። አምራች ኢንዱስትሪው የኮሮና ወረርሽኝን ሁለንተናዊ ተጽዕኖ ለመቋቋም የሚያስችሉ ምርቶችን ለማምረት ሌት ተቀን መድከም አለበት። ከዚሁ ጎን ለጎን እየተባባሰ የመጣውን የኮሮና ወረርሽኝ ተቋቁመን ለመዝለቅ የጥንቃቄ፣ የምርመራና የሕክምና ተግባሮቻችንን ሳንዘናጋ እንፈጽማለን። የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታችንን እያጠናቀቅን በዕቅዱ መሠረት የመጀመሪያውን የውሃ ሙሌት ሥራችንን በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ እናከናውናለን። በዚህ ክረምት ለመትከል ያቀድነው የአምስት ቢሊዮን ችግኞች “የአረንጓዴ አሻራ” መርሐ ግብርም ጥንቃቄ ባልተለየው መልኩ ተግባራዊ እናደርጋለን።

    ምንም እንኳን ዛሬ የደረሰብን ፈተና ቢያሳምመንም የምንሠራው ለሀገር ነውና የነገውን ማየት አለብን። ሕዝብና ሀገር ይቀጥላሉ። ትውልድ ይቀጥላል። የተሻለ ትውልድ ፈጥረን የተሻለች ሀገር ማስረከብ ደግሞ ከእኛ የሚጠበቅ የቤት ሥራ ነው። ነገሮች ወደ በጎ እልህና ቁጭት እንጂ ወደ መጥፎ ቁዘማና ትካዜ ሊወስዱን አይገባም። ችግሮች ትምህርት እንጂ እሥር ቤት ሊሆኑብን አይገባም። ሕዝብ መሥራት ያለበትን በአግባቡ ከሠራ፤ መንግሥትም ያለበትን ኃላፊነት በብቃት ይወጣል። ከከባድ ክረምት ማዶ መልካም አዲስ ዘመን ቆሞ እንደሚጠብቀን ሁሉ የሌሊቱን ግርማ የሚያሸንፍና ጽልመቱን የሚደመስስ የብርሃን ጸዳል ማልዶ ወደኛ እንደሚገሠግሥ ሁላችንም እናውቃለን።

    ኢትዮጵያ በልጆቿ ጥረት ታፍራ፣ ተከብራና በልጽጋ ለዘላለም ትኑር!
    ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!
    የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት
    ሐምሌ 10 ቀን 2012 ዓ.ም.

    የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት

    Anonymous
    Inactive

    የሕግ የበላይነትን ማስከበር እና የዜጎችን ደኅንነት ማስጠበቅ የሀገር ህልውና መሠረት ነው!
    ከኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የተሰጠ ምግለጫ

    በቅርቡ በልጃችን አርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያ እና ይህን ተከትሎ በሀገራችን በደረሰው የንፁሃን ዜጎች ሞትና የንብረት ውድመት የተሰማንን ጥልቅ ሃዘን እየገለፅን ለሟች ቤተሰቦችና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ በድጋሚ መፅናናትን እንመኛለን።

    በአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳ ሞት ምክንያት ሁላችንም ሀዘን እና የልብ ስብራት ውስጥ እንዳለን፥ ግድያውን ተከትሎ የደረሰው የበርካታ ዜጎቻችን ሞትና ከፍተኛ የንብረት ውድመት ሀዘናችንን እጅግ መራር አድርጎታል። የአርቲስቱ ግድያ እና እሱን ተከትሎ በብዙ ዜጎች ሕይወት እና ንብረት ላይ የደረሰው ጥፋት እጅግ አሳሳቢ፣ አሳፋሪ እንዲሁም በሁሉም ኢትዮጵያዊያን ዘንድ የተወገዘ እና በሀገራችን በምንም ዓይነት ሊደገም የማይገባው ድርጊት ነው።

    ኢትዮጵያውያን ከአምባገነናዊ አገዛዝ ነፃ ለመውጣትና የሚመጥነንን ሕዝባዊ አስተዳደር ለመትከል ረጅም ጊዜያትን በትግል አሳልፈናል፣ ብዙ ዋጋም ተከፍሏል። ዋጋ የተከፈለባቸው ሙከራዎች የከሸፉ ቢሆኑም በዚህ ሁሉ የታሪክ ውጣ ውረድ ግን የሀገር ህልውና በዚህ መልኩ ተፈትኖ አያውቅም።

    ሀገራችን ከነችግሮቿ ዘመን ተሻጋሪ ታሪክ ያላት፣ የምናወሳቸው እና የምንዘክራቸው ዛሬ ላለው ትውልድ መኩሪያ እና መመኪያ የሆኑ የማንነታችን መገለጫዎች የሞሉባት ሀገር ናት። በአንድ ወቅት አርቲስ ሃጫሉ እንደተናገረው ኢትዮጵያችን በብዙ የማንነት ቀለማት ኅብር የተዋበች ሀገር ናት። ኢትዮጵያዊነታችን በልዩነት ውስጥ የተጋመደ አንድነት መሆኑ ሃቅ ሆኖ እያለ የዘውግ ማንነት እና የቋንቋ ልዩነቶችን እየመዘዙ በሀገር አንድነት ላይ አደጋ መጣል ማንም አሸናፊ ወደማይሆንበት የቀውስ አዙሪት ውስጥ እንደሚከተን ከመቼውም ጊዜ በላይ አሁን ግልፅ ሆኗል።

    ሀገራችን ኢትዮጵያ ላለፉት አስርተ ዓመታት በተለይም በሕወሃት/ኢህአዴግ ከፋፋይ አገዛዝ ስር ያሳለፈችው የፖለቲካ ትርክት ምን ያህል አደገኛ እንደነበር በግልፅ አይተናል። የህወሓት/ኢሕአዴግ አገዛዝ ምንም እንኳን ያረጀና በሕዝብ ትግል የተሸነፈ ቢሆንም፤ የተከላቸው መርዘኛ ቅራኔዎች በአጭር ጊዜ የሚነቀሉ አልሆኑም። እያየን ያለነው የንፁሃን ዜጎች ሕይወት መቀጠፍ እና በረጅም ጊዜ ድካም የተገነቡ ሀብቶች ውድመት የዚሁ አገዛዝ ቅሪቶች እንጂ የኢትዮጵያዊያን እሴቶች አለመሆናቸውን እንገነዘባለን።

    በሰሞነኛው ብጥብጥ የደረሰው የበርካታ ዜጎች ሕይወት መቀጠፍና ከፍተኛ የንብረት ውድመት እጅግ አስከፊና የትውልዱ ማፈሪያ ከመሆኑ በተጨማሪ በዘውግ ማንነት ላይ የተመሠረተ የፖለቲካ አካሄድ ወደ መቀመቅ እየወሰደን እንደሆነ ሕዝብና መንግሥት ከበቂ በላይ ትምህርት አግኝተዋል ብለን እናምናለን። በኢዜማ እምነት እውነተኛ ፌዴራሊዝም ሁሉም ራሱን በራሱ የማስተዳደር እና በመረጠው የመተዳደር መብት እንደሆነ እያስረገጥን ፖለቲካችን ከዘውግ እና ከሃይማኖት ካልተላቀቀ በስተቀር መጨረሻችን እጅግ አደገኛ እንደሚሆን በተደጋጋሚ ስንገልፅ ነበር። በዘውግ እና በሃይማኖት ልዩነት ላይ የተንጠለጠለ የፖለቲካ አካሄድ ወደ መጠፋፋት እየወሰደን መሆኑን በመገንዝብ በማስተዋል እና በመረጋጋት እንድንጓዝ፤ በአንድ ሀገር ለውጥን ማዋለድ ብዙ ትግልና መስዋትነትን የሚጠይቅ እንደዚሁም ከፍተኛ ትዕግስትና ማስተዋል የሚሻ መሆኑን በተደጋጋሚ ስንገልፅ ብንቆይም ይህ አቋማችን ባንዳንድ ወገኖች እንደመለሳለስ ሲቆጠር ቆይቷል።

    ሰሞኑን በተከሰተው ቅስም-ሰባሪ ጥፋት በሀገራችን ፖለቲካ የሚከተሉትን አበይት ነጥቦች በተለየ እንድንታዘብ አስገድዶናል። እነዚህም፦

    • በድንገት የሚፈጠር ነውጥ ሀገራችንን ከማትወጣው የከፋ አዘቅት ውስጥ ሊያስገባት እንደሚችል፣
    • በዘውግ እና በሃይማኖት ላይ የሚሰበክ የፖለቲካ ትርክት፤ ከዚህ ትርክት ተነስቶ የሚቆሠቆሰው ፍጹም ስሜታዊ ጥላቻ እና ጥላቻው የሚቀሰቅሰው የደቦ እንቅስቃሴ፤ የሰውን ልጅ ከሰብዓዊነት ማማ አውርዶ ወደ አውሬነት ሊቀይረው እንደሚችል ተገንዝበናል። በሌላ መልኩ ደግሞ በዚህ ዓይነት ፍጹም ስሜታዊ ሁኔታም ውስጥ ብሔራቸውን እና ሃይማኖታቸውን ተሻግረው፤ ለሰብዓዊነት እና ለጋራ ህልውናችን ዘብ ቆመው፤ በሁከቱ ምክንያት ለችግር የተዳረጉ ዜጎችን በመሸሸግ እና በማስጠለል የንፁሀንን ነፍስ የታደጉ የምንኮራባቸው ኢትዮጵያዊያን መኖራቸውን፣ ይህንን የመሰለው ዘመን ተሻጋሪ የኢትዮጵያዊያን እሴት ቢፈተንም በዚህ ዘመንም መቀጠሉን፣
    • ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጭምር እንደገለፁት፥ ችግር ፈጣሪዎች በመንግሥት አስተዳደር መዋቅሮች ውስጥ የሚገኙ ኃይሎች ጭምር መሆናቸውን፤
    • ችግሩ በተከሰተበት ጊዜ የመንግስት የፀጥታ ኃይሎች በአንዳንድ አካባቢዎች የዜጎች ሕይወት በአደባባይ ሲቀጠፍ፣ የሀገር ሃብት ሲወድም አይተው እንዳላዩ የማለፍ ሁኔታ እንደነበር፤ የዚያኑ ያክል ደግሞ የሕግና የሞራል ኃላፊነታችውን በመወጣት እየሞቱና እየቆሰሉ ማኅበረሰቡን ከጥቃት የተከላከሉ ብዙ የጸጥታ ኃይሎችን ያየንበት መሆኑ፣
    • በሁሉም የሀገራችን ክፍሎች በተለይም በመዲናችን አዲስ አበባ በወታደራዊው የደርግ አገዛዝ ውድቀት ማግስት የፀጥታ ኃይሎች ባልተደራጁበት እና ከፍተኛ የመንግሥት አስተዳደር ክፍተት በነበረበት ወቅት ነዋሪው ለሰላምና መረጋጋት አኩሪ አሰተዋፅኦ እንዳበረከተ ሁሉ፥ ዛሬም ሕዝባችን በመኖሪያ ቀዬው ራሱን በማደራጀት ራሱን፣ ቤተሰቡን፣ ንብረቱን እና አካባቢውን ለመጠበቅ ያሳየው ቁርጠኝነት እጅግ የሚመሰገን ተግባር ሆኖ ጎልቶ መታየቱ፤

    ከሰኔ 22 በኋላ በጉልህ የታዘብናቸው ክስተቶች ነበሩ።

    በቅርቡ የተከሰተው እና የሀገርን አንድነት የተፈታተነው አውዳሚ ክስተት ለጊዜውም ቢሆን መክሸፉ ችግሩ ዘላቂ የሆነ መፍትሄ አግኝቷል ማለት አይደለም። የሀገራችንን አንድነት የሚፈታተኑ ብዙ ችግሮች ሊያጋጥሙን ይችላሉ። በዚህ ጊዜ እንደ ተፎካካሪ ድርጅቶችም ሆነ እንደ ዜጎች ያለብን ኃላፊነት ምን ያህል ከባድ እንደሆነ ማወቅና በተግባር ለማሳየት መዘጋጀት ይጠበቅብናል። የሀገርን አንድነት እና ሰላም ባጭር ጊዜ፤ ለዘላቂው ደግሞ ለዴሞክራሲያዊ የፖለቲካ ማኅበረሰብ ምሥረታ፤ ከምሩ የቆመ መንግሥት እስካለን ድረስ (በተለያዩ የፖለቲካ እና የፖሊሲ አመለካከት የምናምን የፖለቲካ ድርጅቶችና ዜጎች ብንሆንም እንኳን) ይህን ማዕከላዊ መንግሥት ለማዳከም፤ በዚህም የተለያዩ የጦር አበጋዞች የሚርመሰመሱበት የእርስበርስ ግጭት ውስጥ ሊዳርጉን የሚፈልጉ ኃይሎች የሚያደርጉትን ዘመቻ በማስቆም በኩል ሙሉ ትብብር ማድረግ እንዳለብን ልናውቅ ይገባል። በእነኝህ አንኳር ጉዳዮች ላይ የምንስማማ የፖለቲካ ድርጅቶችም ሆነ ሌሎች የሲቪክ ማኅበረሰብ ተቋማት እና አባላት ለሀገራችን መኖር እና ለሕዝቧ ሰላም ባንድነት በተግባር መቆም እንደሚኖርብን መገንዘብ ያለብን ጊዜ ላይ ደርሰናል።

    ኢዜማ በሀገር አንድነትና በማኅበረሰባችን ሰላም ጉዳይ ላይ ምንም ዓይነት ድርድር መኖር የለበትም ብሎ ያምናል። እነኝህን ሁለት መሠረታዊ እሴቶች በዋናነት የማስጠበቅ ኃላፊነት ያለበት ደግሞ ሀገራዊ መንግሥቱ ነው። ያለ ሀገር ፖለቲካም ሆነ ዴሞክራሲ ትርጉም የላቸውም። ለዘላቂው የሀገር አንድነት እና ሰላም ከዴሞክራሲያዊ ፖለቲካ መኖር፤ ከፍትህ መኖር፤ ከዜጎች እኩልነት መረጋገጥ ወዘተ… ጋር በጥብቅ የተቆራኙ መሆናቸውን እናምናለን። ስለሆነም ሁሉም የሀገራችን ዜጎች ይህን ፈታኝ ጊዜ በትግስት፣ በማስተዋልና በጥንቃቄ እንዲሻገሩት እና የሀገራችንን አንድነት እና ሰላም በማስጠበቅ ረገድ ሁላችንም ያለብንን ኃላፊነትና ድርሻ የመወጣት ግዴታ እንዳለብን በማሰብ ኢዜማ በሚከተሉት ወሳኝ ነጠቦች ላይ በድርጅታችን መርሆዎች ላይ የተመሠረተ የአቋም መግለጫ አውጥተናል፤

    1. የሰው ልጅ ማኅበራዊ ፍጥረት በመሆኑ በተለይም ፈታኝ ጊዜያትን ያሳለፈው፣ ከፍጥረታት ልቆ የቆየው እና ተፈጥሮን ገርቶ ትውልድን ማስቀጠል የቻለው በተለያዩ ማኅበራዊ አደረጃጀቶች አቅም ፈጥሮ በመተጋገዝ ነው። በአደረጃጀቱ አያሌ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎችን ተቋቁሞ አሳልፏል፤ ከእነዚህም አደረጃጀቶች መካከል «መንግሥት» ትልቁ የሰው ልጅ አደረጃጀት ሲሆን በውስጡ በርካታ አደረጃጀቶችን እንደያዘ ግልፅ ነው።

    የእነዚህ አደረጃጀቶች ዋና መሠረት ደግሞ የቆየው ማኅበራዊ አደረጃጀት ነው። በሀገራችንም በርካታ የቆዩ የአደረጃጀት ዓይነቶች አሉ። ይህንን ማጠናከር የሀገርን ህልውና እና የዜጎችን ደኅንነት ለማስጠበቅ በእጅጉ ይረዳል የሚል እምነት አለን። ማኅበራዊ ፍትህ በነገሰባቸው በርካታ ሀገራት በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ነፃ ማኅበራዊ አደረጃጀቶች አሉ። እኛም ሀገር ሰሞኑን በተፈጠረው ችግር ሕዝቡ በየመኖሪያ ቀዬው ተደራጅቶ ሰላሙን ሲያስከብር ተመልክተናል። በተለይም በአዲስ አበባ እና በአንዳንድ ከተሞች የታየው አደረጃጀት ትልቅ ትምህርት ሰጪ ነበር። አዲስ አበባ ከተማ ሁሉንም የሀገራችንን ማኅበረሰቦች አቅፋ የምትኖር፤ በዓለማችን በቀዳሚነት ከሚጠቀሱ የዲፕሎማቲክ ከተሞች አንዷ እንደመሆንዋ በውስጧ ያቀፈቻቸው ዜጎች በነፃነት የሚንቀሳቀሱባትና ልዩልዩ አስተሳሰቦችና እምነቶች ተከባብረው የሚኖሩባት ከተማ ናት። ይህን መሰሉ ማኅበራዊ እሴት ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት እናምናለን። ይሁን እንጂ ሰሞነኛው ክስተት እንደሀገር ለከፍተኛ ውርደት የዳረገን የታሪካችን ማፈሪያ ሆኖ አልፏል። በሌላ በኩል የአዲስ አበባ ሕዝብ ዘመኑን በሚመጥን እና በሠለጠነ መንገድ በዘውግ ማንነት፣ በሃይማኖት ወይም በፖለቲካ አመለካከት ልዩነት ሳያደርግ በመደራጅት ቤተሰቡን እና አካባቢውን ከጥፋት ከመከላከሉም ባሻገር ከተማዋን እጅግ ከከፋ ውድመት ታድጓታል። ለዚህም አክብሮት እና ምስጋናችንን ለማቅረብ እንወዳለን።

    ይህን ዓይነቱ መሰባሰብ ለወቅታዊ ችግሮች ብቻ ሳይሆን ለዘላቂውም ጭምር ጠቀሜታው የጎላ ስለሆነ የማኅበረሰቡ የቆዩ አደረጃጀቶች እንዲበረታቱ መሥራት ያስፈልጋል። ከዚህ አንፃር አሁን እየታዩ ያሉ አደረጃጀቶችን በየአካባቢው በሕዝብ በሚመረጡ አካላት ማጠናከር፣ እውቅና መስጠት እና የፀጥታ ጉዳይን በሚመለከት አደራጃጀቶቹን ከማኅበረሰብ አቀፍ ፖሊስ እና የመንግሥት የጸጥታ አካላት ጋር የማጣመሩን ተግባር መንግሥት እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በተቻለ ፍጥነት ተግባራዊ እንዲያደርጉ ጥሪያችንን እናቀርባለን። አደረጃጀቶቹ የጋራ ደኅንነትን ከመጠበቅ በተጨማሪ የከተማዋ ምልክት የሆነውን ሁሉም ዓይነት ማንነቶች ተከብረውባት፣ ዜጎች ተጋግዘው እና ተባብረው የሚኖሩባት ከተማ መሆኗን በቀጣይነት ለማረጋገጥም የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት እንዲወጡ አደራ እንላለን።

    እነዚህ አደረጃጀቶች በሌሎች ኃይሎች እንዳይጠለፉ እና ዜጎች በሚኖሩበት አካባቢ ደኅንነታቸውን ከመንግሥት ፀጥታ አስከባሪዎች ጋር እንዲያስጠብቁ ከማስቻል ያፈነገጠ ዓላማ ማስፈፀሚያ መሣሪያ እንዳይሆኑ ከፍተኛ ጥንቃቄ መደረግ እንደሚገባም ልናሳስብ እንወዳለን።

    1. የደኅንነት እና የፀጥታ ተቋማት ዋና ተግባር የሀገርን ደኅንነት እና የሕዝብን ሰላም ማስጠበቅ ነው። ሰሞኑን ሀገራችን በገባችበት ችግር ዙሪያ ማብራሪያ ሲሰጡ የነበሩ የፀጥታ ተቋማት ኃላፊዎች ችግሩ እዚህ ደረጃ እስኪደርስ የዘገዩት በሆደ-ሰፊነት የፖለቲካውን ምህዳር ለማስፋት መንግሥት በያዘው አቋም ምክንያት መሆኑን ሲገልፁ ሰምተናል። ይህ ተቋማዊ ኃላፊነታቸውን የዘነጋ አካሄድ እና አገላለፅ በቶሎ ሊታረም ይገባል። የዜጎችን ሕይወት እና ንብረት ለከፋ አደጋ ዳርጎ ሆደ-ሰፊነት ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ እንደሆነ መነገር የለበትም። ይህንን የማድረግ መብትም ሆነ የሕግ ድጋፍም የላቸውም። የፀጥታ ተቋማት በየደረጃው ተቀናጅተው በመሥራት እና ሀገርን እና ዜጎችን ከውስጥም ሆነ ከውጭ ጥቃት መታደግ ነው ዋና ተልዕኳቸው። በተለይም በእንደዚህ ዓይነት ወቅት ሕዝብን በማስተባበር አደጋ ከመድረሱ ቀድሞ የማክሸፍ ሥራ በመሥራት፤ አንዴ ከተፈጠረ ደግሞ በፍጹም ቁርጠኝነት ሀገርን እና ሰላማዊ ሕዝብን ከጥቃት መከላከል የፀጥታ አካላት ከምንም ነገር በላይ ቅድሚያ ሊሰጡት የሚገባ ተግባር እንደሆነ በአንክሮ እንገልፃለን።
    2. ለዘመናት የታገልንለት ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት እና የመገናኛ ብዙኃን ነፃነት ሀገርን እና ሕዝብን ለአደጋ እስከሚያጋልጥ ልቅነት ድረስ መሆን እንደሌለበት ደጋግመን ስንገልጽ ቆይተናል። አሁን እንደምናየው የግል የብዙሃን መገናኛዎች የተወሰኑት በፓርቲ ልሳንነት፣ የተወሰኑት ደግሞ በጥቅም አሳዳጅነት ሀገርን እና ዜጎችን አደጋ ላይ ሲጥሉ ሥልጣን የተሰጠው አካል አፋጣኝ እርምጃ መውሰድ ነበረበት፤ አለበትም። ከዚህ አንፃር የግል ብዙሃን መገናኛዎች የሀገሪቱን ሕግና የሙያውን ሥነ-ምግባር ጠብቅው እንዲሠሩ ጥሪ እናቀርባለን። በሌላ በኩል የመንግሥት የመገናኛ ብዙሃን ደግሞ ሚዛናዊነት በጎደለው መልኩ በተለይም የመንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት ቃለመጠይቆችን ብቻ በማስተናገድ መሪ አዘጋገብ እና ፍረጃ ውስጥ መግባታቸው የዜጎችን በፍርድ ቤት ጥፋተኛነታቸው እስኪረጋገጥ ድረስ እንደነፃ የመታየት መብት የሚጋፋ እና የፍትህ ተቋማቱን አካሄድ የሚያዛባ በመሆኑ በአስቸኳይ እንዲያርሙት እናሳስባለን። የመገናኛ ብዙሃን እንዲመሠረት የምንፈልገውን የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መርህ የተከተሉ፣ የሕዝብ መረጃ ማሳወቂያ፣ ማስተማሪያ እና ማረጋጊያ መሆን እንሚገባቸውም በአፅንዖት እንገልፃለን። የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን በሕግ በተሰጠው ሥልጣን መሠረት የብዙሃን መገናኛ ተቋማትን በቅርበት እየተከታተለ የማስተካከያ እርምጃ እንዲወስድም አበክረን እናሳስባለን።
    3. የእውነተኛ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መመሥረት ለዘላቂ ሀገራዊ መረጋጋት መሠረት መሆኑን እናምናለን። ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የሚመሠረተውም በዴሞክራሲያዊ መንገድ ማለትም በእውነተኛ ውይይትና ድርድር ብቻ ነው።

    ይህንን ለማድረግም ሁሉም የፖለቲካ ኃይሎች ዘመናዊ፣ የሠለጠነ ፖለቲካ እና የጨዋታ ሜዳውን ሕግ ያከበረ አካሄድ መከተል ይገባናል። ይሁን እንጂ ከዚህ ቀደምም ሆነ ሰሞኑን የተከሰተው የመገዳደልና የመጠፋፋት ፖለቲካ ወደ ሰለጠነ ፖለቲካ የሚወስደን ሳይሆን ከዚህ ቀደም ዋጋ ወደከፍልንባቸው የተወሳሰቡ ችግሮች ውስጥ መልሶ የሚዘፍቀን አካሄድ ነው። በዚህ ረገድ የሁሉም ድርሻ አስፈላጊ ቢሆንም በሀገር አንድነት፣ በሰላማዊ እና በሠለጠነ የፖለቲካ ትግል እንዲሁም ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የሚደረግ ሽግግርን ከሚያምኑ ወገኖች ጋር ለሚደረግ ውይይት ገዢው ፓርቲ ወሳኝ ድርሻ አለው። በአንድ በኩል የሀገርን ህልውና እና የዜጎችን ደኅንነት ማስጠበቁን አጠናክሮ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ብዙ መስዋዕትነት የተከፈለበትን ሽግግር እውን ለማድረግ የሚያስችል እና ለሁሉም ተሰፋ የሚሰጥ የባለድርሻዎች ውይይት ሳይውል ሳያድር እንዲጀመር እንጠይቃለን።

    1. የሙያ እና የሲቪክ ማኅበራት በአጠቃላይ በዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ፤ በተለይ ደግሞ እንደኛ ሀገር ፖለቲካችንን ሰቅዞ ከያዘው የዘውግ ፖለቲካ ወደ ጤናማ የሀሳብ ፖለቲካ በማሸጋገር እንቅስቃሴ ውስጥ የሚኖራቸው ሚና እጅግ የጎላ እና ሚዛንን ማስጠበቅ የሚያስችል እንደሚሆን ይታመናል። ባለፉት 27 ዓመታት በሀገራችን ሲንቀሳቀሱ የነበሩ የሙያ ማኅበራት በገዢው ፓርቲ ተፅዕኖ ስር የወደቁ እና ተዳክመው የቆዩ መሆናቸውን እንረዳለን።

    ረጅም ጊዜ ከቆየ አምባገነናዊ ሥርዓት ወደ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት የሚደረግ ሽግግር ውስጥ ለረጅም ጊዜ የተጠራቀሙ ዘርፈ ብዙ ችግሮች ሁሉ በቶሎ እንዲፈቱ መጓጓት እና ዜጎች ጥያቄዎቻቸውን እና ፍላጎቶቻቸውን የሚያቀርቡበት እና እንዲመለስላቸው ጫና ለማሳደር ኃይልን የቀላቀለ መንገድ መከተላቸው ትልቅ ተግዳሮት ይፈጥራል። የሙያ እና የሲቪክ ማኅበራት ራሳቸውን ከነበረባቸው ጭቆና ነፃ አውጥተው እና ተጠናክረው የተለያዩ መድረኮችን በመፍጠር እና ተደራሽ የሆኑ ብዙሃን መገናኛዎችን በመጠቀም ስለ ሰላማዊ ተቃውሞን የማሰሚያና ጫና የማሳደሪያ መንገዶች በሰፊው በማስተማር ከሕዝብና ከእውነት ጎን ቆመው ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ እና ለሀገር መረጋጋት የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ ጥሪ እናቀርባለን።

    1. በሀገራችን በተደጋጋሚ ጊዜ ፖለቲካዊ ሽፋን እየተሰጣቸው ከተነሱ ረብሻዎች ጋር በተያያዘ በርካታ የንፁሃን ዜጎች ሕይወት በከንቱ ሲቀጠፍ እና የግል ባለሃብቶችም ንብረት በሚያሳዝን ሁኔታ ሲወድም እየተመለከትን ነው። እነዚህ ረብሻዎች እንዳይከሰቱ፣ ከተከሰቱም የሰው ሕይወት እና ንብረት ላይ አደጋ እንዳያደርሱ መቆጣጠር እና የዜጎችን ደኅንነት የመጠበቅ ኃላፊነት ዋነኛ የመንግሥት ሥራ በመሆኑ፣ መንግሥት ይህን ኃላፊነቱን በሚገባ ሳይወጣ ቀርቶ ጉዳት ለደረሰባቸው ዜጎች እና ቤተሰቦቻቸው እንዲሁም ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ በይፋ ወጥቶ ይቅርታ መጠየቅ እና ከዚህ በኋላ እንደዚህ ዓይነት ጥፋት በፍፁም እንደማይደገም ቃል ሊገባ እና ሊያረጋግጥ ይገባዋል።

    መንግሥት የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን ግድያ እና የአርቲስቱን ሞት ተከትሎ ሕይወታቸውን ያጡ ዜጎች ጉዳይ ባስቸኳይ አጣርቶ ፍትህ እንዲያገኙ ሊያደርግ ይገባል። እንደዚሁም የሀገራችን ኢኮኖሚ ዳዴ በሚልበት በዚህ ፈታኝ ወቅት ባለሀብቶች አንጡራ ሃብታቸውን አፍስሰው የገነቧቸው መሠረተ ልማቶች እንደዘበት ወድመው፣ ተቃጥለው እና ሠራተኞች ተበትነው ማየቱ እጅግ ያሳዝናል። በቀጣይም ሃብታቸውን አፍስስው ሊያለሙ የሚችሉ ባለሃበቶችም ዋስትና ስለማይኖራቸው መዋዕለ ንዋያቸውን ከማፍሰስ ይታቀባሉ። ከዚህ አንፃር በሰሞኑ ክስተት ቤት ንብረታቸውና ትልልቅ የንግድ ተቋሞቻቸው ለወደመባቸው ዜጎች መንግሥት ተገቢውን ካሳ ከፍሎ እንዲያቋቁማቸው አበክረን እንጠይቃለን።

    በመጨረሻም አሁን ያለንበት ሁኔታ ለሀገራችን እጅግ ፈታኝ መሆኑ ግልፅ ነው። ዓለም አቀፍ ስጋት የሆነው የኮቪድ-19 ወረርሺኝ ከዕለት ዕለት እየተስፋፋ መጥቷል። ከአባይ ወንዝ ውሃ አጠቃቀም በተለይም ከህዳሴው ግድብ የውሃ ሙሌት ጋር በተያያዘ ግብፅ የፈጠረችው እሰጥአገባ ያመጣው ጫና ከሀገራችን አልፎ የዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ መነጋገሪያ ሆኗል። ኢትዮጵያውያንም በእነዚህ አንገብጋቢ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ከምንግዜውም በላይ በጋራ መቆም የሚገባን ትክክለኛው ሰዓት ላይ እንገኛለን።

    በመሆኑም የውስጥ ልዩነቶቻችንን በሰለጠነ ፖለቲካ አሰታርቀን እንደሀገር የተደቀኑብንን ተደራራቢ ፈተናችዎች በፅናት ማለፍ ካልቻልን ለትውልድ የምትሆን ሀገር ማሻገር ይቅርና እኛ ራሳችን ከማንወጣው የከፋ አዘቅት ውስጥ ገብተን እንደምንዳክር መረዳት ይኖርብናል። ስለሆነም የሕግ የበላይነትን በማክበር፣ በወንድማማችነትና በእህትማማችነት በመተባበር እና በኢትዮጵያዊ ጨዋነት አሁን ካለንበት ውስብስብ ችግር ወጥተን ሀገራችንን ወደ እውነተኛ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት በጋራ እንድናሻግር ለኢትዮጵያውያን በሙሉ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን።

    የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ)
    ሐምሌ 6 ቀን 2012 ዓ.ም.

    የሕግ የበላይነትን ማስከበር እና የዜጎችን ደኅንነት ማስጠበቅ የሀገር ህልውና መሠረት ነው

    Anonymous
    Inactive

    አርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳን በመግደል የተጠረጠሩ ሁለት ግለሰቦች ተያዙ፤ ኦነግ ሸኔ ከተባለው ቡድን ጋር ግንኙነት አላቸው።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የኢፌዲሪ ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ድምጻዊ ሃጫሉ ሁንዴሳን በመግደል ዋነኛ የተባሉ ሁለት ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ሐምሌ 3 ቀን 2012 ዓ.ም. አስታውቋል። ሦስተኛው ተጠርጣሪ ደግሞ እየተፈተለገ ነው ብሏል።

    ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ክብርት አዳነች አቤቤ ሐምሌ 3 ቀን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አንደኛው ተጠርጣሪ ጥላሁን ያኒ የተባለ ሃጫሉ የተገደለበት ገላን የተባለዉ የአዲስ አበባ አካባቢ ነዋሪ እንደሆነ አስታዉቀዋል። በግድያው ተባባሪ የተባለዉ ሁለተኛ ተጠርጣሪ አብዲ ዓለማየሁም በቁጥጥር ስር መዋሉን ክብርት አዳነች ተናግረዋል።

    ዋነኛ የተባለው ተጠርጣሪ ጥላሁን ያኒ በሰጠው የእምነት ክህደት ቃል መሣሪያውን የተኮሰው እሱ መሆኑን እና ተልዕኮውንም ከኦነግ ሸኔ መቀበሉን ማመኑ ተገልጿል። ጥላሁን ያኒ ለፖሊስ በሰጠው የእምነት ቃል ድርጊቱን የፈፀመው “ኦነግ ሸኔ” ከተባለው ክንፍ በተሰጠው ተልኮ መሆኑን መግለፁን፤ ተልኮውን የሰጡት ግለሰቦችም ሁለት መሆናቸውን አምኖ መቀበሉን ክብርት አዳነች አስረድተዋል።

    ጠቅላይ ዐቃቤ ክብርት ሕግ አዳነች አቤቤ አያይዘው እንደገለጹትም ከበደ ገመቹ የተባለ ሦስተኛ ተጠርጣሪ እስካሁን በቁጥጥር ስር እንዳልዋለ እና በፖሊስ እየተፈለገ ነው።

    የኢትዮጵያ መንግሥት ኦነግ ሸኔ እያለ የሚጠራቸውና ራሱን “የኦሮሞ ነፃነት ጦር” ብለው በሎ የሚጠራው (ከዋናው የኦሮሞ ነጻነት ግንባር ተከፍሎ ጫካ የቀረው) ቡድን ሀገር ወስጥ በተደጓጋሚ ጥቃት እያደረሰ ለንጹሃን ዜጎች ሞት፤ መቁሰል እና ለንብረት መጥፋት ምክንያት እንደሆነ ይታወቃል። ለምሳሌ የካቲት 13 ቀን 2012 ዓ.ም. በኦሮሚያ ክልል የቡራዩ ከተማ ፖሊስ አዛዥን የገደለውና የካቲት 15 ቀን 2012 ዓ.ም. በአምቦ ከተማ ውስጥ ለድጋፍ ሰላማዊ ሠልፍ በወጡ ነዋሪዎች ላይ ቦምብ በመወርወር የአካል ጉዳት ያደረሰው ኦነግ ሸኔ የተባለው ቡድን መሆኑን የኦሮሚያ ክልል አስታውቆ ነበር።

    በታህሳስ ወር 2012 ዓ.ም. ደግሞ የቤኒሻንል ጉሙዝ ክልል ምክር ቤት ሠራተኛ የነበሩት አቶ አብዱላሂ ሳጆር ከአሶሳ ወደ ነቀምት ለሥራ ጉዳይ በመሄድ ላይ እያሉ ዛሬ በታጣቂዎች መገደላቸውን፤ ጥቃቱንም የፈጸመው ትጥቅ ያልፈታው ኦነግ ሸኔ መሆኑን የክልሉ ኮሙኒኬሽን ጉዳዩች ጽ/ቤት አስታውቆ ነበር።

    በምዕራብ ኦሮሚያ በተለያዩ ዞኖች በመንቀሳቀስ የሰላማዊ ሰዎችን ኖሮ እና እንቅስቃሴ የሚያውከውን የኦነግ ሸኔ ቡድን ድርጊት በማውገዝ የቄለም ወለጋ፣ የምዕራብና ምስራቅ ወለጋ እንዲሁም ቡሎ በደሌ የተለያዩ ወረዳዎች ነዋሪዎች ሰኔ 19 ቀን 2011 ዓም የተቃውሞ ሰልፍ አካሂደው ነበር። በሰላማዊ ሰልፉም ላይ ነዋሪዎቹ ኦነግ ሸኔ የተባለው ቡድን እንደማይወክላቸው፣ ይልቁንም የሕዝቡን ሰላም እያደፈረሰ መሆኑን ገልጸው ነበር።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳ ገዳዮች ኦነግ ሸኔ ከተባለው ቡድን ጋር ግንኙነት አላቸው

    Anonymous
    Inactive

    በኦሮሚያ ክልል “ከአንድ ብሔር ተወላጅ ናቸው” በተባሉ ዜጎች ላይ ዘግናኝ ጥቃት መድረሱን ነዋሪዎች ተናገሩ ― የአሜሪካ ድምፅ

    በኢትዮጵያ የአንድ ብሔር ተወላጅ ናቸው በተባሉ ዜጎች ላይ በተነጣጠረ ጥቃት ቁጥራቸው ለጊዜው ያልታወቁ ኢትዮጵያውያን በአሰቃቂ ሁኔታ መገደላቸውን ከጥቃቱ የተረፉ ነዋሪዎች ለአሜሪካ ድምፅ (ቪኦኤ) ገልፀዋል።

    በሌላ በኩል ጥቃቱ የተፈፀመው “ከአንድ ብሔር የመጡ ናቸው” የሚሉ ሰዎች ላይ በማነጣጠር ቢሆንም፥ ሕብረተሰቡ የተጋባና የተዋለደ በመሆኑ ተጎጂ ከሆኑት ውስጥ ከተለያየ ብሔር የተወጣጡ ሰዎች መሆናቸውን ነዋሪዎችም፣ የዞኑ አስተዳዳሪም ተናግረዋል።

    ሰኞ ሰኔ 22 ቀን 2012 ዓ.ም. ምሽት በአዲስ አበባ ገላን ኮንደሚኒየም አካባቢ ባልታወቁ ሰዎች የተገደለውን ዝነኛውን የኦሮሚኛ ቋንቋ ድምፃዊ ሃጫሉ ሁንዴሳን ሞት ተከትሎ በተለያዩ የኦሮሚያ ክልል ከተሞች እጅግ አሰቃቂ በሆኑ ሁኔታዎች የተፈጸሙ ግድያዎች፣ አካል ማጉደል፣ ዘረፋና በከፍተኛ ሁኔታ ንብረት ማቃጠል መከሰቱንም ተጎጂዎችና የዓይን እማኝ መሆናቸውን የተናገሩ ለአሜሪካ ድምፅ (ቪኦኤ) ገልፀዋል።

    አንዳንዶቹ ግድያዎች በደቦ የተፈፀሙ ሲሆኑ፥ አንዳንዶቹ ግን በሰለጠኑ እና ተኩሰው በማይስቱ ታጣቂዎች የተፈፀሙ መሆናቸውንም ነዋሪዎቹ ተናግረዋል። የአሜሪካ ድምፅ ቤተሰቦቻቸው ፊት ለፊታቸው እደተገደሉባቸው የሚናገሩ፣ ንብረታቸው እንደተቃጠለባቸውና ያለ መጠለያ መቅረታቸውን የሚገልፁ በተለያዩ ከተማ የሚገኙ ወደ 20 የሚጠጉ ሰዎችን ያነጋገረ ሲሆን፥ በዛሬው ዕለት (ሰኔ 29 ቀን) በአርሲ ዞን ዶዶታ ወረዳ ዴራ ከተማ እና አካባቢው የሚገኙ ከጥቃት ከተረፉት መካከል የተወሰኑትን አስደምጧል።

    በሌላ በኩል የአርሲ ዞን ዋና አስተዳደሪ አቶ ጀማል አልዩ በአርሲ ዞን ውስጥ እርሳቸው ከሚያስተዳድሯቸው 25 ወረዳዎችና ሦስት ከተሞች መካከል በስድስቱ ውስጥ በተፈፀሙ አሰቃቂ ግድያዎች የ34 ሰዎች ሕይወት ማለፉን ገፀዋል። ድርጊቱ በአካባቢው ከነበረው ፖሊስ አቅም በላይ እንደነበርና የፀጥታ አባል ጭምር መገደሉን አረጋግጠዋል። የኦሮሚያ ክልል መንግሥት እና የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት በተለያዩ ከተሞች ጥቃቶቹ መፈፀማቸውን አምነዋል።

    ድርጊቱ የተፈፀመው በሁለት ብሔሮች መካከል የተካረረ ፀብና ግጭት በመቀስቀስ ኢትዮጵያን ለማፍረስ ዓላማቸው ባደረጉ አካላት ነው ሲሉም ከግጭቱ ጀርባ ሌሎች ቡድኖች እንዳሉ ጥቆማ ሰጥተዋል። መንግሥት ይህንን በአስቸኳይ በመረዳት የፌደራል ፖሊስ እና የመከላከያ ሠራዊት አባላቱን ከክልል የፀጥታ ጥበቃ አባላት ጋር በማዋቀር የመከላከል ሥራ በመሥራቱ እንጂ ከዚህም የባሰ ጥቃት ይደርስ ነበር ሲል መንግሥት መግለጫ ሰጥቷል።

    የኦሮሚያ ክልል ምክትል ፖሊስ ኮሚሽነር ግርማ ገላን እስካሁን የ145 ሰላማዊ ዜጎች እና የ11 የፀጥታ ኃይሎች ሕይወት በድምሩ የ156 ዜጎች ሕይወት ማለፉን አረጋግጠዋል። የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ጌቱ አርጋው ደግሞ በአዲስ አበባ የሁለት የፀጥታ ኃይሎችና የስምንት ሲቪሎች በድምሩ የ10 ሰዎች ሕይወት ማለፉን አረግጋጠዋል። በአጠቃላይ ከመንግሥት የተገኘው መረጃ 166 ሰዎች በቦምብ፣ በጥይት፣ በድንጋይና በመሳሰሉት ሕይወታቸው ማለፉ ይጠቁማል።

    (ዘገባውን ከተያያዘው የድምፅ ፋይል ያዳምጡ)

    ምንጭ፦ የአሜሪካ ድምፅ

    ከአንድ ብሔር ተወላጅ ናቸው በተባሉ ዜጎች ላይ ዘግናኝ ጥቃት

    Anonymous
    Inactive

    ኦሮሚያ ክልል ውስጥ በዘር ላይ ያነጣጠረ ጥቃት በአፋጣኝ ይቁም!!

    (ያሬድ ኃይለማርያም*)

    በ1994 እ.ኤ.አ. ሩዋንዳ ውስጥ የተከሰተውን የዘር ማጥፋት ወንጀል በዋናነት የመሩት ሁለት ሬድዮ ጣቢያዎች ነበሩ። አንዱ በመንግሥት ስር የነበረው ሬድዮ ሩዋንዳ (Radio Rwanda) የሚባለው ሲሆን ሁለተኛው እና ዋናው የእልቂቱ አነሳሽና ቀስቃሽ የነበረው Radio Télévision des Milles Collines (RTLM) ተብሎ የሚጠራው ጣቢያ ነበር። ይህ ጣቢያ በወቅቱ በወጣቶች ዘንድ ከፍተኛ ተደማጭነት የነበረው ስለነበር በሀገሪቱ ውስጥ የነበሩ ሥራ አጥ ወጣቶችን እና የቀኝ አክራርሪ የሆኑትን የሁቱ ኢንተርሃሞይ ሚሊሻዎችን (Interahamwe militia) በቀላሉ ወደ ጥላቻ በመንዳት በመምራት እና እልቂት እንዲፈጽሙም በማነሳሳት ትልቅ ሥራ ሠርቷል። ይህ ጣቢያ ከእልቂቱም በፊት ቢያንስ ለአንድ ዓመት ያህል ጥላቻን ሲሰብክ ቆይቷል።

    ዛሬ ደግሞ ተራው የእኛ በሚመስል ሁኔታ እጅግ ተመሳሳይ በሆነ መልኩ ለዓመታት ጥላቻን ለኦሮሞ ወጣቶች እና ለኦነግ ሽኔ ታጣቂዎች ሲሰብክ የነበረው OMN የተባለው ሚዲያ የወንድማችንን ሀጫሉ ሁንዴሳን ግድያ ተከትሎ ባስተላለፋቸው ተከታታይ የአመጽ እና የእልቂት ጥሪዎች እና ቅስቀሳዎች ኦሮሚያ ክልል ውስጥ በዘር ላይ ያነጣጠሩ ጥቃቶች እንዲፈጸሙ ምክንያት ሆኗል። ይህ የቴሌቪዥን ጣቢያ ልክ የሩዋንዳው RTLM እንዳደረገው ሁሉ ጥሪው ክልሉ ውስጥ ላሉ ሥራ-አጥ ወጣቶች እና በሽኔ ስም ለሚጠሩት ሚሊሺያዎች ነበር። በዚህም እጅግ ለመስማትና ለማየት የሚሰቀጥጡ ዘር ተኮር ጭፍጨፋዎች በተለያዩ የኦሮሚያ ክልል ከተሞች እንዲፈጸሙ ተደርጓል። ሰዎች እቤታቸው ውስጥ እንዳሉ ከነቤተሰቦቻቸው በእሳት ጋይተዋል፤ ህጻናት፣ ሴቶች እና ሽማግሌዎች ሳይቀሩ በስለት እና በቆንጨራ ተቆራርጠው ተገድለዋል፤ እናት ከህጻን ልጇ ጋር በአንድ ገመድ ታንቃ ተገድላለች፤ ከፍተኛ ግምት ያለው ንብረት ወድሟል፤ ብዙዎች ከቤታቸው ሸሽተው በተለያዩ ጊዜያዊ መጠለያዎች ውስጥ ተደብቀዋል።

    አንዳንድ እማኞች በመገናኛ ብዙኃን ምስክርነታቸውን እንደሰጡት እና እኛም ማረጋገጥ እንደቻልነው ለጥቃት የተሰማሩት ኃይሎች በቂ ዝግጅት ያደረጉ፣ የተለያዩ የጥቃት መሣሪያዎችን የያዙ እና የጥቃት ዒላማ የሆኑ ሰዎችን ስም እና አድራሻም ይዘው እንደሚንቀሳቀሱ ለማወቅ ተችሏል። ነገሩን እጅግ አሳሳቢ የሚያደርገው ደግሞ በክልሉ ውስጥ ያሉ የክልሉ ታጣቂ ኃይሎች ይህ ሁሉ እልቂት ሲፈጸም ድርጊቱን ለማቆም አፋጣኝ እርምጃ አለመውሰዳቸው ነው። በአሜሪካ ድምጽ (ቬኦኤ) እና አንዳንድ ሚዲያዎች እንደተዘገበውም በተወሰኑ ቦታዎች የመንግሥቱ ታጣቂዎች ትዕዛዝ አልተሰጠንም በሚል ጥቃት ሲፈጸም እያዩ ዝምታን መርጠው መቆየታቸው ነው። በሩዋንዳም የዘር ማጥፋት ጥቃት ሲፈጸም የሆነው ይሄው ነበር። እነዚህ ኃይሎች በምንም መልኩ የኦሮሞን ሕዝብ አይወክሉም። በኦሮሞ ሕዝብ መሃል የበቀሉ እንክርዳዶች ናቸው። በመሆኑም እንዲህ ያሉ እኩይ ተግባር የሚፈጽሙ ቡድኖችን እና ነገሩን በቸልታ ሲያዩ በነበሩ የክልሉ ኃላፊዎች ላይ በቂ ምርመራ ሊካሔድ እና በሕግ ሊጠየቁ ይገባል።

    OMN አዲስ አበባ ያለው ጽሕፈት ቤቱ ቢዘጋም ተመሳሳይ የእልቂት ጥሪዎችን ከሀገር ውጭ ባሉ ባልደረቦቹ በኩል ሲያስተላልፍ ቆይቷል። ዛሬ ደግሞ ይህ ቴሌቪዥን ጣቢያ ከግጭቱ ጋር ተያይዞ አየር ላይ ያዋላቸውን እና በዩቲዩብ (YouTube) የተላለፉ ዝግጅቶቹን ከአየር ላይ እያወረደ እና መረጃዎችን ለማጥፋት ጥረት እየተደረገ ነው። ይሁንና ለማስተላለፍ የምፈልገው መልዕክት፦

    (ኛ) የእነዚህ የእልቂት ጥሪዎች ቅጂዎቻቸው ጣቢያው በመንግሥት ቁጥጥር ስር ከዋለበት ጊዜ ጀምሮ በመንግሥት እጅ ስለሚገኙ እና የብሮድካስቲንግ ኤጀንሲውም የእነዚህ ቅስቀሳዎች ቅጂ እንዳለው ባለሥልጣኑ ስለተናገሩ ጣቢያው መረጃ ለማጥፋት እያደረገ ያለው ጥረት ይሳካል ብዬ አላምንም። ነገር ግን እነዚህ መረጃዎች በመንግሥት በኩል በቂ ጥበቃ ተደርጎላቸው በክልሉ ውስጥ ለተፈጸመው ዘር ተኮር ጭፍጨፋ ያላቸው አስተዋጽኦ በአግባቡ ሊመረመር ይገባል፤

    (ኛ) በOMN የተላለፉ የዘር ተኮር ቅስቀሳ ቪዲዮዎች እና ዘገባዎች በእጃችው ላይ የሚገኝ እና ጉዳዩ የሚያሳስባችው ግለሰቦች፤ እንዲሁም በተለያዩ የክልሉ ከተሞች እና አንዳን አካባቢዎች የተፈጸሙ ዘር ተኮር የሆኑ ጥቃቶችን የሚያሳዩ የፎቶ ግራፍ፣ የቪዲዮ እና ሌሎች ዝርዝር መረጃዎች ያላችሁ ሰዎች በዚህ የኢሜል አድራሻ end.empunity.eth@gmail.com እንድታቀብሉን በታላቅ አክብሮት እንጠይቃለን።

    ዘር ተኮር ጥቃት ይቁም!

    አቶ ያሬድ ኃይለማርያም መቀመጫውን ጄኔቭ ከተማ፥ ስዊዘርላንድ ያደረገ ስብስብ ለሰብዓዊ መብቶች በኢትዮጵያ (Association for Human Rights in Ethiopia) የተባለ ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ናቸው።

    ኦሮሚያ ክልል ውስጥ በዘር ላይ ያነጣጠረ ጥቃት በአፋጣኝ ይቁም

    Anonymous
    Inactive

    የአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያን አስመልክቶ የኦሮሚያ ክልል መሪ አቶ ሽመልስ አብዲሳ፣ ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ እና ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ያስተላለፉት መልዕክት

    አዲአ አበባ (EBC) – የታዋቂዉና ተዋዳጁ አርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያ አስመልክቶ ከኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ርዕሰ መስትዳደር አቶ ሽመልስ አብዲሳ ሀዘናቸውን ገለፁ።

    በአዲስ አበባ ከተማ በአቃቂ ክፍለ ከተማ ጀግናችን፣ የቅርብ አካላችን የትግልና የለዉጥ ምልክት የሆነዉ አርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳ በጥይት መመታቱን ሰምቻለሁ ሲሉ አሳዛኙ ዜና እንዴት እንደደረሳቸው አስረድተዋል። ሕይወቱንም ለማትረፍ ጥረት ቢደረግም ሕይወቱ ሊተርፍ አለመቻሉንም ነው ያስታወቁት።

    በአርቲስቱ ህልፈተ ሕይወት እንደ ግለሰብና እንደ አብሮ አደግ አብሮም እንደኖረ ሰዉ እንደ ታጋይና የትግል አጋር እንደ የችግር ጊዜ ጀግና ትልቅ ሀዘን ተሰምቶኛል ብለዋል ርዕሰ መስተዳደሩ።

    ሃጫሉ ሁንዴሳ አርቲስት ብቻ ሳይሆን ታጋይም ነዉ ያሉት ርዕሰ መስትዳደሩ፥ ለእኔ ደግሞ ወንድሜም መካሪዬም ነዉ።  ይህንን ጀግና ነዉ ያጣነዉ ብለዋል አቶ ሽመልስ።

    የዚህ ጀግና ግድያም እንደቀላል እና ለቀላል ነገር የተፈጸመ ወንጀል አይደለም። ታስቦበት እና ታቅዶበት የተፈጸመ ድርጊት ነዉ። ይሄ ምንም ጥርጥር የለዉም ሲሉም ነው አቶ ሽመለስ የገለጹት። በዚህ ወንጀል የተጠረጠሩ የተወሰኑት ግለሰቦች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የገለጹት ርዕሰ መስትዳደሩ፥ ምርመራም እየተካሄደ ይገኛል ብለዋል።

    የጸጥታ አካላት በሁሉም አቅጣጫ ተሰማርቷል። የዚህ ግድያ ዓላማም ሕዝብና ሕዝብን በማጋጨት፣ ሀገር ለማፍረስ፣ ሲዝቱ የነበሩ ኃይሎች ድርጊት ነው ብለዋል።

    ከለዉጡ ወዲህ እንደዚህ ዓይነት ብዙ ሙከራዎች ተደርገዋል። አብዛኛዎቹን በማክሸፍ የኢትዮጵያ ሕዝቦች፣ ብሔር ብሔረሰቦች አንድ ላይ ቆመዋል። አሁን ያለዉን ለዉጥ ለማደናቀፍ ብዙ ሙከራዎች ተደርገዋል ሲሉ አስረድተዋል። ርዕሰ መስተዳደሩ እንደገለጹት፥ ይህንን ለማክሸፍ የኦሮሚያ ፖሊስና የሀገሪቱ የጸጥታ ኃይሎችም ትልቅ ሥራ ሠርተዋል ብለዋል። ዛሬ ደግሞ ይህንን የግድያ ወንጀል በመፈጸም ብሄር ብሄረሰቦችን ለማጋጨት ሀገር ለማፍረስ፣ አቅደዉ እንደተነሱ ጥርጥር የለዉም ነው ያሉት። ለዚህ ደግሞ የኦሮሞ ሕዝብ ከኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች ሕዝቦች እርስ በርስ በመደማመጥ፣ አንድላይ በመቆም ጀግናችን የከፈለለትን መስዋዕትነት፣ ይህ ለዉጥ እንዲሳካ እጅ ለእጅ ተያይዘን ሁሉም ሰዉ በእርጋታ ይህንን አስቸጋሪ ጊዜ እንድንሻገር ጥሪ አቅርበዋል።

    መንግሥታዊ መዋቅሩም ይህንን አደጋ ለመታደግ በአንድነት ሊቆም ይገባል ብለዋል አቶ ሽመልስ አብዲሳ። ለቤተሰቦቹ ፣ ለኦሮሞ ሕዝብና ለመላዉ የሀገራችን ሕዝቦች መጽናናትን እንደሚመኙ አቶ ሽመልስ አብዲሳ ገልጸዋል።

    ከአርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያ ጋር በተያያዘ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ በተወዳጁና ጀግናው አርቲስት ሃጫሉ ሞት የተሰማቸውን ከባድ ሀዘን ገልፀዋል።

    ጠቅላይ አቃቤ ሕግ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ፥ “ሃጫሉ ቢሞትም መሞት የማይችል ሥራ ሠርቷል። ማንም ይሁን ማን ሃጫሉን የገደለው ሰው ከሕግ ማምለጥ አይችልም። የእኩይ እና አስነዋሪ ሥራውን ዋጋ በሕግ ያገኛል። የአርቲስት ሃጫሉን ነብስ ፈጣሪ በገነት ያኑር! ለቤተሰቡና ለመላው ሕዝባችን ፈጣሪ ትዕግስቱን፣ ብርታትና መጽናናትን ይስጠን!” ብለዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ባስተላለፉት የሐዘን መልእክት ደግሞ፥ “ለመላው የሀገራችን ሕዝቦች፥ ውድ ሕይወት አጥተናል። የዚህ ድንቅና አንፀባራቂ ወጣት አርቲስት ሃጫሉ ሁንዴሳ ሕይወት መቀጠፍ ከተሰማ ጀምሮ በከባድ ሀዘን ውስጥ ለምንገኝ ሁሉ መፅናናትን እመኛለሁ ። የዚህን ክፉ ድርጊት ሙሉ የፖሊስ ምርመራ ሪፖርት እየተጠባበቅን እንገኛለን። የድርጊቱን መጠን በመረዳት በሀገራችን ውስጥ ስለሚከናወኑ እንቅስቃሴዎች ትኩረት ሰጥተን የምንከታተልበት ወቅት ላይ ነን። ሀዘናችንን ራሳችንን በመጠበቅ እና ተጨማሪ ወንጀልን በመከላከል እንግለፅ” ብለዋል።

    ሃጫሉ ሁንዴሳ

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 68 total)