Search Results for 'አዲስ አበባ'

Home Forums Search Search Results for 'አዲስ አበባ'

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 495 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የዲጅታል የባንክ ሥርዓት በጊዜያዊነት መቋረጥን አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የተሰጠ መግለጫ

    መጋቢት 7 ቀን 2016 ዓ.ም በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የዲጅታል የባንክ ሥርዓት ላይ ባጋጠመ ችግር ምክንያት የባንኩ መደበኛ አገልግሎቶች ለተወሰኑ ሰዓታት መቋረጣቸዉ ይታወቃል።

    እንደሚታወቀው ቀልጣፋና ደህንነቱ የተጠበቀ አገልግሎት ለመስጠት ባንኮች በሥርዓቶቻቸዉ ላይ በየጊዜዉ የደህንነት ፍተሻ እንዲሁም የማሻሻያ ሥራዎችን ያከናዉናሉ። በሥርዓቶቹ ላይ በሚከናወን ለዉጦችና ፍተሻዎችም የባንኮች አገልግሎት አልፎ አልፎ ሊቋረጥ ይችላል።

    በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መጋቢት 7 ቀን፤ 2016 ዓ.ም. የተከሰተዉ የአገልግሎት መቋረጥ ከዚሁ ጋር የተያያዘ መሆኑን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ለማረጋገጥ ችሏል። ችግሩ ከተከሰተበት ሰዓት አንስቶ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን የባንኩን እና የደንበኞቹን ደህንነት ለማረጋገጥ ከፍተኛ ክትትል ሲያደርግ ቆይቷል። በመሆኑም የባንኩ መደበኛ አገልግሎቶች በአጭር ጊዜ ዉስጥ እንዲጀምሩና ባንኩ ወደተለመደው እንቅስቃሴው እንዲመለስ ማድረግ ተችሏል።

    በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ላይ የተከሰተዉ የአገልግሎት መቋረጥ ባንኩ በመደበኛነት በሥርዓቶቹ ላይ በሚያደርገዉ ማሻሻያና ፍተሻ ምክንያት የተከሰተ እንጂ የባንኩን፣ የደንበኞቹን እንዲሁም አጠቃላይ የፋይናንስ ሥርዓቱን አደጋ ላይ የሚጥል ክስተት አለመሆኑን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ለማረጋገጥ ችሏል።በችግሩ ምክንያት የተከሰቱ የደንበኞች መጉላላትን ጨምሮ ሌሎች ጉዳቶችን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ አስፈላጊዉን ምርመራ በማድረግ ወደፊት ለሕብረተሰቡ የሚያሳዉቅ መሆኑን ያረጋግጣል።

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የፋይናንስ ተቋማት የሚጠቀሟቸዉን ሥርዓቶች ደህንነታቻዉ የተጠበቀ፣ አስተማማኝ፣ ቀልጣፋና የደንበኞችን ፍላጎት የሚያሟሉ ስለመሆናቸዉ በየጊዜዉ ክትትልና ቁጥጥር ያደርጋል። በመሆኑም በአሁኑ ጊዜ በሁሉም የፋይናንስ ተቋማት የሚገኙ የፋይናንስ ሥርዓቶች ደህንነቸዉ የተጠበቀ በመሆኑ ሕብረተሰቡ ያለምንም ስጋት የፋይናንስ አገልግሎቶችን መጠቀም መቀጠል ይችላል።

    የገንዘብ (የፋይናንስ) ተቋማትም የሥርዓቶቻቸዉን ደህንነትና ቀልጣፋነት ይበልጥ ለማሳደግ የቴክኖሎጂ ተለዋዋጭ ባህርይ በማየት በቀጣይነት መሥራት እንደሚኖርባቸዉ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በጥብቅ ለማሳሰብ ይወዳል።

    በመጨረሻም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ አጠቃላይ የፋይናንስ ሥርዓቱ ደህንነት የበለጠ የተጠበቀ፣ አስተማማኝ እና የተረጋጋ ሆኖ እንዲቀጠል አስፈላጊ እርምጃዎችንና የአሠራር ሥርዓት ማሻሻያዎችን መዉሰዱን ይቀጥላል።

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ
    አዲስ አበባ፥ ኢትዮጵያ

    Semonegna
    Keymaster

    ዳሸን ባንክ እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ አዲስ የአየር ትራንስፖርት ክፍያ (የበረራ ክፍያ) አገልግሎት ይፋ አደረጉ

    አዲስ አበባ – ዳሸን ባንክ እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ደንበኞች የአየር ትራንስፖርት አገልግሎት ተጠቅመው ክፍያውን ቆይተው የሚከፍሉበትን አዲስ የክፍያ አማራጭ በጋራ አስተዋወቁ።

    አቶ ዮሃንስ ሚሊዮን የዳሽን ባንክ ዲጂታል ባንኪንግ ዋና መኮንን፥ ‘ጉዞዎ ይቀድማል ክፍያው ይደርሳል’ በሚል የተሰየመው ይህ አገልግሎት በደንበኞች ምርጫ መሠረት በ6 ወር ወይም በ12 ወር የብድር ክፍያ የሚሰጥ መሆኑን አመልክተዋል። ደንበኞች የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ለመሆን በዳሸን ባንክ የሂሳብ ቁጥር መክፈት እንደሚገባቸው እና በተጨማሪም በባንኩ ቢያንስ ለሦስት ወራት አገልግሎት ያገኙ መሆን እንደሚኖርባቸውም ጠቁመዋል።

    አቶ ዮሃንስ አክለውም አገልግሎቱን ለማግኘት ደንበኞች አቅራቢያቸው ወደሚገኝ የዳሸን ባንክ ቅርንጫፍ በሚያመሩበት ወቅት አስፈላጊ ሰነዶችን ማሟላት የሚገባቸው ሲሆን፥ ማስያዣም ማቅረብ እንደሚጠበቅባቸውም ገልፀዋል።

    ስምምነቱን አስመልክቶ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና የንግድ ሥራ አስፈፃሚ አቶ ለማ ያዴቻ የሚከተለውን መልዕክት አስተላልፈዋል፣ “የኢትዮጵያ አየር መንገድ ደንበኛ ተኮር አሠራርን እንደመከተሉ የተለያዩ ዘመናዊ እና ለመጠቀም ቀላል የሆኑ ቴክኖሎጂዎችን እያስተዋወቀ ይገኛል። የምናበለጽጋቸው ቴክኖሎጂዎች ለደንበኞቻችን ምቹ መሆናቸው እንደተጠበቁ ሆኖ የሀገር ውስጥ የፋይናንስ ተቋማት ከሚሰጡት አገልግሎት ጋርም የተጣጣሙ እንዲሆኑ እናደርጋለን። ዛሬም አጋራችን ከሆነው የዳሽን ባንክ ጋር በመተባበር ለደንበኞቻችን ያቀረብነው አዲስ የክፍያ አማራጭ ተግባራዊ እንዲሆን የሞባይል መተግበሪያችን ከአዲሱ የክፍያ አገልግሎት ጋር የተቀናጀ እንዲሆን አድርገናል። በዚሁም መሠረት ደንበኞች ስለክፍያ ሳይጨነቁ ጉዟቸውን ማቀድ የሚጀምሩበትን ‘Fly Now Pay Later‘ ተብሎ የተሰየመውን የክፍያ አማራጭ ተግባራዊ ማድረጋችንን ስንገልጽ በደስታ ነው። ይህ የድኅረ-ጉዞ ክፍያ አማራጭ ፕሮጀክት እውን እንዲሆን ከአየር መንገዳችን እና ከዳሽን ባንክ በኩል ለተሳተፉ አካላት ያለኝን ምስጋና በዚሁ አጋጣሚ ለመግለጽ እፈልጋለሁ።”

    አዲሱን የበረራ ክፍያ አገልግሎት ለመጠቀም አንድ ደንበኛ አስፈላጊ ቅድመ-ሁኔታዎችን ካሟላ በኋላ በቅርንጫፉ የተፈቀደለትን የብድር መጠን የሚወስድ ሲሆን፥ የተፈቀደለትን ገንዘብ ለመጠቀም የሚያስችል የአንድ ጊዜ መለያ ቁጥር መልዕክትም በተንቀሳቃሽ ስልኩ የሚደርሰው ይሆናል። በመቀጠልም ደንበኛው የተሰጠውን መለያ ቁጥር በአየር መንገዱ የሞባይል መተግበሪያ ላይ በማስገባት ትኬት መቁረጥና የአገልግሎቱ ተጠቃሚ መሆን ይችላል።

    ደንበኞች የተፈቀደላቸው የብድር መጠን ሲያልቅ ማደስ የሚችሉ ሲሆን፥ በአንዴ የወሰዱትን ብድርም ለተለያዩ በረራዎች ከፍለው መጠቀም ይችላሉ።አገልግሎቱ በተለይም በንግድ ሥራ ላይ ለተሰማሩ፣ ጅምላ አስመጪዎች እና ለዕረፍት ከቤተሰቦቻቸው ጋር ወደ ውጭ ለሚሄዱ ደንበኞች አመቺ ነው።

    በሁለቱ ተቋማት ስምምነት በቀረበው በዚህ አገልግሎት ተጠቃሚ ለመሆን የሚፈቀደው የብድር ገንዘብ መጠን እስከ ስድስት መቶ ሺህ (600,000) ብር የሚደርስ ነው። የሚፈቀደው ብድር ወለድ የሚታሰብበት ሲሆን፥ ይህም ደንበኛው በመረጠውና ብድሩን በወሰደበት የጊዜ ገደብ ከብድሩ ጋር አብሮ የሚከፈል ነው።

    አየር መንገዱ እና ዳሽን ባንክ ወደፊትም የደንበኞችን አገልግሎት ለማዘመን አዳዲስ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን በመጠቀም በትብብር መሥራታቸውን ይቀጥላሉ።

    ምንጭ፦ ዳሸን ባንክ

    Semonegna
    Keymaster

    ጋዜጠኛ መዓዛ ብሩ የክብር ዶክትሬታቸውን ከባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ተቀበሉ

    ባሕር ዳር፥ ኢትዮጵያ (ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ) – ባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ሐምሌ 16 ቀን፥ 2015 ዓ.ም ባካሄደው የተማሪዎች ምረቃ ለጋዜጠኛ መዓዛ ብሩ የክብር ዶክትሬት መስጠቱ ይታወሳል። በዕለቱ ጋዜጠኛ መዓዛ ብሩ በሥራ መደራረብ ምክንያት በምረቃ ዕለቱ ተገኝተው ባለመቀበላቸው፥ ኅዳር16 ቀን፥ 2016 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ ስካይላይት ሆቴል በአካል ተገኝተው ተቀብለዋል።

    በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የ2015 ዓ.ም የተማሪዎች ምረቃ ሥነ-ሥርዓት ላይ የመጀመሪያዋ የክብር ዶክትሬት ተሸላሚ የጠንካራ ጋዜጠኝነት ተምሳሌቷ እና የባለታሪኮች ባለአደራ ጋዜጠኛ መዓዛ ብሩ ናት።

    የክብር ዶክተር መዓዛ ብሩን ለክብር ዶክትሬት ሽልማት ያበቋቸው ሥራዎች በዝርዝር:-

    • በኢትዮጵያ የመጀመሪያው የግል ኤፍ ኤም ሬዲዮ (ሸገር ኤፍ ኤም 1) መሥራች እና ባለቤት፤
    • የመጀመሪያዋ ሴት የሬዲዮ ማሰራጫ ድርጅት መሥራችና ባለቤት፤
    • በእንግዶች ምርጫዋ፤ በምርምር በተደገፈ የመጠይቅ ዘይቤዋ፣ በትህትናዋ፣ በአነጋገር ለዛዋ በቀጥታ አዘጋጅታ ከምታቀርባቸው መርሃ ግብሮች (የቅዳሜ ጨዋታ እና ሸገር ካፌ) በተጭማሪ በተለያዩ የሸገር ሬዲዮ መርሃ ግብሮች እንዲሁም በሌሎች ሬዲዮም ሆነ ቴሌቪዥን መርሃ ግብሮች ላይ አሻራ የተወች እና ባጠቃላይ በዚህ ዘርፍ ለተሰማሩ ጋዜጠኞች አርአያ የሆነች፤

    ምናልባት ከሁሉ በላይ ታዋቂ የሆነችበትና አምሳያ የሌለው የላቀ አስተዋፅኦ ተብሎ ሊወሰድ ከሚችሉት ሥራዎቿ ውስጥ አንዱ፥ በቀላሉ ተተኪ የማይገኝላቸውን በርካታ ባለታሪክ ምሁራን፣ የመንግሥት ሥራ ኃላፊዎች፤ የኪነ-ጥበብ ሰዎች፤ ጋዜጠኞች እና ሌሎች ባለሙያዎች የህይውት ታሪክ፣ ሥራ፣ አስተሳሰብ እና ለሌሎች አርአያ የሚሆነውን የሕይወት ፍልስፍናቸው በራሳቸው አንደበት ተሰናድቶ ለታሪክ እንዲቆይ ማድረጓ ነው። በዚህም ለኢትዮጵያውያን በዓይነቱ ተወዳዳሪ የሌለውና ከጊዜ ወደጊዜ እያደገ የሚሄድ የታሪክ የድምጽ መዘክር አበርክታለች ማለት ይቻላል። የጨዋታ እንግዳ መሰናዶ እንግዶቿ ያካበቱት ልምድ፤ አበርክቶታቸው፤ ያልተጻፉ ሃገራዊ ጉዳዮች እና ሚስጥሮች ከኃላፊ ባለታሪኮቹ ጋር እንዳያልፉ፤ በመቅረጸ-ድምጽ ተሰንቀው በሰፊው እንዲታወቁ እና ከትውልድ ትውልድ እንዲተላለፉ አድርጋለች። በእርግጥም ጋዜጠኛ መዓዛ ብሩ ከየተደበቁበት ፈልጋ ቃለ መጠይቅ ካደረገቻቸው ጉምቱ እንግዶች መካከል ጥቂት የማይባሉት አሁን በመሃከላችን አይገኙም፤ ታሪካቸው ግን ህያው ሆኗል።

    ጋዜጠኛ መዓዛ ብሩ በ1950 ዓ.ም አዲስ አበባ ከተማ የተወለደች ሲሆን፥ ዘጠኝ ዓመት ገደማ እስኪሆናት በምዕራብ ሃረርጌ በምትገኘው ሂርና ከተማ አደገች። ሂርና ሳለች ጎረቤቶቿ የኦሮሞ፣ የሃረሪና የሶማሌ እንዲሁም የየመን ተወላጆች ስለነበሩ በተለያዩ ባሕላዊ ዕሴቶች እና እርስ በእርስ ትስስር የዳበረ አስተዳደግ ነበራት። ይህም ለሥነ-ጽሁፍ ከነበራት ዝንባሌ ጋር ተዳምሮ ለዛሬው ማንነቷ መሠረት ሆኗታል።

    • ጋዜጠኛ መዓዛ ብሩዘጠኝ ዓመት ሲሆናት ወላጆቿ አዲስ አበባ ወደሚገኘው የቅድስተ ማርያም የልጃገረዶች ካቶሊክ አዳሪ ትምህርት ቤት አሰገቧት።
    • 1967 ዓ.ም. የሁለትኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ እያለች በእድገት በሕብረት ዘመቻ ወደ ውቅሮ፥ ትግራይ ተልካ ለስድስት ወራት አገልግላለች።
    • በ1970 ዓ.ም. አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ገብታ በሥነ ልሳን ትምህርት ዘርፍ የመጀመሪያ ዲግሪዋን ተቀብላለች።
    • ከሬዲዮ ሥራ ጋር ለመጀመሪያ ጊዜ የተዋወቀችው የመጨረሻ ዓመት ተማሪ ሳለች በአጋጣሚ ሲሆን፥ በወቅቱ ተወዳጅ ከነበረው የእሁድ ፕሮግራም ጋር ለነበራት ለስምንት ዓመታት ያክል የቆየ ትስስር ምክንያት ሆኖታል። ይሁን እንጂ በመጀመሪያ በቋሚነት የተመደበችበት ሥራዋ በባህል ሚኒስቴር ስር የመርሃ ስፖርት ጋዜጣ የስፖርት ዘጋቢነት ነበር።
    • በመቀጠልም በኢትዮጵያ ሬዲዮ የእሁድ ፕሮግራም ተሳትፎዋን ሳታቆም በባህል ሚኒስቴር የዓለም አቀፍ አግልግሎት ክፍል አገልግላለች።
    • ከዚያም በብሔራዊ ባንክ የብሪቱ መጽሄት ዋና አዘጋጅ በመሆን የፋይናንስ ዜናዎችን እና አጫጭር ታሪኮችን በመጻፍ እና በአርትኦት አገልግላለች።
    • በ1984 ዓ.ም የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርን ተቀላቅላ የፕሬስ እና ኮሚኒኬሽን ኦፊሰር በመሆን ለአራት ዓመታት ሠርታለች።
    • ከዚያም በግል በአማካሪነት እና በሕዝብ ግንኙነት እና ማስታወቂያ ስትሠራ ከቆየች በኋላ፤ በ1987 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ሬዲዮ በ1 የሬዲዮ ጣቢያን የአየር ሰዓት በመጠቀም የቅዳሜ ከሰዓት የጨዋታ መርሀ ግብርን ከባለቤቷ ከአርቲስት አበበ ባልቻ እና ከረዥም ጊዜ ጓደኛዋ አርቲስት ተፈሪ ዓለሙ ጋር የማዘጋጀት ዕድል አግኝታ መርሀ ግብሩን ለስምንት ዓመታት ያክል ስታቀርብ ቆይታለች።
    • በመጨረሻም በ2000 ዓ.ም. አንጋፋና ተወዳጅ የሆነውን ሸገር ኤፍ ኤም1ን እዉን ለማድረግ በቅታለች።

    በአጠቃላይ ጋዜጠኛ መዓዛ ብሩ በኢትዮጵያ የጋዜጠኝነት ሙያ የጥንካሬ ተምሳሌትና በዘርፉ ለበርካቶች አርአያ ለመሆኗ ተገቢ ዕውቅና ይሆን ዘንድ የባሕር ዳር ዩኒቨርሰቲ ሴኔት በከፍተኛ ትምህርት አዋጅ ቁጥር 1152 / 2011 በተሰጠው ስልጣን መሠረት በአርት የዓመቱ የክብር ዶክትሬት እንዲሰጣቸው ወስኗል።

    ምንጭ፦ ባሕር ዳር ዩኒቨርሰቲ

    Semonegna
    Keymaster

    ዳሸን ባንክ እና ማስተርካርድ የመጀመሪያውን ቨርቹዋል ዓለም አቀፍ ቅድመ ክፍያ ካርድ አስተዋወቁ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ዳሸን ባንክ ዓለም አቀፍ ቅድመ ክፍያ ካርድ ከማስተርካድ (Mastercard) ጋር በመተባበር ከተለመደው በስም ከሚታተም የፕላስቲክ ካርድ በተጨማሪ በኢትዮጵያ የባንክ ኢንዱስትሪ ታሪክ የመጀመሪያ የሆነ ቨርቹዋል ካርድን (virtual card) በማምጣት ነሐሴ 15 ቀን፥ 2015 ዓ.ም በሸራተን አዲስ ሆቴል አስተዋውቀዋል።

    የዳሸን ባንክ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ አስፋው ዓለሙ በሥነ-ሥርዓቱ ላይ ባደረጉት ንግግር፥ ዳሸን ባንክ ይህን በዓይነቱ የተለየ ካርድ ማስተዋወቁ ባንኩ ለደንበኞቹ ቀላል፣ ምቹና አስተማማኝ የፋይናንስ አገልግሎቶችን ይበልጥ ለማቅረብ ያለውን ቁርጠኝነት ያሳያል ብለዋል። ካርዱ ደንበኞች በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ገንዘባቸውን ያለምንም ስጋት መጠቀም የሚችሉበት አማራጭ መሆኑንም አመልክተዋል።

    የማስተርካርድ የምሥራቅ አፍሪካ ሥራ አስኪያጅ ሸህርያር አሊ በበኩላቸው፥ ማስተርካርድ ከዳሸን ባንክ ጋር የፈጠረው ጥምረት በኢትዮጵያ እንደ ዓለም አቀፍ ካርድ ያሉ አገልግሎቶችን በማስተዋወቅ ማኅበረሰቡ ይበልጥ የዲጂታል አገልገሎቶችን ተጠቃሚ እንዲሆን ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚፈጥር ገልፀዋል።

    “ከዳሸን ባንክ ጋር በመጣመር የተለያዩ የዲጂታል አገልግሎቶችን ለማቅረብና ይህን መሰል የክፍያ አማራጭ ለንግዱ ማኅበረሰቡና ሌሎች ደንበኞች ተጠቃሚ እንዲሆኑ በማስቻላችን ትልቅ ክብር ይሰማናል” ብለዋል።

    በዳሸን ቅድመ ክፍያ ማስተርካርድ ደንበኞች ከኤቲኤም (ATM) እና ፖስ (PoS) በተጨማሪ በኢ-ኮሜርስ ክፍያ መክፈል የሚያስችላቸው ሲሆን፤ ደንበኞች ፕላስቲክ ወይም ቨርቹዋል (virtual) ካርድ በመውሰድ መጠቀም ይችላሉ። ከዚህ በተጨማሪ ፕላስቲክ ካርዱ ስም የታተመበትና ስም ያልታተመበት የካርድ ዓይነቶችን የያዘ ነው።

    ደንበኞች ዳሸን ማስተርካርድ ላይ የተሞላው የውጪ ምንዛሬ ሲያልቅ እንደገና በመሙላት መጠቀም የሚያስችላቸው ሲሆን ካርዱን ኤቲኤምና ፖስ ማሽን ላይ በማስገባት ወይም ያለ ንክኪ ገንዘብ ማውጣት ወይም ክፍያ መፈፀም ያስችላቸዋል።

    ፕላስቲክ ካርዱ በሚስጢር ቁጥር የተጠበቀ ሲሆን ቨርቹዋል ካርዱ ደግሞ በአንድ ጊዜ የይለፍ ቃል ደህንነቱ የተጠበቀ ነው። ደንበኞች ካርዱን ለመጠቀም አቅራቢያቸው በሚገኝ የዳሸን ባንክ ቅርንጫፍ ፓስፖርት፣ ቪዛ እና የበረራ ቲኬት በመያዝ አገልግሎቱን ማግኘት ይችላሉ።

    ዳሸን ባንክ እና ማስተርካርድ ከካርዱ በተጨማሪ የንግድ ተቋማት ክፍያቸውን በበይነ መረብ ከየትኛውም የዓለም ክፍል መቀበል የሚያስችል የማስተርካርድ የክፍያ መቀበያ ማስተርካርድ ጌትዌይ /MasterCard Payment Gateway System/ አስተዋውቀዋል።

    ይህ የማስተርካርድ ጌትዌይ/ MasterCard Payment Gateway System/ ሦስት የካርድ አይነቶችን በመቀበል የተሻለ የአገልግሎት አማራጭ መሆኑ ተመልክቷል። ይህም ለንግድ ተቋማት ክፍያ ለመቀበል እና ሽያጭ ለማከናወን ለምግባረ ሰናይ ድርጅቶች እርዳታ እና የአባልነት ክፍያ ለመሰብሰብ እና ለሌሎች አገልግሎቶች ዘመናዊ የክፍያ መፈጸሚያ መስመር ነው።

    ምንጭዳሸን ባንክ

    Semonegna
    Keymaster

    የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በሁሉም መመዘኛዎች ውጤታማ አፈፃፀም ማስመዝገቡን አስታወቀ
    የባንኩ ጠቅላላ ሃብት 1 ነጥብ 3 ትሪሊየን ብር ደርሷል
    የንብ ኢንተርናሽናል ባንክ ከፍተኛ ሥራ አስፈጻሚዎች ሹመት ጸደቀ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በሁሉም መመዘኛዎች ውጤታማ አፈፃፀም ማስመዝገቡን ፤ እንዲሁም የባንኩ ጠቅላላ ሃብት 1 ነጥብ 3 ትሪሊየን ብር መድረሱን አስታውቋል።

    በባንኩ ዋና መሥሪያ ቤት የመሰብሰቢያ አዳራሽ ከሚያዝያ 17-19/ 2015 ዓ.ም በተካሄደው የሥራ አፈፃፀም ግምገማ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በተቀማጭ ገንዘብ አሰባሰብ፣ ብድር በመስጠትና በመሰብሰብ፣ የዲጂታል ባንክ አገልግሎትን ተደራሽ በማድረግ፣ በውጭ ምንዛሪ ግኝትና አቅርቦት እንዲሁም በሌሎች ፋይናንስና ፋይናንስ ነክ ባልሆኑ አፈፃፀሞች ውጤታማ ሥራ መሠራቱ ተጠቁሟል።

    በዘጠኝ ወራት ውስጥ ከ123 ቢሊየን ብር በላይ ተጨማሪ ተቀማጭ ገንዘብ መሰብሰብ መቻሉ በጉባዔው የተገለፀ ሲሆን፣ የባንኩ ጠቅላላ ሃብትም 1 ነጥብ 3 ትሪሊየን ያህል ብር መድረሱ ታውቋል።

    የዲጂታል ባንክ አገልግሎትን ተደራሽ በማድረግ ባንኩ ወጤታማ እንደነበር የተብራራ ሲሆን፤ በዘጠኝ ወራት ውስጥ በዲጂታል ባንክ አማራጮች ብቻ 2 ነጥብ 1 ትሪሊዮን ብር ተንቀሳቅሰሷል ብሏል ባንኩ በሥራ አፈፃፀም ግምገማው።

    ባንኩ በዘጠኝ ወራት ውስጥ በሁሉም መመዘኛዎች መልካም አፈፃፀም ነበሩት ያሉት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዝዳንት አቶ አቤ ሳኖ በቀጣይ በተለይ ዋና ዋና የትኩረት ዘርፎች በሆኑት በተቀማጭ ሃብት አሰባሰብ፣ በዲጂታል ባንክ አገልግሎት፣ በብድር አሰጣጥና አሰባሰብ፣ በውጭ ምንዛሪ ግኝት እንዲሁም የባንኩን የሪፎርም (reform) ሥራዎች በማስቀጠል በትኩረት ሊሠራ ይገባል ብለዋል።

    የባንኩ የዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ተክለወልድ አጥናፉ በበኩላቸው ፋይናንስም ሆነ ፋይናንስ ነክ ባልሆኑ ዘርፎች የታዩትን አፈፃፀሞች፤ መልካሞቹን በማጠናከር ድክመቶችን ደግሞ በማረም በቀጣይ የተሻለ አፈፃፀም ለማስመዝገብ ሁሉም የባንኩ ማህበረሰብ በአንድ ልብ ሊሠራ እንደሚገባ ነው ያሳሰቡት።

    በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የዘጠኝ ወራት የሥራ አፈፃፀም ግምገማ ላይ የባንኩ የዳይሬክተሮች ቦርድ አባላት፣ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባላትና ከፍተኛ የሥራ አመራሮች፣ የሁሉም ዲስትሪክቶች ዳይሬክተሮች እና የልዩ ቅርንጫፍ ሥራ አስኪያጆች ተሳትፈዋል።

    ከባንክ ዜና ሳንወጣ፥ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ አምስት የንብ ኢንተርናሽናል ባንክ ከፍተኛ ሥራ አስፈጻሚዎችን ሹመት ማጽደቁን አስታውቋል። በዚህም መሠረት፥ አቶ ሰይፉ አገንዳ ኬርጋ – ቺፍ የከስተመርና ኦፕሬሽንስ ኦፊሰር (Chief Customer and Operations Officer)፣ አቶ ሰለሞን ጎሽሜ በጅጋ – ቺፍ የኮርፖሬት ሰርቪስስ ኦፊሰር (Chief Corporate Services Officer)፣ አቶ መልካሙ ሰለሞን ይመር – ምክትል ፕሬዚዳንት ሂዩማን ካፒታል (Vice President of Human Capital)፣ አቶ አብርሃም ተስፋዬ አበበ – ምክትል ፕሬዚዳንት የስትራቴጂና ማርኬቲንግ (Vice President of Strategy and Marketing) እና አቶ አሚነ ታደሰ ተስፉ – ምክትል ፕሬዚዳንት የኢንተርናሽናል ባንክ ኦፕሬሽን (Vice President of International Bank’s Operation) ሆነው ተሹመዋል።

    ብሔራዊ ባንክ ሹመቱን ማጽደቁን ባሳወቀበት ደብዳቤ ላይ እንደገለጸው፥ በባንክ ሥራ አዋጅ ቁጥር 592/2000፣ በተሻሻለው አዋጅ ቁጥር 1159/2011 እና ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ መመሪያ ቁጥር SBB/79/2021 አንጻር የተላኩለትን ሰነዶች እና ሌሎች ማስረጃዎች ላይ ተገቢውን ማጣራት አድርጎ መሆኑን አረጋግጧል።

    ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ በቅርቡ የስትራቴጂክ (መሪ) እቅድ ክለሳ ያደረገ ሲሆን፤ ይኸው የከፍተኛ ኃላፊዎች ሹመትም ከዚሁ ክለሳ ጋር ተያይዞ የተዘጋጀውን አዲስ የባንኩን አደረጃጀት መሠረት ያደረገ ነው።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክንብ ኢንተርናሽናል ባንክ

    Semonegna
    Keymaster

    የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት በ2022 ዓ.ም በአፍሪካ ቀዳሚ ተቋም ለመሆን እየሠራ ነው

    አዲስ አበባ (አዲስ ዘመን) – የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት በ2022 ዓ.ም በአፍሪካ ቀዳሚ ተቋም ለመሆን እየሠራ መሆኑ ተገለጸ። አስራ ሰባት (17) ችግር ፈቺ ምርምሮች ተሠርተው ወደ ግምገማ እና ትግበራ ገብተዋል።

    ከኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ጋር ቆይታ ያደረጉት የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክተር አቶ ተስፋዬ ዘውዴ እንደተናገሩት፥ ተቋሙ በ2022 ዓ.ም ከአፍሪካ ካሉ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩቶች ቀዳሚው ለመሆን እየሠራ ነው።

    በዚህም 17 የሚሆኑ ችግር ፈቺ ምርምሮችን እያካሄደ መሆኑንና ከፊሉ ወደ ትግበራ ማስገባታቸውን፥ እንዲሁም የተቀሩትን ምርምሮች ወደ ትግበራ ለማስገባት በግምገማ ላይ መሆናቸውን አብራርተዋል።

    ምርምሮቹም በጤና፤ በትምህርት፤ በአገልግሎት አሰጣጥና በፋይናንስ ዘርፍ ግልጋሎት እምርታዊ ለውጥ የሚያመጡ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ መተግበሪያዎች መሆናቸውን አስረድተዋል። ለአብነት ያህልም በጤናው መስክ፥ የተለያዩ የሕክምና ዘርፉን ሊያዘምኑ ወይም ሊያሻሽሉ የሚችሉ ሥራዎች እየተሰሩ ነው ያሉት አቶ ተስፋዬ፣ ውስን የሆኑ የሕክምና ባለሙያዎች የሚገኙባቸው ሴክተሮች ላይ ተጨባጭ ውጤት ያመጣልም ብለዋል።

    የጭንቅላት እጢ፣ የጡት ካንሰር፣ የቆዳ በሽታ ልየታን ማከናወን የሚችሉ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ መተግበሪያዎች መዘጋጀታቸውንም አብራርተዋል። በአዲስ አበባ ስማርት ሲቲ (smart city) ግንባታ ላይ ወሳኝ ሚና ያላቸው የስማርት ሴኩሪቲ (smart security) ግንባታዎች እየተካሄዱ እንዳሉ የገለጹት አቶ ተስፋዬ፥ በርካታ ዓለም አቀፍ ሁነቶች በሚካሄዱባት አዲስ አበባም በሺዎች የሚቆጠሩ የአርተፊሻል ኢተለጀንስ ካሜራዎች መገጠማቸውን አንስተዋል። ካሜራዎቹ የፊት ገፅታን እና የመኪና ሰሌዳ ቁጥሮችን የሚለዩ እና የሚመዘግቡ መሆናቸውን አያይዘው ጠቅሰዋል።

    በፋይናንስ ሴክተር የውይይት መለዋወጫ ሮቦት (ቻትቦት/chatbot) በማዘጋጀት ዘርፉን የሚያዘምኑ ሥራዎች እየተከወኑ እንዳሉ በማብራራትም፤ ቻትቦቶቹ በተመረጡ ሀገርኛ ቋንቋዎች ጭምር ግልጋሎት ይሰጣሉ ብለዋል። የደረቅ ጭነት የተቀናጀ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል መተግበሪያ ደግሞ ለትራንስፖርት እና ሎጂስቲክ ሚንስቴር አበርክቶ መተግበሪያዎቹ ግልጋሎት መስጠት መጀመራውን የኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተሩ አትተዋል።

    በትምህርቱ መስክ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የመረጃ አሰጣጥ አገልግሎታቸውን ማዘመን የሚያስችል እና የሀሰተኛ የትምህርት ማስረጃዎችን ማስቀረት የሚያስችል እጅግ ዘመናዊ የሆነ መተግበሪያ ለምቶ ትግበራ ላይ መዋሉንም ጨምረው ጠቅሰዋል። የተለያዩ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ሥርዓቶች በቅልጥፍና እንዲሠሩ እና ለመረጃ ቋትነት ግልጋሎት የሚሰጥ ማዕከል ግንባታም በተቋሙ ውስጥ ተከናውኗል ያሉት ዳይሬክተሩ አቶ ተስፋዬ ዘውዴ፥ የመረጃ ቋት መኖሩ ለተማሪዎችም ይሁን ለመምህራን ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ እንዳለው ጠቁመዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት

    Semonegna
    Keymaster

    “መደበኛ ፓስፖርት ለማውጣት አገልግሎት አሰጣጡ ምቹ ባለመሆኑ ለእንግልት ተዳርገናል” ― ተገልጋዮች
    “በጉዳዩ ላይ በቅርቡ መግለጫ እሰጣለሁ” ― የኢምግሬሽን፣ ዜግነትና ወሳኝ ኩነት ኤጀንሲ

    አዲስ አበባ (አዲስ ዘመን) – መደበኛ ፓስፖርት ለማውጣት ከፍተኛ መጉላላት እየደረሰባቸው መሆኑን ተገልጋዮች ቅሬታ አቀረቡ። የኢምግሬሽን፣ ዜግነትና ወሳኝ ኩነት ኤጀንሲ በበኩሉ ከኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ለቀረበለት ተደጋጋሚ ጥያቄ በጉዳዩ ላይ በቅርቡ መግለጫ እሰጣለሁ ከማለት ውጪ መረጃ ሊሰጥ አልቻለም።

    በአዲስ አበባ መደበኛ ፓስፖርት ለማውጣትም ሆነ ለማደስ ወደተቋሙ የሚሄዱ ተገልጋዮች በተቋሙ ባለው ምቹ ያልሆነ አሠራር ምክንያት ለከፍተኛ እንግልት እየተዳረጉ መሆኑን ይገልጻሉ። ተገልጋዮቹ እንደሚሉት በተቋሙ አገልግሎቱን ለማግኘት ከሌሊት 9፡00 ሰዓት  ጀምሮ ተሰልፎ ወረፋ ከመጠበቅ ጀምሮ ፓስፖርቱ አልቆም ለማግኘት ያለው ሂደት ውስብስብና ለከፍተኛ እንግልት የሚዳርግ ነው።

    ነዋሪዎቹ እንደሚሉት ፓስፖርት አገልግሎትን ለማግኘት በኦንላይን (online) አማካኝነት ምዝገባ የሚካሄድ ቢሆንም፥ ከዚያ በኋላ በተቀጠሩበት ዕለት ሌሊት ወጥቶ ወረፋ መጠበቅ፣ ከዚያም በኋላ ሂደቱን ሲያልፉ ፓስፖርት ለማግኘት ያለው አሠራር ተገልጋይን የሚያማርር ነው።

    የአዲስ አበባ ነዋሪ የሆኑት ወይዘሮ መዲና ጂብሪል፥ ለልጆቻቸው ፓስፖርት ለማውጣት በስም ዝርዝር ምደባ መሠረ ከካዛንቺስ ፖስታ ቤት እንዲወስዱ የተገለጸላቸው ቢሆንም፥ ከታኅሣሥ ወር ጀምሮ ከፖስታ ቤቱ አልደረሰም የሚል ምላሽ እንደተሰጣቸው ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ገልጸዋል።

    ወደ ኢሚግሬሽን መሥሪያ ቤት ተመልሰው መጠየቅ እንዳለባቸው የተነገራቸው ወይዘሮ መዲና፥ ከዋናው መሥሪያ ቤት ወደፖስታ ቤት በየጊዜው እያመላለሷቸው መቸገራቸውን በምሬት አስረድተዋል።

    ከዚህ ባለፈ በኢምግሬሽን መግቢያ በሮች ላይ ጥበቃዎችና ተራ አስከባሪዎች ወደ ውስጥ እንዳታስገቡ የሚል ትዕዛዝ ተሰጥቶናል በሚል ተገልጋዮችን ለመምታት የሚጋበዙ መሆናቸውን ገልጸው፤ በዚህም የሚመለከተውን አካል ለመጠየቅም ሆነ ለማነጋገር እንዳልቻሉ ጠቁመዋል።

    ችግሩን በተመለከተ ለማን አቤት ይባላል የሚሉት ወይዘሮ መዲና፥ ዜጎችን የሚያጉላሉ አሠራሮችን ማስተካከልና አገልግሎቱን የተሟላ ማድረግ ይገባል ብለዋል። መደበኛ ፓስፖርት ለማውጣት አስፈላጊውን ማስረጃ ከሰጠችና ከተመዘገበች አንድ ወር ከአሥራ አምስት ቀን እንደሆናት የምትገልጸው ሌላኛዋ የአዲስ አበባ ነዋሪ ወይዘሪት ሰናይት ንጉሴ ነች።

    የአስቸኳይ ፓስፖርት ከመከልከሉ በፊት መደበኛ ፓስፖርት ለማውጣት ወደ ዋናው መሥሪያ ቤት በመሄድ ማመልከቷን ትገልጻለች። ኦርጅናል የልደት ካርድ፤ መታወቂያና የትምህርት ማስረጃዎችን እንዲሁም አስፈላጊውን መረጃ ሁሉ አሟልቻለሁ። አሻራ የሰጠሁ ቢሆንም ማስረጃውን አጣርተን እንጠራሻለን የሚል ምላሽ ቢሰጠኝም እስካሁን ምላሽ አላገኘሁም ትላለች።

    እኔ ሻይና ቡና በመሸጥ የምተዳደር ነኝ። በሕጋዊ መንገድ ወደ ሌላ አገር ሄጄ ለመሥራት ብዩ ፓስፖርት ለማውጣት ፈልጊያለሁ ስትል ሁኔታዋን አስረድታለች።፡ ከለሊቱ 9፡00 ሰዓት ጀምሮ ተራ ለመያዝ ወደኢምግሬሽን የምትሄድ መሆኑን በመግለጽ፤ እንግልቱ ግን ወደ ኢምግሬሽን በተደጋጋሚ የሄደች ቢሆንም ሳንደውል ለምን ትመጫለሽ የሚል ምላሽ እንደተሰጣትና፤ ጉዳዩን ለተቋሙ ቅሬታ ሰሚዎች ያቀረበች ቢሆንም ምንም ማድረግ እንደማይችሉ እንደተነገራት አስረድታለች።

    የጅማ ከተማ ነዋሪው አቶ አብዲሳ ታደሰ በበኩላቸው፥ በከተማው የኢምግሬሽን፣ ዜግነትና ወሳኝ ኩነት ኤጀንሲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት በተደጋጋሚ ያቀረበው የፓስፖርት ይሰጠኝ ጥያቄ ምላሽ ባለማግኘቱ ወደዋናው መሥርያ ቤት ቢመጡም እዚህም ምላሽ ሊያገኝ እንዳተሰጣቸው ይገልጻሉ።

    አቶ አብዲሳ አስፈላጊ ናቸው የተባሉ መረጃዎችን ሁሉ ይዘው መቅረባቸውን በመጥቀስ ከጥቅምት ወር 2015 ዓ.ም ጀምሮ አገልግሎቱን ሳያገኙ እየተጉላሉ መሆኑን ገልጸዋል። የፓስፖርት ሂደቱን ሲጀምሩ በሦስት ወር እንደሚሰጣቸው የተነገራቸው ቢሆንም በተቀጠሩበት ቀን ፓስፖርቱን መውሰድ እንዳልቻሉ ጠቁመዋል።

    የቅርጫፉን ኃላፊ ስለጉዳዩ ማነጋገሩን የሚገልጸው አቶ አብዲሳ፥ ፖስታ ቤት ሂድ በማለት እንደመለሱለት ቢናገርም ፖስታ ቤት ግን ፓስፖርቱን ሊያገኝ እንዳልቻለ አስረድቷል። በዚህ የተነሳ ወደውጭ አገር ለመሄድ ያሰበውን የቪዛ ዕድል ማጣቱን በምሬት ገልጿል።

    ችግሩ ከዋናው መሥሪያ ቤት ነው የሚል ምላሽ እንደተሰጠው ጠቁሞ፤ በወቅቱ ወደአዲስ አበባ ኢምግሬሽን ለመምጣት የመሸኛ ደብዳቤ እንዲሰጡት በጠየቀበት ወቅት ተጨማሪ 600 ብር በድጋሚ መክፈል እንደሚጠበቅበት የተገለጸለት መሆኑን አስረድቷል።

    የፓስፖርት አገልግሎትለማግኘት እየተጉላሉ የሚገኙ ዜጎች ቀልጣፋ አሠራር እንዲፈጠርና በኢሚግሬሽን አገልግሎትና በፖስታ ቤቶች መካከል ተገቢው መናበብ ሊፈጠር ይገባል ሲሉ ጠይቀዋል።

    ጉዳዩን በተመለከተ የኢምግሬሽን፣ ዜግነትና ወሳኝ ኩነት ኤጀንሲን በስልክና በደብዳቤ በተደጋጋሚ በመጠየቅ ምላሽ ለማግኘት የተደረገው ጥረት ሳይሳካ ቀርቷል። ኤጀንሲው በጉዳዩ ላይ ጋዜጣዊ መግለጫ እንደሚሰጥ በቃል ደረጃ ቢያሳውቅም ይህን ዜና የዘገበው የአዲስ ዘመን ጋዜጣ ወደህትመት እስከገባበት ሰዓት ድረስ ምንም ዓይነት መግለጫ እንዳልተሰጠ ማረጋገጥ ተችሏል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት

    Semonegna
    Keymaster

    ኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ የትምህርት ጆርናል ለማስጀመር በምሁራን አስገመገመ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – በማስተማርና በምርምር ሥራዎቻቸው ዕውቅናን ያተረፉ ፕ/ር አማረ አስግዶም እና ፕ/ር ያለው እንዳወቅ እንዲሁም በኢፌዲሪ የትምህርት ሚኒስቴር የከፍተኛ ትምህርት ምርምርና ስርጭት (research and dissemination expert) ከፍተኛ ባለሙያ የሆኑት ዶ/ር ተስፋማርያም ሽመክት፣ ብሎም የዩኒቨርሲቲው ምሁራን በተገኙበት የኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ ‘ኮተቤ የትምህርት ጆርናል’ (Kotebe Journal of Education, KJE) የተሰኘውን ጆርናል ለማስጀማር ዝግጅቱን አጠናቆ ለዚሁ ዓላማ የተሰነዱ ፖሊሲንና መመሪያን የካቲት 16 ቀን፥ 2015 ዓ.ም አስገምግሟል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶ/ር ብርሃነመስቀል ጠና በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ ኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ በአዋጅ ከተቋቋመ እነሆ አንድ ዓመት ከጥቂት ወራት በሆነ ጊዜ ውስጥ በርካታ የማቋቋም ሥራዎችን ሲሠራ ቆይቷል ። ከእነዚህም አንዱ ዩኒቨርሲቲው የሚታወቅበት የራሱ መለያ ጆርናል እንዲኖረው ማስቻል ነው። ጆርናል ምሁራን ጥናትና ምርምሮቻቸውን ከዩኒቨርሲቲው ባሻገር ለሶስተኛ ወገን ተጠቃሚ የሚያደርሱበት ድልድይ ነው። ለዩኒቨርሲቲ ይህ ድልድይ አንዱ የሀገራዊነት እና ከዚያም ባሻገር መለኪያ ነውና በጥንቃቄ የምንይዘው ነው ብለዋል። በመሆኑም ይህንኑን እውን ለማድረግ ስንሠራ ቆይተን የሚተገበርበትን አሠራር (ፖሊሲ እና የአሠራር መመሪያ) ቀርፀን ለዛሬ ማስጸደቂያ ቀን (validation) አድርሰናልና፤ ለስኬቱ አስተዋጽኦ ላደረጋችሁ በሙሉ ትልቅ አክብሮት አለኝ ሲሉ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

    በመልዕክታቸው አያይዘውም ፕሬዝዳንቱ ‘ኮተቤ የትምህርት ጆርናል’ (KJE) በዓይነቱ ለየት ያለ፣ ሀገራችንን፣ ተቋማችንን እና ትውልዱን የሚያሻግር እንዲሆን ከፍተኛ ጥንቃቄ በተሞላበትና ደረጃውን በጠበቀ መልኩ እንዲታተም ለዚሁ ሥራ አመራርነት ለተሠየመው ቲም አደራ ብለዋል።

    የ‘ኮተቤ የትምህርት ጆርናል’ አስመልክቶ የተዘጋጀ ፖሊሲን ያቀረቡት የጆርናሉ ዋና አርታኢ የሆኑት ዶ/ር ሩቂያ ሀሰን፥ የጆርናሉ ዋና ዓላማ ላቅ ባለ ሁኔታ ለተመራማሪዎች ሀገራዊ እና ዓለም ዓቀፋዊ የትምህርት እና የምርምር ውጤቶቻቸውን የሚያሳትሙበትን ተጨማሪ ዕድል መፍጠር መሆኑን ገልፀዋል። የጆርናሉ ተባባሪ አርታኢ ሆነው የተመደቡ ዶ/ር ይታያል አዲስም በበገለጻቸው የሚቀርቡ ጽሑፎች ከዚህ በፊት በማንኛውም ጆርናል ላይ ያልቀረቡና ሳይንሳዊ ሥነ-ዘዴዎችን (guidelines) ያሟሉ ስለመሆናቸው በጥብቅ ዲሲፕሊን ተገምግመውና የተቀመጠላቸውን መስፈርቶችን አሟልተው ሲገኙ ብቻ ለህትመት እንደሚበቁ ተናግረዋል። የዩኒቨርሲቲው የመረጃና ግንኙነት ቴክኖሎጂ (ICT) መሠረተ ልማት ቡድን መሪ አቶ ማቲያስ አድማሱ በበኩላቸው፥ ለህትመት የሚቀርቡ ጽሑፎች በኦንላይን ሲስተም ሆነው ጆርናሉ ለህትመት እስኪበቃ ድረስ ያለው ሂደት ደህንነቱ የተጠበቀና አስተማማኝ እንዲሆን ይሠራል ብለዋል።

    ምንጭ፦ የዩኒቨርሲቲው የኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት

    Semonegna
    Keymaster

    ኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል የሚያግዝ የመምህራን አቅም ማጎልበቻ ፍኖተ-ካርታ ማዘጋጀቱን ገለጸ

    አዲስ አበባ (ኢዜአ) – ኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል የሚያግዝ የመምህራን አቅም ማጎልበቻ ፍኖተ-ካርታ ማዘጋጀቱን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶክተር ብርሀነመስቀል ጠና ገለጹ።

    መንግሥት ዩኒቨርሲቲው በትምህርት ዘርፍ ያሉ ችግሮችን ለመቅረፍ እያከናወናቸው ያሉ ተግባራትን በመደገፍ ረገድ የጀመረውን ሥራ አጠናክሮ እንዲቀጥልም ጥሪ አቅርበዋል።

    የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶክተር ብርሀነመስቀል ጠና ከኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) ጋር ባደረጉት ቆይታ፥ ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ በትምህርት ሥርዓቱ ላይ ከመዋቅር ጀምሮ ማሻሻያዎች እየተደረጉ ስለመሆናቸው ተናግረዋል።

    ለአብነትም 10ኛ ክፍል ይሰጥ የነበረው ብሔራዊ ፈተና በ12ኛ ክፍል እንዲሰጥ ከማድረግ ጀምሮ በዩኒቨርሲቲዎች በ3 ዓመት ይመረቁ የነበረውን ወደ 4 ዓመት እንዲያድግ መደረጉን አስታውሰዋል።

    ባለፉት ዓመታት በተለይ በትምህርት ፍኃዊነትና ተደራሽነት ላይ በርካታ ሥራ የተሠራ ቢሆንም በትምህርት አግባብነትና ጥራት ላይ የተሳካ ወይንም አጥጋቢ ሥራ ባለመሠራቱ ውጤት ሊመዘገብ አልተቻለም ብለዋል። ለዚህም በቅርቡ የወጣው የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና ውጤት የኢትዮጵያ የትምህርት ጥራት ችግር ምን ላይ እንዳለ በግልጽ አሳይቷል ብለዋል።

    በተመሳሳይ ከዚህ ቀደም ለመምህራን ምዘና ተሰጥቶ በርካቶቹ ዝቅተኛ ውጤት ማስመዝገባቸውን አውስተው፤ ይህ ለትምህርት ጥራት ችግሩ ዓይነተኛ አስተዋፆኦ እንዳለው ነው ያስረዱት። ለተማሪዎቹ ዝቅተኛ ውጤት መመዝገብ መምህራንን ጨምሮ አጠቃላይ የትምህርት ማኅበረሰቡ ኃላፊነት ያለበት በመሆኑ ችግሩን በጋራ መፍታት ይገባል ነው ያሉት።

    መንግሥት የትምህርት ዩኒቨርሲቲ አለመኖር ለትምህርት ጥራት መጓደል አንዱ ምክንያት መሆኑን በመረዳት ችግሩን ለማቃለል ኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ ማቋቋሙን ገልፀዋል። ጨምረውም፥ በተለያዩ ችግሮች እየተፈተነ የሚገኘውን የኢትዮጵያ የትምህርት ዘርፍ ለማከም ኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ በርካታ ሥራዎችን እየሠራ እንደሚገኝ አንስተዋል።

    ዩኒቨርሲቲው የመምህራንን ትምህርት ዋነኛ ምሰሶ በማድረግ የትምህርት አመራሮች፣ ተመራማሪዎች፣ አማካሪዎችና ፖሊሲ አውጪዎችን ማፍራት ላይ አተኩሮ እየሠራ እንደሚገኝም ተናግረዋል። በመሆኑም ዩኒቨርሲቲው የትምህርት ስብራቱን ለመጠገን የሚያስችል የመምህራን አቅም ማጎልበቻ ፍኖተ-ካርታ ማዘጋጀቱን ነው የተናገሩት። ፍኖተ-ካርታው በቀጣይ ለትምህርት ሚኒስቴር እንደሚቀርብም ነው የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶክተር ብርሃነመስቀል ጠና የገለጹት።

    መንግሥት ዩኒቨርሲቲው በትምህርት ዘርፍ ያሉ ችግሮችን ለመቅረፍ እያከናወናቸው ያሉ ተግባራትን በመደገፍ ረገድ የጀመረውን ሥራ አጠናክሮ እንዲቀጥልም ጥሪ አቅርበዋል። ሁሉም ባለድርሻ አካላት የመምህራን ሙያ በማክበርና የማስከበር ኃላፊነት እንዳለባቸው ገልፀው፥ የመምህራን ዕውቀትንና አቅምን ማጎልበት ደግሞ ለነገ የማይባል የዛሬ የቤት ሥራ መሆኑን አመላክተዋል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ

    Semonegna
    Keymaster

    ኢስት አፍሪካን ሆልዲንግ አክስዮን ማኅበር በቢሾፍቱ ከተማ የኢንዱስትሪ ፓርክ ሊገነባ ነው

    አዲስ አበባ – ኢስት አፍሪካን ሆልዲንግ አክስዮን ማኅበር በ108 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር ኦሮሚያ ክልል ውስጥ በቢሾፍቱ ከተማ የኢንዱስትሪ ፓርክ ለመገንባት ከኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ጋር የካቲት 17፥ ቀን 2015 ዓ.ም ስምምነት ተፈራረመ።

    በስምምነቱ ሥነ ሥርዓት ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ ዳንኤል ተሬሳ፥ ኢትዮጵያ ዘላቂ የኢኮኖሚ ዕድገት ለማምጣት ዘርፈ ብዙ ፖለቲካዊ እና ምጣኔ ሀብት-ተኮር (ኢኮኖሚያዊ) ማሻሻያዎችን እያደረገች እንደምትገኝ ጠቁመው፤ ማሻሻያዎቹ አዳዲስ እና ያሉትንም ኢንቨስትመንቶች አቅም ለማሳደግ ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ ይገኛሉ ብለዋል።

    እንደ ምክትል ኮሚሽነሩ ገለጻ፥ ኢንቨስትመንትን የበለጠ ለማጠናከር ልዩ የኢኮኖሚ ዞኖች እና የኢንዱስትሪ ፓርኮችን በልዩ ሁኔታ የሚደግፉ ፖሊሲዎች እና ማሻሻያዎች ጸድቀው ወደ ሥራ በመግባት አመርቂ ውጤቶች እየተመዘገበ ነው። ለአብነትም ባለፉት ስድስት ወራት ከሁለት ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር በላይ የውጪ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት (foreign direct investment) መሳብ ተችሏል ብለዋል ።

    የኢስት አፍሪካ ሆልዲንግ አክስዮን ማኅበር ሊቀመንበር ዶክተር ብዙአየሁ ታደለ በበኩላቸው እንደገለጹት፥ የፓርኩ ግንባታ ሲጠናቀቅ ስፋቱ ወደ 100 ሄክታር የሚያድግ ሲሆን ለ15 ሺህ የሰው ኃይል የሥራ ዕድል ከመፍጠሩም ባሻገር ለቴክኖሎጂ ሽግግር ዕድል የሚፈጥር ነው።

    የማስፋፊያ ፕሮጀክቱ በ108 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር የሚለማ ሲሆን ንድፉ የኢንዱስትሪያል ፓርክ አጠቃቀም ሥርዓትን የተከተለ፣ መሠረተ ልማት የተሟላለት፣ 40 ሜጋ ዋት የኃይል አቅርቦት የሚኖረው እና ታዳሽ ኃይል (renewable energy) ላይ በትኩረት የሚሠራ እንዲሁም ኤክስፖርትን የሚያሳድግ ነው ሲሉ አብራርተዋል። በተጨማሪም የአካባቢውን አርሶ አደሮች በምርት አቅርቦት የሚያስተሳስር እና ለሀገር ውስጥ ግብዓት ልዩ ትኩረት የሚሰጥ ነው ሲሉ አክለዋል።

    እንደ ዶክተር ብዙአየሁ ገለጻ፥ የኢንዱስትሪ ፓርኩ ሙሉ ለሙሉ ወደሥራ ሲገባ ምርቶችን ለሀገር ውስጥ ፍጆታ ከማቅረብ ባሻገር ኤክስፖርት በማድረግ የውጭ ምንዛሬ የሚያስገኝ ይሆናል።

    የኢንዱስትሪ ፓርኩ ከአዲስ አበባ በ40 ኪሎ ሜትር ላይ መገኘቱ እና ከኢትዮ-ጂቡቲ ምድር ባቡር ጣቢያ በቅርብ ርቀት እንደሚገኝ ገልጸው፤ ከአዲስ አበባ – አዳማ ፈጣን መንገድ በሦስት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገነባ መሆኑ እና ከሞጆ ደረቅ ወደብ በ15 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኝ መሆኑ ፓርኩን ልዩ እንደሚያደርገው ገልጸዋል።

    ኢስት አፍሪካ ሆልዲንግ አክስዮን ማኅበር በውስጡ የተለያዩ ኢንቨስትመንቶችን የያዘ የሀገር በቀል ኩባንያ ሲሆን፤ ከዚህም መካከል የኢንዱስትሪ ፓርክ ልማት፣ ሲሚንቶ ምርት፣ አላቂ እቃዎች፣ የሪል ስቴት ልማት፣ ማዕድን ልማት እና ሎጀስቲክ የንግድ ዘርፍ የያዘ እና ከስድስት ሺህ በላይ ቋሚ እና ጊዜያዊ ሠራተኞች የሥራ ዕድል መፍጠር የቻለ ድርጅት ነው።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት

    Semonegna
    Keymaster

    በ2014 ዓ.ም የ12ኛ ክፍል ፈተና ግማሽ (50%) እና ከዚያ በላይ ውጤት ያስመዘገቡ
    እና የማጠናከሪያ መርሐ ግብር የሚከታተሉ ተማሪዎች ወደ ከፍተኛ ትምህርት እንደሚገቡ ተገለፀ

    አዲስ አበባ (ትምህርት ሚኒስቴር) – የትምህርት ሚኒስቴር የ2014 ዓ.ም 12ኛ ክፍል ፈተና የዉጤት ትንታኔ፣ ወደ ከፍተኛ ትምህርት መግቢያ ውጤትና ተያያዥ ጉዳዮች አስመልክቶ መግለጫ ሰጥቷል።

    መግለጫውን የሰጡት የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ የተገኘው የፈተና ውጤት ከስርቆትና ከኩረጃ በፀዳ መልኩ በትክክል የተመዘገበ መሆኑን ገልጸዋል።

    በ2014 ዓ.ም ለተሰጠው ፈተና በጠቅላላ የተመዘገቡት ተፈታኞች ቁጥር 985,354 ሲሆኑ፤ ከእነዚህ ውስጥ 92 ከመቶ የሚሆኑት ፈተናውን ወስደዋል። 20,170 ተማሪዎች በፈተናው ከተገኙ በኋላ በተለያዩ የደንብ ጥሰቶች ምክንያት ተባረዋል።

    ከፍተኛ ውጤት የተበመገበበት የትምህርት መስክ — በተፈጥሮ ሳይንስ 666 ከ700 ከፍተኛ ውጤት ሆኖ የተመዘገበ ሲሆን በማህበራዊ ሳይንስ ደግሞ 524 ከ600 ከፍተኛ ውጤት ሆኖ ተመዝግቧል። በሀገር አቀፍ ደረጃ ፈተናውን ካስፈተኑ ትምህርት ቤቶች ውስጥ ሰባት ትምህርት ቤቶች ያስፈተኑትን ተማሪዎች 100% አሳልፈዋል ተብሏል።

    በጾታ ደረጃ የወንዶች አማካይ ውጤት 30.2 ከመቶ ሲሆን፤ የሴቶች አማካይ ውጤት ደግሞ 28.1 ከመቶ እንደሆነ፥ ይህም በወንዶች እና በሴቶች መካከል በአሐዛዊ ምልከታ (statistically) የጎልላ ልዩነት እንዳለና፤ ወንዶች ከሴቶች አሐዛዊ ብልጫ (statistically higher) ውጤት እንዳስመዘገቡ አስረድተዋል።

    በክልሎች ደረጃ በዉጤት ደረጃ የጎላ ልዩነት እንደሌለ ገልፀው፤ አዲስ አበባ፣ ድሬዳዋ ከተማ አስተዳደሮች እንዲሁም የሐረሪ ክልል አሐዛዊ የተሻለ (statistically significantly higher) ውጤት ያስመዘገቡ መሆኑን ፕሮፌሰር ብርሃኑ አብራርተዋል።

    በ2014 ዓ.ም በተሰጠው የ12ኛ ክፍል ፈተና ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሊያስገባ የሚችል ወጤት፥ ማለትም ግማሽ (50%) እና ከዚያ በላይ ያስመዘገቡት ተማሪዎች ቁጥር ሲታይ፥ የተፈጥሮ ሳይንስ ፈተና ከወሰዱት አጠቃላይ 339,642 ተማሪዎች መካከል 22,936 (6.8%) ተማሪዎች፣ የማኅበራዊ ሳይንስ ፈተና ከወሰዱት አጠቃላይ 556,878 ተማሪዎች መካከል 6,973 (1.3%) ተማሪዎች ግማሽ (50%) እና ከዚያ በላይ አስመዝግበዋል።  የሁለቱም የትምህርት መስኮች በድምር ሲታይ፥ ፈተናውን ከወሰዱት 896,520 ተማሪዎች ውስጥ 29,909 (3%) የሚሆኑት ተማሪዎች 50% እና ከዚያ በላይ ያስመዘገቡ መሆናቸውን ገልፀዋል።

    ከተፈጥሮ ሳይንስ ተፈታኞች የተገኘው አማካይ ውጤት 31.6 ከመቶ ሲሆን፤ ከማኅበራዊ ሳይንስ ተፈታኞች የተገኘው አማካይ ውጤት ደግሞ 27.8 ከመቶ ነው። በሁሉም የትምህርት ዓይነቶች የተፈጥሮ ሳይንስ ተፈታኞች አማካይ ውጤት ከማኅበራዊ ሳይንስ ተፈታኞች አማካይ ውጤት አሐዛዊ ጉልህ (statistically significant) ብልጫ እንዳላቸው ሚኒስትሩ አመላክተዋል።

    በአጠቃላይ ከፍተኛ ውጤት፥ በመላው ሀገሪቱ በማኅበራዊ ሳይንስ  ከ500 በላይ (ከሙሉ 600 ነጥብ) ያስመዘገቡ 10 (አስር) ተማሪዎች ብቻ ሲሆኑ፤ በተፈጥሮ ሳይንስ ከ600 በላይ (ከሙሉ 700 ነጥብ) ያስመዘገቡ ደግሞ 263 (ሁለት መቶ ስድሳ ሦስት) ተማሪዎች ናቸው። ወደፊት ጊዜው ሲደርስ እነዚህን እጅግ ከፍተኛ (great distinction) ላመጡ ተማሪዎች ትምህርት ሚኒስቴር ልዩ እውቅና እንደሚሰጣቸው ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ አስታውቀዋል።

    ፈተናውን ከወሰዱ አጠቃላይ 485,393 ወንድ ተማሪዎች መካከል ግማሽ (50%) እና ከዚያ በላይ ያገኙት 20,343 (4.2 በመቶ) ወንድ ተፈታኞች ሲሆኑ፤ ከተፈተኑት አጠቃላይ 411,127 ሴት ተማሪዎች መካከል ግማሽ (50%) እና ከዚያ በላይ ያገኙት 9,566 (2.3 በመቶ) ሴት ተፈታኞች ናቸው።

    ወደ ዩኒቨርሲቲ መግቢያ ውጤት ያላመጡ ተማሪዎች በማጠናከሪያ መርሐግብር (remedial program) እንደ ዩኒቨርሲቲዎቹ የመቀበል አቅም ተማሪዎችን ውጤት መሠረት አድርጎ በሚጸም የምልመላ መስፈርት ለዚህ ዓመት ብቻ ወደ ዩኒቨርሲቲዎች ገብተው በልዩ ሁኔታ በደከሙባቸው የትምህርት ዓይነቶች የተሻለ ዉጤት እንዲያስመዘግቡ የሚያስችል ድጋፍ ተደርጎላቸዉ ፈተና ተፈትነው የሚያልፉ ተማሪዎች የከፍተኛ ትምህርታቸውን እንዲቀጥሉ ይደረጋል ብለዋል። በዚህ የማጠናከሪያ መርሐግብር መሠረት፥ ዩኒቨርሲቲ ከሚቀላቀሉት እና መደበኛ ትምህርት (regular course) ከሚጀምሩ 29,909 ተማሪዎች ውጭ ያሉ ሌሎች ከ100 ሺህ የሚልቁ ተማሪዎች በውጤታቸው ተለይተው እንደ ዩኒቨርሲቲዎች የመቀበል አቅም እየታየ ለአንድ ዓመት የማሻሻያ ትምህርት ወስደው በድጋሚ እንዲፈተኑ ይደረጋል ብለዋል።

    የዚህ ዓመት የ12ኛ ክፍል ፈተና አንድምታ ለዓመታት ሲንከባለል የቆ የበርካታ ችግሮች መገለጫ እና ተሸፋፍኖ የቆየውን እውነተኛ የትምህርት ሥርዓታችን ያለበትን ደረጃ ያመላከተ መሆኑን የሚያሳይ ሲሆን ለዚህም ሁሉም የትምህርት ባለድርሻ አካላት በጋር የሚወስዱት ኃላፊነት በመሆኑ ለቀጣይ ሥራ መረባረብ ይገባል ብለዋል።

    ከዚሁ ጋር በተያያዘ የትምህርት ሚኒስትሩ ከተገኘው የፈተናና የተፈታኞች ውጤት ባሻገር፥ አጠቃላይ ስለ አዲሱ የትምህርት እና ምዘና ሥርዓት አንዳንድ ማብራሪያዎችን ሰጥተዋል። ከዚህ በፊት የነበረው የትምህርት እና ምዘና ሥርዓት በርካታ ብልሹ አሠራሮች እንደነበሩበት ያነሱት ሚንስትሩ፤ የአሁኑ የፈተና ሥርዓት ይህን ብልሹ አሠራር ለማረም የተወሰደ የመጀመሪያ እርምጃ ነው ብለዋል።

    የዚህ ዓመት ውጤት አንድምታ ሲታይ፥ ለዓመታት ከትውልድ ትውልድ ሲንከባለል የተሻገረውን እና ተሸፋፍኖ የቆየውን የትምህርት ሥርዓት ብልሽት የሚያሳይ ነው ብለዋል ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ በመግለጫቸው።

    ለዚህም መንግሥት የትምህርት ሥርዓቱን ባለማሻሻል፣ ወላጆች ልጆቻቸውን ባለመከታተልና በሥነ ምግባር ባለመቅረፅ፣ ትምህርት ቤቶች እና ባለሀብቶች በጋራ የወድቀቱ ተጠያቂ ናቸው ብለዋል። ከላይ የተጠቀሱ አካላት ቀጣይ መፍትሄዎች ላይ የአንበሳውን ድርሻ በመውሰድ ሊሰሩ እንደሚገባ አሳስበዋል።

    በ2014 ዓ.ም ከተሰጠው ፈተና እና ተፈታኞች የተገኘው ውጤትአስደንጋጭ እንደሆነ እንረዳለን ያሉት ሚኒስትሩ፥ ነገ የተሻለ ትውልድ ለመፍጠር በዚህ ውስጥ ልናልፍ ግድ ይለናል፤ ይህ የማንቂያ ደወል ሊሆን ይገባል ብለዋል። በበጎ ጎን ከተነሱጥ ነጥቦች መካከል፥ ፈተናው ሙሉ ለሙሉ ከስሮቆት የፀዳ እንደነበረም ተነስቷል።

    የፈተናው አሰጣጥ በብዙ ፈተናዎች ውስጥ ያለፈ እንደሆነ አንስተው፤ በስኬት ለመጠናቀቁ አስተዋፅኦ ላበረከቱ አካላት ምስጋና አቅርበዋል።

    ምንጭ፦ ትምህርት ሚኒስቴር/ ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የ12ኛ ክፍል ፈተና ውጤት መግለጫ ከትምህርት ሚኒስቴር

    Semonegna
    Keymaster

    “ዱቤ አለ” – ዳሸን ባንክ በቴክኖሎጂ የታገዘ የዱቤ ግብይት አስተዋወቀ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – ዳሸን ባንክ በቴክኖሎጂ የታገዙ አገልግሎቶችን በማስተዋወቅ በሚሊዮን የሚቆጠሩ የተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች የባንክ አገልግሎቶችን በቀላሉ እንዲያገኙ በማድረግ ላይ ይገኛል።

    ባንኩ አዳዲስ አገልግሎቶችን የማስተዋወቅ ጥረቱን በመቀጠል አሁንም ከኢግልላየን ሲስተም ቴክኖሎጂ (EagleLion System Technology) ጋር በመተባበር የቆየውን የአብዛኛው ኢትዮጵያውያን የዱቤ ግብይት በዘመናዊ ቴክኖሎጂ እና አስተማማኝ የባንክ አሠራር በማገዝ “ዱቤ አለ” የተሰኘና ሸማቾች በዱቤ በፈለጉት ጊዜ ያሻቸውን ገዝተው ቆይተው መክፈል የሚችሉበትን አሠራር እና መተግበሪያ ጥር 02 ቀን 2015 ዓ.ም. በሸራተን አዲስ ሆቴል አስመርቋል።

    በምረቃ ሥነ- ሥርዓቱ ላይ የዳሸን ባንክ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ አስፋው ዓለሙን ጨምሮ በርካታ የንግድ ማኅበረሰቡ አባላት ተገኝተዋል።

    ይህ “ዱቤ አለ” ተብሎ የተሰየመው አገልግሎት ዳሸን ባንክ ከተለያዩ የንግድ ተቋማት ጋር በመተባበር ሕብረተሰቡ ቋሚና አላቂ ዕቃዎችንና በርካታ አገልግሎቶችን በ3 ወር፣ በ6 ወርና በ12 ወር በሚመለስ ዱቤ በወለድና ያለወለድ መግዛት የሚያስችል አማራጭ ነው። ይህም የማኅበረሰባችንን የኑሮ ጫና ይቀንሳል፤ በገበያው ውስጥ ምርት እንዲገላበጥ፣ አገልግሎቶችም ይበልጥ ጥቅም ላይ እንዲውሉ እና የንግድ ማኅበረሰቡ ሽያጭ እንዲያድግ ብሎም ኢኮኖሚው እንዲነቃቃ ጉልህ ድርሻ ይኖረዋል።

    “ዱቤ አለ” የምርትና አገልግሎት አቅራቢዎች ለደንበኞቻቸው እጅግ አመቺ የሆነ የዱቤ አገልግሎት በማቅረብ ተመራጭነታቸውን እንዲያሳድጉም ይረዳል።

    ደንበኞች መተግበሪያውን ከጉግል ፕሌይ ስቶር (Google Play Store) ወይም ከአፕ ስቶር (App Store) በማውረድ ለአገልግሎቱ መመዝብ ይችላሉ። ከተመዘገቡ በኋላም ወደ ዳሸን ባንክ ቅርንጫፍ በማምራት የዱቤ ገደብ ማስፈቀድና የአገልግሎቱ ተጠቃሚ መሆን ይችላሉ።

    ዳሸን ባንክ ጠንካራ የቴክኖሎጂ መሠረተ ልማት መገንባት የቻለ ሲሆን በቅርቡ በግል ባንኮች ታሪክ የመጀመሪያው ትልቅና ዘመናዊ የሆነውን የመረጃ ማዕከል አስመርቋል። በዚህ ጠንካራ መሠረተ ልማት ላይ ተንተርሶም አሞሌ በተሰኘው የዲጂታል ባንክ አገልግሎቱ ሰፊውን የማኅበረሰባችን ክፍል ተጠቃሚ አድርጓል። በቅርቡም አነስተኛ ቁጠባና ብድር ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር በመተባበር መጀመሩ ይታወሳል።

    ዳሸን ባንክ ኢትዮጵያ ውስጥ ካሉት የግል ባንኮች ቀዳሚና አንጋፋው ሲሆን፣ ሀገር ውስጥ በስፋት ከሚንቀሳቀሱት እንዲሁም እጅግ ትርፋማ ከሆኑት የባንክና ፋይናንሻል ተቋማ አንዱ ነው። ባንኩ በመላው ሀገሪቱ ከ675 በላይ ቅርንጫፎች፣ ዘጠኝ ዓለም አቀፍ የገንዘብ ምንዛሪ አገልግሎት የሚሰጡ ቢሮዎች፣ ከ400 በላይ የገንዘብ ማውጫ ማሽኖች (ATM machines)፣ እና ከ1300 በላይ ፖይንት ኦፍ ሴል ተርሚናሎች (point-of-sale terminals) አሉት።

    Dube Ale ዱቤ አለ

    Semonegna
    Keymaster

    ፀደይ ባንክ ጠቅላላ ተቀማጭ ገንዘቡ 24.5 ቢሊዮን ብር መድረሱን ገለጸ፤ 1.5 ቢሊዮን ብር ማትረፍ ችሏል

    ባሕር ዳር (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – ፀደይ ባንክ የባለ አክሲዮኖች 1ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባዔውን በባሕር ዳር ከተማ ተካሂዷል። የፀደይ ባንክ በ2014 የሒሳብ ዓመት ጠቅላላ ተቀማጭ ገንዘቡ 24.5 ቢሊዮን መድረሱን የባንኩ የቦርድ ሰብሳቢ አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ገልጸዋል።

    በ2014 ዓ.ም ባንኩ ከተለያዩ መለኪያዎች አንፃር አበረታች ውጤት እንዳስመዘገበም አቶ ገዱ የተናገሩት። አያይዘውም የባንኩ ተቀማጭ ገንዘብ በ12 በመቶ አድጎ 24.5 ቢሊዮን ጠቅላላ ተቀማጭ ገንዘብ መድረሱንም ገልጸዋል።

    ሰኔ 2020/21 በተደረገ ሪፖርት ባንኩ 38.9 ቢሊዮን ብር ካፒታል እንዳስመዘገበና 9.5 ቢሊዮን ብር ጠቅላላ የተጣራ ካፒታል ማካበቱንም አንስተዋል።

    ባንኩ የቁጠባ መጠኑን 28.1 ቢሊዮን ብር ያደረሰ ሲሆን፤ በ2014 የሒሳብ ዓመት 1.5 ቢሊዮን ብር ጠቅላላ ትርፍም አግኝቷል ብለዋል። ካለፈው የሒሳብ ዓመት ጋር ሲነፃፀር በ29 በመቶ እድገት አሳይቷል የተባለ ሲሆን ለበርካታ ዜጎችም የብድር አገልግሎት መስጠት መቻሉም ተነስቷል።

    አቶ ገዱ በሪፖርታቸው ካቀረባቸው ነጥቦች ዋና ዋናዎቹ፦

    • የፀደይ ባንክ እስከ ፈረንጆቹ ሰኔ 2022 አጠቃላይ ሀብቱ 44 ቢሊዮን ብር ደርሷል።
    • ጠቅላላ ካፒታሉ 11 ቢሊዮን ብር ነው።
    • ጠቅላላ የተከፈለ ካፒታል7 ቢሊዮን ብር ነው።
    • የባንኩ ጠቅላላ ተቀማጭ ገንዘብ5 ቢሊዮን ብር ደርሷል። ይህም ከባለፈው ዓመት ከነበረበት በ12 በመቶ እድገት አሳይቷል።
    • ባንኩ የእቅዱን 94 በመቶ ማሳካት ችሏል።
    • የባንኩ ጠቅላላ የብድር ክምችት6 ቢሊዮን ብር ደርሷል።
    • የብድር መጠኑንም በ29 በመቶ አሳድጓል።
    • ባንኩ በበጀት ዓመቱ ለተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች1 ቢሊዮን ብር አበድሯል።
    • ፀደይ ባንክ 5 ቢሊዮን ብር ወጭ ማድረጉም በሪፖርቱ ተመላክቷል።
    • በ2014 የሒሳብ ዓመት 5 ቢሊዮን ብር ትርፍም አስመዝግቧል፤ የ2015 የሒሳብ ዓመት ትርፉን ወደ 1.66 ቢሊዮን ብር ለማሳደግ አቅዷል።
    • ትርፉ ካለፈው የሒሳብ ዓመት ጋር ሲነጻጸር 3 በመቶ ማደጉን የቦርዱ ሰብሳቢ አቶ ገዱ ገልጸዋል።

    ባንኩ በቀጣይ ከ100 በላይ ቅርንጫፎችን በመክፈት የአገልግሎት አድማሱን እንደሚያሰፋ ነው የተገለጸው። ፀደይ ባንክ ሀገር ችግር ውስጥ በገባችበት ወቅት 100 ሚሊየን ብር ወጭ በማድረግ ለወገን ደራሽነቱን አስመስክሯል። እንደሀገር የተከሰተውን የዋጋ ንረት ለመቋቋምም አጥብቆ ይሠራል ነው የተባለው።

    በአጠቃላይ 471 ቅርንጫፎችን በማቀፍ በብድርና ቁጠባ ተቋምነት (የአማራ ብድርና ቁጠባ ተቋም) ሲንቀሳቀስ ቆይቶ በቅርቡ ወደ ባንክ ተቋምነት የተሸጋገረው ፀደይ ባንክ፥ በአሁኑ ሰዓት ከ150 በላይ ቅርንጫፎቹ ውስጥ ከ12,200 በላይ ሠራተኞችን ቀጥሮ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል። ከዚህ በተጨማሪም አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ 36 ወለሎች ያሉት ዋና ቅርንጫፍ እያስገነባና፥ ግንባታውም በ2015 የሒሳብ ዓመት ይጠናቀቃል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተዘግቧል።

    ንግድና ኢንዱስትሪ ነክ ዜናዎች ― ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ፀደይ ባንክ

    Semonegna
    Keymaster

    ለኢንቨስትመንት ዘርፍ ተጨማሪ አቅም የሚሆነው ሲዳማ ባንክ

    ቀደም ሲል “ሲዳማ ማይክሮፋይናንስ ተቋም” በመባል የሚታወቀው የብድርና ቁጠባ ተቋም “ሲዳማ ባንክ አክሲዮን ማኅበር” ሆኖ በባንክነት ለመደራጀት በሐምሌ ወር 2014 ዓ.ም ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ፈቃድ አግኝቷል።

    አዲስ አበባ (አዲስ ዘመን) – በአንድ ሀገር የምጣኔ ሀብት እንቅስቃሴ ውስጥ የጎላ ሚና ካላቸው ባለድርሻ አካላት መካከል የፋይናንስ ተቋማት በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳሉ። እነዚህ ተቋማት በሀገራዊ የምጣኔ ሀብት እንቅስቃሴ ውስጥ ካላቸው ሚና መካከል አንዱ ለኢንቨስትመንት ተግባራት የፋይናንስ ምንጭ መሆናቸው ነው።

    የብድርና ቁጠባ ተቋማትን ጨምሮ ባንኮችና የመድን (insurance) ድርጅቶች በአነስተኛም ሆነ በትልልቅ የኢንቨስትመንት ተግባራት ላይ ለተሰማሩ ግለሰቦች፣ ማኅበራትና ኩባንያዎች የሥራ ማከናወኛ የገንዘብ ምንጮች እና የንብረት ዋስትናዎች ሆነው ይሠራሉ። ውጤታማ የኢንቨስትመንት ተግባራት አስተማማኝ የፋይናንስ አቅርቦት የሚፈልግ በመሆኑ በኢትዮጵያም ሆነ በሌላው ዓለም ያሉ የኢንቨስትመንት ሥራዎች ከእነዚህ የገንዘብ ተቋማት ተሳትፎ ውጭ የሚታሰቡ አይደሉም።

    ላለፉት ሁለት አስርት ዓመታት የበርካታ ዜጎችን ሕይወት በበጎ የለወጡት የብድርና ቁጠባ ተቋማት ለአነስተኛና መካከለኛ የኢንቨስትመንት ሥራዎች ውጤታማነት የነበራቸው ሚና ከፍተኛ እንደሆነ አይዘነጋም። በኢትዮጵያ የብድር እና ቁጠባ ተቋማት ደንበኞች ቁጥር ከባንክ ደንበኞች ቁጥር በብዙ እጥፍ የላቀ ነው። ይህም ለአብዛኛው ሕዝብ የብድር አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኙት እነዚህ ተቋማት እንደሆኑ አመላካች ነው። አንጋፋ የሚባሉት የብድርና ቁጠባ ተቋማት የፋይናንስ አቅማቸው ከብዙ አዳዲስ ባንኮች ጭምር የተሻለ ነው። ዛሬ በትልቅ ስምና አቅም የሚታወቁ ብዙ የኢንቨስትመንት ድርጅቶች መነሻቸው እነዚህ የብድርና ቁጠባ ተቋማት ናቸው።

    የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የብድርና ቁጠባ (የማይክሮፋይናንስ) ተቋማት አስተማማኝና ፍትሐዊ በሆነ አሠራር እንዲሠሩና ሕዝባዊ ተዓማኒነት እንዲኖራቸው እንዲሁም ባንክ ሆነው ለመንቀሳቀስ የሚስችላቸው ሕጋዊ ማዕቀፍ እንዲኖራቸው የሚያስችል መመሪያ ከሁለት ዓመታት በፊት ማውጣቱ ይታወሳል። የብድርና ቁጠባ ተቋማቱ ያላቸውን ግዙፍ የደንበኛና የፋይናንስ አቅም ትልልቅ በሆኑና የተሻለ ትርፍ ሊያመጡ በሚችሉ ኢንቨስትመንቶች ላይ እንዲያውሉት የተዘጋጀው ይህ መመሪያ፤ ብዙ የብድርና ቁጠባ ተቋማት ወደ ባንክ እንዲሸጋገሩና ወደ መደበኛ የባንክ ሥራ እንዲገቡ እያስቻለ ነው።

    በዚሁ መመሪያ መሠረት ቀደም ሲል “ሲዳማ ማይክሮፋይናንስ ተቋም” (Sidama Microfinance In­stitution) በመባል የሚታወቀው የብድርና ቁጠባ ተቋም “ሲዳማ ባንክ አክሲዮን ማኅበር” (Sidama Bank S.C.) ሆኖ በባንክነት ለመደራጀት በሐምሌ ወር 2014 ዓ.ም ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ፈቃድ አግኝቷል። ባንኩ 1,988 ባለአክሲዮኖች ያሉት ሲሆን፥ የተፈረመ ካፒታሉ አንድ ቢሊዮን 447 ሚሊዮን ብር ነው። ከዚህ ውስጥ ከ583 ሚሊዮን ብር በላይ የሚሆነው ገንዘብ የተከፈለ ካፒታል ነው።

    የሲዳማ ባንክ የዳይሬክተሮች ቦርድ ሊቀ መንበር አቶ አብርሃም ማርሻሎ ባንኩ ከብሔራዊ ባንክ የሥራ ፈቃድ ማግኘቱን ተከትሎ በባንክ ዘርፍ ተግባራት ላይ ለመሰማራት የሚያስችሉትን የቅድመ ዝግጅት ሥራዎችን እንዳከናወነ ይናገራሉ። አቶ አብርሃም በዚህ ረገድ ስለተከናወኑ ተግባራት ሲገልፁ “የባንኩ የውስጥ አሠራር የሚመራባቸውን መመሪያዎችን የማዘጋጀት፤ በብሔራዊ ባንክ መስፈርት መሠረት ውስጣዊ አደረጃጀቶችን የማሟላት፣ ከባንክ ዘርፉ ወቅታዊ እድገት ጋር የሚጣጣምና ባንኩን ተወዳዳሪ ለማድረግ የሚያስችል የኮር ባንኪንግ ሶፍትዌር ግዢ ለመፈፀምና ባንኩ የሚመራበትን የአምስት ዓመታት ስትራቴጂካዊ እቅድ ለማዘጋጀት ቅድመ ዝግጅት ተግባራትን የማጠናቀቅ፣ የሠራተኞችን አቅም በስልጠና የመገንባትና ተቋሙን በብቁ ሰው ኃይል የማጠናከር፣ በመጀመሪያ ዙር የተሟላ የባንክ አገልግሎት የሚሰጡ 10 ቅርንጫፎችን በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የማዘጋጀት እንዲሁም በብሔራዊ ባንክ የውጭ ምንዛሬ ሂሳብን ጨምሮ የመጠባበቂያና የክፍያ ሂሳቦችን የመክፈት ተግባራት ተከናውነዋል” ሲሉ ያብራራሉ።

    እንደ እርሳቸው ገለፃ፥ ባንኩ ባለፈው የበጀት ዓመት 142.3 ሚሊዮን ብር ዓመታዊ ገቢ ለመሰብሰብ አቅዶ 177 ሚሊዮን ብር በመሰብሰብ ከእቅድ የበላይ የሆነ አፈፃፀም አስመዝግቧል። ይህም ካለፈው ዓመት የባንኩ አፈፃፀም ጋር ሲነፃፀር የ58 በመቶ ብልጫ እንዲኖረው አድርጓል። 48 ሚሊዮን ብር ለማትረፍ አቅዶ 83 ሚሊዮን ብር በማትረፍ በባንኩ ታሪክ የተሻለ ውጤት ሆኖ ተመዝግቧል። በጠቅላላው 165 ሚሊዮን ብር ተቀማጭ ገንዘብ በመሰብሰብም ከቀዳሚው ዓመት አፈፃፀም የ29 በመቶ እድገት አሳይቷል።

    በብድር አቅርቦት ረገድ ደግሞ ባንኩ የሰጠውን ብድር በ86.6 ሚሊዮን ብር (በ29 በመቶ) በማሳደግ ለተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች የሰጠውን ብድር 462.5 ሚሊዮን ብር ማድረስ ችሏል። “የባንኩ የተበላሽ ብድር ምጣኔ 3.6 በመቶ ሲሆን፣ ይህም ብሔራዊ ባንክ ካስቀመጠው የአምስት በመቶ ምጣኔ አንፃር ሲታይ የሲዳማ ባንክ የተበላሸ የብድር ምጣኔ ጤናማ እንደሆነ አመላካች ነው” ይላሉ።

    የሲዳማ ባንክ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ታደሰ ሐጢያ ባንኩ ማይክሮፋይናንስ ተቋም በነበረበት ጊዜ አነስተኛ ገቢ ያላቸውን የሕብረተሰብ ክፍሎች ሲያገለግል እንደነበር አስታውሰው፤ አገልግሎቱ አዋጭና ሕብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርግ በመሆኑ በብሔራዊ ባንክ ሕጋዊ ማዕቀፍ መሠረት ባንኩ ይህን አገልግሎቱን እንደሚቀጥልም ይናገራሉ። ባንኩ ከሚያከናውናቸው ተግባራት መካከል አንዱ የባንክ አገልግሎትን በገጠርና በከተማ ለሕብረተሰቡ ተደራሽ ማድረግ መሆኑም ይህን አገልግሎቱን የማስቀጠል አካል ነው።

    እርሳቸው እንደሚሉት፥ ተቋሙ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ የሕብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ አድርጓል። ቀደም ካለው ጊዜ ጀምሮ የባንኩን አገልግሎት የሚጠቀሙ በእርሻ፣ በሆቴልና በሌሎችም የኢንቨስትመንት ዘርፎች ላይ የተሰማሩ ባለሀብቶች አሉ። የተቋሙ በባንክ አሠራር መደራጀት ደግሞ ይህን አገልግሎት ለማስፋትና ለማዘመን ተጨማሪ ዕድልና አቅም ይፈጥራል።

    ተቋሙ ወደ ባንክ ሲሸጋገር ብሔራዊ ባንክ ያስቀመጠውን አነስተኛ መነሻ ካፒታል ለማሟላት የአክስዮን ሽያጭ ያከናወነ ሲሆን፣ የተፈረሙ አክሲዮኖች ተከፍለው እንዲጠናቀቁ በማድረግ ከመደበኛ የባንክ ሥራዎች በተጨማሪ ዓለም አቀፍ የባንክ ሥራዎችን ለማከናወን እየሠራ ይገኛል። “ወደ ባንክ ሥራ ስንገባ የጠንካራ የፋይናንስ አቅም ባለቤት መሆን ያስፈልጋል፤ አለበለዚያ አቅም ካላቸው ከሌሎች ባንኮች ጋር ለመወዳዳር አስቸጋሪ ይሆናል። ለትልልቅ የኢንቨስትመንት ሥራዎች ብድር ማቅረብም ሆነ በፋይናንስ ገበያው ላይ ተፎካካሪ መሆን አይቻልም” ይላሉ። ይህን ለማሳካትም የተፈረሙ አክሲዮኖች እንዲከፈሉና የኮርባንኪንግ (Core Banking) ሥራን ለመጀመር የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ እንደሆነ አቶ ታደሰ ያስረዳሉ።

    የውጭ ባንኮች ወደ ኢትዮጵያ ገበያ እንዲገቡ መፈቀዱ መልካም ዕድሎችና ፈተናዎች እንደሚኖሩት የሚገልጹት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፥ መልካም ዕድሎችን መጠቀም ከተቻለ ፈተናዎቹን መቀነስና ተወዳዳሪ መሆን እንደሚቻል ነው የተናገሩት። የባንኮቹ መግባት የሀገር ውስጥ ባንኮች ውድድሩን ለመቋቋም ራሳቸውን እንዲያጠናክሩ፣ በዚህም ተገልጋዩ ሕብረተሰብ ተጠቃሚ እንደሚሆን ይገልጻሉ። የኢትዮጵያ ባንኮች በካፒታል አቅምም ሆነ በቴክኖሎጂ አጠቃቀም ረገድ በሚጠበቅባቸውና ወቅቱ በሚፈልገው ልክ እየተንቀሳቀሱ አለመሆናቸውን ተናግረው፥ እነዚህን ክፍተቶች በማስተካከል ለውድድር መዘጋጀትና ለተገልጋዩ እርካታ መሥራት እንዳለባቸው ይመክራሉ። ከዚህ አንፃር ሲዳማ ባንክ ትልቅ አቅም ያላቸውን ባለሀብቶችን እንዲሁም ዳያስፖራውን ማሳተፍን ጨምሮ ያሉትን መልካም አጋጣሚዎች ሁሉ ተጠቅሞ በባንክ ኢንዱስትሪው ዘርፍ ተወዳዳሪ ለመሆን ማቀዱን አቶ ታደሰ ገልፀዋል።

    ሲዳማ ባንክ ለኢንቨስትመንት ዘርፍ የሚኖረውን አዎንታዊ አስተዋፅኦ በተመለከተም አቶ ታደሰ ሲናገሩ፥ “ገበያው አዋጭ በመሆኑ ባንኩ ለኢንቨስትመንት ሥራዎች የፋይናንስ ምንጭ የመሆን አቅም አለው። ቀደም ሲልም የባንኩን አገልግሎት የሚጠቀሙ በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች ላይ የተሰማሩ ባለሀብቶች አሉ። ወደፊትም ባንኩ ይህን ተግባሩን በስፋት አጠናክሮ ይቀጥላል” ብለዋል።

    ሲዳማ ባንክ በማይክሮፋይናንስ ደረጃ ከነበረበት ጊዜ ጀምሮ አነስተኛ ገቢ ያላቸውን የሕብረተሰብ ክፍሎችን ሲያገለግልና ለግለሰቦች እንዲሁም በአነስተኛና ጥቃቅን የንግድና ኢንቨስትመንት ሥራዎች ላይ ለተሰማሩ ማኅበራት የፋይናንስ ምንጭ ሆኖ ቆይቷል። ብዙ ግለሰቦችና ማኅበራትም በተቋሙ የብድርና ቁጠባ አገልግሎት ሥራቸውን አሳድገው ዛሬ ትልልቅ ኢንቨስተሮች ለመሆን በቅተዋል።

    የሲዳማ ክልል የንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ምክትል ፕሬዝደንት አቶ መስፍን ቂጤሳ እንደሚናገሩት፣ ተቋሙ በግል ንግድ ላይ ለተሰማሩ በርካታ ግለሰቦችና ድርጅቶች ባለውለታ ነው። እርሳቸውም ከባንኩ ጋር ያላቸው ደንበኝነት የቆየ መሆኑን አስታውሰው፥ “ከባንኩ የወሰድነው ብድር በጣም ጠቅሞናል፤ ትርፋማ ሆነን እንድንሠራ አግዞናል” በማለት የባንኩ የብድር አገልግሎት ለውጤታማነታቸው አጋዥ እንደሆናቸው አስረድተዋል።

    “አካባቢው በቡና ምርት የታወቀ ስለሆነ ባንኩም ለቡናው ዘርፍ ትልቅ ድጋፍ እያደረገ ነው” የሚሉት አቶ መስፍን፤ ለቡና አብቃዮችና ነጋዴዎች እንዲሁም ለተደራጁ ማኅበራትም የፋይናንስ ዕድል እንደሚያመቻች ይገልፃሉ። በቀጣይም ከባንኩ ጋር ያላቸውን ደንበኝነት አጠናክረው፥ በይርጋለም የተቀናጀ አግሮ ኢንዱስትሪ ፓርክ የተፈጠረውን መልካም ዕድል በመጠቀም ቡናን እሴት ጨምሮ ለውጭ ገበያ ለማቅረብ እቅድ እንዳላቸው ተናግረዋል።

    “ከዚህ ቀደም የነበረው የባንኮች ተደራሽነት ውስን ስለነበር ብድር ለማግኘት ችግሮች ነበሩ። ሲዳማ ባንክ ለኢንቨስትመንት ሥራዎች ብድር በማቅረብ ጥሩ ዕድል ይፈጥራል፤ ለልማት በተለይ ለኢንቨስትመንት ትልቅ አስተዋፅኦ እያደረገ የሚገኝ ባንክ ነው። ጥሩ ተስፋ ያለው ባንክም ነው” በማለት አቶ መስፍን ባንኩ ለኢንቨስትመንት ዘርፍ ስለሚኖረው አስተዋፅዖ ይናገራሉ።

    በግል የንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩት ወይዘሮ አየለች ዱካሞም የባንኩ ደንበኛ ናቸው። “ቀደም ሲል የሲዳማ ማይክሮ ፋይናንስ አገልግሎት ተጠቃሚ ነበርኩ” የሚሉት ወይዘሮ አየለች፥ ተቋሙ ባንክ ከሆነ በኋላ ከባንኩ ብድር መውሰዴ ሥራዬን ሰፋ አድርጌ እንድሠራ አግዞኛል። ብዙ ሰው ከሲዳማ ባንክ ብድር እየወሰደ እየሠራ ነው፤ እየተለወጠም ነው። ከባንክ ጋር መሥራት ጥቅሙ ብዙ ነው” ሲሉ ይገልጻሉ። ሲዳማ ባንክ በጥቃቅንና አነስተኛ የንግድ ሥራዎች ላይ ለተሰማሩ ግለሰቦችና ድርጅቶች ትልቅ ድጋፍ ሲያደርግ እንደነበር አስታውሰው፤ ከባንኩ ብድር ወስደው ከአነስተኛ የንግድ ሥራ ተነስተው ለትልቅ ደረጃ የበቁ ሰዎችን እንደሚያውቁም ነው የጠቀሱት። ወደፊትም ከባንኩ ጋር ብዙ ሥራዎችን የመሥራት እቅድ እንዳላቸው ተናግረዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት

    ሲዳማ ባንክ Sidama Bank

    Semonegna
    Keymaster

    በሀገር አቀፍ ደረጃ የተቀናጀ የኩፍኝ መከላከያ ክትባት ዘመቻ ተጀመረ 

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ ኢትዮጵያ) – ከታኅሳስ 13 ቀን እስከ ታኅሳስ 22 ቀን፥ 2015 ዓ.ም በሀገር አቀፍ ደረጀ የሚካሄደው የተቀናጀ የኩፍኝ መከላከያ ክትባት ዘመቻ የኩፍኝ በሽታ መከላከያ ክትባት፣ የኮቪድ-med19 መከላከያ ክትባት፣ የአጣዳፊ የምግብ እጥረት ልየታ፣ የቫይታሚን ኤ ጠብታ እደላ፣ የሆድ ጥገኛ ትላትል መድኃኒት እደላ፣ የሕፃናት የዞረ እግር ልየታ እንዲሁም በወሊድ ምክንያት የሚከሰት ፊስቱላ ልየታ በቅንጅት የሚሠራበት ዘመቻ ነው።

    በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ወረዳ 8 ሰርጢ ጤና ጣቢያ የማስጀመሪያ መርሃ-ግብር ላይ የተገኙት የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶ/ር ደረጀ ዱጉማ እንደገለጹት፥ ለእናቶች እና ለሕፃናት ትኩረት ያደረገው የጤና ፖሊሲ ውስጥ አንዱ እና ባለፉት አራት አስርት ዓመታት በትግበራ ላይ የቆየው የክትባት ፕሮግራም መሆኑን ገልፀው፤ እንደሀገር ከ14 በላይ የሚሆኑ የክትባት ዓይነቶችን በመስጠት ዜጎችን ከህመምና ከሞት መታደግ እንደተቻለ ገልጸዋል።

    በሀገራችን በተወሰኑ አካባቢዎች ተከስተው በነበሩ ሰው ሠራሽና ተፈጥራዊ ችግሮች ምክንያት በሥርዓተ ምግብ እጥረት እና በኩፍኝ በሽታ የሚያዙ ሕፃናት ከፍ ብሎ መታየቱን የገለፁት ዶ/ር ደረጀ ዱጉማ፥ በዚህ ዘመቻ ዕድሜያቸው ከዘጠኝ ወር እስከ አምስት ዓመት የሆኑ ሕፃናትን የኩፍኝ በሽታ መከላከያ ክትባት፣ የአጣፊ የምግብ እጥረት፣ የዞረ እግር ልየታ እንደሚከናወን እና በወሊድ ምክንያት የሚከሰት ፊስቱላ ልየታም ይካሄዳል።

    ሕፃናት በመደበኛ ክትባት መርሃ-ግብር የሚሰጠውን የኩፍኝ በሽታ መከላከያ ክትባት ካልወሰዱ በቀላሉ በኩፍኝ በሽታ የመያዝና ለከፋ የጤና ችግር የመጋለጥ ዕድላቸው ከፍተኛ  ነው ያሉት የእናቶች እና ሕፃናት ጤና ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር መሠረት ዘላለም፥ በአሁኑ ጊዜ በሀገራችን  ባለፉት 3 ወራት ብቻ የኩፍኝ በሽታ ወረርሽኝ በ6 ክልሎች የታየ ሲሆን፤ በወረርሽኙም ከተያዙ ውስጥ 47 በመቶ  የሚሆኑት ዕድሜያቸው ከአምስት ዓመት በታች የሆኑ ሕፃናት ሲሆኑ፥ ከእነዚህም መካከል 46 በመቶ የሚሆኑት ምንም ዓይነት የኩፍኝ በሽታ መከላከያ ክትባት ያልወሰዱ ናቸው ብለዋል። ለዘመቻው እንቅስቃሴ መሳካት አጋርና ለጋስ አካላት ላደረጉት የተቀናጀ አስተዋጽኦ አመስግነዋል።

    በአዲስ አበባ ከተማ ከ5 ዓመት በታች ለሆናቸው ለ520 ሺህ ሕፃናት ክትባቱ እንደሚሰጥም እና በስድስት የመንግሥት ሆስፒታሎች በ101 የመንግሥት ጤና ጣቢያዎች ከሰኞ አስከ አርብ በሥራ ሰዓት እንደሚሰጥ የገለጹት ደግሞ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጤና ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር ዮሐንስ ጫላ ናቸው።

    ሀገር አቀፍ የተቀናጀ  የኩፍኝ መከላከያ ክትባት ዘመቻ  የማስጀመሪያ መርሃ-ግብሩ የጤና ሚኒስቴር እና የአዲስ አበባ ከፍተኛ አመራሮች፣ የሀይማኖት አባቶችና የተለያዩ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ተካሂዷል።

    ዘመቻው ለአስር ቀን የሚቆይ ሲሆን ከ15 ነጥብ 5 ሚሊዮን በላይ ሕፃናት የኩፍኝ መከላከያ ክትባት ተደራሽ የሚሆን ሲሆን፤ የኮቪድ-19 መከላከያ ክትባት መርሃ-ግብርም በተያያዘ የሚከናወን ይሆናል። ለዘመቻው ስኬታማነት በየተዋረድ ያሉ የጤናው ዘርፍ ባለሙያዎችና አመራሮች፣ አጋር ድርጅቶችና የየመገናኛ ብዙኃን አካላት ትብብር እንዲያደርጉ ጥሪ ቀርቧል።

    ምንጭ፦ የጤና ሚኒስቴር

    የኩፍኝ መከላከያ ክትባት

Viewing 15 results - 1 through 15 (of 495 total)