በሀገራችን ኢትዮጵያ የተፈጸመውን ግፍ እውነታ በመረጃ የማሳየትና ማስረዳት ግዴታ ሁላችንም አለብን ― አቶ ነአምን ዘለቀ

Home Forums Semonegna Stories ነፃ አስተያየት (ስለኢትዮጵያ በኢትዮጵያውያን) በሀገራችን ኢትዮጵያ የተፈጸመውን ግፍ እውነታ በመረጃ የማሳየትና ማስረዳት ግዴታ ሁላችንም አለብን ― አቶ ነአምን ዘለቀ

#15549
Semonegna
Keymaster

በሀገራችን ኢትዮጵያ የተፈጸመውን ግፍ እውነታ በመረጃ የማሳየትና ማስረዳት ግዴታ ሁላችንም አለብን
(ነአምን ዘለቀ)

ሰላም ወገኖቼ ኢትዮጵያውያን፦

ሀገራችን ኢትዮጵያን ከምንም ችግር ለመታደግ የሚያስችል ከፍተኛ ብቃቱም የሀገር ፍቅሩም ያላችሁ አያሌ የኢትዮጵያ ልጆች በውጪው ዓለም ትኖራላችሁ። የኢትዮጵያ ችግር እንደሚያሳስባችሁና በጎዋ ደግሞ እንደሚያስደስታችሁም ግልጽ ነው። ነገር ግን አብዛኞቻችሁ በተለያየ ምክንያት የዳር ተመልካች መሆንን መምረጣችሁ ሀገራችንንና ወገኖቻችንን ብዙ ዋጋ እያስከፈለ እንደሆነ እያየን ነው። ሄዶ ሄዶ ያልተጠበቀና ከእስካሁኑም በከፋ ሁኔታ ሀገራችንንና ሕዝባችንን ለማይወጡት አደጋ ለማጋለጥ እየተመቻቸን እንደሆነ ስጋቴን ልገልጽላችሁ እፈልጋለሁ።

በኦሮሞ ጽንፍ ኃይሎች መሪነት የኢትዮጵያ ጥላቻ ያላቸው ባዕዳን እንዲሁም የህወሓት ዲያስፓራ ሚዲያዎችና ካድሬዎች በጋራ በመሆን የአሜሪካ፣ የካናዳንና የአውሮፓን የሕግ አውጪዎችና አስፈጻሚዎች በማወናበድ ጸረ-ኢትዮጵያ አጀንዳ ለማራመድ በስፋት ጠንካራ እንቅስቃሴ እያደረጉ ይገኛሉ ። ይህም በሰፊው እየወሰዷቸው ካሉ በርካታ አፍራሽ እርምጃዎች እንዱ ብቻ ነው። እነኚህ ኃይሎች ያለማጋነን ላለፉት 27 ዓመታት የጸረ-ወያኔ ሁለንተናዊ የትግል ቆይታዬ ያላየሁትን ከፍተኛ የዓላማ አንድነት (unity of purpose)፣ ቅንጅትና መናበብ በመፍጠር ከዳር እሰከ ዳር እየሰሩ ለመሆናቸው ብዙ መረጃዎች ይገኛሉ።

ከዚህ መልዕክት ጋር ያያያዝኩት የአሜሪካ ኮንግሬስ አባላት ለአሜሪካ ስቴት ሴክሬታሪ/የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማይክ ፖምፔዮ (Mike Pompeo) የጻፉት ደብዳቤ የዚህ ሴራ አንዱ ውጤት ነው። በተቀናጀ መልክ የሀገራችንን እውነታና ሂደት በማዛባት፣ የሃሰት ትርክቶችን በመደራረት የውጭ ኃይሎችንና መንግሥታትን ለማወናበድ ያለተቀናቃኝ በመንቀሳቀስ ላይ ናቸው። ይህን ማድረግ የቻሉት ደግሞ በእነሱ ጥንካሬ ሳይሆን ለኢትዮጵያ ሀገራዊ አንድነት፣ ለፍትህ፣ ለሕዝብ እኩልነት፣ ለሕግ የበላይነት ቀናዊ የሆነው ኢትዮጵያዊ ጎራ (silent majority) የተበታተነ መሆኑና የሚያምንበትን የሀገርና ሕዝብ አንድነት እውን ለማድረግ የድርሻውን ለመወጣት ቁርጠኛ አለመሆኑ ነው።

“ነፍጠኛን ምታ፣ አቃጥል፣ ግደል፤ ቁረጥ” የሚሉ ያልተቋረጡ የጥላቻ ዘመቻዎች በሶሻል ሚዲያና በኦኤምኤን (OMN) ሚዲያ እንደሚክያሄድ ታውቃላችሁ ብዬ አምናለሁ። የዚህ ዘመቻ ውጤትም ብዙ መቶ ወገኖቻችን በኦሮሞ ጽንፈኞች አርመኔያዊ በሆነ መንገድ መጨፍጨፍ ነው። ይህም ግፍ በቅድመ ጄኖሳይድ (pre-genocide) ደረጃ የሚመደብ የዘርና የሃይማኖት ተኮር ፍጅት ነው ማለት ከእውነቱ የራቀ አይደለም። እውነታው ይህ ሆኖ ሳለ ይህን ሀቅ በመካድ አፈናቃይና ገዳዮቹ በተገላቢጦሽ ከሳሽ በመሆን “መንግሥት በኦሮሞ ሕዝብ ላይ የሚያደርገው አፈና” ያለ በማስመስል የተቀናጀ የሀሰት ትርክት በማሥራጨት ላይ ይገኛሉ። ዓላማቸውም የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ አመንስቲ (Amnesty) እና ሂውማን ራይትስ ዎች (Human Rights Watch) የመሳሰሉ የሰብዓዊ መብት ድርጅቶችን፣ የአሜሪካ፣ የአውሮፓና፣ የካናዳ የሕግና የፓሊሲ አውጪዎችን ከጎናቸው ለማሰለፍ ሲሯሯጡ ይታያሉ።

በአሜሪካና በአንዳንድ ሀገሮች የሚገኙ የኢትዮጵያ ኤምባሲዎች ይህን የሀሰት ትርክት ለመለወጥ ጥረት ያደረጋሉ። ነገር ግን አብዛኞቹ ኢትዮጵያ ኤምባሲዎች አደጋውን መመከት በሚቻልበት ልክ የአቅምና ፓለቲካ ቁርጠኝነት ይዘው ሲንቀሳቀሱ አይታዩም። ከዚህ ከተያያዙት የተመልካችነትና ተከላካይነት ውሱን እንቅስቃሴ አልፈው የዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ፣ ዓለም አቀፍ ድርጅቶችና፣ የየሀገሩን የፓሊሲና የሕግ አውጪዎችን እውነታውን ለማስጨበጥ በቂና አጥጋቢ ሥራ መሥራት ይጠበቅባቸዋል።

ይህ በጽንፈኞች የተቀነባበረ ርብርብና ዘመቻ በጊዜ ካልተገታ ኢትዮጵያን አንድ አድርጎ የያዘውን መንግሥት እየቦረቦረ እንዳያዳክመው ስጋት አለ። ከህወሓት እስከ ኦነግ ሽኔ በተለያዩ አፍራሽ ኃይሎች ተወጥሮ የሚገኘው በዶ/ር ዓብይ አህመድ የሚመራው መንግሥት ከተዳከመ ሀገሪቷን ለትርምስ፣ ለሁከትና ሌላም የከፋ አደጋ ሊያጋልጥ ይችላል። ስለዚህም እንደሕዝብና ሀገር ከፊታችን የተደቀነውን አደጋ በቀላሉ ማየት የለብንም።

አደጋው በጣም የሚያስፈራው ደግሞ ቅራኔው በመንግሥትና በሕዝብ መካከል ብቻ መሆኑ ቀርቶ የ27 ዓመቱ የጥላቻ ቅስቀሳ ስር ሰዶ ሕዝብ አቃቅሯል። በየጊዜው የምናየው ግድያ፣ መፈናቀልና ንብረት መውደም የዚህ የጥላቻ ፖለቲካ ውጤት ነው። “ብሔር ለብሔር” ቅራኔዎችና ግጭቶችን እነማን ለምን ዓላማ ሲያራግቡ፣ ሲደግፉና ሲቆሰቁሱ እንደነበሩና ዛሬም ድረስ ያማያርፉበት፣ የሚተጉበት መሆኑን ሁላችንም የምናውቅም ይመስለኛል።

እነዚህን የውስጣዊና የውጭ ከባድ አደጋዎች ድምር ለመግታትም በተደራጀ መልክ በካናዳ፣ በአሜሪካና በአውሮፓ የተናበቡ ሥራዎች መሥራት ግድ ይላል። ለየሀገራቱ የሕግ አውጪ (lawmakers) እና የሥራ አስፈጻሚ/የፓሊሲ ወሳኞች (policymakers) በሀገራችን ኢትዮጵያ የተፈጸመውን ግፍ እውነታ በመረጃ የማሳየትና ማስረዳት ግዴታ ሁላችንም አለብን። ስለዚህም ሁላችንም በየሀገሩና በየከተማው መሰባሰብ፣ መነጋገር፣ መተባበር፣ መቀናጀትና ጠንካራ የአድቮኬሲ ቡድን (advocacy group) ማቋቋም ይኖርብናል። ከዛሬ ሁለት ወር በፊት ገደማ በሀገርና በሕዝብ ላይ የመጣው አደጋ አሳስቧቸው የተሰባሰቡ በርካታ ምሁራን፣ አክቲቪስቶች፡ የፓለቲካ፣ የአድቮኬሲ፣ የድርጅታዊ ልምድና ተሞከሮ ያላቸው ኢትዮጵያውን የሚገኙበት ዓለም ኣቀፍ ኔትዎርክ እገዛ ያደርግላችኋል። ይህን መሰል እንቅስቃሴ የምታደርጉ ለማድረግ የተዘጋጃችሁ ሁሉ፣ አሰፈላጊውን የሰነድ፣ የምክር፣ የአቅጣጫ ድጋፍ ልናደርግላችሁ ፈቃደኞችና ዝግጁዎች ስለሆን በውስጥ መስመር (messenger inbox) ልታገኙን ትችላላችሁ።

ነአምን ዘለቀ
bit.ly/NeaminZeleke

ሰሞነኛ ኢትዮጵያ፦ በሰሞነኛ ድረ-ገጽ የአማርኛ ፎረም (semonegna.com/forums) ላይ የሚገኝ ማንኛውም ጽሑፍ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንጸባርቅ ሲሆን፥ ጽሑፉ የሰሞነኛ ኢትዮጵያንንም ሆነ የተሳታፊዎችን አመለካከትና ምልከታ ላይወክል ይችላል።

በሀገራችን ኢትዮጵያ የተፈጸመውን ግፍ እውነታ በመረጃ የማሳየትና ማስረዳት ግዴታ ሁላችንም አለብን