Search Results for 'ኤርሚያስ አመልጋ'

Home Forums Search Search Results for 'ኤርሚያስ አመልጋ'

Viewing 3 results - 1 through 3 (of 3 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – በአዳዲስ የቢዝነስና የሥራ ፈጠራ ሃሳቦች አፍላቂነታቸውና በፈር-ቀዳጅ ኢንቬስተርነታቸው (entrepreneur) በሚታወቁት ኢትዮጵያዊው ኢኮኖሚስትና ባለሃብት በአቶ ኤርሚያስ አመልጋ የሕይወት ታሪክና ሥራዎች ዙሪያ የሚያጠነጥነውና በደራሲና ጋዜጠኛ አንተነህ ይግዛው የተጻፈው < የማይሰበረው – ኤርሚያስ አመልጋ > የተሰኘው የሕይወት ታሪክ (biography) መጽሐፍ ከሐምሌ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ በገበያ ላይ ይውላል።

    አጠቃላይ ዝግጅቱ ከስድስት ዓመታት በላይ ፈጅቶ የተጠናቀቀው ይህ መጽሐፍ፥ ከወላጆቻቸው የበስተጀርባ ታሪክ አንስቶ የአቶ ኤርሚያስ አመልጋን የልጅነት ሕይወትና አስተዳደግ፣ የወጣትነት ዘመንና የትምህርት ቆይታ እንዲሁም ወደ አሜሪካ አቅንተው ከዘበኝነትና የዩኒቨርሲቲ ተማሪነት እስከ ግዙፉ የዓለማችን የፋይናንስ ማዕከል ዎልስትሪት (Wall Street) የኢንቨስትመንት ባንኪንግ ስመጥር ባለሙያነት የዘለቁበትን የረጅም ዓመታት ጉዞ የሚያስቃኝ ሲሆን፥ ወደ ኢትዮጵያ ከተመለሱ በኋላ ከ20 ዓመታት በላይ የተጓዙበትን በስኬትና በውድቀት የታጀበ፣ ፈተናና ውዝግብ ያልተለየው ረጅም የሕይወት ጎዳናም በዝርዝር ይዳስሳል።

    ኤርሚያስን የትኛው “ወንጀል” ሊያሳስረው ይችላል?

    አቶ ኤርሚያስ አመልጋ በተለይም ወደ ኢትዮጵያ ከተመለሱ በኋላ የወጠኗቸውን አዳዲስና ሰፋፊ የፋይናንስ፣ የንግድና ኢንቨስትመንት ዕቅዶቻቸውን ከዳር ለማድረስ ባደረጉት እልህ አስጨራሽ ጉዞ ውስጥ ያጋጠሟቸውን እሾህ አሜካላዎች፣ የተጋፈጧቸውን ፈተናና እንቅፋቶች በዝርዝር የተረኩበት መጽሐፉ፣ ከባለታሪኩ የግልና የሥራ ሕይወት ጋር በተያያዘ ከዚህ ቀደም ተሰምተው የማይታወቁ በርካታ አዳዲስና አነጋጋሪ መረጃዎችን ያካተተ ነው።

    በሁለት ክፍሎች ተከፋፍሎ የቀረበውና 12 ዋና ዋና ምዕራፎች ያሉት < የማይሰበረው – ኤርሚያስ አመልጋ > የሕይወት ታሪክ መጽሐፍ፣ “ማረፊያ አንቀጾች” እና “ድህረ-ታሪክ” የሚሉ ተጨማሪ ንዑሳን ክፍሎችን ጨምሮ አጠቃላይ የገጽ ብዛቱ 394 ነው።

    < የማይሰበረው – ኤርሚያስ አመልጋ > በአዲስ አበባና በሁሉም የክልል ዋና ዋና ከተሞች በሚገኙ መጽሐፍት መደብሮችና በአዟሪዎች፣ በአዲስ አበባ በሁሉም የዳሽን ባንክ ቅርንጫፎችና በሸዋ ሱፐርማርኬቶች፣ በስልክ ትዕዛዝ የቤት ለቤት እደላና በአማዞን ድረ-ገጽ አማካይነት ከመጪው ሰኞ ጀምሮ የሚሸጥ ሲሆን፣ የመሸጫ ዋጋውም 300 ብር እንደሆነ ተነግሯል።

    ዘመን ባንክ እንደ ይሁዳ – (ኤርሚያስ አመልጋ – ከቂሊንጦ ማረሚያ ቤት)

    በኢትዮጵያ የመጀመሪያውን የታሸገ ውሃ “ሃይላንድ” ለገበያ በማቅረብ እንዲሁም “ዘመን ባንክ” እና “አክሰስ ሪል ስቴት”ን ጨምሮ ባቋቋሟቸው የተለያዩ ኩባንያዎች የሚታወቁት አወዛጋቢው ኢኮኖሚስት አቶ ኤርሚያስ አመልጋ፥ ከብረታ ብረት ኮርፖሬሽን የሙስና ክስ ጋር በተያያዘ ተጠርጥረው ከወራት በፊት በቁጥጥር ስር መዋላቸውና በአሁኑ ወቅትም በቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ሆነው የፍርድ ሂደታቸውን በመከታተል ላይ እንደሚገኙ ይታወቃል።

    ጸሃፊው ደራሲና ጋዜጠኛ አንተነህ ይግዛው ከዚህ ቀደም “መልስ አዳኝ” እና “ባቡሩ ሲመጣ” የተሰኙ የአጫጭር ልቦለድ ስብስብ መጽሐፍትን ለንባብ ያበቃ ሲሆን፥ ለ54 ተከታታይ ሳምንታት በፋና ኤፍ ኤም 98.1 የተላለፈውንና “ስውር መንገደኞች” የተሰኘውን ተከታታይ የሬዲዮ ድራማ በደራሲነትና በተዋናይነት ለአድማጭ ማብቃቱም ይታወሳል።

    ለተጨማሪ መረጃ፦
    Email: yemayseberew@gmail.com, amelgaermiyas283@gmail.com
    Facebook: Ermyas Tekil Amelga
    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የማይሰበረው - ኤርሚያስ አመልጋ


    Anonymous
    Inactive

    ኤርሚያስ ሊታሰር የሚችለው ከፈጠራና ሙግቱ በተያያዘ እንደሆነ ትልቁን ግምት መውሰድ ይቻላል። የኤርሚያስ ትልቁ “ወንጀል” ገዥዎቹና ገዥዎችን ተጠልለው የከበሩትን በእውቀት ላይ ተመስርቶ ስለሚሞግትና ስለሚወዳደራቸው፣ ስጋት ስለሆነባቸው ይመስለኛል።

    ኤርሚያስን የትኛው “ወንጀል” ሊያሳስረው ይችላል?
    (ጌታቸው ሽፈራው)

    ኤርሚያስ አመልጋን የማውቀው ሚዲያ ላይ ነበር። 2008 ዓ.ም. ክረምት ላይ ያልጠበኩት ቦታ አገኘሁት። ማዕከላዊ ጠባብ ክፍል ውስጥ። ትኋን ከጣራው የሚዘንብበት “ሸራተን” የሚባል አስቀያሚ እስር ቤት ውስጥ ነው የሆነች ጥግ ይዞ ያገኘሁት። ሀብታሞች እስር ቤት ሲገቡ ትሁት ለመሆን ጥረት ያደርጋሉ። የኤርሚያስ ግን ሳይለይ አይቀርም። የምሩን ይመስለኛል። ብዙ ሰው ጓደኛው ነው። ወጣቶች ጓደኞቹ ናቸው። ሀብታሞቹ ፈልገውት ይመጣሉ። እሱ ግን በአብዛኛው ውሎው ከሌሎቹ ጋር ነው።

    ከምንም በላይ የገረመኝ በዛን ወቅት የነበረው የፖለቲካ ዝንባሌው ነው። ወቅቱ 2008 ዓ.ም. ነው። በዚህ ወቅት ብዙ ጉዳይ ይበላሽብኛል የሚል ሀብታም የማይነካውን አጀንዳ ኤርሚያስ አይፈራውም። ውሎው በሽብር ከተከሰሱት ጋር መሆኑ አይደለም። ሰላይ በሞላበት እስር ቤት በወቅቱ በሽብር የተፈረጁት የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎች መካከል “ማን ሊጠቅመን ይችላል? እንዴትስ ከግብ ይደርሳሉ? ምን ይደረግ?” የሚል ውይይት ላይ በቀጥታ ይሳተፍ ነበር። በፖለቲካ አመለካከታቸው የተለያየ ጠርዝ ላይ የተቀመጡ የፖለቲካ ድርጅት አመራሮችንና አባላትን፣ ግለሰቦችን ሰብስቦ ያወያይ ነበር። የውይይት መሪው ራሱ ነበር። ያከራክር ነበር። በዛ ጠባብና ማንም ውይይቱን በሚሰማበት ቤት መድረክ መሪው ኤርሚያስ ነው።

    በአንድ ክፍል ውስጥ በነበረችን ጥቂት ቆይታ እንዳጫወተኝ አቶ ኤርሚያስ መለስ ዜናዊንም በኢኮኖሚ ፖሊሲው በደንብ ሞግቶታል። መለስ የኤርሚያስን ፈጠራ ችሎታ ባይክድም ሙግቱን አልወደደለትም። እየቆዩ ግን ገዥዎቹ ፈጠራውንም አልወደዱለትም። አብዛኛው አሠራራቸው ጋር ይጋጫል። ለአብነት ያህል ዘመን ባንክን የመሰረተው ብዙ የግንባታ ወጭ ሳያወጣ በቴክኖሎጅው የትም እንዲያገለግል ነው። ኢህአዴግ ግን የትኛውም ባንክ በዓመት 5 በመቶ የሚሆን የቅርንጫፍ ማስፋፊያ እንዲያደርግ የሚያስገድድ ፖሊሲ አውጥቷል። ከዛም ሲያልፍ ብዙ ሴራዎች እንዳሉ ኤርሚያስ በግልፅ ይናገራል።

    ኤርሚያስ በእስሩ ወቅት ችግር ቢገጥመውም በቀላሉ ሲያልፋቸው አይቻለሁ። ሌላው ቀርቶ ዐቃቤ ሕግ ሚሊዮን ብሮችን የሚያስይዘበትን የዋስትና መብቱን (መጨረሻ ላይ በአንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን መሰለኝ የተለቀቀው) ሲነፍገው እስረኞች እንደሚሰማቸው ብስጭትና ንዴት አይታይበትም። እስረኞች በግፍ ፍትሕ ለተከለከለ እንደሚቆጩት ለእሱም ሲቆጩና ሲናደዱ “ምን አናደዳችሁ?” እያለ የሚቀልድ ሰው ነው። ብርታቱ በፖለቲካ ጉዳይ የሚታሰሩ የተወሰኑ ብርቱዎች የያዙትን እንጅ ከገንዘብ ጋር በተያያዘ ተከሰው እስረኛውን እንቅልፍ ከሚከለከሉት ብዙሃን ነጋዴዎች ጋር የሚመሳሰል አልነበረም።

    ዘመን ባንክ እንደ ይሁዳ – (ኤርሚያስ አመልጋ – ከቂሊንጦ ማረሚያ ቤት)

    ኤርሚያስ ለብዙ ነገሮች ተስፋ ቆርጦ “ሽብርክ” አለማለቱ በገዥዎች የተወደደለት አይመስለኝም። ፈጠራው የተወደደለት አይመስለኝም። በእርግጥ ብዙ የፈጠራ ባለሙያዎች፣ ጎበዝ ነጋዴዎች ይኖራሉ። ነገር ግን ከእነዚህ መካከል አብዛኛዎቹ የራሳቸውን ፈጠራ፣ ብቃትና ሀብት በሌላ ይሁንታ ጭምር እንዲተዳደር የሚፈልጉ ናቸው። ኤርሚያስ ይህ የሚፈቅድ ሰው አይመስልም። በትንሽ ትዝብቴ ፈጠራውን በገዥዎች ይሁንታ የሚያስተዳድር እንዳልሆነ ተገንዝቤያለሁ።

    ከራሱ ፈጠራ ባለፈ ቤተ መንግስት ገብቶ እነ መለስን ፖሊሲያዎቸው ኢኮኖሚውን የማያራምድ፣ ለሀገር ኪሳራ መሆኑን ሞግቷል። በዚያ ጨለማ ወቅት፣ በዚያ ብዙ ባለሀብት ባሽቃበጠበት ወቅት እነ መለስን የሞገተ ሰው የዛሬዎቹን ከመሞገት ወደኋላ እንደማይል ግልፅ ነው። በፖሊሱ ጉዳይ ከመተቸት ባለፈ የወቅቱ ገዥዎችም እንደ ድሮዎቹ ባለሀብቱ ወደራሳቸው ቀየ እንዲጎርፉ ፍላጎት ነበራቸው። ሆኖም ኤርሚያስ ፍላጎት የነበረው አይመስልም። ኤርሚያስ መዋለ ንዋይ ለማፍሰስ የመረጣቸው ቦታዎች እንደነበሩ ሲነገር ቆይቷል። ኤርሚያስ በዚህ የእፎይታ ይመስል የነበረ “የለውጥ” ወቅት በአዲስ ፈጠራ ለመምጣት ጥረት እያደረገ እንደነበር ተገልጿል። ብዙ ዕቅዶች እንዳሉት ያወራ ነበር። ለብዙዎቹ ሀብቶች ፈተና ነው። ገዥዎችንም ይሞግታል። እነሱ ወደፈለጉት ቦታ መዋለ ንዋይ ለማፍሰስም ፈቃደኛ አይመስልም። የኤርሚያስን እስር ሳስታውስ የሚመጡልኝ እነዚህ የገዥዎቹ ወጥመዶች ናቸው። እንጂማ ኤርሚያስ ከአረብ ባለሀብት የተሻለ ሀገሩን መጥቀም የሚያስችል እውቀት አለው። ገንዘቡን ባያፈስ እንኳ ከእነ ፍራንሲስ ፉኩያማ የተሻለ የሀገሩን ባህልና ጥቃቅን ክፍተቶች የሚረዳ ጥሩ አማካሪ መሆን ይችል የነበር ሰው ነው። በኤርሚያስ ላይ እንደ ችግር የተወሰደበት በውጥንቅጥና በኪሳራ ወቅትም እሠራለሁ የሚልበት ሥነ-ልቦናው ይሆናል።

    በአንድ ወቅት ስንከራከር ሊያሳምነኝ ያልቻለ ሙግት ነበረው። የገዥዎቹን ድርጅቶች አቅልሎ ነው የሚያያቸው። ሜዳው ከአፈና እና ወከባ ከተላቀቀ በቀላሉ ከስረው የሚወጡ እንደሆኑ ነው የሚናገረው። በመንግስት ድጎማ፣ ሙስና፣ ሌሎቹን በማፈን እና በገዥዎች ትብብር ትርፍ የሚያግበሰብሱት ተቋማት እውነተኛው ስርዓት ሲመጣ አፍታ ሳይቆዩ ከሜዳው እንደሚወጡ ነው የሚናገረው። የሰው ኃይልን በገፍ አስገብተው ጉልበት እየበዘበዙ የሚያጋብሱት ድርጅቶች የሰለጠነና በእውቀት የሚመራ ጋር ተወዳድረው እንደማይዋጣላቸው ነበር የሚናገረው። በወቅቱ የኢፈርትን ጡንቻ እያሰብኩ ኤርሚያስ የዋህ የሆነ ይመስለኝ ነበር። ከእነዚህ ግዙፎች ጋር ተወዳደሮ ማሸነፍ እንደሚችል በድፍረት ሲናገር ወኔውን አድንቄያለሁ። ይህ ወኔ ግን አግበስብሰው ለሚያተርፉትና አትራፊዎቹን ለያዙት ፈተና ይሆናል። ሳስበው ኤርሚያስ ትክክል ነበር። እነ ሜቴክን እንደምሳሌ መጥቀስ ይቻላል። ዛሬም ሌሎች ባለሜቴኮች አሉ። ኤርሚያስ ለእነዚህ ገንዘብ ከየትም አምጥተው በገዥዎች እገዛ ለሚያተርፉት ሰዎች ስጋት ነው። ኤርሚያስ ከእስር እንደተፈታ ሊያደርጋቸው የሚችላቸውን ጉዳዮች ያወራ ነበር። አንደኛው የኢኮኖሚ ተንታኝ ቡድን ማዋቀር ነው። መሰል ቡድን አዋቅሮ በተሻለ ሜዳ ልወዳደር ቢል በገዥዎቹ እገዛ ሚያተርፈው ስጋት ሊሆን ይችላል። ኤርሚያስን ሊያሳስረው ከሚችሉት ነገሮች መካከል ሳብሰለስል የሚመጡልኝ መሰል ጉዳዮች ናቸው።

    ሁሉም እስረኛ ነፃ ነው ብሎ መደምደም አይቻልም። ሆኖም በዚህ ዘራፊ የገዥዎቹ ቀኝ እጅ ሆኖ በሚኖርበት ሀገር ኤርሚያስ መታሰር አይገባውም ለማለት ሞራል አናጣም። ዘራፊዎች የገዥዎች መመኪያ ሆነው በሚኖሩበት፣ ዘራፊዎች የገዥዎች ከለላ በሚደረግላቸው ሀገር ኤርሚያስ በወንጀል ታሰረ ለማለት ክፉ ሕሊና ይጠይቃል። ቢያንስ ገዥዎችንና ገዥዎችን ታክከው ያገኙትን ገንዘብ እንጅ እውቀታቸውን ተማምነው፣ በእውቀት ተመርተው መነገድ ከማይችሉት አጎብዳጆች የተሻለ መሆኑን መካድ አይቻልም። ቢያንስ ቢያንስ የውጭ ባለሙያዎችን ያህል “አማክረን” ተብሎ ብዙ ሳይለመን ምክር የሚለግስ፣ ለሀገር የሚጠቅም መሆኑን መካድ አይቻልም። ከውጭ እንደሚመጡት አማካሪዎች ብዙ ገንዘብ ሳይጠይቅ የወልስትሬት (Wall Street) ልምዱን በቀናነት ለሀገሩ ሊያካፍል እንደሚችል መካድ አይቻልም። ኤርሚያስ ሊታሰር የሚችለው ከፈጠራና ሙግቱ በተያያዘ እንደሆነ ትልቁን ግምት መውሰድ ይቻላል። የኤርሚያስ ትልቁ “ወንጀል” ገዥዎቹና ገዥዎችን ተጠልለው የከበሩትን በእውቀት ላይ ተመስርቶ ስለሚሞግትና ስለሚወዳደራቸው፣ ስጋት ስለሆነባቸው ይመስለኛል። ኤርሚያስን የፈለገ ወንጀል ሠራ ቢሉን ወንጀለኞች በሚሸለሙበት ሀገር፣ ዘራፊዎች ለገዥዎች በማጎብደዳቸው “ነፃ ሆነው” በሚኖሩበት ሀገር የሚያሳስረው ወንጀልን ለመገመት የሚከብድ ነው።

    ኤርሚያስ ነፃ ይመስለኛል። ነፃ እንኳን ባይሆን ከአጎብዳጆቹ አንፃር ሊሸለም የሚገባው ሰው እንደሆነ አምናለሁ። ኤርሚያስ ባይታሰር ለገዥዎቹ ባይጠቅም፣ ለሀገሩ ብዙ ብዙ ይጠቅማል።

    ኤርሚያስን ፍቱት!

    ጌታቸው ሽፈራው

    ኤርሚያስ አመልጋ


    Semonegna
    Keymaster

    ዘመን ባንክ እንደ ይሁዳ – (ኤርሚያስ አመልጋ – ከቂሊንጦ ማረሚያ ቤት)
    (አጽንቼ ያቆምኩትን ባለውለታውን ዞሮ የወጋው ዘመን ባንክ)

    ከ20 ዓመታት የአሜሪካ ቆይታ በኋላ ወደ አገር ቤት ተመልሼ በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች ላይ ስሥራ እንደመቆየቴ፣ የሥራዬ ባህሪ ከባንኮች ጋር ያገናኘኝ ነበርና አዘውትሬ ወደተለያዩ የአገሪቱ ባንኮች እሄድ ነበር። ሁሉም ባንኮች ግን፣ ዘመናዊ ቴክኖሎጂን የማይጠቀምና የደንበኞችን ፍላጐት በተቀላጠፈ መልኩ የማያረካ፣ ኋላቀር የባንክ አሠራር ይዘው ነበር የማገኛቸው።

    በ2001 ዓ.ም. በባንኩ ዘርፍ ላይ ጥናት ካደረግኩ በኋላ፣ በወቅቱ በተለያዩ የአገሪቱ ባንኮች የሚታየውን ኋላቀር የባንክ አሠራር ወደ ጐን በመተው፣ ለአገሪቱ አዲስ የሆነና ባደጉት አገራት የሚሠራበት ዘመናዊ አሠራር የሚከተል በአይነቱ የተለየ ባንክ ለማቋቋም ወሰንኩ።

    የማቋቁመው ባንክ ከዚህ ቀደም በአገሪቱ የነበሩ ባንኮች ከሚሰጡት የተለየ ቀልጣፋና ዘመናዊ አሠራር የሚከተል እንዲሆን በማሰብም፣ አቅም ላላቸው ደንበኞች ብቻ ትኩረት በመስጠት፣ ከዚህ በፊት በአገሪቱ ባልተለመደ መልኩ በአንድ ቅርንጫፍ ብቻ አገልግሎት መስጠት የሚቻልበት አዲስ የባንክ አሠራር ቀየስኩ። ባንኩ በአንድ ቅርንጫፍ ብቻ አገልግሎት የሚሰጥ ቢሆንም፣ የባንኩ ባለሙያዎች ደምበኞች ያሉበት ቦታ ድረስ ሄደው የሚያገለግሉበትና ተደራሽነት ያለው አዲስ አሠራር እንዲኖር በማድረግ አገልግሎቱ በቅርንጫፍ እጥረት እንዳይስተጓጎል ተጨማሪ በቴክኖሎጂ የታገዙ የአገልግሎት አሰጣጥ ዘዴዎችን ተግባራዊ አደረግኩ።

    ዘመን ባንክ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት 1.1 ቢልዮን ብር ማትረፉንና ይህም ከባለፈው የበጀት ዓመት ጋር ሲነጻጸር በ15.3 መቶ ብልጫ እንዳለው አስታወቀ

    ወደ አክሲዮን ሽያጭና ባንኩን ወደማቋቋም ገባሁ። የአክሲዮን ሽያጩን በአግባቡ ለማከናወንና የሚፈለገውን ያህል ገንዘብ ለመሰብሰብ የባንኩን አጠቃላይ አደረጃጀት፣ የአገልገሎት አሰጣጥና የሥራ ዕቅድ በተመለከተ ለባለሃብቶች የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረኮችን በተደጋጋሚ በማዘጋጀት ሰፊ ማብራሪያ በመስጠት በከፍተኛ ጥረትና መስዋዕትነት ከ3 ሺህ በላይ ከሚሆኑ ባለአክሲዮኖች 150 ሚሊዮን ብር ያህል አሰባሰብኩ።

    ዘመን ባንክን ለማቋቋም የጀመርኩት ጥረት በተለይ በብሔራዊ ባንክ ተደጋጋሚ እንቅፋቶች ገጥመውት ነበር። ያም ሆኖ ግን፣ በከፍተኛ መስዋዕትነት ፈተናዎችን ሁሉ ለማለፍ ተጋሁ። ከእልህ አስጨራሽ ቢሮክራሲና ኢፍትሃዊ ጣልቃገብነት በኋላም፣ ተሳካልኝና ዘመን ባንክን ወደ ሥራ አስገባሁት።

    ዘመን ባንክ በአገሪቱ የባንክ ኢንዱስትሪ ውስጥ የራሱን አዎታዊ ተፅዕኖ የፈጠረ ስኬታማ ባንክ ለመሆን ቻለ። ይዟቸው በመጣቸው አዳዲስ የባንክ አሠራሮች ቀልጣፋና ዘመናዊ አገልግሎት መስጠት የጀመረው ዘመን ባንክ፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ ነው የብዙዎችን ቀልብ መሳብና በርካታ ደንበኖችን ማፍራት እንዲሁም ትርፋማ መሆን የቻለው። ለረጅም አመታት አገልግሎት በመስጠት ከሚታወቁት ሌሎች ነባር ባንኮች ተርታ ለመሰለፍ ጊዜ አልወሰደበትም። በአንድ ቅርንጫፍ ብቻ በዓመት ከታክስ ውጭ 120 ሚሊዮን ብር አትርፏል። ዘመን ባንክ በአጭር ጊዜ ውስጥ የተጐናፀፈው ተጨባጭ ስኬት ብዙዎችን ማስገረሙን ቀጥሏል።

    ዘመን ባንክ በተቋቋመ በሦስተኛው ዓመት…

    በዘመን ባንክ የመመሥረቻ ጽሁፍና የመተዳደሪያ ደንብ ላይ፣ ከባንኩ ዘጠኝ የቦርድ አባላት መካከል ስድስቱ በየሶስት አመቱ መቀየር እንዳለባቸው በግልጽ ተቀምጧል። በዚህም መሰረት በሦስተኛው ዓመት ላይ፣ ከነባር የቦርድ አባላት ስድስቱን ለመቀየር ዝግጅት ማድረግ ጀመርን። እኔም የባንኩ የቦርድ ሰብሳቢ እንደመሆኔ፣ መቀየር አለባቸው ብዬ ያሰብኳቸውን ስድስት የቦርዱ አባላት መርጬ፣ ደንቡና አሠራሩ በሚፈቅደው መሰረት ለባለአክስዮኖች እንዲያጸድቁት አቀረብኩ። የባለአክሲዮኖች ጠቅላላ ጉባኤም፣ ግለሰቦቹ ከቦርድ አባልነታቸው እንዲነሱ ወሰኑ።

    ብርሃን ባንክ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት 410 ሚልዮን ብር ማትረፉን አስታወቀ

    ይሄን ተከትሎ ነው ነገር መበላሸት የጀመረው። በእኔ ጠቋሚነት ከቦርድ አባልነታቸው ከተነሱት ስድስት ሰዎች መካከል ሁለቱ ከአባልነታቸው በመነሳታቸው እጅግ በጣም ተበሳጩ። ከእነዚህ ግለሰቦች በተጨማሪ ለችግሩ መፈጠርና መባባስ መሪ ተዋናይ የሆነ አንድ ልዩ ቂም ያለውና የ500 ሺህ ብር አክሲዮን የገዛ ባለአክሲዮንና ተወካዩ ተጨመሩበት። ይህ ግለሰብ በዘመን ባንክ የምስረታ ዘመን፣ የግሉን ህንጻ እጅግ በተጋነነ ዋጋ ለባንኩ ለማከራየትና 36 ሚሊዮን ብር ያለአግባብ ወደ ኪሱ ሊያስገባ ሲሞክር፣ ዕቅዱን ስላከሸፍኩበት ቂም ይዞ ሊያጠቃኝ ደፋ ቀና ሲልና ባንኩን ሲበጠብጥ የኖረ ሰው ነው። ሌሎቹ ሁለቱም፣ በባንኩ የቦርድ አባልነታቸው የሚያገኙትን ጥቅማጥቅም በማጣታቸው ክፉኛ የተናደዱ ናቸው። እነዚህ ሰዎች በባንኩ ምስረታ ወቅት ስለተፈጸሙ ነገሮች የሚያውቁትን መረጃ መሰረት በማድረግ ነው ሊያጠቁኝ የተዘጋጁት።

    ነገሩ እንዲህ ነው…

    በአገሪቱ ሕግ መሰረት፣ አንድን ባንክ ለማቋቋም ከባለአክሲዮኖች የሚሰበሰበው ገንዘብ በቀጥታ በዝግ የባንክ አካውንት ውስጥ ነው የሚቀመጠው። የተሰበሰበውን ገንዘብ ማንቀሳቀስና ባንኩን ለማደራጀት በሚያስፈልጉ ሥራዎች ላይ ማዋል የሚቻለው፣ ብሔራዊ ባንክ ፈቃድ ከሰጠ በኋላ ብቻ ነው። ፈቃድ እስኪሰጥ ድረስ ምንም መሥራት አይቻልም። ገንዘቡ እስኪለቀቅ ጠብቆ መደበኛ የባንክ ሥራ ለመጀመር ደግሞ፣ ቢያንስ ተጨማሪ የሁለት ዓመት ጊዜ ይፈጃል። እኔ ግን ብሔራዊ ባንክ ለዘመን ባንክ ፈቃድ እስኪሰጥና በዝግ ሂሳብ የተጠራቀመው የባንኩ ገንዘብ እስከሚለቀቅ ድረስ ሥራዎች እንዲጓተቱ አልፈለግኩም። በመሆኑም ለባንኩ ምስረታው የሚያስፈልጉ ወጪዎችን ከራሴ ገንዘብ ለመሸፈን ወስኜ፣ አርባ ሚሊዮን ብር የሚደርስ ገንዘብ ከራሴ ወጪ በማድረግ፣ አጠቃላይ ባንኩን በቁሳቁስና በሰው ሃይል የማደራጀት ሥራ ሠራሁ። ብሔራዊ ባንክ ብዙ ጊዜ ፈጅቶ ፈቃድ በሰጠን በቀናት ውስጥ ነበር፣ ዘመን ባንክን በቀጥታ ወደ ሥራ ያስገባሁት። ይህን በማድረጌም የዘመን ባንክ ባለአክሲዮኖች ሌላ የማንም ባንክ ባለአክሲዮን ያላገኘውን የሁለት ዓመት ትርፍ ጥቅም አስገኝቻለሁ።

    ከላይ ለመግለጽ እንደሞከርኩት፣ በቅን ልቦና ተነሳስቼ በዘመን ባንክ ምስረታ ወቅት የራሴን ገንዘብ እያወጣሁ ሥራዎችን ስሠራ እንደነበር የሚያውቁትና በእኔ ጠቋሚነትና በጠቅላላ ጉባኤው ውሳኔ ከቦርድ አባልነታቸው የተሰናበቱት ግለሰቦች እና ተባባሪያቸው ከአመታት በኋላ ይህን ሁኔታ መሰረት አድርገው የግሌን ጥቅም ለማሳደድ ያደረግኩት ነገር አስመስለው ብሔራዊ ባንክ ሄደው በመክሰስ ሊበቀሉኝ ወሰኑ። በባንኩ ምስረታ ወቅት ህጋዊ አካሄድን ባልተከተለ መልኩ የተለያዩ ሥራዎችን ስሠራ እንደነበርና በሕግ ልጠየቅ እንደሚገባ ለብሔራዊ ባንክ አመለከቱ።

    ወጋገን ባንክ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት አንድ ቢልዮን ብር ማትረፉንና ይህም ከባለፈው የበጀት ዓመት ጋር ሲነጻጸር በ49 መቶ ብልጫ እንዳለው አስታወቀ

    ‘አቶ ኤርሚያስ ዘመን ባንክን ሲያቋቁም የግል ገንዘቡን ተጠቅሟል። የተለያዩ የባንኩ ሥራዎችን ያሠራ የነበረው ጨረታ ሳያወጣና የጥቅም ግጭት በሚያስከትል መልኩ ነበር። የአክሰስ ካፒታልም የዘመን ባንክም ሃላፊ ከመሆኑ ጋር በተያያዘም፣ የጥቅም ግጭት የሚያስከትል አሠራር ይከተል ነበር ወዘተ…’ የሚሉ ውንጀላዎችን በዝርዝር በመግለጽ፣ ጉዳዩ ተጣርቶ አስፈላጊው እርምጃ እንዲወሰድብኝ የሚጠይቅ ማመልከቻ ለብሔራዊ ባንክ አስገቡ።

    የግለሰቦቹ አቤቱታ ለብሔራዊ ባንክ ትልቅ አጋጣሚ ሆነለት። ዱሮም በሄድኩበት ሁሉ እየተከተለ እንቅፋት ሲፈጥርብኝ የኖረውና እንቅስቃሴዬን ለመግታት ሰበብ ሲፈልግ የነበረው ብሔራዊ ባንክ፣ የግለሰቦቹን ማመልከቻ በደስታ ነበር የተቀበለው። ይህን ተከትሎም፣ መጋቢት 6 ቀን 2003 ዓ.ም. በጻፈው ደብዳቤ በዘመን ባንክ የምስረታ ወቅት አንዳንድ ወጪዎች የተደረጉት የጥቅም ግጭት በሚያስከትል መልኩ እንደነበር የሚጠቁሙ ምልክቶች ስለተገኙ በወቅቱ የተደረጉ የፋይናንስ እንቅስቃሴዎች በሙሉ በባንኩ በሚሾም ኦዲተር እንዲመረመር መወሰኑን ገለጸ። ይህም ብቻ አይደለም፤ ጉዳዩ ተጣርቶ እስኪጠናቀቅ ድረስም፣ እኔን ከዘመን ባንክ የቦርድ አባልነቴ በጊዚያዊነት እንዳገደኝ አሳወቀኝ።

    ብሔራዊ ባንክ ባስተላለፈው ውሳኔ መሰረት የተጀመረውና አንድ ዓመት ያህል ፈጅቶ የተጠናቀቀው የኦዲት ምርመራ ሪፖርት ግን፣ በዘመን ባንክ ምስረታ ወቅት ያከናወንኩት ሥራ እንደተባለው የጥቅም ግጭት የሚያስከትል እንዳልነበር አረጋገጠ። የግል ገንዘቤን ወጪ አድርጌ ባንኩን ሳቋቁም፣ የግሌን ተጠቃሚነት ለማስጠበቅ ያከናወንኩትና በሕግ የሚያስጠይቀኝ ምንም አይነት ወንጀል እንዳልሠራሁ መሰከረ።

    ደቡብ ግሎባል ባንክ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት 142 ሚልዮን ብር ማትረፉን አስታወቀ

    የኦዲት ሪፖርቱ በባንኩ ምስረታ ወቅት ተጠያቂ የሚያደርገኝ ህገወጥ ተግባር እንዳልፈጸምኩ ቢያረጋግጥልኝም፣ ብሄራዊ ባንክ ግን ከዘመን ባንክ አመራርነቴ በጊዚያዊነት እንድነሳ የጣለብኝን እገዳ ሊያነሳልኝ አልፈቀደም። የግለሰቦችን ውንጀላ መሰረት አድርጎ የወሰደብኝ እርምጃ አግባብነት የሌለው መሆኑን የሚያሳይና በአፋጣኝ ወደ ሥራዬ እንድመለስ የሚጠይቅና “የዘገየ ፍትህ እንደተነፈገ ይቆጠራል” የሚል ርዕስ ያለው ጽሁፍ አዘጋጅቼ በፎርቹን ጋዜጣ ላይ አወጣሁ። ጽሁፉ በጋዜጣው ላይ በወጣ በሁለተኛው ቀን ግን፣ ከዘመን ባንክ አመራርነት ብቻም ሳይሆን ከማንኛውም የአገሪቱ ባንክ የቦርድ አባልነት እስከመጨረሻው መታገዴን የሚገልጽ ደብዳቤ ከብሔራዊ ባንክ ደረሰኝ።

    40 ሚሊዮን ብር ያህል ገንዘብ ከግሌ ወጪ አድርጌ ባንኩን በማቋቋሜ፣ ወንጀል ሠራህ ተባልኩ። የሠራሁት ወንጀል መኖሩ በገለልተኛ አካል በኦዲት እንዲጣራ ተደረገ፣ የኦዲት ምርመራው ውጤት ወንጀል አለመሥራቴን አረጋገጠ። ብሔራዊ ባንክ ግን፣ ወንጀል አለመሥራቴን ቢያረጋግጥም እኔን ከመቅጣት ወደኋላ አላለም። ራሱ ከሳሽ ራሱ ፈራጅ የሆነውን፣ ባለሙሉ ስልጣኑን ብሔራዊ ባንክ በፍርድ ቤት ለመክሰስና መብትን ለማስከበር ህጉ አይፈቅድልኝም። ስለዚህ ብሔራዊ ባንክን ከስሼ መብቴን ለማስከበር ከመሞከር ይልቅ፣ የደረሰብኝን ግልጽ በደል ለመንግስት ማሳወቅ እንዳለብኝ ተሰማኝ። የተፈጠረውን ነገር በሙሉ በዝርዝር ገልጬ፣ አቤቱታዬን በደብዳቤ መልክ ለቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ላክሁ።

    ደብዳቤውን ከላክሁ ከቀናት በኋላ፣ በወቅቱ በጠቅላይ ሚኒስቴር ቢሮ የመንግስት ተቋማት ድጋፍና ክትትል ሃላፊ የነበሩ ግለሰብ፣ በጉዳዩ ዙሪያ ሊያወያዩኝ እንደሚፈልጉ በመግለጽ ወደቢሯቸው አስጠሩኝ። ደስተኛ ሆኜ ወደቢሯቸው ሄድኩ። ጉዳዩን ከስር መሰረቱ አብራራሁላቸው፤ ዘመን ባንክን ለመመስረት ካሰብኩበት ጊዜ ጀምሮ ብሔራዊ ባንክ የፈጠረብኝን ችግሮች፣ ያደረሰብኝን በደልና በተደጋጋሚ ያስተላለፈብኝን ኢፍትሃዊ ውሳኔዎች በዝርዝር አቀረብኩላቸው። ከሰውዬው ጋር ሰዓታትን የፈጀ ውይይት ካደረግኩ በኋላ ግን፣ ፍትህን ፍለጋ ወደቢሯቸው መምጣቴ ከንቱ ድካም መሆኑን የሚያሳይ ምላሽ ሰጡኝ።

    “አቶ ኤርሚያስ በሆነው ነገር ሁሉ እናዝናለን። አንተን ለማጥቃት ተብሎ የተደረገ ነገር የለም። አንተ የምትሠራቸው ሥራዎች ለአገር ምን ያህል ጠቀሜታ እንዳላቸውና ፈር ቀዳጅ እንደሆኑ እናውቃለን። አንተ ተራ ነጋዴ እንዳልሆንክም እናውቃለን። ተቋማትን ነው የምትገነባው። ሥራዎችህን እና ጥረትህንም እንደግፋለን። ያው እንደምታውቀው ግን፤ ታዳጊ አገር ውስጥ ነው ያለነው። አንዳንዴ መሆን የሌለባቸው ነገሮች ይሆናሉ። በአንተ ላይ የተፈጸመው ነገር ትክክል እንዳልሆነ ይገባናል። ችግሩ በጊዜ ሂደት ይፈታል ብለን እናምናለን። ስሜትህ ሳይነካ፣ ጠንክረህ ሥራህን እንድትቀጥል ነው የምንፈልገው። ከዚህ ውጭ ግን፣ በብሔራዊ ባንክ ስልጣንና ሃላፊነት ውስጥ ጣልቃ ገብተን አስተያየት ለመስጠትም ሆነ ውሳኔውን ለማስቀየር ይከብደናል” የሚል ምላሽ ሰጡኝ።

    ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት 658.7 ሚልዮን ብር ማትረፉን አስታወቀ

    ከፍተኛ መስዋዕትነት ከፍዬ ካቋቋምኩትና ወደትርፋማነት ካሸጋገርኩት ዘመን ባንክም ሆነ፣ አዳዲስ አሠራሮችን አስተዋውቄ ተጨባጭ ለውጥ ከፈጠርኩበት የአገሪቱ የባንክ ኢንዱስትሪ በዚህ መልኩ ያለአግባብ ተገፍቼ እንድወጣ ተደረግኩ። ከዘመን ባንክ አመራርነቴም ከባንኩ ዘርፍም እንድወጣ የተላለፈብኝ ውሳኔ ቢያሳዝነኝም፣ ሌላ የተሻለ ሥራ እንደምጀምርና ነባር ሥራዎችን አጠናክሬ እንደምቀጥል ስለማውቅ ብዙም ትኩረት አልሰጠሁትም – ፊቴን ወደሌሎች ሥራዎች አዞርኩ።

    በዘመን ባንክ መሥራችነቴ ማግኘት የሚገባኝን ጥቅም አለማግኘቴን ያስታወስኩት እንኳን፣ ባንኩ ሥራ በጀመረ በሶስተኛው ዓመት ላይ ነበር። በዘመን ባንክ የመመስረቻ ጽሁፍ አንቀጽ 7 ላይ በግልጽ እንደተቀመጠው፣ የባንኩ መሥራቾችና አደራጆች በመጀመሪያዎቹ 3 አመታት ባንኩ ከሚያገኘው የተጣራ ትርፍ 10 በመቶ የመሥራችነትና የአደራጅነት ጥቅም ያገኛሉ። እኔም የባንኩ መሥራች እንደመሆኔ ከሶስቱ አመታት ትርፍ ይህን ድርሻ ማግኘት ይገባኝ ነበር። በወቅቱ ዋነኛ ትኩረቴ የነበረው ባንኩን ወደላቀ ደረጃ ማሸጋገር እንጂ የግል ገንዘብ በማሳደድ ላይ ስላልነበር፣ ከመጀመሪያውም ሆነ ከሁለተኛው ዓመት የባንኩ ትርፍ ላይ የመሥራችነት ድርሻዬን ተከታትዬ አልተቀበልኩም። ሶስተኛው ዓመት ላይ ግን፣ ቢያንስ ያለፉትን ሁለት አመታት የመሥራችነት የትርፍ ድርሻ አስልቶ እንዲከፍለኝ ለባንኩ ጥያቄ አቀረብኩ።

    ዘመን ባንክ በ2002 ዓ/ም በ2003 ዓ/ም በድምሩ ብር 92,634,690.00 /ዘጠኛ ሁለት ሚሊዩን ስድስት መቶ ሰላሳ አራት ሺ ስድስት መቶ ዘጠና/ ማትረፉ በውጭ ኦዲተሮች በተረጋገጠው መሰረት፣ የዚህ ገንዘብ አስር በመቶ እና የውጭ ኦዲተሮች ባንኩ ማትረፉን ካረጋገጡበት ቀን ጀምሮ ከሚታሰብ ዘጠኝ መቶ ወለድ ጋር በድምሩ 10,359,105.69 /አስር ሚሊዩን ሶስት መቶ ሃምሳ ዘጠኝ ሺ አንድ መቶ አምስት ብር ከ69/100/ እንዲከፈለኝ ነበር የጠየቅኩት። የወቅቱ የዘመን ባንክ የባለአክሲዮኖች ጠቅላላ ጉባኤና ቦርድ፣ ይህ ክፍያ እንዲፈጸምልኝ ወሰነ። የሚገርመው ነገር ግን፣ አሁንም የብሔራዊ ባንክ ኢፍትሃዊ በደል አልቀረልኝም። ብሔራዊ ባንክ ለኤርሚያስ ይከፈል ያላችሁትን ክፍያ አልቀበለውም፤ የባለአክሲዮኖች ጠቅላላ ጉባኤና የቦርድ ውሳኔ የተላለፈበትን ቃለ-ጉባኤም አላጸድቅም አለ። ዘመን ባንክም ይህን የብሔራዊ ባንክ ውሳኔ መሰረት በማድረግ ክፍያውን እንደማይፈጽምልኝ አስታወቀኝ።

    እዚህ ላይ ዝም ማለት አልፈለግኩም። ዘመን ባንክን በፍርድ ቤት ለመክሰስና በመሥራችነቴ ማግኘት የሚገባኝን ክፍያ በሕግ ለማግኘት ወስኜ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ክስ መሰረትኩ። የከፍተኘው ፍርድ ቤት ግን ግንቦት 3 ቀን 2009 ዓ/ም ክሱን ውድቅ አደረገው። ይህን ውሳኔ በመቃዎም ለፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ጠየቅኩ። ፍርድ ቤቱም የከፍተኛው ፍርድ ቤትን ውሳኔ በመሻር የሚገባኝ ገንዘብ እንዲከፈለኝ መጋቢት 18 ቀን 2009 ዓ/ም ወሰነልኝ። ዘመን ባንክ በዚህ ውሳኔ ላይ መሰረታዊ የሕግ ስህተት ተፈጽሟል በማለት የሰበር አቤቱታ ለፌ/ጠ/ፍ/ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት አቤቱታ ቢያቀርብም፣ ፍርድ ቤቱ ግን የተፈጸመ መሰረታዊ የሕግ ስህተት የለም ሲል ውድቅ አደረገው።

    ዳሽን ባንክ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት 1.14 ቢልዮን ብር ማትረፉን አስታወቀ

    በፍርዱ መሰረት ክፍያው እንዲፈጸምልኝ ለፌደራል ከፍተኛ ፍ/ቤት የአፈጻጸም አቤቱታ ባቀረብኩት መሰረት ባንኩ ክፍያውን እንዲፈጽም ሲጠየቅ ግን፣ ክፍያውን ሊፈጽምልኝ አልፈለገም። ይልቁንም የተለያዩ ምክንያቶችን እየደረደረና ሌሎች የጥቅም ግጭት ጥያቄዎችን እያነሳ፣ አዳዲስ ክርክሮችን መፍጠሩን ተያያዘው። አልፎ ተርፎም በእኔ ላይ አዲስ የወንጀል ክስ በመመስረት የተወሰነው ገንዘብ እንዲታገድና እንዳይከፈለኝ አደረገ። ባንኩ የመሰረተብኝ አዲሱ ክስ አሁንም ተጨማሪ የጥቅም ግጭት ነበረ የሚል ክስ ነበር። የቀረበብኝ ክስ የወንጀል ክስ መሆኑ ደግሞ እጅግ በጣም የሚገርምም የሚያሳዝንም ነበር።

    የራሴን ገንዘብ አውጥቼ፣ ከፍተኛ መስዋዕትነት ከፍዬ፣ ብዙ ፈተናዎችንና እንቅፋቶችን አልፌ ያቋቋምኩትና በአጭር ጊዜ ውስጥ ትርፋማ ያደረግኩት ዘመን ባንክ፣ ለውለታዬ እውቅና መስጠትና ስሜን በክብር ማውሳት ባይሆንለት የሚገባኝን ጥቅም ለመከልከል በእኔ ላይ ያልተገባ ክስ መመስረቱ በእጅጉ አሳዝኖኛል።

    የአገሪቱ የባንክ ኢንዱስትሪ ለዘመናት ከኖረበት ኋላቀር አሠራር ተላቅቆ በቴክኖሎጂ የታገዘ ቀልጣፋ አሠራር እንዲዘረጋ በማስቻል ረገድ ፈር ቀዳጅ ሥራ ሰርቻለሁ። ለዘመን ባንክ እዚህ ደረጃ መድረስ ቁልፍ ሚና ተጫውቻለሁ። ገንዘቤን፣ እውቀቴንና ልምዴን ሳልሰስት በመገበር፣ ባንኩንም ባለአክሲዮኖችንም በተለየ ሁኔታ ትርፋማ አድርጊያለሁ። የባንኩ ኢንዱስትሪ ተዋንያንም ሆኑ የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች ውለታዬን ሲዘክሩት ይኖራሉ። የዘመን ባንክ ባለአክሲዮኖችም ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ ለሠራሁት ሥራ እውቅና ሲሰጡኝ ኖረዋል። በቅርቡ አዲስ አበባ ውስጥ ያጋጠመኝ ድንገተኛ ነገር ለዚህ ጥሩ ማሳያ ሊሆን ይችላል።

    አንድ ማለዳ ከወዳጄ ጋር ወደነበረኝ ቀጠሮ እየሄድኩ እያለ፣ መንገድ ላይ አንድ የማላውቀው ሰው ስሜን ጠርቶ አስቆመኝ። ሰላምታ እንኳን ሳይሰጠኝ፣ በደስታ ስሜት ውስጥ ሆኖ አቀፈኝ። በግለሰቡ ድርጊት እየተገረምኩ እያለ፣ በስሜት ተውጦ ምክንያቱን ነገረኝ። ‘አቶ ኤርሚያስ… አንተ አታውቀኝም፤ ከአመታት በፊት ዘመን ባንክን ስታቋቁም ተገናኝተን ነበር። ስለምታቋቁመው ባንክ ማብራሪያ ስትሰጥ ሰምቼ፣ ባንኩ አትራፊ እንደሚሆን በመተማመን በ50 ሺህ ብር አክሲዮን ገዛሁ። ያኔ በ50ሺ ብር የገዛኋት የዘመን ባንክ አክሲዮን፣ ዛሬ ሚሊዬነር አድርጋኛለች… አንተ ባታውቀኝም፣ ባለሃብት ያደረግከኝ ባለውለታዬ ነህ! …’ እያለ ደጋግሞ አመሰገነኝ። ከዘመን ባንክ ያተረፍኩት ነገር፣ በሄድኩበት ሁሉ የሚያጋጥመኝ ይህን መሰሉ የሰዎች ፍቅርና አድናቆት ነው።

    አዋሽ ባንክ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት 1.96 ቢልዮን ብር ማትረፉን አስታወቀ

    ለአመታት ብዙ ነገር የከፈልኩለት ዘመን ባንክ ግን፣ የከፈልኩለትን መስዋዕትነት ከንቱ ሊያስቀረውና የሚገባኝን ጥቅም ሊያሳጣኝ አሁንም ቆርጦ ቆሟል። ወርቅ ያበረከትኩለት ዘመን ባንክ፣ ጠጠር ሊመልስልኝ ደፍሯል። በቅንነት የፈጸምኩትን ተግባር የግል ጥቅሜን ለማሳደድ ያደረግኩት ዝርፊያ በማስመሰል፣ ያለሥራዬ የወንጀል ክስ መስርቶብኛል። ከአገር እንዳልወጣ ሳይቀር አሳግዶኛል። ፍርድ ቤት የዘመን ባንክን መሰረተቢስ ክስ ተቀብሎ የሚያስተላልፈው ውሳኔ ምንም ይሁን ምን፣ ዘመን ባንክ ግን ትልቅ ክህደት እንደፈጸመብኝ ህዝቡ ሊያውቀው ይገባል።

    ዘመን ባንክ የፈጸመብኝን ክህደት በአደባባይ ላወጣው የወሰንኩት፣ የሚገባኝን ጥቅም አለማግኘቴ አንገብግቦኝ አይደለም። የእኔ ጥያቄ የገንዘብ አይደለም – የፍትህ እንጂ። ህይወቴ በዘመን ባንክ 10 ሚሊዮን ብር የታጠረች አይደለችም። እጄ ላይ ያሉት ጅምር ሥራዎችና የሚያንቀሳቅሱት ገንዘብ፣ ከዘመን ባንክና ከነፈገኝ 10 ሚሊዮን ብር ጋር የሚወዳደሩ አይደሉም። ሰበብ እየፈለገ ሲያስረኝና ሲፈታኝ የኖረው መንግስት፣ ባልተሳተፍኩበት አስቂኝ የሙስና ወንጀል እጄን ይዞ ወደ ቂሊንጦ ላከኝ እንጂ፣ በረቀቀ ቴክኖሎጂ የሚከወንና ለአገሪቱ አዲስ የሆነ ግዙፍ ቢዝነስና ኢንቨስትመንት ወደ አገሪቱ ለማስገባት መንገድ ላይ ነኝ።

    በስተመጨረሻም፣ መላው ህዝብ ዘመን ባንክ በእኔ ላይ የሠራውን ግፍና በደል እንዲያውቅልኝ ከቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ጥሪዬን እያስተላለፍኩ፤ ባንኩ የመሰረተብኝን ሃሰተኛ የወንጀል ክስ አንስቶ የሚገባኝን የመሥራችነት መብት እንዲያከብርልኝ ለማስቻል በማደርገው ጥረት ውስጥ ሁሉም ከጎኔ እንዲቆም እጠይቃለሁ!

    ከከበረ ሰላምታ ጋር።
    ኤርሚያስ ጠቅል አመልጋ
    (የዘመን ባንክ መሥራችና የቀድሞ የቦርድ ሊቀመንበር)
    የካቲት 7 ቀን 2011 ዓ.ም.
    ቂሊንጦ ማረሚያ ቤት
    አዲስ አበባ

    ኤርሚያስ አመልጋ እና ዘመን ባንክ


Viewing 3 results - 1 through 3 (of 3 total)