የኦሞ ኩራዝ ቁጥር 3 ስኳር ፋብሪካ እሁድ ይመረቃል

Home Forums Semonegna Stories የኦሞ ኩራዝ ቁጥር 3 ስኳር ፋብሪካ እሁድ ይመረቃል

Viewing 1 post (of 1 total)
  • Author
    Posts
  • #8025
    Semonegna
    Keymaster

    የኦሞ ኩራዝ ቁጥር 3 ስኳር ፋብሪካ መመረቅ ስኳር የሚያመርቱትን ፋብሪካዎች ቁጥር ወደ ስምንት (ወንጂ ሸዋ፣ መተሐራ፣ ፊንጫአ፣ ከሰም፣ ተንዳሆ፣ አርጆ ዲዴሳ፣ ኦሞ ኩራዝ ቁጥር 2 እና 3) ያደርሰዋል።

    ኩራዝ ከተማ፣ ደቡብ ኢትዮጵያ – የኦሞ ወንዝን በሚያዋስኑ በካፋና ቤንች ማጂ ዞኖች የሚገኘውና የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን ያስገነባው የኦሞ ኩራዝ ቁጥር 3 ስኳር ፋብሪካ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት በሚገኙበት እሁድ ጥቅምት 4 ቀን 2011 ዓ.ም ከጠዋቱ 2 ሰዓት ላይ ይመረቃል።

    በኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን ንብረትነት በኦሞ ኩራዝ ስኳር ልማት ፕሮጀክት ስር ከሚገነቡት አራት ስኳር ፋብሪካዎች አንዱ የሆነው ይህ ፋብሪካ የግንባታ ሥራው በይፋ የተጀመረው በመጋቢት ወር መጀመሪያ 2008 ዓ.ም ከቻይና ልማት ባንክ በተገኘ ከ8 ቢሊዮን ብር በላይ ብድር ነው።

    ዋና መቀመጫውን ሃናን ክልል ከተማ ባደረገው ጄንግጆ ከተማ ባደረገው ቻይና ኮምፕላንት ግሩፕ በተባለ የቻይና ኩባንያ የተገነባው ይህ ፋብሪካ በቀን ከ8 ሺህ አስከ 10 ሺህ ኩንታል ስኳር የማምረት አቅም ያለው ግዙፍ ፕሮጀክት ነው።

    ፋብሪካው እጅግ ዘመናዊ ከመሆኑ አንጻር የዓለም ገበያ ፍላጎትን መሠረት በማድረግ ጥሬ ስኳር (raw sugar)፣ ነጭ ስኳር (plantation white sugar) እና የተጣራ ስኳር (refined sugar) ማምረት ይችላል።

    ለአራቱም ስኳር ፋብሪካዎች በ100 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ሸንኮራ አገዳ ለማልማት በኦሞ ወንዝ ላይ የመስኖ መሠረተ ልማት ግንባታ እየተካሄደ ይገኛል። በአጠቃላይ እስካሁን 30 ሺህ ሄክታር መሬት ውሃ ገብ ማድረግ የተቻለ ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥ 16 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ሸንኮራ አገዳ ተተክሏል።

    ሰሞነኛ ዜና፦ በኦሮሚያ ክልል አዳማ ከተማ የተገነባው የአዳማ ኢንዱስትሪያል ፓርክ ተመረቀ፤ በዚህም ወደሥራ የገቡ የኢንዱስትሪ ፓርኮች ቁጥር አምስት ደርሷል

    የሰው ኃይልን በተመለከተ፥ የኦሞ ኩራዝ ስኳር ልማት ፕሮጀክት ከተቋቋመ ከ2003 ዓ.ም አንስቶ በፕሮጀክቱ፣ በኮንትራክተሮች እንዲሁም በጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት በቋሚ፣ በኮንትራትና ጊዜያዊነት ከ110 ሺህ በላይ ለሚሆኑ የአካባቢው ዜጎች የሥራ ዕድል የተፈጠረ ሲሆን፣ በሌላ በኩል ከ300 በላይ የጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማትን አደራጅቶ ወደ ሥራ ለማስገባት ተችሏል።

    በኦሞ ኩራዝ ስኳር ልማት ፕሮጀክት እየተገነቡ ከሚገኙ አራት የስኳር ፋብሪካዎች ውስጥ የኦሞ ኩራዝ ቁጥር 2 ስኳር ፋብሪካ ከመጋቢት 14 ቀን 2009 ዓ.ም ጀምሮ ወደ ሥራ መግባቱ ይታወሳል።

    የኦሞ ኩራዝ ቁጥር 3 ስኳር ፋብሪካ መመረቅ ስኳር የሚያመርቱትን ፋብሪካዎች ቁጥር ወደ ስምንት (ወንጂ ሸዋ፣ መተሐራ፣ ፊንጫአ፣ ከሰም፣ ተንዳሆ፣ አርጆ ዲዴሳ፣ ኦሞ ኩራዝ ቁጥር 2 እና 3) ያደርሰዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን

    የኦሞ ኩራዝ ቁጥር 3 ስኳር ፋብሪካ

Viewing 1 post (of 1 total)
  • You must be logged in to reply to this topic.