Search Results for 'አዲስ አበባ'

Home Forums Search Search Results for 'አዲስ አበባ'

Viewing 15 results - 406 through 420 (of 495 total)
  • Author
    Search Results
  • Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)–በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ከፍተኛ ጥናት ትምህርት ቤት ኅዳር 27 ቀን 2011 ዓ.ም. የዩኒቨርሲቲው የበላይ ኃላፊ ዶ/ር ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ፣ የሥራ አመራር ቦርድ አባላት፣ የዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብ እንዲሁም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ ከባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር፣ ከጀርመን፣ ከፈረንሳይና ከጣልያን የባህል ማዕከላትና ሌሎችም ጥሪ የተደረገላቸው ልዩ ልዩ እንግዶች በተገኙበት በይፋ ተመርቆ ተከፍቷል።

    በቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ከፍተኛ ጥናት ትምህርት ቤት ረዳት ዳይሬክተር መ/ር ተመስገን ዮሐንስ ሙሉ ፕሮግራሙን የመሩት ሲሆን የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ካፈራቸው ምሁራን አንዱ ናቸው።

    በመርሐ ግብሩ መሠረት የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ከፍተኛ ጥናት ትምህርት ቤት በይፋ መጀመሩን ያበሰሩት የዩኒቨርሲቲው የበላይ ኃላፊ ዶ/ር ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ ሲሆኑ በመግቢያ ንግግራቸው ላይ ኮሌጁ በመማር ማስተማሩ ሂደት ዛሬ ላይ ለመድረስ የነበሩትን ብዙ ውጣ ውረዶችን አልፎ ለዩኒቨርሲቲ ደረጃ መድረሱ እግዚአብሔርን ካመሰገኑ በኋላ ዩኒቨርሲቲው አሁን የደረሰበትን ደረጃ እንዲደርስ ሌት ተቀን የሠሩት የቤተ ክርስቲያኒቱ የሥራ ኃላፊዎች ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስን፣ ብፁዓን ሊቃነጳጳሳት፣ የቦርድ የሥራ አመራር አባላትና የዩኒቨርሲቲውን ማኅበረሰብ ከፍ ያለ ምስጋና አቅርበዋል።

    ከብፁዕነታቸው በመቀጠል ንግግር ያደረጉት በዩኒቨርሲቲው የኢትዮጵያ ከፍተኛ ጥናት ትምህርት ቤት ዳይሬክተር ተባባሪ ፕሮፌሰር ኃይሉ ሀብቱ ናቸው።ተባባሪ ፕሮፌሰ ርኃይሉ የኢትዮጵያ ከፍተኛ ጥናት ትምህርት ቤት በቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ከሚገኙ አምስት ኮሌጆችና ት/ቤቶች ውስጥ አንዱ መሆኑን ገልፀው፥ ትምህርት ቤቱ ከጥቅምት 2011 ዓ.ም. ጀምሮ በማስተርስ ኦፍ አርትስ (M.A.) ዲግሪ ደረጃ የድኅረ ምረቃ ትምህርት መስጠት መጀመሩን ተናግረዋል። ፕሮግራሙን ለማጠናቀቅ የሚወስደው ጊዜ ሁለት ዓመት መሆኑንና የአንደኛው ዓመት መርሐ ግብር ለተማሪዎች፦ (1) በኢትዮጵያ ታሪክ፣ (2) በኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ፣ (3) በብሔረሰቦች ወግና ሥርዓት ሰፊጥናትና ጥልቅ ግንዛቤ የሚሰጥ ሲሆን በሁለተኛው መርሃ ግብርም፦ (1) በትውፊታዊ ሥነ መድኃኒት/ ሥነ ፈውስ፣ (2) በትውፊታዊ ሥርዓተ ሕግ፣ (3) በኢትዮጵያ ጥናት አውራ ርዕሰ ጉዳዮች የሚያተኩሩ እንደሆኑ አብራርተዋል። የማስተማሪያ መደበኛ ቋንቋ እንግሊዝኛ ቢሆንም አገርኛ ቋንቋዎች ግዕዝን ጨምሮ እንደ አማራጭ ማስተማሪያ ሆነው ሊያገለግሉ እንደሚችሉ ተናግረዋል።

    የኢትዮጵያ ታሪክ፣ ባህልና ነፃነት ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጋር በእጅጉ የተቆራኘ ነው። ለአብነት ያህል በ17ኛው እና 20ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የነበሩ እንደነ ወለተ ጴጥሮስ፣ አቡነ ጴጥሮስና አቡነ ማካኤልን የመሳሰሉ አባቶችና እናቶች ለኢትዮጵያ ሉአላዊነት ሰማዕት ሆነዋል ብለዋል።

    ከዚህ በመቀጠል የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የሥራ አመራር ቦርድ አባል የሆኑት ዶ/ር የራስወርቅ አድማሴ ንግግር አድርገዋል። ከተለያዩ የመንግሥትና መንግሥታዊያ ልሆኑ የትምህርት ተቅዋማትና ድርጅቶች የመጡትን እንግዶች እንኳን ደህና መጣችሁ በማለት ከልብ አመስግነዋል። በቀጣይም ዩኒቨርሲቲው በትምህርት ጥራት ላይ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሠራ ተናግረዋል።

    በመቀጠልም በፕሮግራሙ መክፈቻ መርሐ ግብር ላይ የተገኙ እንግዶች ለዩኒቨርሲቲው ግብዓት ሊሆኑ የሚችሉ ሀሳቦችና አስተያየቶች የሰጡ ሲሆን ከቅድስት በዓታ ለማርያም ቤተክርስቲያን የመጡ መምህር በዓሉን የሚገልጽ ቅኔ አቅርበዋል።

    በመጨረሻም በቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ከፍተኛ ጥናት ትምህርት ቤት በብራና መጻሕፍት ዝግጅት ክፍል የሚዘጋጁትን የተለያዩ የብራና መጻሕፍት፣ ቀለምና የብራና መሣሪያዎችን በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙ እንግዶች ጐብኝተዋል።

    የቀድሞ ቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በ1935 ዓ.ም. ለመጀመርያ ጊዜ ካህናትንና የቤተክርስቲያን ሊቃውንትን ዘመናዊውንና የአብነት ትምህርታቸውን አስተባብረው እንዲይዙ በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ድጋፍ እንደተጀመረ የታሪክ ድርሳናት ያስረዳሉ። ኮሌጁ በዚህ ደረጃ ለመጀመርያ ጊዜ የመጀመርያ ደረጃ ትምህርት ቤት ሆኖ ያገለገለ ሲሆን፥ በመቀጠልም በከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ማዕረግ በማስተማር ወደ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የሚገቡ ዕጩዎችን ሲያበቃ ቆይቷል። የኮሌጅን ደረጃ በ1960 ዓ.ም. ካገኘ በኋላ ከሦስት ዓመት በኋላ የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የቲኦሎጂ ፋኩልቲ አካል ሆኖ እስከ 1966 ዓ.ም. ድረስ ዘልቋል። የመንግሥት ለውጥን ተከትሎ ፋኩልቲው ሲዘጋ በወቅቱ በትምህርት ገበታ ላይ የነበሩት በሚፈልጉት የትምህርት መስክ ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተዛውረው ትምህርታቸውን እንዲያጠናቅቁ መደረጉ ይታወሳል። መንፈሳዊ ኮሌጁ ተወርሶ አራት ኪሎ ከጎኑ የሚገኘው የሳይንስ ፋኩልቲ ለራሱ የትምህርት መርሐ ግብር እንዲጠቀምበት ተደረገ። በ1987 ዓ.ም. ጀምሮ ኮሌጁ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተመልሶ በነበረው ዕውቅናና ደረጃ የመማር ማስተማሩን ሒደት ሲያከናውን ቆይቷል። ኮሌጁ ከመማር ማስተማሩ ጎን ለጎን ከፍተኛ የሆኑ የልማት ሥራዎችን ሲሠራ ቆይቷል።

    መንፈሳዊ ኮሌጁ እስከ አሁን ድረስ ከ3,500 በላይ ተማሪዎችን አሰልጥኖ ያስመረቀ ሲሆን ከዚሁ በበለጠ መልኩ እንዲጠናከርና የቤተክርስቲያኒቱ የጥናትና የምርምር ተቅዋም እንዲሆን መሉ ዝግጁቱን አጠናቅቆ በመጨረሱ በአሁኑ ሰዓት በቲዮሎጂ (ስነ መለኮት) የትምህርት ዘርፍ በዶክትሬት፣ በማስተርስ ዲግሪ፤ በመደበኛ የመጀመሪያ ዲግሪ፤ በማታው ተከታታይ እና በርቀት ትምህርት መርሃ ግብር የመጀመሪያ ዲግሪ፤ ዲፕሎማ፤ በግእዝቋንቋ (extension) ዲግሪና ዲፕሎማ ተማሪዎችን ተቀብሎ በማስተማር ላይ ይገኛል።

    ቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ከብዙ ድካምና ጥረት በኋላ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ፣ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ፣ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት መልካም ፈቃድ ወደ ከፍተኛ ዩኒቨርሲቲ ደረጃ እንዲያድግ ተደርጓል። በዚሁም መሠረት ከኅዳር 1 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ ቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ተብሎ እንዲጠራ መወሰኑ ይታወሳል።

    ምንጭ፦ ዩኒቨርሲቲው / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ


    Semonegna
    Keymaster

    ድምጻዊ ጎሳዬ ተስፋዬ አዲስ ያወጣው “ሲያምሽ ያመኛል” የተሰኘው የሙዚቃ አልበም አስራ አንድ ዓመታትን እንደፈጀ፤ በግጥም፣ በዜማ እና በቅንብር ከአስራ ሦስት ባለሙያዎች በላይ እንደተሣተፉበት እና ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ ፈሰስ እንደተደረገበት ተዘግቧል።

    አዲሰ አበባ (ሰሞነኛ) – በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው የተወዳጁ ድምፃዊ ጎሳዬ ተስፋዬ አምስተኛ ሙሉ የአልበም ሥራው የሆነውና “ሲያምሽ ያመኛል” የተሰኘው የሙዚቃ አልበም ታህሳስ 26 ቀን 2011 ዓ.ም. በኢትዮጵያና በመላው ዓለም በገበያ ላይ ውሏል።

    አራተኛ አልበሙን “ሳታመሃኝ ብላ” በሚል ርዕስ ካወጣ ከ11 ዓመታት በኋላ ለአድናቂዎቹ ያቀረበው ይህ አዲስ አልበም፥ ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ እንደተደረገበት አከፋፋዩ “ሪቮ ኮሚዩኒኬሽንና ኢቨንት” መግለጹን ሳምንታዊ አዲስ አድማስ ጋዜጣ ዘግቧል።

    በኢትዮጵያ ሙዚቃ ተጽዕኖ ፈጣሪ ከሚባሉትትና የላቀ እውቅናን ከተጎናጸፉት ድምፃዊያን አንዱ የሆነው የድምፃዊ ጎሳዬ ተስፋዬ አዲስ አልበም፣ ለረጅም ጊዜ በጉጉት ሲጠበቅ የቆየ ሲሆን፥ ደረጃውን የጠበቀና የተዋጣለት አልበም ለማድረግ ሲባል 11 ዓመታትን መፍጀቱንና ግጥምና ዜማቸው ተሠርተው ከተጠናቀቁ ከ40 በላይ ሥራዎች ውስጥ 15ቱ ተመርጠው በዚህ አልበም መካተታቸውን አከፋፋዩ ጨምሮ ገልጿል።

    አማርኛ ሙዚቃ፦ ድምጻዊ እሱባለው ይታየው — ዘፈን ማሞቂያ አይደለም

    በዚህ አዲስ አልበም ላይ ከተሳተፉ እውቅ የሙዚቃ አቀናባሪዎች መካከል አበጋዝ ክብረወርቅ ሺዎታ፣ ካሙዙ ካሳአቤል ጳውሎስ፣ መኮንን ለማ (ዶክተሬ)፣ ሚካኤል ኃይሉ (ሚኪ ጃኖ) እና ሱልጣን ኑሪ (ሶፊ) እንደሚገኙበት የገለፀው አከፋፋዩ፥ በግጥምና ዜማውም ከዚህ ቀደም በሠሩት ሥራ አንቱታን ያተረፉት አለምፀሐይ ወዳጆ፣ ይልማ ገ/አብ፣ ሀብታሙ ቦጋለ፣ ቢኒያም መስፍን (ቢኒባና)፣ አለማየሁ ደመቀ፣ መሰለ ጌታሁን እና ራሱ ጎሳዬ ተስፋዬ ተሳትፈውበታል ተብሏል።

    በአገራዊ፣ በማኅበራዊ እና በፍቅር ዙሪያ የሚያጠነጥኑ 15 ሙዚቃዎችን ያካተተው “ሲያምሽ ያመኛል” አልበም ሪከርድ የተደረገው በአሜሪካ ኒው ዮርክ ሲቲ ሲሆን ጥራትና ደረጃውን የጠበቀና ዘመኑ ያፈራው የሪከርዲንግ ቴክኖሎጂ አሻራ ያረፈበት መሆኑም ታውቋል።

    ጎሳዬ ተስፋዬ ከዚህ ቀደም “ሶፊ”፣ ከሌሎች ድምፃዊያን ጋር “ቴክ ፋይቭ”፣ ከአለማየሁ ሂርጶ ጋር “ኢቫንጋዲ” እና በ1999 ዓ.ም ለብቻው የሠራውን “ሳታመሃኝ ብላ” የተሰኙ የሙዚቃ አልበሞችን ለአድናቂዎቹ ማቅረቡ ይታወሳል።

    ◌ ሲያምሽ ያመኛል አልበምን በዲጂታል ለመግዛት: CD Baby Siyamish Yamegnal by Gossaye Tesfaye

    ምንጭ፦ አዲስ አድማስ ጋዜጣ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ተመሳሳይ ዜናዎች፦

    ጎሳዬ ተስፋዬ

    Semonegna
    Keymaster

    የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ኤጀንሲ በቅርቡ ሥራውን በይፋ የሚጀምርበት በዳያስፖራው ማህበረሰብ እና በባለድርሻ አካላት ዘንድ ተልዕኮው በግልፅ ታዉቆ በጋራ እና በቅንጅት ሥራው እንደሚሰራ መገለጹን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመልክታል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– የኢትዮጵያውያንን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያንን አገራዊ ተሳትፎ ለማረጋገጥና መብታቸውን ለማስከበር በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ስር የተቋቋመው የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ኤጀንሲ ሥራ ለመጀመር የመዋቅርና የሕግ ማዕቀፍ ሥራን ማጠናቀቁን አስታወቀ።

    የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ ሰላማዊት ዳዊት እና ምክትል ዳይሬክተር አቶ መሐመድ እንድሪስ ታህሳስ 26 ቀን 2011 ዓ.ም. ለአገር ውስጥ እና ለዉጭ አገር መገናኛ ብዙኃን መግለጫ ሰጥተዋል።

    የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ኤጀንሲ የመዋቅርና የሕግ ማዕቀፍ ሥራን ማጠናቀቁን ገልጸዋል፡፡ የኤጀንሲው ወደ ሥራ መግባት ዳያስፖራው በአገሩ ጉዳይ ብርቱ ተዋናይ እንደሚያደርገው ተናግረዋል።

    በዉጭ አገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያንን መብትና ጥቅሞችን ለማስጠበቅ የዳያስፖራ ምዝገባ እና መረጃ አያያዝ ስርዓት መዘርጋት፣ ዳያስፖራው በዕውቀትና በተክኖሎጂ ሽግግር አስተዋጽኦ እንዲያደርግ ማስቻል እንዲሁም በኢንቨስትመንት፣ በንግድና በቱሪዝም ተሳትፎውን ማጎልበት የኤጀንሲው ዋና ዓላማዎች መሆናቸውን አስረድተዋል።

    ተጨማሪ፦ በውጭ ሀገር የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን በሀገራቸው ኢትዮጵያ ኢንቨስት ለማድረግ እና ለመሥርት ያላቸው ፍላጎትና የሚያጋጥሟቸው ተግዳሮቶች (ቪዲዮ)

    ኤጀንሲው በቅርቡ ሥራውን በይፋ የሚጀምርበት በዳያስፖራው ማህበረሰብ እና በባለድርሻ አካላት ዘንድ ተልዕኮው በግልፅ ታዉቆ በጋራ እና በቅንጅት ሥራው እንደሚሰራ መገለጹን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመልክታል።

    የኢፌዴሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ይህን ኤጀንሲ ለማቋቋም የወሰነው በጳጉሜን ወር 2010 ዓ.ም. ሲሆን፥ በዚያን ጊዜ የሚኒስቴሩ ቃል አቀባይ አቶ መለስ ዓለም በውጭ ሀገር የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በትውልድ ሀገራቸው እድገት ላይ የራሳቸውን አስተዋጽዖ ለማድረግ ከምን ጊዜውም በበለጠ እንደተነሳሱ ገልጸው ነበር።

    በተለያዩ የውጭ ሀገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ቁጥር ከሦስት እስከ አምስት ሚሊዮን እንደሚገመትና ከእነዚህም ውስጥ አብዛኛዎቹ በሰሜን አሜሪካ እና አውሮፓ እንደሚኖሩ ዘገባዎች ያመለክታሉ። እ.ኤ.አ ከ2009 በፊት ኢትዮጵያ ከእነዚህ የዳያስፖራ አባላት የምታገኘው ገቢ (remittance) ከ400 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር በታች እንደነበረና ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ግን ይህ አሀዝ እየጨመረ መምጣቱ ተጠቁሟል።

    በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ ዳያስፖራዎች ወደ ትውልድ ሀገራቸው የሚልኩት የገንዘብ መጠን ከአራት ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር በላይ እንደሆነና ይህም ሀገሪቱ ከወጪ ንግድ (ኤክስፖርት) ከምታገኘው ገቢ ጋር ሲነጻጸር በአንድ ቢሊዮን ዶላር አካባቢ ብልጫ አለው።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ኤጀንሲ


    Semonegna
    Keymaster

    ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ አስተማማኝ ሠላም በዘለቄታ እንዲረጋገጥ ከተለያዩ ማኅበረሰብ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሠራ መሆኑን፣ የሀገሪቱ አቅም በሚፈቅደው ደረጃ የተለያዩ ግብዓቶችን ማሟላትን ጨምሮ ሌሎች አስፈላጊ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር አስታውቋል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)–በተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ተከስቶ የነበረው የሰላም መደፍረስ ችግር በአሁኑ ሰዓት እየተስተካከለ መሆኑን የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር ሚኒስትር ክብርት ዶ/ር ሒሩት ወልደማርያም ገለጹ።

    ዶ/ር ሒሩት ባለፈው ሳምንት ለተለያዩ መገናኛ ብዙኃን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፥ በሁሉም ዩኒቨርሲቲዎች መደበኛው የመማር ማስተማር ሥራ መጀመሪያ አከባቢ በሰላማዊ ሁኔታ ተጀምሮ የነበረ ሲሆን በሂደት ግን የአገራችን ለውጥ ያልተዋጠላቸው አካላት የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ማዕከል በማድረግ ግጭቶችን በማስፋፋት ሠላም እንዳይኖር ታስቦ እንደ ነበር ተደርሶበታል ብለዋል።

    ተመሳሳይ ዜና፦ ሰላሌ ዩኒቨርሲቲ በቂ ዝግጅት በማድረግ አዳዲስ ተማሪዎችን መቀበሉን አስታወቀ

    ግጭቶቹ በግል ደረጃ በተማሪዎች ጠብ ተጀምሮ ወደ ብሔር እንዲያድግም ታስቦ እንደነበርና፥ አሁን ግን ከተለያዩ የትምህርት ባለድርሻ አካላት ከሃይማኖት አባቶች፣ ከአገር ሽማግሌዎች፣ ከዩኒቨርሲቲ ቦርድ አባላት፣ ከዩኒቨርሲቲው አመራር፣ ከአካባቢው ማኅበረሰብ፣ ከጸጥታ አካላት ጋር ሰፊ ውይይት በማድረግ፥ ዩኒቨርሲቲዎች ወደ መደበኛ ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሂደት እንዲመለሱ እየተደረገ ይገኛል ያሉት ሚኒስትሯ፥ ለዚህም በዩኒቨርሲቲ ቦርድ እንዲሳተፉ ከተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲዎች ጭምር ብቁ ምዑራን መመልመላቸውን፣ ሴቶችም በጉዳዩ እንዲሳተፉ ሀምሳ በመቶ (50%) ያህሉ ሴቶች በቦርድ እንዲመረጡ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል።

    በቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ ረዘም ላለ ጊዜ ትምህርት ተቋርጦ የነበረ ሲሆን፥ አሁን ግን ከተለያዩ አካላት እና ከተማሪዎች ጋር በተደረገ ውይይት ከጥር 1 ቀን 2011 ዓ.ም. ጀምሮ ተማሪዎቹ በመደበኛ የትምህርት ገበታቸው እንደሚገኙ ከስምምነት መደረሱን ሚኒስትሯ አክለው ገልጸዋል።

    የዩኒቨርሲቲዎች አስተማማኝ ሠላም በዘለቄታ እንዲረጋገጥ ከተለያዩ ማኅበረሰብ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሠራ መሆኑን፣ የሀገሪቱ አቅም በሚፈቅደው ደረጃ የተለያዩ ግብዓቶችን ከማሟላት በተጨማሪ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የተለያዩ ምሁራንን በመጋበዝ የተማሪ ሥነ-ልቦና ላይ በመሥራት በተማሪዎች ዘንድ የተወዳዳሪነት ስሜት እንዲፈጠር ሥራዎች እየተሠሩ መሆኑንም ክብርት ሚኒስትሯ ገልጸዋል።

    ምንጭ፦ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር | ሰሞነኛ ኢትዮጵያ
    ——
    ተመሳሳይ ዜናዎች፦

    ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ


    Semonegna
    Keymaster

    የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የፈረንሳዩ ጂ ኢ ሪኒዌብልስ አካል ከሆነ ጂ ኢ ኃይድሮ ፍራንስ ጋር የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ለማፋጠን የሚያስችል የ61 ሚሊዮን ዶላር ስምምነት ተፈራርሟል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ሥራዎችን በአዲስ ኃይል ወደቀድሞ ፍጥነት ለመመለስ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ ነው። በውሃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ዶ/ር ኢንጂነር ስለሺ በቀለና በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈፃሚ በዶ/ር ኢንጂነር አብርሃም በላይ የተመራ የልዑካን ቡድን የግድቡን የሲቪልና የብረታብረት ሥራዎች ጎብኝቷል።

    የግንባታው አማካሪዎች ትራክትቤል ኢንጂነሪንግና ኤልክ ኤሌክትሮ ኮንሰልት ተወካዮች እንደገለፁት የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ላይ ለታዩት ችግሮች ቴክኒካዊ መፍትሔ ለመስጠት የሚያስችሉ ሥራዎች እየተከናወኑ ነው። ቀደም ሲል የተጀመሩና የተከናወኑ ከብረታብረት ጋር የተያያዙ ሥራዎች ከ90 በመቶ በላይ ፍተሻ ተደርጎ ችግሮቹን ለማረም የሚያስችሉ ዝግጅቶች መጠናቀቃቸውም ተገልጿል።

    ሚኒስትር ዶ/ር ኢ/ር ስለሺ በቀለ እንደተናገሩት የግድቡ የግንባታ ሥራዎች መነቃቃት እየታየባቸው ነው። በመሆኑም የተለያዩ ሂደቶችን ማለፍ የማይጠይቁ የግንባታ ሥራዎች በፍጥነት እንዲከናወኑ ሚኒስትሩ ማሳሰቢያ ሰጥተዋል። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዶ/ር ኢ/ር አብርሃም በላይ በበኩላቸው የግድቡ ግንባታ ላይ የተፈጠረውን ክፍተት ለማረምና ጉድለቱን ለማካካስ ተቋማቸው አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። የግድቡን ግንባታ ለማፋጠን ቀደም ሲል ከብረታብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ጋር በንዑስ ተቋራጭነት ለመሥራት ውል የነበራቸው ተቋራጮች መካከል የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ከጂ ኢ ኃይድሮ ፍራንስ ጋር ውል ተፈራርሟል።

    የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ስምምነቱን ታህሳስ 22 ቀን 2011 ዓ.ም. በተቋሙ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ውስጥ ነው ጂ ኢ ሃይድሮ ፍራንስ ከተባለው ተቋራጭ ጋር ተፈራርሟል። ጂኢ ሃይድሮ ፍራንስ በቅድሚያ እንዲያመነጩ ታስበው ዲዛይን የተደረጉትን ሁለት ተረባይኖችን ጨምሮ አምስት ኃይል ማመንጫ ዩኒቶች ኮሚሌክስ ከተባለ ድርጅት ጋር በጥምረት ለማምረት፣ ለመግጠምና ለመፈተሽ የ53 ነጥብ 9 ሚሊዮን ዩሮ ስምምነት ተፈርሟል።

    ጂ ኢ ሃይድሮ ፍራንስ ቀደም ሲል ከብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ጋር ተርባይን ጄኔሬተሮችን ለማቅረብ ብቻ የንዑስ ተቋራጭነት ስምምነት እንደነበረው ዶ/ር አብርሃም ገልጸዋል። አዲሱ ስምምነት ደግሞ የማምረት፣ የተጓደሉ አቅርቦቶችን የማሟላት፣ የተከላና የፍተሻ ሥራዎችን ያከተተ ነው ተብሏል።

    በተመሳሳይ ተቋሙ ሲኖ ሃይድሮ ከተባለው የቻይና ኩባንያ ጋር የብረታ ብረት ሥራዎች ጋር በተያያዘ ስምምነት ለመፈራረም ድርድሮች መጠናቀቃቸውም ተገልጿል። ኩባንያው የኃይል ማመንጫ የውሃ ማስተላፊያ ቱቦዎችን፣ የመቆጣሪያ እና የጎርፍ ማስተንፈሻ በሮችን የመገንባትና የማስተካከል ሥራ እንደሚያከናውን ተጠቁሟል። ሲኖ ሃይድሮ የሚሠራው ሥራ የሲቪል ሥራዎች በማፋጠን ከአጠቃላይ የኃይል ማመንጫ ዩኒቶች ሁለቱ አስቀድመው ኃይል እንዲያመነጩ ያግዛል ተብሏል።

    ምንጮች፦ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል፣ ኤፍቢሲ እና ሮይተርስ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ


    Semonegna
    Keymaster

    የሚገነባው የኤሌክትሮኒክ ግብይት (ኢ-ኮሜርስ) ማዕከል በኢትዮጵያ በቀዳሚነት በግል ዘርፉ የሚመራ ሆኖ መንግስት ክበባዊ ሁኔታን የማመቻቸት ሥራ ይሠራል። መንግስት ለማዕከሉ ግንባታ የሚያስፈልገው የቦታ መረጣም ሆነ መሠረት ልማት በፍጥነት እንደሚያሟላም ተጠቁሟል።

    አዲስ አበባ (ኢ.ፕ.ድ)– የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት የኤሌክትሮኒክ ግብይት (ኢ-ኮሜርስ) ማዕከል በኢትዮጵያ ለመገንባት በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር እና በዓለም አቀፍ ፖስታል ዩኒየን መካከል ስምምነት ተደርጓል።

    የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዶ/ር ኢንጂነር ጌታሁን መኩሪያ እና የዓለም አቀፍ ፖስታል ዩኒየን (Universal Postal Union) ዳይሬክተር ጀነራል አምባሳደር ቢሻር ሁሴን ስምምነቱን ተፈራርመዋል። ሚኒስትሩ በተለይ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንደተናገሩት፤ የኢትዮጵያ መንግስት የቦታ አቅርቦትና መሠረተ ልማት የማሟላት ኃላፊነት የተሰጠው ሲሆን፤ የዓለም አቀፍ ፖስታል ዩኒየን ደግሞ ሥርዓቱን የመዘርጋት ኃላፊነቱን ወስዷል።

    እንደ ዶ/ር ኢንጅነር ጌታሁን ገለጻ፥ በአዲስ አበባ ይገነባል የተባለው ማዕከል በአፍሪካ ውስጥ ከሚገነቡ አራት ኢ-ኮሜርስ ማዕከላት አንዱ ሲሆን፥ ቀድሞ የምስራቅ አፍሪካ የኢ-ኮሜርስ ማዕከል ኬንያ ናይሮቢ ሊገነባ ታቅዶ የነበረው ነው። ወደ አገራችን የመጣበት ምክንያት ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂ እያደገች መምጣቷ፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ተለያዩ ሀገራት የሚያደርገው በረራ መበራከቱና የኢትዮጵያ መንግስት ለዘርፉ የሰጠው ልዩ ትኩረት ዋንኞቹ ናቸው።

    ተመሳሳይ ዜና፦ Chinese giant e-commerce Alibaba Group & its affiliate Ant Financial entering Ethiopian market

    ማዕከሉ በኢትዮጵያ በቀዳሚነት በግል ዘርፉ የሚመራ ሆኖ መንግስት ክበባዊ ሁኔታን የማመቻቸት ሥራ ይሠራል። መንግስት ለማዕከሉ ግንባታ የሚያስፈልገው የቦታ መረጣም ሆነ መሠረት ልማት በፍጥነት እንደሚያሟላም ጠቁመዋል።

    የማዕከሉ መገንባት ከፍተኛ ሀገራዊና አህጉራዊ ጠቀሜታ አለው ያሉት ዶ/ር ኢንጅነር ጌታሁን፥ ለ100ሺህ ወጣቶች የሥራ ዕድል እንደሚፈጥርና በሀገሪቱ ውስጥ ከፍተኛ የገንዘብ አቅም እንደሚሆን ተናግረዋል። የአፍሪካ ምርቶች ለማንኛውም ሀገራት በቀላሉ እንዲታዩ በማድረግ ገበያውን በቀላሉ እንዲቀላቀሉ ዕድል ይሰጣል ብለዋል።

    በኢትዮጵያ የገንዘብ ዝውውር በኤሌክትሮኒክ እንዲሆን ማድረግ የሚያስችል የህግ ማዕቀፍ እየተዘጋጀ መሆኑን የጠቆሙት ሚኒስትሩ፥ በቅርቡ ወደ ትግበራ እንደሚገባና የገንዘብ ዝውውርን ለማቀላጠፍና የግብይት ሥርዓቱን ለማዘመን ሚናውን ይወጣል። ዓለም በአሁኑ ወቅት በኤሌክትሮኒክ ግብይት በጣም ርቆ መሄዱን ተከትሎ በአፍሪካ ደረጃ አስፍቶና ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሠራም ተናግረዋል።

    በዘርፉ ኢትዮጵያ ብዙም ተጠቃሚ እንዳልሆነች የገለጹት ሚኒስትሩ፥ ዘመኑ የኤሌክትሮኒክ ግብይት (ኢ-ኮሜርስ) ዓለም ነውና ከዓለም ጋር እኩል ለመጓዝ ማዕከሉን ተግባራዊ ማድረግ ወሳኝ መሆኑን ጠቁመዋል። በዓለም ላይ እንደ አማዞን (Amazon)፣ አሊባባ ግሩፕ (Alibaba Group) እና የመሳሰሉ በኤሌክትሮኒክ ግብይት በዓመት እስከ አምስት ትሪሊን ዶላር እንደሚያንቀሳቅሱ ሁሉ በማዕከሉ አማካኝነት አገሪቱ ለማደግ የሚያስችላትን ተግባራት ሁሉ ትሠራለች ብለዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት (ኢ.ፕ.ድ) | ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ኢ-ኮሜርስ ማዕከል


    Semonegna
    Keymaster

    የገቢዎች ሚኒስቴር የነደፈው ብሔራዊ የግብር ገቢ ንቅናቄ ዜጎች ግብር መክፈል ሀገራዊ ግዴታቸው መሆኑን በማስገንዘብ እና ከዜጎች የሚሰበሰበውን ግብር በመጨመር ሀገሪቱ እ.ኤ.አ በ2025 የመካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገራት ውስጥ ለመመደብ የምታደርገውን ጥረት ይደግፋል ተብሎ ይጠበቃል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ጠንካራ የግብር ዘርፍ እንዲኖር ጠንካራ መሠረተ ልማት እንደሚያስፈልግ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህን ያሉት “ግዴታዬን እወጣለሁ፣ መብቴን እጠይቃለሁ” በሚል መሪ ሀሳብ የሚካሄደውን ብሔራዊ የግብር ገቢ ንቅናቄ (National Tax Revenue Movement) ታህሳስ 12 ቀን 2011 ዓ.ም. በአፍሪካ ህብረት አዳራሽ በይፋ ሲያስጀምሩ ነው።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በመልዕክታቸው እንዳሉት ቁሳዊ መሠረተ ልማቶችና ቁሳዊ ያልሆኑ እንደ ዴሞክራሲ፣ ፍትህ፣ ጸጥታና የመሳሰሉት መሠረተ ልማቶች እጅግ በጣም ወሳኝ ናቸው። “ዜጎች በሚከፍሉት ግብር መንግስት መሠረተ ልማቶች በማስፋፋት፣ የግሉ ዘርፉ ጠንካራና ተወዳዳሪ እንዲሆን ምቹ ሁኔታ ይፈጥራል” ብለዋል።

    ጠንካራና ተወዳዳሪ የሆነ የግል ዘርፍም ለዜጎች ሰፊ የስራ ዕድል ከመፍጠር በላይ ትርፋማነቱን የሚያረጋግጥና ለመንግስትም ትልቅ የገቢ ምንጭ በመሆን የሚያበረክተው አስተዋጽኦ ከፍተኛ እንደሆነ ተናግረዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ያደረጉት የመክፈቻ ንግግር (ቪዲዮ)

    በኢትዮጵያ የተጀመረውን ሰፊ የዴሞክራሲ ግንባታ ለማስቀጠል ጠንካራና ገለልተኛ የዴሞክራሲ ተቋማትን በመገንባት የዜጎችን ዴሞክራሲያዊ ተሳትፎ ማሳደግ እንደሚቻል ጠቁመዋል።

    “ያለበቂ ተሳትፎና ውክልና ግብር የመክፈል ግዴታ ሊኖር አይችልም” ያሉት ዶክተር ዐቢይ “ግለሰባዊ የመብት አያያዝ፣ ማኅበረሰባዊ ደህንነት፣ የዳበረ የፍትህ ስርዓት፣ የላቀ የዕውቀትና ጥበብ አቅም፣ በምግብ ራስን መቻልና መሠረታዊ ጤናን ለሁሉም የማዳረስ ብቃት ሳይቋረጡና ከደረጃቸው ሳይወርዱ ማዳረስ የሚቻለው ያለማቋረጥ ግብር ለመሰብሰብ የሚችል ስርዓትና አቅም ስንፈጥር ብቻ ነው” በማለት መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

    ኢትዮጵያን ለማሳደግና ሰላም እንድትሆን ለዜጎችና ለነዋሪዎች መሠረታዊ ፍላጎቶችን በበቂ ሁኔታ ለማቅረብና ድህነትን በማሸነፍ ወደብልጽግና ለመገስገስ ከተፈለገ ስለግብር ያለው ደካማ አመለካከት መቀየር እንዳለበት ተናግረዋል።

    “ግብር የሚያጭበረብር ሰው እንደ አራዳ መቆጠሩ ቀርቶ አገርና መንግስትን እንደሚጠላ ብቻ ሳይሆን ስለራሱ ልጆች የዛሬና የወደፊት ህልውና ምንም የማይጨነቅ ሞኝ ተደርጎ ሊቆጠር ይገባል” ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ።

    ዜጎችና ነዋሪዎች ግብር በመክፈል አገሪቱን፣ መንግስትንና ልጆቹን እንደሚወድ በይፋ የሚያሳይ ኩሩ ዜጋ መፍጠር እንደሚያስፈልግም አክለዋል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደጠቀሱት ኢትዮጵያ ከጠቅላላ የአገር ውስጥ ምርቷ (GDP) የግብር ገቢዋ (tax revenue) የሚይዘው 10.7 በመቶ ብቻ ሲሆን፥ ይህም ከአፍሪካ ሀገራት አንጻር እንኳን በጣም ዝቅተኛ ነው።

    የገቢዎች ሚኒስቴር የነደፈው ብሔራዊ የግብር ገቢ ንቅናቄ (National Tax Revenue Movement) ኢትዮጵያውያን ለግብር ያላቸውን ዝቅተኛ ብሎም የተሳሳተ አመለካከት በመቀየር፥ ይልቁንም ግብር መክፈል ሀገራዊ ግዴታ እና ማንኛምው ገቢ የሚያገኝ ሰው መክፈል ያለበት ነገ መሆኑን በማስገንዘብ ከዜጎች የሚሰበሰበውን ግብር በመጨመር ሀገሪቱ እ.ኤ.አ በ2025 የመካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገራት ውስጥ ለመመደብ የምታደርገውን ጥረት ይደግፋል ተብሎ ይጠበቃል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) | ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    ብሔራዊ የግብር ገቢ ንቅናቄ

    Semonegna
    Keymaster

    ታካሚው ከቀዶ ህክምና ወጥቶ ወደ ቤቱ እንዲሄድና የአእምሮ ህክምና በአእምሮ ህክምና ስፔሻሊስቶች ክትትል እንዲደረግለት እየተመቻቸ መሆኑን የቅዱስ ጴጥሮስ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል የቀዶ ህክምና ስፔሻሊስት ተናግረዋል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) በቅዱስ ጴጥሮስ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ጥቅምት 10 ቀን 2011 ዓ.ም. ከአንድ የ33 ዓመት ወጣት ሆድ በቀዶ ህክምና 120 ሚስማሮች፣ አንድ መርፌ ቁልፍ፣ ሁለት መርፌ፣ ሁለት ስትኪኒና ሁለት ስባሪ ብርጭቆዎች ማውጣት መቻሉ ይታወሳል። ይህ ታካሚ በአሁ ሰዓት ሙሉ ለሙሉ ከህመሙና ከቁስሉ ማገገሙን የሆስፒታሉ የቀዶ ህክምና ስፔሻሊስት ዶ/ር ዳዊት ተዓረ አስታውቀዋል።

    ዶ/ር ዳዊት እንደገለጹት፥ ታካሚው ቀዶ ህክምና ከተደረገለት ሁለት ወር ሲሆነው በአሁኑ ሰዓት ከድኅረ ቀዶ ህክምና (post-surgery recovery) አገግሞ ሙሉ ጤንነት ላይ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።

    ታካሚው ከቀዶ ህክምና ወጥቶ ወደ ቤቱ እንዲሄድና የአእምሮ ህክምና በአእምሮ ህክምና ስፔሻሊስቶች ክትትል እንዲደረግለት እየተመቻቸ መሆኑን ዶክተር ዳዊት ተናግረዋል።

    Ethio-American Doctors Group (EADG): Building a regional healthcare system & medical tourism

    ታካሚው ወደ ህክምናው ሲመጣ የነበረበት የጤና ችግር በጣም አጣዳፊና ከባድ ነበር ያሉት ዶ/ር ዳዊት፥ ሚሰማሮቹ ብዙ ስለነበሩ ጨጓራውን ሙሉ ይዘውት ስለነበር ምግብ መውሰድ አይችልም ነበር ብለዋል። በዚህም ሳቢያ ከፍተኛ የሆነ የምግብ እጥረት ይታይበት ስለነበር በዚህ ሁኔታ ላይ ኦፕሬሽን ማድረግ በጣም አስቸጋሪ እንደነበር ዶክተሩ ተናግረዋል።

    በሁለት ወር የህክምና ጊዜ ውስጥ የምግብ እጥረት ስለነበረበት ቁስሉ ቶሎ ማገገም እንዳይችል ማድረጉን የገለጹት ዶ/ር ዳዊት፥ በአሁኑ ሰዓት ታካሚው ሁሉም ነገር ድኖለት መንቀሳቀስና መመገብ መቻሉን ተናግረዋል። ዶክተሩ አክለውም በህይወታቸውና በሙያ አገልግሎታቸው ደስተኛ ካደረጉዋቸው የህክምና ሥራዎች አንዱ ይሄ መሆኑንም ተናግረዋል።

    ታካሚው በበኩሉ ምግብ በአግባቡ እየተመገበ መሆኑን ገልጾ ወደ ቤቱ መግባት እንደሚፈልግ ተናግሯል።

    ምንጭ፦ የቅዱስ ጴጥሮስ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል

    የቅዱስ ጴጥሮስ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል
    ——
    ሌሎች ዜናዎች፦


    Semonegna
    Keymaster

    የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል የካንሰርና የልብ ህክምና ማዕከል ግንባታ 56 በመቶ ደርሷል

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሌኒየም ሜዲካል ኮሌጅ ከ986 ሚሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የሚያስገነባው የካንሰርና የልብ ህክምና ማዕከልን በተያዘለት ግዜ ለማጠናቀቅ እየተሠራ መሆኑን ተገለጸ።

    የሆስፒታሉ የምህንድስና ኢንጂነሪንግ ክፍል አስተባባሪ ኢንጅነር ሞቲ አሰፋ ለ ኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) እንደገለጹት እየተገነቡ ያሉት የካንሰርና የልብ ህክምና ማዕከላት መጀመሪያ አካባቢ ቶሎ ወደ ሥራ ያለመግባትና በብረት ዋጋ ንረት ምክንያት መዘግየት የታየበት ቢሆንም ግንባታው 56 በመቶ ደርሷል።

    የማዕከላቱ መሠረት በ12 ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ያረፈ ሲሆን ባለ12 እና 10 ወለል ህንፃዎች ይኖሩታል ብለዋል። ህንፃዎቹ ከ600 በላይ የመኝታ ክፍሎች እንደሚኖራቸው ነው ኢንጂነር ሞቲ ያብራሩት።

    ከዚሁ ጎን ለጎን ከተጀመረ ስምንት ዓመታትን ያስቆጠረውና ከ350 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገበት የእናቶችና ህጻናት ማዕከል ባለ 8 ወለል ህንፃም በመጠናቀቅ ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

    በህንጻ ተቋራጩ እና ክትትል በሚያደርገው ተቆጣጣሪ ድክመት ምክንያት ተጓትቶ የነበረው ፕሮጀክቱ ባለሙያዎችን በመቀየር በአሁኑ ወቅት ሥራው በመጠናቀቅ ላይ እንደሚገኝና በዚህ ሳምንት ከፊሉን ሥራ ለማስጀመር እንቅስቃሴ እየተደረገ ነው ብለዋል።

    ◌ Ethiopia: Are Ethiopian hospitals constructed in environment-suitable and climate-friendly way?

    የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ሜዲካል ኮሌጅ ሜዲካል አገልግሎት ዋና ፕሮቮስት ዶ/ር ወንድማገኝ ገዛኸኝ በበኩላቸው ማዕከላቱ አገልግሎት መስጠት ሲጀምሩ በሀገሪቱ በካንሰርና በልብ ህመም ለሚሰቃዩ ዜጎች የሚሰጡት ጥቅም ከፍተኛ ነው ብለዋል። በተለይ ህክምናዎቹ የሚጠይቁት ወጪ ከፍተኛ በመሆኑ አብዛኛውን ህብረተሰብ ተጠቃሚ ያደርጋል ነው ያሉት።

    ከሰባት ዓመት በፊት ሆስፒታሉ በቀን ከ500 ያልበለጡ ህሙማንን ብቻ ያስተናግድ እንደነበር የተናገሩት ዶክተር ወንድማገኝ፥ በአሁኑ ወቅት በየቀኑ ለሁለት ሺህ ሰዎች ህክምና አገልግሎት እያገኙ ነው ብለዋል።

    በአሁኑ በወቅት በወር ለ1 ሺህ 500 እናቶች የወሊድ አገልግሎት እየተሰጠ ሲሆን በግንባታ ላይ የሚገኘው የእናቶችና ህፃናት ህንፃ ሲጠናቀቅ በቀን ለ400 እናቶች የወሊድ አገልግሎት መስጠት እንደሚችል ጠቁመዋል።

    ህንፃው 15 የማዋለጃ ክፍሎች እንደሚኖሩት የጠቀሱት ዶ/ር ወንድማገኝ በቅርቡ አገልግሎቱን ለማስጀመር ከጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ጋር በቅንጅት እየተሠራ መሆኑን አንስተዋል።

    የሆስፒታሉ ሀኪም ዶ/ር ዮናስ ገብረጊዮርጊስ በበኩላቸው የሚገነቡት የካንሰርና የልብ ህክምና ማዕከላት በሀገሪቱ በመንግስት በብቸኝነት አገልግሎት እየሰጠ ካለው የጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ተጨማሪ በመሆን ህብረተሰቡ የጤና አገልግሎቱን በአቅራቢያው እንዲያገኝ ያስችላል ብለዋል።

    የማዕከላቱ መገንባት በሀገሪቱ ከጊዜ ወደጊዜ እየጨመረ የመጣውን የካንሰር ህመም ለመከላከል የሚሰጠው ፋይዳ ከፍተኛ መሆኑን የተናገሩት ዶክተር ዮናስ ግንባታው በተያዘለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረግ ይገባል ብለዋል።

    ፕሮጀክቱ በሁለት ዓመት ውስጥ ሙሉ ለሙሉ ተጠናቅቆ አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምርም ተነግሯል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የካንሰርና የልብ ህክምና ማዕከል

    Semonegna
    Keymaster

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– የጃፓን መንግስት በኢትዮጵያ ለትምህርትና ጤና አገልግሎት የሚውል ከ452 ሺህ ዶላር በላይ ድጋፍ አደረገ። የጃፓን መንግስት አዲስ አበባ በሚገኘው ኤምባሲው በኩል ያደረገው የገንዘብ ድጋፍ በተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች የሚገኙ አራት ፕሮጀክቶችን ለመገንባትና ለማስፋፋት ያስችላል።

    በኢትዮጵያ የጃፓን አምባሳደር ዲያሱኬ ማሱናጋ (Daisuke Matsunaga) የፕሮጀክት ግንባታና ማስፋፊያ ከሚደረግላቸው ትምህርት ቤቶች ኃላፊዎች ጋር የድጋፍ ስምምነት ተፈራርመዋል።

    ፕሮጀክቶቹ በደቡብ ክልል ጉራጌ ዞን የጉንችሬ እና እነሞር ወረዳ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ግንባታና በኦሮሚያ ክልል በሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ዞን የሀሮ ሾጤ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ማስፋፊያ ናቸው።

    በተጨማሪም ለሻሻመኔ ከተማ የአረጋዊያንና አካል ጉዳተኞች የምግባረ ሰናይ መጠለያ ግንባታና ለጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የዩሮሎጂ እና ድንገተኛ ክፍል የህክምና መሣሪያዎች ግዥ የሚውል ነው።

    እነዚህ አራት የትምህርት እና የጤና ፕሮጀክቶች ከአራት ሺህ በላይ ህዝብ ተጠቃሚ ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል ሲል የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) ዘግቧል።

    አምባሳደር ዲያሱኬ ማሱናጋ እንዳሉት አገራቸው ለኢትዮጵያ ልማት ተሳትፎ የምታደርገውን ድጋፍ አጠናክራ ትቀጥላለች። ጃፓን በኢትዮጵያ እ.አ.አ ከ1989 ጀምሮ በተለያዩ ክልሎች ከ400 በላይ ፕሮጀክቶችን በመሥራት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ እያደረገች ነው።

    በትምህርት፣ በቴክኒክና ሙያ ስልጠና፣ በንጹህ ውሃ አቅርቦት፣ በኢኮኖሚ ልማትና ሌሎችም መስኮች ድጋፍ ስታደርግም ቆይታለች።

    በስምምነቱ ላይ የተገኙት የኢትዮጵያ ስፖርት ኮሚሽነር እርስቱ ይርዳው የተደረገው ድጋፍ የዝቅተኛውን የህብረተሰብ ክፍል የትምህርት ፍላጎት ለማሟላት እንደሚያስችል ገልጸዋል።

    ድጋፉ በተለይም ትምህርት ቤት ባልተዳረሰባቸው አካባቢዎች መሆኑ የትምህርት ሽፋንን በማስፋት የመንግስትን ጥረት እንደሚያግዝም ተናግረዋል፡፡

    ከዚህ ጋር በተያያዘ የጃፓን ኤምባሲ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ የሚገኘውን የራስ መኰንን አዳራሽ ለማደስ የ85 ሺሕ 679 ዶላር (2,403,500 ብር) ዕርዳታ መለገሱን ሪፖርተር ጋዜጣ በእሁድ ታህሳስ 7 ቀን 2011 ዓ.ም. እትሙ ዘግቧል።

    አምባሳደር ዲያሱኬ ማሱናጋ እና የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም ዳይሬክተር አህመድ ሐሰን (ዶ/ር) የእርዳታ ስምምነቱን የተፈራረሙ ሲሆን፣ ገንዘቡም የራስ መኰንን አዳራሽ ባህላዊና ታሪካዊ ዳራው ሳይጠፋ ለማደስ፣ የተበላሹ ክፍሎችን ለመጠገን፣ ውስጣዊ ክፍሉን ለማደስ እና አዳዲስ ቁሳቁስ ለማስገባት መሆኑ ታውቋል።

    የጃፓን መንግስት ትምህርታዊ ድጋፍ ከማድረጉም በተጨማሪ የራስ መኰንን አዳራሽን ለማደስ መነሳቱ፣ የኢትዮጵያ ጥናት ተቋም ኢትኖሎጂካል ሙዚየም በርካታ ጎብኚዎች እንዲስብ ያስችላል ተብሏል።

    በሙዚየሙ ከአሥር ሺሕ በላይ የኢትዮጵያ ባህላዊና ሃይማኖታዊ እሴቶች የሚገለጹባቸው አልባሳትና ቁሳቁሶች አሉ፤ ይህም በአፍሪካ አንዱ ታዋቂ ሙዚየም እንዲሆን አስችሏል።

    በቀድሞው የገነተ ልዑል ቤተ መንግሥት ሕንፃ ውስጥ የሚገኘው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም፣ ከ50 ዓመታት በላይ ዕድሜው በስሩ ያቀፋቸው ቤተ-መጻሕፍት፣ የኢትኖግራፊክ ሙዚየም የምርምርና የጥናት ማዕከልን ነው። በውስጡም መጻሕፍት፣ ታሪካዊ ሰነዶችና መዛግብት፣ የዳግማዊ ምኒልክና የእቴጌ ጣይቱን ጨምሮ የድምፅና የምስል ቅጂዎች፣ ከመጀመሪያ ዲግሪ እስከ ሦስተኛ ዲግሪ ማሟያ የጥናት ድርሳኖች፣ ጆርናሎች፣ ረጅም ዕድሜን ያስቆጠሩ የብራና መጻሕፍትንም ይዟል።

    እንዲሁም እስከ 20 ሺሕ የሚደርሱ የኅትመት ክምችቶች ከቅድመ ምረቃ እስከ ድኅረ ምረቃ ተማሪዎች፣ ለተመራማሪዎች ጥናትና ምርምር አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል።

    የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በ2010 ዓ.ም. መስከረም ወር ከጃፓኑ ኪዮቶ ዩኒቨርሲቲ ጋር ትምህርታዊ ልውውጥና የጥናት ትብብር ለማድረግ የመግባቢያ ሰነድ መፈረሙ ይታወሳል።

    ምንጭ፦ ኢዜአ እና ሪፖርተር ጋዜጣ

    የጃፓን መንግስት

    Semonegna
    Keymaster

    የመንገዶች የመብራት አገልግሎት አለመስጠት ምክንያቱ ኃይል ያልተለቀቀላቸው በመኖራቸው፣ መሠረተ ልማቶች ስለሚዘረፉ፣ የምሰሶና የአምፖል ማርጀት እንደሆነ የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ጠቅሷል።

    አዲስ አበባ (ኢዜአ)–በአዲስ አበባ ከተማ ካሉት መንገዶች ውስጥ የመብራት አገልግሎት እያገኙ ያሉት ከ40 በመቶ እንደማይበልጥ ያስታወቀው የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን እስከሚቀጥለው ዓመት ዘጠና በመቶ የከተማዋ መንገዶች መብራት እንዲኖራቸው ከአዲስ አበባ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ቢሮ ጋር እየሠራሁ ነው ብሏል።

    የመንገዶች የመብራት አገልግሎት አለመስጠት ምክንያቱ ኃይል ያልተለቀቀላቸው በመኖራቸው፣ መሠረተ ልማቶች ስለሚዘረፉ፣ የምሰሶና የአምፖል ማርጀት እንደሆነ የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ጠቅሷል።

    የመብራት ምሰሶዎች በየመንገዱ ቢተከልም ከሁለት ዓመት ወዲህ አብዛኛዎቹ አገልገሎት እንደማይሰጡ የጠቀሱት የአፍንጮ በር ነዋሪ አወል አማን፥ በምሽት ወደ መስጊድ ሲሄዱና ከሥራ አምሽቶ ወደ ቤት ለመግባት ስጋት ፈጥሮብናል ብለዋል። አክለውም ምሰሶዎችና አምፖሎች ተሰባብረው እንደሚገኙ ያነሱት ነዋሪው አገልግሎት የማይሰጡ መብራቶች እንዲጠገኑ ጠይቀዋል።

    የጉለሌ አካባቢ ነዋሪ አቶ ፀጋዬ መኩሪያ መኪና አሽከርካሪ ሲሆኑ፥ መንገዶች የምሽት መብራት ከሌላቸው ለአሽከርካሪዎች ፈታኝ በመሆኑ የትራፊክ አደጋ ይከሰታል ብለዋል። አቶ ጸጋዬ እንደሚሉት ጉለሌ አካባቢ በርካታ መኪናዎችና እግረኞች የሚተላለፉበት ቢሆንም የምሽት መብራት የላቸውም፤ ብዙዎችም አደጋ እየደረሰባቸው ነው።

    ኢትዮጵያ ውስጥ አዲስም ሆነ አሮጌ መኪናዎች ከሚገባው በላይ ውድ የሆኑበት ምክንያት ምንድን ነ?

    የላዳ ታክሲ አሽከርካሪ ማቲዮስ ታምር ሥራው በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች እንዲዘዋወር ስለሚያደርገው በርካታ መንገዶችን እንዳየና መብራት እንደሌላቸው ተናግሯል። ውስጥ ለውስጥና በዋና መንገዶች መብራት በብዛት አለመኖሩ መሪን ያለ አግባብ የመጠቀም ዕድል ስለሚኖር የመጋጨት አጋጣሚውም ሰፊ ነው ብሏል።

    ከስድስት ኪሎ ሽሮ ሜዳ፣ ከሰሜን ማዘጋጃ እንጦጦ፣ ከእንቁላል ፋብሪካ ዊንጌት ባሉ መንገዶች እንደሚሰሩ የገለፁት በአዲስ አበባ የጉለሌ ክፍለ ከተማ የትራፊክ ቁጥጥር አባል ምክትል ኢንስፔክተር አያሌው በለጠ ከነዚህ መንገዶችም አብዛኛዎቹ መብራት የላቸው ብለዋል።

    መዲናዋ በተሽከርካሪዎችና በእግረኞች የተጨናነቀች በመሆኗ በጨለማ ወቅት መብራት አለመኖሩ የትራፊክ አደጋን አባብሷል ነው ያሉት ምክትል ኢንስፔክተሩ።

    መብራት ከሌለ አሽከርካሪዎች ረጅም መብራት የመጠቀም ዕድላቸው ሰፊ ነው ያሉት ረዳት ኢንስፔክተር መራጭ ድንጌቻ፤ ከፊት ለፊት የሚመጡ መኪናዎችን እይታ ሙሉ ለሙሉ በመሸፈን ለአደጋ ያጋልጣል ብለዋል።

    “ከእንቁላል ፋብርካ እስከ ዊንጌት ብዙ ሆስፒታሎች ስላሉ ህሙማንን የያዙ ተሽከርካሪዎች ቀንና ሌሊት ይመላለሳሉ፤ ባለፈው ዓመት በዚያ መንገድ በርካታ ሰዎች ተገጭተዋል” ነው ያሉት።

    ምክትል ኢንስፔክተር አያሌው “ከዚህ ቀደም በአዲሱ ገበያ ዊንጌት በሚወስደው መንገድ አንዲት ሴት ተገጭታ መብራት ባለመኖሩ ምክንያት ሌሊቱን ሙሉ መኪና ሲመላለስባት አድሮ የገላዋ ዱቄት ነው የተነሳው” ሲሉ ያጋጠማቸውን አሳዛኝ ክስተት ነግረውናል።

    በአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን የመንገድ መብራት ክትትል ባለሙያ ኢንጅነር ደረጀ ኃይሉ የከተማዋ መንገዶች አንዳንዶቹ የመብራት አገልግሎት እንደሌላቸው ገልጸው “ከጉርድ ሾላ ኦቨር ፓስ፣ መገናኛ ያለው የትራንስፖርት አገልግሎት መስጫ ከስድስት ወር በፊት ተጠይቆ የዋጋ ግምት አልተመለሰልንም” ነው ያሉት።

    የቦሌ አራብሳ መንገድ ከሁለት ዓመት በፊት ለአገልገሎት ክፍት ሆኖ የመብራት ምሰሶ ቢተከልም መብራት እንዳልተለቀቀ የገለጹት ኢንጅነር ደረጀ ከስድስት ኪሎ ፈረንሳይ ጉራራ ኪዳነምኅረት የምሰሶ ተከላና የገመድ ዝርጋታ የማሟላት ሥራ ተከናውኖ የኃይል ዋጋ ግምት እንዲላክለት ከአንድ ወር ወዲህ መጠየቁን ተናግረዋል።

    በባለስልጣኑ የድንገተኛና አንሰለሪ ጉዳዮች ቡድን መሪ አቶ ዘውዱ ባይህ በበኩላቸው መብራት ተቋርጦባቸው የነበሩ 37 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር የቀለበት መንገዶች ባለፈው ዓመት ተጠግነው አገልግሎት እየሰጡ መሆኑን ተናግረዋል።

    ጨለማን ተገን አድርገው ዝርፊያ የሚፈጽሙ አካላት የመብራት ቁሳቁሶችን ከአገልግሎት ውጪ እያደረጉና እየዘረፉ መሆኑን የተናገሩት አቶ ዘውዱ ከዮሴፍ-ቦሌ ሚካኤል፣ ከአየር መንገድ አደባባይ-ኢምፔሪያል፣ ሸጎሌ ከጎጃም በር-እስከ ዊንጌት እንዲሁም 18 ማዞሪያ፣ ከ3 ቁጥር ማዞሪያ-አለርት ቁሳቁሶቹ በየጊዜው እየጠፉ ተቸግረናል በማለት አስረድተዋል።

    የተበላሹትን ወደ አገልገሎት ለመመለስ በራስ ኃይልና በጨረታ እየተጠገኑ መሆኑን ያነሱት ቡድን መሪው አሮጌ መብራቶችን ደረጃቸውን የጠበቁ ለማድረግ እየተሠራ ነው ብለዋል።

    በከተማዋ መንገዶች ከ40 በመቶ የማይበልጡ የመብራት አገልግሎት ያላቸው ሲሆን ባለሥልጣኑ 25 ሚሊዮን ብር በመመደብ ጥገና እየሠራ ነው፤ በዚህ በጀት ዓመትም ሽፋኑን 90 በመቶ ለማድረስ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል።

    የአዲስ አበባ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ቢሮ የኮሙዩኒኬሽን ሥራ አስኪያጅ አቶ በቀለ ክፍሌ በበኩላቸው የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ከኤሌክትሪክ አገልግሎት ጋር ባለው ውል መሠረት ቆጣሪና ትራንስፎርመር እየገጠምን ነው ብለዋል።

    ሆኖም የሲቪል ሥራዎች በመንገዶች ባለስልጣን በኩል ባለመጠናቀቃቸውና የመንገድ ርክክብ ባለማድረጋቸው ምክንያት መብራት የማያገኙ መንገዶች መኖራቸውን ተናግረዋል።

    “የካ አባዶ አንድ መንገድ፣ ከስድስት ኪሎ ፈረንሳይ ጉራራ መንገድ ተገምቷል፣ ቦሌ አራብሳ እየተገመተ ነው፣ ጎሮ ቱሉ ዲምቱ ትራንስፎርመርና ቆጣሪ ተገጥሟል፣ ከሲኤምሲ አደባባይ እስከ ካራ ትራንስፎርመርና ቆጣሪ ቢገጠምም መንገዱን ርክክብ አላደረጉም፣ ከዊንጌት አደባባይ እስከራስ ደስታ ሆስፒታል ላለው መንገዶች ባለስልጣን ግምት አላመጣም፣ ዓለም ባንክ ቤቴል አየር ጤና ፍርድ ቤት ያሉት ያልተጠናቀቁ የሲቪል ሥራዎች ሲጠናቀቁ ኃይል ይለቀቅላቸዋል” ብለዋል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) / ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን

    Semonegna
    Keymaster

    ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ ከግብር በፊት ያገኘው ትርፍ ብር 658.75 ሚሊዮን ሲሆን ይህም ባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ተመዝግቦ ከነበረው ትርፍ ጋር ሲነጻጸር 13.97 ሚሊዮን ወይም 2.2 በመቶ ዕድገት አሳይቷል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– በአገሪቱ የፋይናንስ ዘርፍ እውቅና ካገኙ የግል ባንኮች መካከል አንዱ የሆነው ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ 19ኛ መደበኛና 17ኛ ድንገተኛ የባለአክስዮኖች ጠቅላላ ጉባኤ ኅዳር 22 ቀን 2011 ዓ.ም በሚሊኒየም አዳራሽ አካሄደ።

    በጉባኤው ላይ በቀረበው የዳይሬክተሮች ቦርድ ሪፖርት መሠረት፥ በበጀት ዓመቱ መጨረሻ የባንኩ አጠቃላይ ሀብት ብር 26.7 ቢሊዮን ደርሷል። ይህም ባለፈው ተመሳሳይ ወቅት ከነበረው ብር 21.1 ቢሊዮን ጋር ሲነጻጸር የ26.4 በመቶ ዕድገት ያሳየ ሲሆን፣ ባንኩ ቀጣይነትና ዘላቂነት ያለው ዕድገት ማስመዝገብ መቀጠሉን ያመለክታል።

    ከግብር በፊት ባንኩ ያገኘው ትርፍ ብር 658.75 ሚሊዮን ሲሆን ይህም ባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ተመዝግቦ ከነበረው ትርፍ ጋር ሲነጻጸር 13.97 ሚሊዮን ወይም 2.2 በመቶ ዕድገት አሳይቷል። በበጀት ዓመቱ መጨረሻ የባንኩ አጠቃላይ ሀብት ብር 26.7 ቢሊዮን በማድረስ ባለፈው ዓመት ከነበረው ብር 21.1 ቢሊዮን ጋር ሲነጻጸር የ26.4 በመቶ ዕድገት አሳይቷል። በ2010 የበጀት ዓመት መጨረሻ ላይ የባንኩ አጠቃላይ ተቀማጭ ገንዘብ መጠን ብር 21.6 ቢሊዮን ደርሷል። ይህም አሃዝ ካለፈው በጀት ዓመት ጋር ሲነጻጸር የብር 5.1 ቢሊዮን ወይም የ30.6 በመቶ ዕድገት የሚያሳይ ነው።

    Nib International Bank announces 658.7 million birr pre-tax profit in the fiscal year

    በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ብድር የወሰዱ 541 ደንበኞችን ጨምሮ እስካሁን ወደ 11,626 የሚሆኑ ደንበኞች በተለያዩ ወቅቶች ለተለያዩ ዓላማዎች የብድር ተጠቃሚ ሆነዋል። በዚሁ መሠረት በ2010 በጀት ዓመት የባንኩ የብድር መጠን ወደ ብር 13.5 ቢሊዮን ያደገ ሲሆን ይህም አሃዝ ካለፈው ዓመት ተመመሣሣይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የብር 2.8 ቢሊዮን ወይም 26.5 በመቶ ዕድገት አሳይቷል።

    በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት የባንኩ አጠቃላይ ካፒታል ብር 3.4 ቢሊዮን የደረሰ ሲሆን ይህ አሃዝ ካለፈው ዓመት ተመሣሣይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የብር 414.5 ሚሊዮን ወይም የ14 በመቶ ዕድገት አሳይቷል። በበጀት ዓመቱ የባንኩ የተመዘገበ/የተፈረመ ካፒታል ብር 2.2 ቢሊዮን፣ የተከፈለ ካፒታል ደግሞ ብር 2.2 ቢሊዮን ደርሷል።

    ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ ያለውን ጠንካራ መሠረት ለመጠበቅ እንዲቻል የባንኩ ዋና መሥሪያ ቤት፣ አራት ኪሎ የሚገኘው፣ በሆሳዕናና በሐዋሣ ከተሞች የሚገኙት ሕንጻዎች የግንባታ ሥራ በማፋጠን ላይ ሲሆን፤ በወልቂጤና በዱከም ከተሞች አስገንብቶ ያስመረቃቸው ሕንፃዎችም የተለያዩ አገልግሎቶችን ለመስጠት በእንቅስቃሴ ላይ ይገኛሉ። የባንኩ ቋሚ ንብረት በባለፈው ዓመት ከነበረበት ብር 495.6 ሚሊዮን ወደ ብር 1.9 ቢሊዮን ማደጉንም በስብሰባው ላይ ተገልጿል።

    ምንጭ፦ NibBankSC.com
    ——
    ተመሳሳይ ዜናዎች፦

    ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ


    Semonegna
    Keymaster

    ኢትዮጵያ እና የአፍሪካ ልማት ባንክ ለተቀናጀ የግብርና-ኢንዱስትሪ ፓርኮች ፕሮጀክት ማስፈፀሚያ የሚውል የ15 ሚሊዮን የአሜርካ ዶላር (420 ሚሊዮን ብር) ስምምነት ተፈራረሙ

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ) – ኢትዮጵያ እና ዘርፈ ብዙ የኢኮኖሚያዊ እና ማኅበራዊ ልማቶችን በገንዘብ የሚደግፈው የአፍሪካ ልማት ባንክ ለተቀናጀ የግብርና-ኢንዱስትሪ ፓርኮች ፕሮጀክት ማስፈፀሚያ የሚውል የ15 ሚሊዮን ዶላር ስምምነት ተፈራረሙ።

    የፋይናንስ ስምምነቱን የፈረሙት በኢትዮጵያ በኩል የገንዘብ ሚኒስትር አቶ አህመድ ሽዴ ሲሆኑ በአፍሪካ ልማት ባንክ በኩል ደግሞ የባንኩ የኢትዮጵያ ሥራ አስኪያጅ አብዱል ካማራ (ዶ/ር) ናቸው።

    ዋና መቀመጫነቱ በአቢጃን ከተማ (አይቮሪኮስት) የሆነው የአፍሪካ ልማት ባንክ የገንዘብ ድጋፉን ያደረገው በኢትዮጵያ በግብርና – ኢንዱስትሪ (agro-industry) ዙርያ እየተከናወኑ ያሉ ፕሮጀክቶችን ለመደገፍ ነው። ድጋፉ በአማራ፣ በኦሮሚያ፣ በትግራይ እና በደቡብ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልላዊ መንግስታት ስር እየተገነቡ ላሉ አራት ኢንዱስትሪ ፓርኮችን እንደሚውል ተገልፃል።

    ፕሮጀክቱ ሦስት ዋና ዋና ክፍሎችን ለመደገፍ የሚውል ሲሆን በኢንዱስትሪ ፓርኮች መሠረተ-ልማትን ለማሳደግ፣ በዘላቂነት የግብርና-ኢንዱስትሪ ልማት ዘርፍ እንዲኖር ለማሰቻል እና በፕሮጀክት አስተዳደርና አተገባበር ላይ ለአራቱ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስታት እና ለንግድ እና ኢንዱስትሪ የአቅም ግንባታ ሥራዎችን ለማከናውን ይውላል።

    African Development Bank Group approves US$123 million grant for Ethiopia’s Basic Services Transformation Program

    የገንዘብ ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ አህመድ ሽዴ በፊርማ ሥነ-ሥርዓት ወቅት እንደተናገሩት፥ ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ በ2025 መካከለኛ ገቢ ካለቸው የአፍሪካ ሀገራት ተርታ ለመሰለፍ የተለያዩ መርሀ ግብሮችን ነድፋ እየተንቀሳቀሰች የምትገኝ ሲሆን፥ በተለይም ሁሉን አቀፍ እድገት እንዲኖር ማስቻል፣ ድህነት ቅነሳ እና ለወጣቶች የሥራ ዕድል እንዲፈጠር የማደረግ ተግባራትን እያከናወነች ትገኛለች ብለዋል።
    የገንዘብ ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ ወደ ኢንዱስትሪ ልማት በስፋት ለመግባት እያደረገች ላለው ጥረት የአፍሪካ ልማት ባንክ እያደረገው ላለው ድጋፍ ምስጋናቸው አቅርበዋል።

    ባለፈው ወር የአፍሪካ ልማት ባንክ ኢትዮጵያ የዘረጋቸውን መሠረታዊ አገልግሎቶች ማሻሻያ መርሀ ግብር (Basic Services Transformation Program) ለመደገፍ 123 ሚሊዮን ዶላር ድጎማ ማድረጉን መዘገባችን ይታወሳል።

    ምንጭ፦ የገንዘብ ሚኒስቴር
    ——
    ተጨማሪ ዜናዎች፦

    የአፍሪካ ልማት ባንክ


    Semonegna
    Keymaster

    ታስረው ከነበሩ ሰዎች የተፈጸመውን ግፍ የሰማውና ጠንቅቆ የሚያውቀው ሕዝብ በሌሎችም በርካታ አጋጣሚዎች በዜጎች ላይ የተፈጸመውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሲሰማ የኖረው ሕዝብ የከረረ ተቃውሞ ቢያሰማ አሻፈረኝ ቢል ምንም አይፈረድበትም።

    መሐመድ አማን (የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት)

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)–ከሰሞኑ በተለያዩ የቴሌቪዥን ማሰራጫ ጣቢያዎች የቀረበው የሰብዓዊ መብት ጥሰት ዘጋቢ ፊልም በሕዝብና በዜጎች ላይ የተፈጸመው ግፍና በደል መጠን የለሽ እንደነበር ያሳያል። ገራሚው ነገር እኩልነት በተግባር ተረጋግጧል በሚባልበት ሀገር ዜጎች በብሔራቸውና በጎሳቸው መነሻነት ተለይተው እጅግ ዘግናኝና በጭካኔ የተሞላ አረመኔያዊ ድርጊት የተፈጸመባቸው መሆኑ በእጅጉ አሳዝኗል። የት ሀገር ላይ ነበርንም ያሰኛል።

    ይህ ዓይነቱ ጸያፍ ድርጊት በዓለም ደረጃ ይፈጸም የነበረው በተለይ በናዚ ጀርመን የማሰቃያና የመግረፊያ በጋዝ መርዝ ሰዎች ይገደሉባቸው በነበሩ ካምፖች ነበር። በተለያዩ የቴሌቪዥን ማሰራጫ ጣቢያዎች የተላለፈው የሰብዓዊ መብት ጥሰት ዘጋቢ ፊልምም ድፍን ሀገርን በእንባ አራጭቷል።

    የግፉና የአረመኔያዊ ድርጊቱ ጫፍና ጣሪያ ከሚገመተው በላይ የሆነ በተለይም ዘርና ብሔርን ኢላማ ያደረገ መሆኑ ደግሞ እጅጉን ያማል። ሰው የሆነ ሰው፤ ቤተሰብ ልጅ እህት ወንድም ወገን ያለው ሰብዓዊ የሆነ ፍጡር እንዲህ ዓይነቱን ድርጊት ይፈጽማል ብሎ ለማመን ይከብዳል፤ ግን ደግሞ ሆነ፤ ተደረገም።

    ይህን በዘረኝነት ጥላቻ የተሞላ ከአፍ እስከ ገደፉ ሞልቶ የፈሰሰን እጅግ አረመኔያዊ ድርጊት ለመግለጽ ቃላቶች አቅም ያጥራቸዋል። ሰው በአገሩ እንዲህ ዓይነት በደልና ግፍ በአረመኔነት ተሞልቶ ሲፈጸምበት ሀገሬ አይደለችም አላውቃትም ቢል አይፈረድበትም።

    የፍትህ ሰቆቃ ― አማርኛ ዘጋቢ ፊልም

    ከሥልጣኔና ከዕውቀት፣ ከመልካም ሥነ-ምግባር የተፋቱ ሰብዓዊነት የሚባል ነገር ያልፈጠረባቸው አረመኔ አውሬዎች ቀጣዩን ትውልድ እንዳይበክሉት መጠንቀቅ ለሕግና ለፍትህ ማቅረብ ግድ ይላል።

    ሕዝብና የሕዝብ ልጆችን ማሰቃየት፣ ብልታቸውን ማኮላሸት፣ ገልብጦ በእንጨት ላይ አንጠልጥሎ መግረፍ፣ ሰቅሎ ማቆየት፣ ዘርን ለይቶ መሳደብ ማንቋሸሽ፣ አፍ ላይ መጸዳዳት፣ ወንድ ላይ የግብረ ሰዶማዊነትን መፈጸም፣ ሴትን ልጅ እርቃኗን እያዩ መሳለቅ፣ ከዚያም አልፎ ወሲብ መፈጸም ሌላ ሀገር ሳይሆን እዚሁ ኢትዮጵያ ውስጥ የተፈጸመ ድርጊት ነው። ያውም የአፍሪካ መዲና በሆነችው አዲስ አበባና ፈጣሪውን የሚፈራ ሩህሩህ ሕዝብ አለበት በሚባል ሀገር።

    ይህ ሁሉ ድርጊት በኃይል፤ በጉልበት፤ በጠመንጃ አፈሙዝ አስገብሬና አስፈራርቼ እገዛለሁ በሚል የደንቆሮዎች እምነት መከወኑ ያሳፍራል። ጉዳዮቹ በጥብቅ ምስጢር ተይዘው ሲሠራባቸው የነበሩና የምስጢር ዘበኞቹም ራሳቸው ስለሆኑ ይህን ጉዳይ በአልፎ አገደም ከምንሰማው ውጪ እንዲህ የሰብዓዊ መብት ጥሰት የተፈጸመባቸው ሰዎች አደባባይ ወጥተው ድምጻቸውን ለማሰማት የማይችሉባቸው በርካታ ሁኔታዎች ነበሩ። ቀን ሲፈቅድ ሁሉም ይሆናል እንዲሉ ሆነና ቀን በደሉን ግፉን አረመኔነቱንና ጭካኔውን ግፈኝነቱን እንዲህ በአደባባይ አሰጣው።

    ግፍ ሠርቶ መደበቅ፣ ዘርፎ መንደላቀቅ አይቻልም ― የጠቅላይ ሚኒስትሩ መግለጫ

    ምስጋናው ለሰው ሳይሆን ለቀን ነው የሚሆነው። ለውጡን ላመጣው የሕዝብ ትግልና ለውጡን ከዳር ለማድረስ ሪፎርሙን እየመሩ ላሉት ሰዎች። ይህን ያህል ግፍ በጭካኔና አረመኔያዊነት በዘር ጥላቻ ላይ የተፈጸመ ሰቅጣጭ ድራማ በአገራችን ምድር ላይ ተፈጽሞ እናያለን ብሎ የገመተም የጠበቀም አልነበረም። ያለፈው (የደርግ) ሥርዓት እንዲህ ዓይነት እጅግ ነውረኛና ዘረኛ አረመኔያዊና ፋሽስታዊ ድርጊት በዜጎቹ ላይ ስለመፈጸሙ አልሰማንም።

    በፖለቲካ ልዩነት እንጂ በደርግ ዘመን እንኳን በዜጎቹ መካከል ልዩነትን ፈጥሮ ማጥቃት አልተስተዋለም፤ ብሔር እየመረጠ አልረሸነም፤ ብሔር እየመረጠም አልጠቀመም። የደርግ አምባገነናዊ ባህሪይው እንደተጠበቀ ሆኖ በእንዲህ መልኩ አሰቃቂ የግፍ ተግባራት ስለመፈጸማቸውም ያጠራጥራል። ይሁንና በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ወጣቶች ክቡር ህይወታቸውን ገብረው ለሰብዓዊ መብት መከበር የከፈሉትን መስዋዕትነት ገደል የሚከት ተግባር በእነዚህ ጥቂት አረመኔዎች ተፈጽሟል። የሀገሬ ሰው እንደሚለው “ወንበሬን ማን ነክቶት አይሉም አይሉም፤ ሚስቴንስ ማን ዓይቷት አይሉም አይሉም፤ ቀን የፈቀደ ዕለት ይደረጋል ሁሉም” እንዲሉ ሁሉንም ይፋ ያወጣው ቀን ሆነ። በቀላሉ ይፋ የማይወጡ ሊታወቁ የማይችሉ ምስጢሮች ለአደባባይ በቁ።

    መቼም አንዱ ሄዶ ሌላው ሲመጣ አዲስ ለውጥና ሂደት ቢጠበቅም በዚህ ዓይነት ደረጃ መዝቀጥና መውረድ ይኖራል ተብሎ አይታሰብም ነበር። እነዚህ ሰዎች የፈጸሙትን አረመኔያዊ ድርጊት የጀርመኑ አዶልፍ ሂትለር ስድስት ሚሊዮን አይሁዶች በመፍጀት አሳይቷል። በማቃጠያና መግደያ ካምፖቹ ውስጥ በማስገባት በጋዝ መርዝ ጭስ ተሰቃይተው ከሞቱ በኋላ አስከሬናቸው ተፈጭቶ ወደ ሳሙናነት እስኪለወጥ ድረስ ሠርቷል። ይህን ዓይነቱን አረመኔያዊ ድርጊት በራሱ ዜጎች ላይ ግን አልፈጸመም።

    ሙሶሎኒ ፋሽስት ስለሆነ ኢትዮጵያን በቅኝ ግዛት ለመግዛት ቋምጦ በመጣውና መሪ በነበረው ግራዚያኒ አማካኝነት ኢትዮጵያ ውያንን በአካፋና በዶማ አስጨፍጭፏል። ቤት ውስጥ እንዲገቡ ካደረገ በኋላ እሳት ለኩሶ አንድዷቸዋል። የዘር ማጥፋት ፍጅት ፈጽሟል።

    የተላለፈው እጅግ የከፋ የሰብዓዊ መብት ጥሰትን የተመለከተው ዘጋቢ ፊልም እነዚህ ሰዎች ከባሕላችን፤ ከእሴቶቻችን፤ ከሀይማኖታዊ እምነታችን በእጅጉ የራቁ፤ በዘረኝነት ጭፍን ጥላቻ የታወሩ፤ የክፍለ ዘመናችን ጥቁር ፋሽስቶች መሆናቸውን ደግሞ ደጋግሞ ያረጋግጣል።

    የራሳችን ሰዎች የሆኑ ኢትዮጵያውያን ምን ያህል ጸያፍ ሥራ ሲፈጽሙ እንደኖሩ፤ አገርንና ሕዝብን እንዳዋረዱ፤ ወደፊትም በዚሁ አሳፋሪ ሥራቸው ቀና ብለው ለመራመድ እንደሚቸገሩ በእርግጠኝነት ለመናገር ይቻላል። ታስረው ከነበሩ ሰዎች የተፈጸመውን ግፍ የሰማውና ጠንቅቆ የሚያውቀው ሕዝብ በሌሎችም በርካታ አጋጣሚዎች በዜጎች ላይ የተፈጸመውን የሰብዓዊ መብት ጥሰት ሲሰማ የኖረው ሕዝብ የከረረ ተቃውሞ ቢያሰማ አሻፈረኝ ቢል ምንም አይፈረድበትም።

    እንዲህ ዓይነቱ ፋሽስታዊ ድርጊት ከምድራችን ተነቅሎ እንዲጠፋ፤ ሕግና ተጠያቂነት እንዲሰፍን፤ ሁሉም ዜጋ የየበኩሉን አስተዋጽኦ ማድረግ ይጠበቅበታል። በመዲናዋ አዲስ አበባና በሌሎችም ከተሞች ህቡእ ከመሬት ስር ያሉ እስር ቤቶችን ከፍቶ ዜጎችን ማሰቃየት፣ መግረፍ፣ መግደል፣ የወንጀሎች ሁሉ የከፋው ወንጀል ከመሆኑም በላይ አስቸኳይ የሕግ ውሳኔን ይጠይቃል።

    ዋናውና ትልቁ ጥያቄ ይህ ሁሉ ግፍና በደል ሲፈጸም ዜጎች ሲደፈሩ፤ ግብረሰዶም ሲፈጸምባቸው፤ አፋቸው ላይ ሲጸዳዱ፤ ሴቶች እርቃናቸውን ሆነው መጫወቻ ሲሆኑ፤ መንግሥት ተብሎ የሚጠራው መንግሥት ምን ሲሠራ ነበር ብሎ መጠየቅ ይገባል። ሀገሬ የተፈጸመብሽ ግፍ አረመኔነት ጭካኔ ከጣሪያ በላይ ወጣ። የናቁሽ የረገጡሽ ያዋረዱሽ ሁሉ ውርደትን ሽንፈትን ውድቀትን ይከናነቡ ዘንድ ፍርዱ የአምላክም የሕዝብም ይሆናል። ይሁንና ከዚህ ልንማረው የሚገባው ጉዳይ ልክ እንደ ዘራፊዎች ጨካኞችም የትኛውንም ብሔር እንደማይወክሉና የሕዝብ ጠላቶች እንደሆኑ ነው። ሕዝባችንም ለእነዚህ ዓይነት ጨካኞች ምን ዓይነት የመደበቂያ ከለላ ሳይሰጥ የወገኖቼ ጠላቶች ናችሁ ብሎ ሊያወግዛቸው ብሎም ለፍርድ ሊያቀርባቸው ይገባል። ስህተት በሌላ ስህተት አይታረምምና መንግሥትም እነዚህ አካላት ከፈጸሙት ተግባር በተቃራኒው ሄዶ ሰብዓዊነትን የሚማሩበትን የፍርድ ሂደት ማከናወን ጊዜ ሊሰጠው የማይገባው ተግባሩ ሊሆን ይገባል።

    ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት

    የሰብዓዊ መብት ጥሰት

    Semonegna
    Keymaster

    የዘንድሮው የፀረ-ሙስና ቀን በአገር አቀፍ ደረጃ ለ14 ጊዜ በዓለም አቀፍ ደረጃ ደግሞ ለ16ኛ ጊዜ የተከበረ መሆኑን በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የትራንስፖርት ፕሮግራሞች ማስተባበርያ ጽህፈት ቤት ዘግቧል።

    አዲስ አበባ (ሰሞነኛ)– በአዲስ አበባ ከተማ መንገድና ትራንስፖርት ቢሮ እና በአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ትብብር የተዘጋጀው ዓለም አቀፍ ዓመታዊ የፀረ-ሙስና ቀን “ሁለንተናዊ ሰላማችንና እድገታችንን ለማረጋገጥ በሙስና ላይ በጋራ እንዝመት፤ ጊዜው የተግባር ነው” በሚል መሪ-ቃል በፓናል ውይይት እሁድ ኅዳር 30 ቀን 2011 ዓ.ም. ተከብሮ ውሏል።

    በዕለቱም የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የአዲስ አበባ መንገድና ትራንስፖርት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ታከለ ሉሊና ሙስና ተሸሞንሙኖ የሚጠራ ሳይሆን ሌብነት እንደሆነ ሁሉም ዜጎች ተገንዝበው መታገል እና ሙስና በዓይነቱም የተለያየ እንደሆነ በመግለፅ ሁላችንም ተረባርበን መከላከል አለብን ብለዋል።

    አቶ ታከለ አያይዘውም ከትንሽ ከህዝብና መንግስት ሰዓትና ንብረት ጀምሮ ትኩረት በመስጠት ያለአግባብ እናዳይባክኑ በቀጣይነትም ልንሠራ ይገባል፤ ለዚህም ሁላችንም የበኩላችንን ሚና መወጣት አለብን ብለዋል።

    በዓሉን አስመልክቶ በተዘጋው የፓናል መወያያ መነሻ ሃሳብ ላይም የኢፌዲሪ ፀረ-ሙስና ኮሚሽን የአዲስ አበባ ማስተባበሪ ቅርንጫፍ የሕግ ባለሙያ አቶ ተስፋዬ ከፋለ እንደተናሩት በርካታ የሙስና መገለጫዎች አሉ እነዚህንም እንደየዓይነታቸው ነጣጥለን መከላከል ያስፈልጋል፤ ህብረተሰቡም ሊያግዝ ይገባል በጉዳዩም ላይ ባለቤት ነኝ ይመለከተኛል ማለት ይገባል ብለዋል።

    ሙስና በአሠራር፣ በአስተሳሰብ፣ በአመለካከት፣ በጥቅም ትስስር፣ በዝምድናና በመሳሰሉት የሚፈፀም በረቀቀና ሚስጢራዊ በሆነ መንገድ የሚከወን በመሆኑ የኮሚሽኑን ስራም በተገቢው እንዳይወጣ ሲያደርግ እንደነበርም አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

    የአዲስ አበባ ከተማ የመኪና ማቆሚያ ቦታ ችግሯን ለመፍታት አማራጮች እየተፈለጉ ነው

    አክለውም ሙስና ለአገር ዕድገት ፀር፣ ለዲሞክራሲ ጋንግሪን እንደሆነ በማስታወስ ለአንዲት አገር ህዝብ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና ማኅበራዊ ውድቀት የሚያስከትል በመሆኑ ሁሉም ዜጋ እንደሚመለከተው በማብራራት ይህን ለመከላከል ሁሉም ቁርጠኛ መሆን እንዳለበት አስረድተዋል።

    በመጨረሻም እንደአገራችን ተጨባጭ ሁኔታ መንግስት ትኩረት ሰጥቶ እየሠራበት ያለው የኮንስትራክሽኑ ዘርፍ በመሆኑና ብዙውን ጊዜ ከዚህ ጋር ተያይዘው የሚታዩ የሙስና ወንጀሎችን ለመቀነስ በትኩረት መሠራት እንዳለበት ጠቁመዋል።

    የዘንድሮው የፀረ-ሙስና ቀን በአገር አቀፍ ደረጃ ለ14 ጊዜ በዓለም አቀፍ ደረጃ ደግሞ ለ16ኛ ጊዜ የተከበረ መሆኑን በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የትራንስፖርት ፕሮግራሞች ማስተባበርያ ጽህፈት ቤት (TPMO) ዘግቧል።

    የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሙስናን ለመዋጋት የተደረገው ስምምነት (United Nations Convention Against Corruption) እ.ኤ.አ ጥቅምት 31 ቀን 2003 ቀን መጽደቁን ተከትሎ በየዓመቱ ኅዳር 30 ቀን  “የፀረ-ሙስና ቀን” ሆኖ እንዲከበር ተወስኗል።

    ምንጭ፦ TPMO | ሰሞነኛ ኢትዮጵያ

    የፀረ-ሙስና ቀን

Viewing 15 results - 406 through 420 (of 495 total)