አድማስ ዩኒቨርስቲ አይ ኤስ ኦ የምስክር ወረቀት (ISO Certificate) ለማግኘት የሚያስችል ሥራ እየሠራ መሆኑን ገለጸ

Home Forums Semonegna Stories አድማስ ዩኒቨርስቲ አይ ኤስ ኦ የምስክር ወረቀት (ISO Certificate) ለማግኘት የሚያስችል ሥራ እየሠራ መሆኑን ገለጸ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #11540
    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – አድማስ ዩኒቨርሲቲ በኢትዮጵያ የጥራት ደረጃዎች ኤጀንሲ የተዘጋጁት ስታንዳርዶች በተገቢው መልክ በመፈፀም በ2012 ዓ.ም. በተቋም ደረጃ አይ ኤስ ኦ የምስክር ወረቀት (ISO Certificate) ለማግኘት የሚያስችለውን ተግባራት እያከናወነ መሆኑን ገለጸ።

    የዩኒቨርሲቲው የአካዳሚክ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ብሩ አስማረ እንደገለጹት፥ ዩኒቨርሲቲው የትምህርት አሰጣጥ ጥራት ደረጃውን በማሳደግ ለዚሁ ተገቢ የሆነ እውቅና ለማግኘት የሚያስችለው ብቃት ላይ ይገኛል።

    በቴክኒክና ሙያ ኮሌጀች የትምህርት ሥልጠና ጥራት ለማስጠበቅና በየሙያ ደረጃው የሥርዓተ ትምህርት ክለሳ አድርጓል ያሉት ምክትል ፕሬዚዳንቱ የማስልጠኛ መሳሪያዎች (Training Teaching and Learning Materials /TTLM) ዝግጅት በሁሉም የብቃት አሃዶች ማዘጋጀቱንና የትብብር ሥልጠናን አፈፃፃምን የሚያሻሻሉ የተለያዩ ተገባራት እያከናወነ መሆኑን አስረድተዋል።

    አቶ ብሩ አስማረ አያይዘውም የምዘና ሥርዓቱን ለማጠናከርና በዩኒቨርሲቲው የሚተገበረውን የተከታታይ ማጠቃለያና ተቋማዊ ምዘና ዝግጅትና አፈፃፃም ደረጃውን የጠበቀ እንዲሆን መደረጉንም አስረድተዋል።

    በኢትዮጵያ የደረጃ ኤጀንሲ (Ethiopia Standard Agency) የተዘጋጁ የጥራት ምዘናዎችን (stadards) ማለትም የስርዓተ ትምህርት (Curriculum Requirement ES. 6259-1: 2018)፣ የመሣሪያዎች ማሽነሪዎች (Tools, Machines and Equipment Requirement ES 6259-8: 2018)፣ የምዘናና የማሰልጠኛ መሣሪያዎች (Assessment & Instructional Materials ES 6299-9: 2011 ) እና የመሳሰሉትን ተግባራዊ እያደረገ መሆኑን አቶ ብሩ ገልጸዋል።

    ምክትል ፕሬዚዳንቱ አያይዘውም በዩኒቨርሲቲው የሚስጠውን የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ሥልጠና በምርምር ለማገዝ እንዲቻል የተለያዩ ጥናቶች በማካሄድ ያሉ ችግሮችን የመለየት ሥራ በየጊዜው እየተካሄደ መሆኑን ጠቁመዋል።

    በጥቅምት ወር 1990 ዓ.ም. “አድማስ የቢዝነስ ማሰልጠኛ ማዕከል” በሚል ሥራውን የጀመረው ይህ የከፍተኛ ትምህርት ተቋም፥ በፍጥነት ራሱን በማሳደግ በሚያዝያ ወር 1991 ዓ.ም. የኮሌጅነት ደረጃ አግኝቶ ስሙን “አድማስ ኮሌጅ” ብሎ በመሰየም ሥራውን አስፋፋ። ቀጥሎም በመጋቢት ወር 1999 ዓ.ም. “አድማስ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ” በሚል ስም የትምህርትና የስልጠና ተግባሩን አሳደገ። የከፍተኛ ትምህርት አዋጅ ቁጥር 650/2009 የሚጠይቃቸውን አስፈላጊ ቅድመ ዝግጅቶች በሙሉ በማሟላት በሐምሌ ወር 2006 ዓ.ም. የሙሉ ዩኒቨርሲቲ ደረጃን አግኝቶ “አድማስ ዩኒቨርሲቲ” ተባለ።

    አድማስ ዩኒቨርሲቲ የዘንድሮን ተመራቂዎችን ጨምሮ ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ከ70 ሺህ በላይ ተማሪዎችን በተለያዩ የትምህርት ዘርፎችና እርከኖች አስመርቋል።

    በአሁኑ ወቅትም በውጭ/ጎረቤት ሀገራት ሶማሌላንድና ፑንትላንድ በሚገኙት ካምፓሶቹ ያሉትን ጨምሮ በጠቅላላው ከ20 ሺህ በላይ ተማሪዎችን ተቀብሎ እያስተማረ ነው።

    ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    አድማስ ዩኒቨርስቲ የአካዳሚክ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ብሩ አስማረ


Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.